October 20, 2023
20 mins read

የአብይ አህመድና የቲያትሩ ውድቀት

Abiys dron

ከአልማዝ አሸናፊ

Imzzassefa5@gmail.com
Wyoming, USA

Abiys dronሕይወት በሦስት የጊዜ ክፍሎች ትከፈላለች: ያለፈው፣ ያለውና (የአሁንና) የሚሆነው (የወደፊቱ/መጭው) ናቸው። ካለፈው ድርጊቶችና ሁኔታዎች በመማር በአሁኑ ጊዜ የተሻለ ድርጊት በማድረግ ጥሩ ሁኔታዎችን ለማግኘት : ካለው ወይም ከአሁኑ ደግሞ ተምረን የወደፊቱና ወይም መጭው እጅግ ያማረና ያመረቀነ ኑሮ ለመኖር እንዲቻል ነው::

ሆኖም የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውያን ዕጣ በደመናው ውስጥ ትንሽ የብርሃን ጨረር ይታያቸውና የተሻለ ቀን ይመጣል ሲባል ደመናው ጉም እየሆነ የበለጠ እየጨለመና ተስፋ  ሚያስቆርጥ ጊዜ እየሆነባቸው መጥቷል:: የዛሬዎቹ ካለፉት ስህተቶች ተምረው ዛሬን የተሻለ በማድረግ ለመጪው ጊዜ አምራቂ ሁኔታዎችን ያወርሳሉ ተብለው ሲጠበቁ : እንዳለፉት በስህተት ውስጥ እየወደቁ በመንከባለል የኢትዮጵያ ፖለቲካ አመድ ከመልበስ ሊጠራ አልቻለም::

የፖለቲካው ቲያትር አርእስትና ጭብጥ መልእክቱ በጊዜ ተገድቦ ተመርምሮ ተፈትሾ ተፈትኖ ያለፈው ተገምግሞ የሚያስተምረው ውጤቱ ታይቶ የሚተረክ ሳይሆን የፖለቲካው ቲያትር ተጫዋቾችና ደጋፊ ተዋናዮች መቀያየር ነው:: ሰፊው ሕዝብም እነዚህ የፖለቲካ ተጫዋቾችና ደጋፊ ተዋናዮች ያቀረቡትን ቲያትር በፍርሃት መመልከት እንጂ ቲያትሩ አልጣመኝም ብሎ የመተቸት መብቱ መገፈፉን ጥንቅቅ አድርጎ ስላወቀ የቀረበለትን ቲያትር በትዝብት ማየት ግድ ይለዋል:;

መረሳት የሌለበት ቲያትር አዘጋጅዎቾና ተዋናዮች የራሳቸው ቲያትር ተራኪዎችና ተችዎች መሆን አይችሉም:: ልታረምና ሊሆኑ ይችላሉ:: ይህም የሚሆነው ለሰው ልጅ ሃሳቢነት : ሰብአዊነት : ለእውነት መቆምና መልካምነትን በልባቸውና በሂሊናቸው የተጎናፀፉ ከሆኑ ነው:: እውነተኛና የተሻለ ቲያትር ደራሲ አቀነባባሪና ተዋናይ መሆን የሚፈልግ በቅድሚያ ተመልካቾች የሚፈልጉትና የሚጥማቸው ምንድነው ብሎ ማሰብና መገናዘብ ይኖርበታል:: የትያትሩን ማራኪነት ጥሩነት ወይም ተቃራኒ መሆኑን የሚገመግሙትና የሚዳኙት የቲያትሩ ተመልካች ሰፊው ሕዝብ መሆኑን ውጤታማ መሆን የሚፈልግ ቲያትረኛ መረዳት ይችላል:: በዚያ መሰረት ቲያትሩን ያዘጋጃል:: ትያትሩ አልጣመኝም ብሎ ሰፊው ሕዝብ ሲያጉረመርም የቲያትሩ ደራሲዎች አቀነባባሪዎችና ተዋናዮች ተመልካቾችን በግድ ቲያትራችንን ማየት አለብህ ብሎ ማስፈራራትና ማስገደድ ለቲያትሩም ሆነ ለደራሲዎቹ አቀነባሪዎቹና ተዋናዮቹ ዘለቄታ አይፈጥርም::

