መጻሕፍተ መነኮሳት ፡-የፓትርያሪክ፣ የጳጳሳትና የሌሎችም መነኮሳት የግብር ሚዛን!

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)

መጻሕፍተ መነኮሳትና የቤተክርስትያን ሊቃውንት የሚሉት መኩሰ ሞተ ነው፡፡ መንኩሰ ሞተ ማለትም አንድ ሰው ሲመንኩስ ሥጋውን አድቅቆ ወይም ገድሎ መንፈሱን ግን ያገዝፋል ማለት ነው፡፡ ዛሬ የምናየው ግን የተገላቢጦሹን ነው፡፡ በአሁኑ ዘመን የምናየው ገላውን እንደ ቦክሰኛ ያደነደነና አካሉን በልብስ ያሸበረቀ መንፈሱን ግን የበሬ ሸኮና እንዳረፈበት እምቧይ ያፈረጣና ያፈሰሰ  ነው፡፡

ይህ ለኢትዮጵያ እንግዳ ነገርና መቅሰፍት ነው። ዓለም እንደሚታወቀው መንፈሳዊና ሃይማኖታዊ እሴት ኢትዮጵያን በአለት ላይ የገነባ ፀጋ ነው፡፡ ይኸንን ፀጋ እየተመገቡ በሰላም ጊዜ በነፍስ አባትነት፣ በሽምግልና፣ በመምህርነትና በፈላስፋነት የሚያገለግሉ፤ ሰላምን የሚነሳ ሰይጣን የላከው ወራሪ ሲመጣም ጦር ሜዳ ሄደው እስከ መዋጋት የሚደርሱ የሃይማኖት አባቶች ቁጥር እልቆ መሳፍርት አልነበረውም፡፡

የኢትዮጵያ መነኮሳት ዓለም ስትበቃቸው የሚመመንኩሱትና የምንኩስና ኑሯቸው የሚመሩት በመጻሕፍተ መነኩሳት መጻሕፍት በመመራት ነው፡፡

መጻሕፍተ መነኮሳት የመነኮሳትን ቃል ኪዳን፣ ግብር፣ ታሪክ፣ ተጋድሎና ተመከራም የሚያገኙትን ትሩፋት የሚያስተምር ተአዋልድ መጻሕፍት አንዱ ነው፡፡ የአዋልድ መጻሕፍት ትርጉም የመጻሕፍት ልጆች ማለት ሲሆን ወላጆችም ብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳን ናቸው፡፡

ተብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳን የተወለዱት መጻሕፍተ መነኮሳትም ሶስት ናቸው፡፡

ልጅ አንድ፡- ማር ይስሐቅ ስለመነኮሳት ቃል ኪዳን፣ ግብር፣ጾምና ተጋድሎ ያስትምራል፡፡

ልጅ ሁለት፡- ፊልክስዩስ ስለ መነኮሳት የገዳም ታሪክና ተጋድሎ ያስረዳል

ልጅ ሶስት፡- አረጋዊ መንፈሳዊ መነኮሳት መከራን ተቀብለው ስለሚያገኙት ፀጋ ወይ ትሩፋት ያስተምራል፡፡

አረጋዊ መንፈሳዊ ሥርዓተ ብሕትውናን ጳውሎስ፤ ሥርዓተ ምንኩስናን ደሞ እንጦስ እንደ ጀመረው ያስተምራል፡፡ [1] የናጠጠ ባለጠጋ ልጅ የነበረው እንጦስ ሥርዓተ መንኩስናን የጀመረው ቤሳ ሳያስቀር ሐብቱን ሁሉ ለዓለማውያን ትቶ ነው፡፡ የእርሱን ፈለግ በመከተል ቁጥር ስፍር የሌላቸው የኢትዮጵያ መነኮሳት ይህችን ዓለም ንቀው ገዳም ገብተው ቃል ኪዳንን እንደጠበቁ፣ በጾም አካላቸውን አድቀው በፀሎት ደግሞ መንፈሳቸውን አጠንክረው ሰይጣን የላከውን በፀሎት ብቻ ሳይሆን በመሳሪያም ታግለው እንዳለፉ ታሪክና ብቻ ሳይሆን ብዙ ቋሚም በዓይኗ በብረቷ ያየው ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ማን ቼ ፖለቲካ - ሲና ዘ ሙሴ 

ፊልክስዩን(ከመጻሕፍተ መነኮሳት አንዱ) “የዋህ ሁን ለክፉ ግን የዋህ አትሁን” [1] የሚለውን መልዕክት ተከትለው መነኮሳት በእንቁላል ቀቃይ ባንዳዎች እየተመራ ሕዝብ የፈጀውን ፋሽሽት መሳሪያ ታጥቀው እንደተዋጉ የሚታወቅ ነው፡፡ የበቁ መነኮሳት  በደብረ ሊባኖስና በሌሎች ገዳማትም እንደተረሸኑ አፍ ቢኖራቸው ስጋቸውን የበሉት ሜዳዎችና ተራሮች እንደዚሁም ደማቸውን የጠጡት ወንዞች የሚመሰክሩት ነው፡፡

