August 9, 2024
25 mins read

በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት በኢትዮጵያ – የህልም አለም – በክቡር ገና

454675300 908075688018961 958075838079961065 nኢትዮጵያ ሰሞኑን ከውስን የውጭ ምንዛሪ ተመን ወደ በገበያ ላይ ተመሰረተ ነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት መሸጋገሯ አብይ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ለውጥ ማድረጓን ያሳያል፡፡ ይህ ለውጥ በተለይ በምእራቡ አለም ተወድሷል፡፡ በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ደጋፊዎች ነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመን ተግባራዊ መደረጉ የኢኮኖሚ መሰረታዊያንን በመጥቀስ ገበያው ዋጋን እንዲወስን ያስችላል ሲሉ ይሞግታሉ፡፡ አያይዘውም ባለሀብቶች በመንግስት ቁጥጥር ከሚደረግበት የውጭ ምንዛሪ ተመን ይልቅ በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአትን ስለሚመርጡ ነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን ይስባል ሲሉ ያክሉበታል፡፡

በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት አመንጪዎች፣ አስፈጻሚዎችና ደጋፊዎች ነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ምንም እርኩስ የሌለበት ቅዱስ ነው ቢሉም የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ በሚገባ የሚያውቁና ስለሀገሪቱ የሚቆረቆሩ ወገኖች ደግሞ ይህ ስርአት በመጀመሪያ ደረጃ ከፍተኛ የዋጋ ንረት በማስከተል የማህበረሱን ህይወት ያናጋል ሲሉ ስጋታቸውን ይገልጻሉ፡፡ በእንቀርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚባለው ወትሮኑም ቢሆን የዋጋ ግሽበቱ ጣሪያ በነካበት ሁኔታ ነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመን ሲታከልበት ጉዳዩን ከድጡ ወደ ማጡ ያስገባዋል ሲሉም ይሞግታሉ፡፡ በዚያ ላይ በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ተግባራዊ መደረጉን ተከትሎ ከአለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት የተገኘውን የብድር ዕዳና አገልግሎት ለመክፍል የሚወጣው ወጪ በአጠቃላይ በንግዱ ማህበረሰብና በመላው ሸማቹ ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደሩ አይቀርም ሲሉ ጉዳይ አልጋ ባልጋ እንዳልሆነም ያሳስባሉ፡፡

ይህ በአንዳንድ ወገኖች ይበል የተባለና በሌሎች ደግሞ የተወገዘ ነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት በአለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም የሚደገፍና የሚወደስ ቢሆንም በበርካታ ሀገሮች ተሞክሮ የከሰረ ስርአት መሆኑን የሚያረጋግጡ ተጨባጭ ማሳያዎች አሉ፡፡ እ.ኤ.አ በ2003 በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአትን ተግባራዊ ያደረገችው ባንግላዴሽ መጀመሪያ አካባቢ ውጤት ብታስመዘግብም በአሁኑ ወቅት ግን ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ውስጥ ትገኛለች፡፡ እንዲሁም ጋና እ.ኤ.አ በ1986 በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአትን ተግባራዊ አድርጋ ሳይሳካላት ቀርቶ እ.ኤ.አ በ2003 ኪሳራ ወስጥ መውደቋን ይፋ አድርጋለች፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ዛምቢያም እ.ኤ.አ በ2003 ይንኑ ስርአት ተቀብላ ተግባራዊ ካደረገች በኋላ እ.ኤ.አ በ2022 መክሰራን አለም ይወቅልኝ ብላለች፡፡

በግልጽ እንነጋገር ከተባለ ከውጭ ምንዛሪ ጋር በተያያዘ ከሚከሰቱት ችግሮች መካከል አንዱ ዶላር የሁሉም የውጭ ምንዛሪዎች ማነጻጸሪያ መሆኑ ነው፡፡ ለምሳሌ የዩናይትድ ስቴት አሜሪካ የወለድ መጠን ሲያድግ ችግር የሚፈጥረው በአሜሪካ ኢኮኖሚና የባንክ ዘርፍ ላይ ብቻ ሳይሆን በከፍተኛ ዕዳ በተዘፈቁ ታዳጊ ሀገሮች ጭምር ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ ድሀ ሀገሮችን ይበልጥ ወደ አዘቅት የሚከት መሆኑን ማስተዋል አይሳነንም፡፡