የኢትዮጵያ ፖለቲካ ቲያትር ባለፈውም ሆነ በአሁን ጊዜ የሚፃፈው የሚቀነባበረውና የሚተወነው ሰፊውን ሕዝብ ተመልካች ግንዛቤ ውስጥ በመክተት ሳይሆን በፖለቲካው ቲያትር ሠራተኞች ፍላጎትና እሽት ላይ የተመሠረተ ብቻ ነው:: ሰፊውን ተመልካች ሕዝብ ፍላጎትና ስሜት የማይካትት የፖለቲካ ቲያትር ጨዋታ የቲያትሩን ደራሲዎች እቀነባባሪዎችና ተዋናዮች ለጊዜው ያኖራል ያስደስታል እንጂ እነሱንም እንዲሻሻሉና ጥልቀት ያለው እድገት አያመጣላቸውም:: ስራቸውም ተቀባይነት ኖሮት የወደፊት የስራቸው ወራሾችን አይፈጥርም:: አያዳብርም:: ያለፉትን እነሱ አንኳሰው ሂስና ትችት እንዳቀረቡባቸውና የተሻለ ቲያትር እነሰራለን ብለው ተመልካች ሰፊ ሕዝብ እንዳጡ : በዚያው ሁኔታ ያሁኑ ቲያትራቸው እንዳለ ከቀጠለ መጭው ቲያትረኛም በተረኝነት ስሜት ውስጥ የሚዘፈቅ እኔ አውቅልሃለሁና የማቀርብልህን ቲያትር ሳታጉረመርም ዝም ብለህ ተመልከት የሚል ተረኛ እንጂ የቲያትሩ አስቀጣይ ወራሽ እንዳልሆነ መገመት አያቅትም::

ያለፉት 60 ዓመታት የኢትዮጵያ ታሪክ ያሳየን የፖለቲካ ቲያትር በዋሻ ውስጥ እንዳለ ብርሃን ነው:: በዋሻው ውስጥ የምናየው ብርሃን (LIGHT IN THE TUNNEL) በዋሻው መውጫ በር የገባ ሳይሆን ከዋሻው አናት ባለች ትንሽ ጉድጏድ ፀሃይ ቀጥታ በጉድጏዱትክክል ስታልፍ ብልጭ ያለች ጮራ ነች:: ምክንያቱም ዋሻው መውጫ በሩ ተደፍኖ የሚጠበቀው ብርሃን ድምድም ብሎ ጠፍቷል:: የቋጠርነውም ተስፋም በተቀደደ ከረጢት ውስጥ ነው:: ቲያትሩም የሚታየውና የሚጨበጨብለት የቲያትሩ ቤት ጠባቂዎችን ቁጣና ግልምጫ በመፍራት እንጂ ሰፊው ተመልካች ቲያትሩ ጥሞትና አስደስቶት እንዳልሆነ ባለቲያትሮቹም ይገነዘቡታል::

አሁን ያሉት የፓለቲካው ቲያትር ደራሲዎችና : መሪ ተወናዋዮች : ያለፉትን የኢትዮጵያ ፖለቲካ ቲያትር ደራሲዎችንና መሪ ተዋናዮችን : ጥሩ ቲያትሮች አልፃፉም ትወናቸውም የማይጥሙ ናቸው ብለው እንደወነጀሏቸው እነሱም እንዳይወነጀሉ : ፈጣሪ ልቦና ሰጥቷቸው ለሰፊው ተመልካች ሕዝብ እስካሁን የሚያቀርቧቸው ቲያትር ድርሰቶች ካለፉት የተሻሉ ካለመሆናቸውም ሌላ : አስከፊ መሆናቸውን ተረድተው ለሰፊው ተመልካች ሕዝብ የተሻለ የሚጠቅምና የሚያስደስት ቲያትር አዘጋጅተው ቢያቀርቡ ሕዝቡም የተሻሻለውን ቲያትርና ትወና በድጋፍ ጭብጨባ ይቀበለዋል የሚል ግምት ይኖራል:: ቲያትር ያለሰፊ ሕዝብ ተመልካችና ተቀባይነት አያምርም:: ሰፊውን ሕዝብ የሚያስደስትና ደጋግሞ ለማየት የሚፈልገውን ቲያትር ማዘጋጀትና ማቀነባበር ለቲያትር ቤቱም ሞቅታና ለቲያትረኞቹ ዘለቄታ ያመጣል::