ከሰላሳ ዓመታት ወዲህ ግን ምንኩስና እንደ እንጦስና የቀድሞ ኢትዮጵያውያን አባቶች ከባለጠጋነት ወደ ድህነት የሚሸጋገሩበት መንፈሳዊ ድልድይ ሳይሆን ከድህነት ወደ ባለጠጋነት የሚሸጋገሩበት አካላዊ መሰላል እንደሆነ ሁሉም በየሰፈሩ የሚያየው ነው፡በፓትርያሪክነት፣ በጵጵስናና በተለያዩ የክህነት መንበሮች የተቀመጡ መነኮሳት የመጻሕፍተ መነኮሳትን መለኮታዊ መመሪያ እረግጠው ለመመረጥ ቅስቀሳ ሲያደርጉ፣ ለጥቅም በካድሬነት ነፈሰ ገዳይ ገዥዎችን ሲያገለግሉ፣ ገንዘብ ሲመዘብሩ፣ በደመወዝ ከምእመናን ጋርና እርስ በርሳቸው ሲጨቃጨቁ መታየታቸው ወዘተርፈ እንኳን መለኮትን ሰይጣንንም የሚያስገርም ነው፡፡

ማር ይስሐቅ መነኮሳት እንዴት መኖር እንዳለባቸው ሲያስተምር “ለሰውነትህ እረፍትን ኅድዓትን ታገኝ ዘንድ ዘወትር መጽሐፍትን መመልከት ውደድ፤ ከንዑሳን ሕጣውእ ተከልከል” ይላል፡፡ ንዑሳን ሕጣውእንም “ማየት፣ መስማት፣ ያለመጠን መብላትና መጠጣት ናቸው” ይላል፡፡[3]  ማር ይስሐቅ ማስተማሩን ሲቀጥልም “የእንጨት ብዛት እሳቱን እንደሚያበዛው የምግብ ብዛትም ዝሙትን ያበዛል፡፡ በልቼ ጠጥቼ፤ አይቼ ሰምቼ፣ ንጽሕናየን ጠብቄ ከሴት ርቄ መኖር ይቻላል አትበል” ይላል፡፡ [4]ማር ይስሐቅ መነኮሳትን ስለገንዘብ ማሳደድ ሲያስጠነቅቅም “ድሀ ትሆን ዘንድ ውደድ፣ ተርታ ልብስ መልበስን ውደድ” ይላል፡፡ [5]

መለኮት ምስጋና ይግባውና ኢትዮጵያ የማር ይስሃቅንም ሆነ የሌሎቹን መጻሕፍት መነኮሳት ትዕዛዛት በትክክል የፈፀሙ ባህታውያን ገዳም ነበረች፡፡ ዛሬ ግን የእውነተኛ መነኩሴ ድርቅ መቷት በምእመናን መስዋእትነት፣ ደምና አጥንት የራሳቸው ወንበርና ጥቅም አስጠብቀው ቤተክርስትያኗን ሊያፈርሱ ድንጋዩን ሁሉ ሲፈነቅሉ ለሚያድሩ ከንቱዎች ተላላኪ ሆነው የሚያገለግሉ ብፁእ ቅዱስ ነን እያሉ በመለኮትም በሚቀልዱ ፓትርያሪክና ጳጳሳት ተሞልታለች፡፡  ድንበር ተሻግሮ የስንቱን ሕይወት እንደሚታደገው የዓለም ረጅሙ ወንዝ ዓባይ ስንቱን ውቂያኖስ ተሻግራ የዓለም ቤተመጻሕፍትን በመንፈሳዊ ሐብት የምትመግበው ኢትዮጵያ ዛሬ ቀን ጥሏት ጠንካራ አማኝና የመንፍስ አባት ጣልልኝ እያለች  እጆቿን ወደ ሰማይ ዘርግታ ትማጸናለች፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  [የሚኒሶታው ደብረሰላም መድሃኔዓለም ጉዳይ] - ማን ለጠበቃ ፈረመ???

ኢትዮጵያውያን ሆይ! ፓትርያሪክ፣ ጳጳሳትም ሆነ ሌሎቹ መነኩሳት የሚመዘዘኑት በመመዘኛው መጻሕፍተ መነኮሳት ነው፡፡ ስለዚህ ለመደገፍም ሆነ ለመንቀፍ በመጀመርያ መጽሐፈ መነኮሳትን አንብቡ፡፡ አንብባችሁም ፓትርያሪኩ፣ ጳጳሳትና ሌሎችም መነኩሳት ምናልባትም አንብበውት የማያውቁትን መጻሕፍተ መነኮሳት  እንዲያነቡ፣ አንብበውም በትእዛዛቱ እንዲገዙ፣ ካልቻሉም መጽሐፍቱ እንደሚያዝዙት ቆባቸው ተአጥር፣ ካባቸውንም ተምድር ጥለው ማታላለን እንዲያቆሙ ጠይቁ፡፡ አመሰግናለሁ፡፡

ዋቢ፡-መጻሕፍተ መነኮሳት 1928 ዓ.ም ብርሃንና ሰላም እትም

  1. አረጋዊመንፈሳዊ፡ መቅድም ገጽ 3
  2. ፊልክስዩስ ገጽ 252-253
  3. ማር ይስሐቅ ገጽ 10
  4. ማር ይስሐቅ ገጽ 57
  5. ማር ይስሐቅ ገጽ 14

 

ይቆይን!

ሐምሌ ሁለት ሺ አስራ አምስት ዓ..

2 Comments

  1. Realistically powerful !!! Yes, if we are desperate enough about why and how we keep going not up but very deep down in all aspects of our lives ( politically, socio-economically, morally, culturally , psychologically and above all spiritually ) ; we seriously and desperately need to get out of our very self- degrading and shameful comfort zone of very ugly hypocritical way of doing things and face the very hard reality with a very strong sense of honesty !!!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share