እናም በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ላይ ያለንን መረዳት ታሳቢ አድርገንና በውጭ ምንዛሪ ፍላጎትና አቅርቦት መካከል ያለውን የሚዛን መዛባት ስጋት ስናጤን የማታ ማታ አለም አቀፉ ገበያ በአወንታዊም ሆነ በአሉታዊ መልኩ የውጤቱ ወሳኝ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

በገበያ ላይ ከተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ጋር በተያያዘ ይህ ስርአት ገበያውን አንደሚያረጋጋና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ከውድቀት እንደሚታደግም ተነግሮናል፡፡ ሆኖም ግን ይህ ስርአት ተግባራዊ ሳይደረግም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ከገባበት ቀውስ ማዳኛ በርካታ መላዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ መንግስት ለባንኩ መንቀሳቀሻ ካፒታል በመመደብ ወይም የቦንድ ሽያጭ በማድረግ ካፒታሉን ማሳደግና እንዲረጋጋ ማድረግ ይችላል፡፡ ተፈላጊውን ጥሬ ገንዘብ ለማሰባሰብ ቦንዱ በአክሲዎን መልክ ለገበያ ሊቀርብም ይችላል፡፡

ከዚህ በተለየ መልኩ ባንኩ በዋና ስራው ላይ ብቻ እንዲያተኩርና ውጤታማ እንዲሆን የተበላሹ ብድሮችንና መሰል የፋይናንስ ቀውሶችን የሚፈታና እልባት የሚሰጥ የተለየ ክፍል ማቋቋም ይቻላል፡፡ በተጨማሪም የባንኩን ሰማይ ጠቀስ ህንጻ ለሽየጭ አቅርቦ ካፒታሉን በማሳደግና ሌሎች ወጪ ቆጣቢ እርምጃዎችን በመውሰድ ከቀወስ እንዲወጣና በአስተማማኝ መሰረት ላይ እንዲቆም ማድረግ ይቻላል፡፡

የአሁኑ መንግስት ለባንኩ ውድቀት የቀድሞውን መንግስት ተወቃሽ ቢያደርግም ሁለቱም መንግስታት ለባንኩ እድገትና መጎልበት ትኩረት በመንፈግ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጤነኛ እንዳይሆን የየድረሻቸውን ተጽዕኖ አድርሰውበታል፡፡

ወደ በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ስንመለስ ይህ ስርአት ጥሩ አይደለም ጎጂ ነው ካልን ውስን የውጭ ምንዛሪ ተመን ጥሩ ነው ማለታችን ነው? ለረጅም ጊዜ በኢትዮጵያ ይሰራበት የነበረው ውስን የውጭ ምንዛሪ ተመን ጥሩ እንዳልነበረና የሚያሰራ እንዳልነበረ ለሁሉም ግልጽ ነው፡፡

በበርካታ ታዳጊ ሀገሮች የመልካም አስተዳደር እጦት ባለበት፣ ሙስና በተንሰራፋበትና የመጠባበቂያ ውጭ ምንዛሪ ክምችት ጠኔ ባለበት የውጭ ምንዛሪ ረሀብ ስለሚጠና መንግስት በውጭ ምንዛሪ ላይ ጥብቅ ቁጥጥር ከማድረጉም በላይ በርካታ ክልከላዎችንና እገዳዎችን ተግባራዊ ያደርጋል፡፡ በኢትዮጵያም የነበረው እውነታ ይኧው ነው፡፡

ውስን የውጭ ምንዛሪ ተመን ጥቁር ገበያው እንዲያብብና እንዲንሰራፋ የሚያደርግ ሲሆን ከዚህም ተጠቃሚ የሚሆኑት ዶላርና ዩሮ ማግኘት የሚችሉ ከመንግስት አካላት ጋር የሚሰሩ፣ የውጭ ምንዛሪ ከውጭ የሚላክላቸውና ከባንክ ሲስተም ውጭ በጥቁር ገበያ የሚመነዝሩና የጥቁር ገበያው አንቀሳቃሾች ናቸው የውስን የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት አትራፊዎች፡፡