ትያትሩ በሕዝብ ተቀባይነቱና እሰየው የሚያሰኘው : ድርሰቱ በአገር ደረጃ ካየነው የሰፊው ሕዝብን : በቲያትር ተመልካችነት ክተረጎምነው : የታዳሚውን ፍላጎትና ስሜት አቃፊ ነው ወይ ብለን በመጠየቅ : የምናገኝው ምላሽ ነው:: ደራሲው (በአገር ደረጃ : የአገር መሪ) የሚፅፈው ቲያትር (አገር አስተዳደር) : የሚፃፈው ለታዳሚዎች (ለሕዝብ) እንጂ ለተዋናኞች (ለመንግስት ባለስልጣናትና ከበድን ላልተሻሉ የፓርላማ አሻንጉሊቶች) ከሆነ : ደራሲውና ቲያትሩ በታዳሚዎች (በአገር ደረጃ በሕዝቡ) ተቀባይነት አይኖራቸውም::

ይህንን ሃቅ መገንዘብ የማይችል ቲያትር ደራሲና (በአገር ደረጃ የአገር መሪ) ድርሰቱ (በአገር ደረጃ የመንግስት አመራር) በታዳሚዎች (በአገር ደረጃ በሕዝብ) ተቀባይነት ካላገኘ ውድቀቱን ገምቶ እንዴት ልሻሻል ማለት ይገባዋል:: ግን ተስፋ የተጣለበት የአቢይ አህመድ መንግስት : ከመንግስቱ ኃይለማሪያም የደርግ አስተዳደርና የጎሳ ፖለቲካን ለ27 ዓመታት ዘርግቶ የ3000 ዓመት የነፃነት ታሪኳን ገፎ ዛሬ ኢትዮጵያን ለደረሰችበት የማንነት ጥያቄ ላይ የጣላትን የወያኔን ጎሰኛ አመራር የተካው የአብይ አህመድ አጭበርባሪ መንግስት : ከሱ አመራር በፊት የነበሩትን የደርግና የወያኔን መንግስታት : እንዴት የተሻሉ እንደነበሩ ዛሬ አብይ የሚመራት ኢትዮጵያ ትመሰክራለች:: ኢትዮጵያ ለ3000 ዓመታት ለቆየችበት ዘመናት ኦሮሞ ኢትዮጵያውያን ድርሻቸውን አበርክተዋል:: ግን ዛሬ ኢትዮጵያን እንመራለን የሚለው በኦሮሞ ስም የሚነግደው የአብይ አህመድ ስግብግብና ጎሰኛ መንግስት ኦሮሞ ኢትዮጵያውያንን ከተቀረው ኢትዮጵያውያን ከማለያየት በስተቀር : ለኦሮሞ ተወላጅ የሚያመጣው ጥቅም የለም:: ይህ መንግስት እስካለ ኢትዮጵያ በፊት የነበራትን ክብርና ሞገስ እንደማይኖራት የተረጋግጠ መሆኑን አብይ አህመድ ለመረዳት የአስተሳሰብ አቅም እንደሌለው በየዕለቱ እያስመስከረ ነው:: የኦሮሞን ጎሳኝነት የበላይ አድርጎ ከ82 ጎሳዎች በላይ ያላትን አገር አስተዳድራለሁ ብሎ ማሰብ “ላም አለኝ በሰማይ: ወተቷንም አላይ::” የሚለውን ተረት ከማሰማት በስተቀር : ኢትዮጵያን ያንድ ጎሳ የበላይነት የማድረግ ችሎታ ማንም የቲያትር ደራሲ አይኖረውም:: ምክንያቱም እንደዚያ ዓይነት በጠባብ ጎሰኝነት ላይ የተመሰረተ ቲያትር : ተመልካችና አዳማጭ እንደሌለው : ለቲያትር ደራሲው (አብይ አህመድ) እና ለተወናዋዮቹ (ለአብይ እህመድ መንግስት ተወካዮች) እንደማይሰራ እንዲገነዘቡ ማድረግ እስፈላጊ ነው::