በኢትዮጵያ እንደሚታወቀው የትይዩ ገበያው ከመደበኛው የባንክ ምንዛሪ ተመን እጥፍ ሲመነዘር እንደነበር የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ኢኮኖሚውን የሚያመነምን ብቻ ሳይሆን ባለሀብቶችን በተለይም በወጪ ንግድ ላይ ተሰማሩትን ባለሀብቶች የሚያቀጭጭና የሚያገኙትን የውጭ ምንዛሪ ከትይዩ ገበያው በግማሽ አሳንሶ በመደበኛው የባንክ ተመን እየከፈለ ጠፍንጎ አስሯቸው ኖሯል፡፡

በሌላ መልኩ ደግሞ ውስን የውጭ ምንዛሪ ተመን ተግባራዊ ሲያደርጉ የነበሩ አንዳንድ ፈጣን እድገት ያስመዘገቡ ሀገሮች ደግሞ ይህንኑ ስርአት ተከትለው ኢኮኖሚያቸውን ሲያረጋጉና እድገት ሲያስመዘግቡ ተስተውለዋል፡፡

በኢትዮጵያ ሁለት አይነት የውጭ ምንዛሪ ተመን የነበረ ሲሆን አንዱ መደበኛው ሌላው ደግሞ የትይዩ ወይም የጥቁር ገበያው ነበር፡፡ መደበኛው የውጭ ምንዛሪ ተመን እንደ ምግብ፣ መድሀኒትና ነዳጅ የመሳሰሉትን ወሳኝ ምርቶችን ከውጭ ለማስገባት ይውል የነበረ ሲሆን ተመኑም በብሄራዊ ባንክ ቁጥጥር የሚደረግብት ነበር፡፡

አብዛኛውን ጊዜ ጥቁር ገበያ የሚንሰራፋው በመደበኛው የውጭ ምንዛሪ ተመንና በገበያው የውጭ ምንዛሪ ፍላጎት መካከል ከፍተኛ ልዩነት ሲፈጠር ነው፡፡ በኢትዮጵያ የጥቁር ገበያው ምንዛሪ ከመደበኛው እጥፍ ሲሆን በመደበኛው ተመን የውጭ ምንዛሪ ማግኘት ያልቻሉ አስመጪዎች የቅንጦት እቃዎች የሚባሉትን ሸቀጦች ለማስገባት፣ ለአንዳንድ የንግድ ስራዎችና ለጉዞ ጥቅም ላይ ሲውል ቆይቷል፡፡

ከብዙ አቅጣጫ ሲታይ ሁለት አይነት ወይም መንታ የውጭ ምንዛሪ ተመን ተግባራዊ ማድርግ የታቀደና ፈጣን እድገት ለማስመዝገብ ያስችላል፡፡ ሁለቱንም የውጭ ምንዛሪ ተመኖችን ጥቅም ላይ ማዋል በጣም አስፈላጊና እስከዚህም አንገብጋቢ ያልሆኑ ግብይቶችን በተለያየ የውጭ ምንዛሪ ተመን በማስተናገድ መንግስታት ለኢኮኖሚ እድገትና ለሀገር ደህንነት ወሳኝ ሚና ላለቸው ዘርፎች ቅድሚያ እንዲሰጥ ያስችለዋል፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ መደበኛ የውጭ ምንዛሪ በአነስተኛ የምንዛሪ ተመን እንደ ምግብ፣ መድሀኒትና ነዳጅ ያሉትን ወሳኝ ምርቶች ወደ ሀገር ለማስገባት ይረዳል፡፡ እነዚህ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋገ ለህብረተሰቡ መቅረባቸው መሰረታዊ ፍላጎቶች እንዲሟሉና ማህበራዊ መረጋጋት እንዲሰፍን ያስችላሉ፡፡ ከዚህም በላይ ተፈላጊ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ መገኘታቸው የዋጋ ንረት እንዳይከሰት፣ የማህበሰብ ጤና እንዲጠበቅና ምርታማ እንዲሁን በማስቻል ኢኮኖሚያዊ ቀውስ እንዳይፈጠርና ዘላቂ ልማት እንዲረጋገጥ ይራደሉ፡፡

በሁለተኛ ደረጃ ምቹ የሆነ የውጭ ምንዛሪ ተመን የሀገሬው ገንዘብ (ብር) ጠንካራና የተረጋጋ እንዲሆን በማድረግ የውጭ ኢንቨስትመንትን መሳብ ይችላል፡፡ የውጭ ኢንቨስትመንት ሲያድግ ደግሞ የቴክኖሎጂ ሽግግርን፣ የመሰረተ ልማት እድገትንና የስራ እድልን በማስፋት ለፈጣን ኢኮኖሚያዊ እድገት አስተዋጽኦ ያበረክታል፡፡

የጥቁር ገበያው በበኩሉ አንገብጋቢ ያልሆኑ ምርቶችን ወደ ሀገር ለማስገባት ያለውን ፍላጎት በማስተናገድ የመደበኛው የውጭ ምንዛሪ ክምችት እንዳይሟጠጥ ያግዛል፡፡ በመሆኑም ሁለቱንም የውጭ ምንዛሪ ተመኖች መጠቀም መደበኛው ውጭ ምንዛሪ ተመን ለቅንጦት ሸቀጦች ውይም አንግብጋቢ ላልሆኑ ምረቶች ግብይት ከማዋል ይልቅ ወሳኝ ለሆኑ ግብአቶች እንዲውል በማድረግ ሀገሪቱ ያላትን ወስን የውጭ ምንዛሪ በአግባቡ ለመጠቀም ያስችላታል፡፡ ይህም መንግስት የውጭ ምንዛሪው አለአግባብ እንዳይወጣና የክፍያ ሚዛኑም እንዲጠበቅ ያግዘዋል፡፡

በተጨማሪም መንታ የውጭ ምንዛሪ ተመን ጥቅም ላይ ማዋል መንግስት በገንዘብ ፖሊሲው ላይ የተሻለ ቁጥጥር እንዲኖረው ያስችለዋል፡፡ መንገስት የውጭ ምንዛሪ ተመኑን በብሄራዊ ባንክ አማካይነት በመቆጣጠር የዋጋ ንረትን፣ የወለድ ተመንንና አጠቃለይ ኢኮኖሚው አንዲረጋጋ ማድረግ ይችላል፡፡ ቁጥጥር የሚደረግበት የውጭ ምንዛሪ ተመን ለኢኮኖሚ ቀውስ የሚዳርግ የገንዘብ ዋጋ መርከስን ይከላከላል፡፡

እናም የኢትጵያ መንግስት በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ምርጫ የሌለው ምርጫዬ ነው ካለ ይህን አወዛጋቢ ስርአት ተግባራዊ ሲያደርግ በርካታ ፈታኝ ሁኔታዎች ከፊቱ እንደሚጋረጡ ታሳቢ አድርጎ ወገቡን ማጥበቅ ይጠበቅበታል፡፡

ከነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ጋር በተያያዘ ስለ ኢኮኖሚክስ አንዳንድ ነጥቦችን ማንሳት ተገቢ ነው፡፡ በዛሬ ጊዜ ኢኮኖሚክስ ከገሀዱ አለም እውነታ ጋር የተፋታ ይመስላል፡፡ ዘርፉ ከራሱ መንጭቶ ወደ ራሱ በሚፈስ መረጃና አስተሳሰብ የረካ ከመሆኑም በላይ የዘርፉ ምሁራንም ለአቻዎቻቸው ሀሳብና አስተያየት ብቻ ትኩረት የሚሰጡ ሆነዋል፡፡ በመሆኑም ኢኮኖሚክስ አስፈላጊነቱ እየቀነሰና ችግር ፈቺነቱም አጠያያቂ እየሆነ መጥቷል፡፡

የገሀዱ አለም እጅግ ውስብስብ ነው፡፡ የኢኮኖሚክስ ጥናትና ምርምር ምርቱ፣ ስርጭቱና ግብይቱ እንዴት እየሰራ እንዳለ አጠቃላይ ግንዛቤ ይሰጥ እንደሆን እንጂ የገሀዱን አለም ገጽታ በተሟላ መልኩ አይገልጸውም፡፡ በርካታ ኢኮኖሚስቶች የኢኮኖሚውን ሁኔታ ለመተንበይ ሞዴሎችን ቢጠቀሙም የገሀዱ አለም ሁኔታ ወስብስብ በመሆኑ ትንበያው ከገሀዱ አለም እውነታ ጋር ሲጣረስ ይታያል፡፡ ስለሆነም የኢኮኖሚክስ ሞዴሎች በአንድ ርእሰ ጉዳይ ላይ ግንዛቤ እነዲኖረን የሚጠቅሙ ቢሆኑም በመንግስት ወይም በንግድ ስራዎች ላይ ቀጥተኛ ተጽእኖ ማሳረፍ የለባቸውም ወይም መንግስትና የንግድ ስራዎች ሞዴሎቹን እንዳለ ወስደው ተግባራዊ ማድረግ አይጠበቅባቸውም፡፡