አብይ አህመድ በ2018 የደረሰውና ያቀነባበረው ቲያትር በእሱ መሪ ተወናዋይነትና ከየጎሳዎች የተመለመሉ ረዳት ተወናዋዮች ድጋፍ የተሰራው ትያትር : ካለፉት ቲያትሮች ለየት ባለ ስለተጫወቱት : ለመጀመሪያ ጊዜ በተመልካቾች ተቀባይነትን አግኝቶ አድናቆትን አትርፎ ነበር:: ብዙም ሳይቆዩ : ተመልካቾች የአጨዋወት ስልቱ ከበፊቶች ስልቶች ይለያል: ይሻሻላል ብሎ እየጠበቀ ሳለ : መሪ ተወናዋዩና ረዳቶቹ ያለፈውን ቲያትሮች አስመስለው ሲያቀርቡ : ተመልካቾቹም ቲያትሩን ማየትና ማድነቅ ቀርቶ ተወናዋዮቹን ለማየትም አሻፈረኝ እያለ ይገኛል:: ይህንን ቲያትር ለማየት እንቢ እያሉ ያሉትን የቲያትሩን ተመልካቾችን : ደራሲውም : አቀነባሪውም ሆነ ተወናዋዮቹ ፍፁም ሊረዱ አልቻሉም:: የማይረባና የረከሰ ትወናቸውን : ውደዱልን : ተቀበሉት : አጩብጭቡለት : ጥሩ ነው በሉ በማለት ተመልካቾቹን እያስጨነቁት ይገኛሉ:: ተመልካቾቹም ግፊቱ ስለመረራቸው : ይህንን አስከፊና አስቀያሚ ጎሳ ላይ የተመሰረተውን ቲያትር አናይልህም:: አናጨበጭብልህም:: እስቲ የምትሆነውን እናያለን በማለት ቲያትሩን ላለማየትና መሪ ተወናዋዩንም ሆነ ረዳት ተወናዋዮቹን ከቲያትሩ ለማስወጣት ተፋጧል:: ቲያትር መድረስ : ማቀነባበርና መተወን ይቻላል:: ተመልካችና ተቀባይ የሌለው ቲያትር : ቲያትር ሊመስል አይችልም:: ቲያትር ተመልካቾቹን ማወቅ በጣም አስፈላጊ ነው:: ምክንያቱም ትክክለኛ ሰዎችን ዒላማ ለማድረግ : ፍላጎቶቻቸውን የሚያውቅና ፍላጎቶቻቸውን የሚናገር ይዘት ለመፍጠርና የቲያትሩን መልእክት ከተመልካቾች ጋር የሚስማማ መሆኑን ያረጋግጣል።

የዘመኑ የአብይ አህመድ ቲያትር ሲጀምር ታዳሚዎቹን አውቆ ነበር:: የታዳሚዎችን ፍላጎቶች ከማወቅ በተጨማሪ የቲያትሩ ይዘት ፍላጎታቸውን መናገር ጀምሮ ነበር::vመልእክቱም ተስማሚ መስሎ ነበር:: ግን ከቲያትሩ መግቢያ በስተቀር : የአብይ አህመድ ቲያትር ፍሬ ነገሩ ለታዳሚዎች የማይስማማ : ፍላጎታቸውን የናቀና መደምደሚያው የትያትሩን ውድቀት የሚያመጣ መሆኑን እያሳየን ነው:: ስለዚህ ጥሩ ቲያትር ፀሐፊ የተመልካቾቹን ፍላጎት የሚያውቅና የሚናገር በመሆን ለተመልካቾች የሚስማማ መልእክት ማቅረብ ይገባዋል:: ያማረና ያስደስታል ተብሎ ትልቅ ተስፋ ተጥሎበት የነበረው የአብይ አህመድ ቲያትር ተመልካቾችን እጅግ ተስፋ ከማስቆረጡም ሌላ ቲያትረኛውንና ቲያትሩን ላለማየትና ላለመስማት የሚያስወግዱበትን መንገድ እየፈለጉ ይገኛሉ::