ኢትዮጵያ በቅርቡ ተግባራዊ ያረገችው ከውስን የውጭ ምንዛሪ ተመን ወደ ገበያ መር የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት ያደረገችው ሽግግር ከላይ በተጠቀሰው የኢኮኖሚክስ ሞዴል ምክረ ሃሳብ መሰረት የተከናወነ ነው፡፡ በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ትረካ መሰረት ኢትዮጵያ በገበያ ላይ የተመሰረተ የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአትን ተግባራዊ ካደረገች ምርትና የንግድ ስራዎች ያብባሉ፣ የውጭ ኢንቨስትመንት ወደ ሀገር በገፍ ይፈሳል፣ ህዝቡ ይበለጽጋል፣ ሀገሪቱም እዳዋን የመክፈል አቅሟ ይጎለብታል፣ ወዘተ …. ተብሏል፡፡

መሪዎቻችን እርምጃውን የወሰዱት የኢኮኖሚክስ ሳይንስን መሰረት አድረገው እንደሆነ ቢነግሩንም ኢኮኖሚክስ ለተወሰነ ኢኮኖሚያዊ ህመም ፈውስ የሚሆን ፍቱን መድሀኒት ማዘዝ እንደማይችል ልብ ይሏል፡፡

የገጠመንን ችግር ለመፍታት ከዚህ ቀደም ተፈትኖ የወደቀ ስልት ሳይሆን ተግባራዊ መድርግ ያለብን በልዩ ሁኔታ ችግራችንን የሚፈታና እየወደቀን እየተነሳን የምናሳካውና ከኛ ነባራዊ ሁኔታ ጋር የሚጣጣም መላ ነው የሚያስፈልግን፡፡ ከዚህ በተረፈ በህልም አለም ያለን ይመስል የገሀዱን አለም ውስብስብ ሁኔታ ዘንግተን በነጻ ገበያ የሚወሰን የውጭ ምንዛሪ ተመን ስርአት የጽድቅ መንገድ ነው የምንል ከሆነ አጉል የተስፋ ዳቦ መግመጥ ነው፡፡ እንግዲህ መሪዎቻችን የሳቱ እዚህ ላይ ነው፡፡

የውጭ ምንዛሪ ተመን ለውጡን በተመለከተ መሪዎቻችን ያለምንም ተጨባጭ መነሻ ለውጡ ብልጽግና እንደሚያጎናጽፍና ስኬትን እንደሚያቀዳጅ አጋናው ከመናገራቸው ይልቅ በግልጽ ‹‹ ሕዝቤ ሆይ በእውነቱ ይህ ለውጥ በእርግጠኝነት ውጤት ስለማስገኘቱ አናውቅም›› ቢሉ የተሸለ ይሆን ነበር፡፡

እርግጥ ነው በህዝቡ አይን ሲታይ ለአብዛኞቹ መሪዎች በጣም አስቸጋሪ መልስ ‹‹ እኔ አላውቅም›› የሚለው ነው፡፡ አንዳንዴ መሪዎች ‹‹ እኔ አላውቅም›› የሚል ምላሽ መስጠታቸው በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ምክንያቱም ፈታኞች እራሳቸው መልሱን ላያውቁት ይችላሉና፡፡ መሪዎች መልስ ነው ብለው የማይጨበጥ ተስፋ ከመስጠታቸው ይልቅ ‹‹ ይህ ከባድና አስቸጋሪ ችግር መሆኑን እንረዳለን፡፡ እናም በዚህ ወቅት ይህንን ተግባራዊ ለማድረግ ወስነናል፡፡ በቀጣይነት ግን በሂደት ሁኔታውን እያየን ለውጦችንና ማሻሻያዎችን ተግባራዊ እናደርጋለን›› ቢሉ መልካም ነበር፡፡ መሪዎቻችን ግን አላደረጉትም፡፡

ውድ አንባቢዎች ኢትዮጵያ ከአለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ደጃፍ ለገንዘብ ድጋፍ ምጽዋት መቆሟ ‹‹ እንኳን ደስ አለን›› የሚያሰኝ አይደለም፡፡ ህዝቡ ስለ ነጻ የውጭ ምንዛሪ ተመኑ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡ በጭለማ ውስጥ ነው ያለው ማለት ይቻላል፡፡ ህዝቡ በሚቀጥሉት ጊዚያት ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ስለመፈጠሩም ሆነ ስላለመፈጠሩ እርግጠኛ አይደለም፡፡ በምንዛሪ ለውጡ ምክንያት ስለሚከፍለው መስዋዕትነትም መገመት እንኳ አይችልም፡፡ ነገር ግን የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ህዝቡ መሪዎቹ ጥሩ ነገር ይዘውለት እንዳልመጡ ይረዳል፡፡

በስተመጨረሻም ነገራችንን ስንቋጭ የእውነተኛ ኢኮኖሚ ልማትና እድገት ስኬት ቁልፍ ጉዳይ የአለም አቀፍ የገንዘብ ተቋም የፖሊሲ ግቦች፣ የዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች የተራቀቁ የኢኮኖሚ ትንታኔዎችና ሞዴሎች ሳይሆን ህዝቡ በነጻነት አምርቶና የንግድ ስራዎችን ከውኖ ሀብት መፍጠር ሲችል እንደሆነ መዘንጋት የለበትም፡፡

መሪዎቻችንን ከህልም አለም ያንቃልን – አሜን!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

192986
Previous Story

አብይአህመድ “ደካማ፥ አቅመ ቢስ፥ አረመኔ፥ በስልጣን ጥም ያበደ፥ ክፉ ነው” አቶ ገዱ እንዳርጋቸው

192994
Next Story

በጎጃም ተሽከርካሪዎች ታገዱ | የባህርዳር ኦፕሬሽን – “ስልጣኑን ውሰዱ” ስልጣን ለመልቀቅ የጠየቁ 4 ባለስልጣናት| ሃላፊው ተሸኘ | ጄ/ሉ መርዶ ላኩ “ዋና ዋና መስመሮች በፋኖ ተይዘዋል”|

Latest from Blog

“መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የሚለው የዲያስፖራ ከንቱ አታካራ! – ክፍል ሁለት

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com) በአንዳንድ ስብሰባዎችና የሕዝብ መገናኛ መድረኮች የሚታየው የአንዳንድ ዲያስፖራዎች  “መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የበከተ ከንቱ አታካራ በልጅነታችን ወላጆቻችን ትምህርት እንዲሆነን ይተርኩልን የነበረውን ከጫጉላ ወጥተው ጎጆ ለመመስረት የታከቱ ሁለት ያልበሰሉ ባልና ሚስትን ታሪክ

መነሻችን አማራ መድረሻችን አማራ እና ወያኔያዊ መሠረቱ

የማይወጣ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል። የዛሬን አያድርገውና የትግሬ ልሂቆች “ትግራይ የጦቢያ መሠረት ናት ።  ጦቢያ ያለ ትግራይ፣ ትግራይ ያለ ጦቢያ ሊታሰቡ አይችሉም” በማለት ጦቢያዊ ከኛ ወዲያ ላሳር እያሉ አለቅጥ ይመጻደቁ፣ ይኩራሩ፣ ይታበዩ ነበር። ወያኔ

አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱባቸው ወንጀሎች ጥፋተኛ ተባሉ

ለአመታት በእረስር ላይ የሚገኙት  አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱባቸው የጥላቻ ንግግር ማሰራጨት እና የዕርስ በዕርስ ግጭት መቀስቀስ ወንጀሎች ጥፋተኛ መባላቸው ታውቋል፡፡ አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱበት ክሶች በዛሬ ቀጠሮ የጥፋተኝነት ፍርድ የሰጠው የፌደራል ከፍተኛ

ከ”ችርቻሮ” ድል አልፎ ለመሄድ የአንድነት አስፈላጊነት – ግርማ ካሳ

በአሁኑ ጊዜ ሁለት የፋኖ አሰላለፎች አሉ:: መኖር ያልነበረበት:: አንከር ሜዲያ ከሁለቱም አሰላለፎች፣ ሁለት ፋኖ መሪዎች ጋር ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ ሁለቱን አደመጥኩ፡፡ በሰማሁት ነገር ተደስቻለሁ:: ትልቅ ተስፋ እንድሰንቅም አድርጎኛል:: የአማራ ህዝባዊ ድርጅት የፖለቲካ
Go toTop