አብይ አህመድም ቲያትሬንና ትወናዬን በግድ ካላያችሁ በማለት ከተመልካቾቹ ጋር ግብግብ ተያይዟል:: ለጊዜው ጠንካራ መስሎ ቢታይም : ከእሱ በፊት እንደነበሩት ቲያትር ደሪሲዎች : መሪ ተወናዋዮች : እቀነባባሪዎችና ረዳት ቲያትረኞች በቲያትራቸውና በትወናቸው ያልተማረኩ ተመልካቾች እንቅረው እንደተፏቸው ያለመገንዘቡ : አብይ አህመድ ምን ያህል በተሳተተ እምነት ውስጥ እየዋዠቀ እንዳለ ሊረዳ አልቻለም:: አጭበርባሪነቱ : ውሸታምነቱ : አስመሳይነቱ : አረመኔነቱ : ትላንትና የተናገረውን ረስቶ ዛሬ የትላንትናውን ተቃራኒ ሲናገር የማያፍር : ካለሱ አዋቂ እንደሌለ በማስብ ጤነኛ ባልሆነ ራሱን በማግነን ስሜት የሚሰቃይና የሾማቸውን ሰዎች እንደሰው የማያከብር ግብዝ ሰው መሆኑን ግልፅ አድርጎ ከማሳየቱ በፊት : የኢትዮጵያ ዘር እንጂ : የኦሮሞ የአማራ የትግራይ ወዘተ ዘር የለም በማለት ስለእንድነት : ስለአብሮ መኖር : የፃፈውን ቲያትርና ትወናን ሁላችንም እውነት መስሎን በያለንበት በውስጥና በውጭ መድረኮችና : በሬድዮም : በዩቱዪቡም : በቲቪም : በኦንላይንም በደስታ አይተን : እንዴት ዓይነት ግሩም የምንፈልገው የቲያትር ደራሲ :አቀነባባሪና መሪ ተወናዋይ በኢትዮጲያ ውስጥ ተፈጠረ? በማለት አደነቅነው:: መከራና ሃዘንን የሚፈጥሩ ብቻ ቲያትሮች ሲቀርቡለት የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝብ በአብይ አህመድ የመተዋወቅያው ቲያትር የተደሰተው ሰፊው ተመልካች : ተስፋውን አጣጥሞ ሳይጨርስ : አብይ አህመድም ሰፊውን ተመልካች የሚያስለቅስና ለምን ተፈጠርኩ የሚያሰኘውን ቲያትር ማሳየት ጀመረ::

አገርን አገር የሚያሰኘው ሕዝብ ነው:: ሕዝብን አጥፍቶ አገር መገንባት አይቻልም:: ቅድሚያ ለሕዝብ ደህንነት መሰጠት ይገባል:: የሚደረሰው : የሚቀነባበረውና የሚተወነው ቲያትር ለሕዝብ ደስታ ማድረግ የቲያትሩ ዓላማ መሆን አለበት:: አለበለዚያ ደራሲውና ቲያትሩ ተመልካች አልባ ይሆናሉ:: ዛሬ አብይ አህመድና ቲያትሩ ያጋጠማቸው እንዲ አይነት ውድቀት ነው::

ፈጣሪ ለአገራችን ሰላም : ለሕዝባችን አንድነት : ለመሪዎች ሰብዓዊነት : እስተዋይነትና ርህራሄነት ይለግሳቸው::

Leave a Reply

Your email address will not be published.

186601
Previous Story

በኢትዮጵያ ለተከሰተው ረሃብ ግሎባል አሊያንስ የድጋፍ ጥሪ አደረገ

Fano is the people
Next Story

የሚያሸንፈው ፋኖ ወይስ መንግስት?

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop