ክልል መፍትሔ አይደለም! – አንዱ ዓለም ተፈራ

አንዱ ዓለም ተፈራ
ሐሙስ፡ ነሐሴ  ፭ ቀን፣ ፳ ፻ ፲ ፬ ዓ. ም. (8/11/2022)

የኢትዮጵያ አስተዳደራዊ መዋቅር፤ በረጅም ጊዜ ሂደት፤ ከነበረበት እንዳመቺነቱ ሲስተካከል ኖሯል። በዚህ ጸሐፊ የልጅነት ወቅት፤ ባሌ ከሐረር ተቀንሶ ራሱን የቻለ ክፍለ አገር ሆኗል። ሸዋ ክፍለ አገር እንደሰፋና ጎንደር ክፍለ አገር እንደጠበበም አስተውሏል። ባጠቃላይ ለአስተዳደር አመቺነቱ ሲባል፤ ክፍለ አገራት ብቻ ሳይሆኑ፤ አውራጃዎችና ወረዳዎችም ይህ መስተካከል ተደርጎባቸዋል። ይህ ሀቅ የተቀየረው፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር በሥልጣን ላይ ሲወጣ ነው። ከክፍለ አገር አስተዳደር ወደ ክልል እንዴትና ለምን ተቀየረ? ክልል ምንድን ነው? ለምን ለመሠረተ? የክልል የመጨረሻው ግብ ምንድን ነው? ጠቀሜታና ጉዳቱ ምንድን ናቸው? እኒህ ናቸው የዚህ ጽሑፍ ትኩረቶች።

ክልል፤ ከአስተዳደር አመቺነት ወጥቶ፤ የማንነት ፖለቲካ የለበሰ መዋቅር ነው። በኢትዮጵያ፤ ኢትዮጵያዊ ማንነት ተቀይሮ፤ ትግሬ፣ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ሶማሊ፣ አፋር፣ ሲዳማ፣ ወላይታ፣ ቤንሻንጉል፣ አደሬ/ሐረሬ፣ አዲስ አበቤ፣ ጋምቤላ፣ ደቡብ ኢትዮጵያዊ የሚል የፖለቲካ ማንነት ተፈጠረ። በዚህ ስሌት፤ እያንዳንዱ ክልል የራሱ የሆነ መንግሥት አለው። እናም፤ ሌሎች በዚያ እንዳይገቡ፣ በክልሉ ፖለቲካ እንዳይሳተፉ፣ በዚያ ቦታ ተገኝተው የራሳቸውን ቋንቋ እንዳይናገሩ፣ ሀብት አፍርተው እንዳይኖሩ፣ ልጆቻቸውን በራሳቸው ቋንቋ እንዳያስተምሩ፣ . . . ሌሎች ገደቦችም ተቀምጠዋል። ይህ ማለት፤ ኢትዮጵያ የኒህ ክልሎች ስብስብ እንጂ የኢትዮጵያዊያን አይደለችም፤ ማለት ነው። እኒህ ክልሎች የየራሳቸው ማንነት ብቻ ካላቸው፤ ከኢትዮጵያዊነት ጋር ያላቸው ዝምድና፤ ጥቅም የመቀራመቻና ከነሱ ይልቅ ለኔ የበለጠ ይድረሰኝ! ብሎ መከራከሪያ መድረክ ላይ መገኘታቸው ብቻ ነው። ይሄ ወደ የት ያመራል? ለምን ይሄን ማድረግ ተፈለገ?

“የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ክልልን ሲመሠረት፤ ዋና ምክንያቱ ምንድን ነበር? “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” “ወከልኩ ብሎ የታገለለትና ነፃ ሊያወጣው የፈለገው፤ የኢትዮጵያን ሕዝብ ስድስት ከመቶ የሆነውን የትግራይ ወገናችን ነው። እውነት ይሄን ወገናችን ይወክለው ነበር! የሚለውን ለጊዜው እንግታውና፤ ሥልጣን ሲወጣና ከዚያም እስካሁን የያዘው ስሙ እንደሚያመለክተው፤ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ነው! እንበል። ይሄን ስድስት ከመቶ የሆነውን ክፍል የሚወክል ድርጅት፤ ዘጠና አራት ከመቶ የሆነው ክፍል ሊገዛና ሊቆጣጠር የሚችለው፤ አንድም በብልጠት አለያም በጉልበት ነው። “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር”፤ በዚያን ጊዜ በጦርነቱ ሂደት ጉልበቱን ያፈረጠመበትና መላውን የአገራችንን መንግሥት መገንባትና ማዋቀር ሂደቱን የተቆጣጠረበት ሁኔታ ነበር። እናም ይህ ግንባር ሁለቱንም መንገዶች ተጠቅሞ፤ የሁለቱም ዘዴዎች ለዛ እስኪሟጠጥ ድረስ ገዛ። እኒህን ሁለት ዘዴዎች እንመርምር።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የበረከትና አላሙዲ ልሳን (ከኢየሩሳሌም አረአያ)

በብልጠት እንዴት ገዛ? አገርን ከኋላ ቀርነት ለማውጣት የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ ይሄ ጸሐፊ በታታሪነት የተሳተፈበት፤ በአስራ ዘጠኝ መቶ ስድሳ ስድስት ዓመተ ምህረት የተነሳበትን ዓላማ፤ በወቅቱ የተደራጀና ጠንካራ ዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ ድርጅቶች ባለመኖራቸው፤ የአረመኔው መንግሥቱ ኃይለማርያም ደርግ መንግሥት፤ ክፍተቱን ሞልቶ ሥልጣኑን ተቆጣጠረ። ሆኖም ግን፤ መንግሥቱ ኃይለማርያም ራዕይም ሆነ ብቃቱ ስላልነበረው፤ በጉልበት መግዛት ያዘ። የጉልበት ግዛት መጨረሻው ተገዢ እስኪጎለብት ነውና፤ ሕዝቡ ሲነሳ፣ አገሪቱን እንዳትሆን አድርጎ፣ መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ጅራቱን ቆልፎ ዝምባብዌ ፈረጠጠ። በክፍተቱ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ሰተት ብሎ አዲስ አበባ ገባ። ይሄ ስድስት በመቶ የሆነውን የአገራችን ወገን ወከልኩ የሚለው ግንባር፤ በደርግ የነበረውን አረመኔነት በብልጠት ቀጠለበት። በዕድገቱ፤ መጀመሪያ “የትግራይ ነፃ አውጪ ግንባር”ን አጠፋ። የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ሕብረትን አጠፋ። የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲን አጠፋ። ከሻዓቢያ ጋር ሆኖ ጀብሃን አጠፋ። ከማንም ሌላ ድርጅት ጋር አብሮ የመሥራት ችሎታውም ሆነ ፍላጎቱ ስላልነበረው፤ ሌሎችን ለማጥፋት እንጂ፤ በማንኛውም መንገድ አብሮ ለመተባበርም ሆነ ለመወዳደር አቅሉ አልነበረውም። እናም ራሱ ጠፍጥፎ የፈጠራቸውን የአማራ፣ የኦሮሞ፣ የሌሎችንም ድርጅቶች ይዞ፤ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር፤ (ኢሕአዴግ) በማለት ሥልጣን ላይ ወጣ። ይሄን ቋሚ የሚያደርግና የግንባሩን ዕድሜ የሚያስረዝም ሕገ-መንግሥት አወጣ። ይህ ብልጠቱ ነው።

በሌላ በኩል ደግሞ፤ በዚያ ወቅት አረመኔው የመንግሥቱ ኃይለማርያም ደርግ መንግሥት ተንኮታኩቶ ሲወድቅ፤ በቦታው የተገኘ ሌላ ጉልበታም ባለመኖሩ፤ የፈለገውን ለማድረግ ተመቸው። ይሄን ጉልበተኛ ወደ ትክክለኛ መንገድ እንዲገባ የሚያስገድደው ምንም ኃይል አልነበረም። እናም በብልጠትና በጉልበት አገራችንን ገዛ። የብልጠቱና ጉልበቱ ለዛ ሲያልቅ ደግሞ ጅራቱን ቆልፎ መቀሌ ገባ። እንግዲህ ይሄ ክልል የሚለው ግንዛቤ፤ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ቅምርና ስሌት ከሆነና የሱ መገልገያ ከነበረ፤ ይሄ ቀማሪው “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ከሥልጣን ሲወገድ፤ ክልል ለምን አብሮ አልተወገደም? ይሄን ጥያቄ ከመመለሴ በፊት፤ ከላይ የጠቆምኩትን የክልልን መመስረት ጥቅምና ጉዳት እዚህ ላንሳው። ክልል፤ አንድ ገዢ አካል፤ ሌሎችን ለማስገደድ ወይንም ለማታለል የፈጠረው መሰሪ የፖለቲካ ዘዴ ነው። እናም ቋሚነቱ የፈጠረው ገዢ አካል በሥልጣን ላይ እስካለ ድረስ ብቻ ነው። ወይም ደግሞ፤ የዚያን ፈጣሪ ገዢ አካል እምነትና ፍላጎት “የኔ!” ያለ ሌላ ገዢ አካል ሲተካ ነው። “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር”፤ የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅትን፣ ብሔራዊ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄንና ሌሎችን ጠፍጥፎ ጋግሯል። ከሶስት ዓመታት በፊት፤ ሕዝቡ በየቦታው አምጾ ሲነሳ፤ የኒህ ድርጅቶች መሪዎች፤ ፈጣሪያቸውን “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ወጊድ ብለው፤ ሥልጣኑን ተረከቡ። እኒህ ሥልጣን የተረከቡ መሪዎች፤ በዚያን ወቅት የፖለቲካ ዓለማም ሆነ ለኢትዮጵያ የሚሆን ራዕይ አልነበራቸውም። ድንገት ሥልጣን በጃቸው የገባው መሪዎች፤ የሚያውቁትና ያደጉበት፤ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” የፖለቲካ ቅመራና፤ በቦታው ተዋቅሮ ያለው መንግሥታዊ አስተዳደር ነው። እናም ሁሉንም ነገር እንዳለ ቀጠሉበት። “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” አምባገነን ሆኖ የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባርን ወታደሮች እንዳጠፋ ሁሉ፤ እኒህ የተተኩትም አምባገነን ከመሆንና ርስ በርስ ከመጠፋፋት ሌላ፤ የተለየ ሂደት የላቸውም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  “ባለቤት ካልጮኸ ገላጋይ አይደርስም ” - ማላጅ

ባሁኑ ሰዓት በኢትዮጵያ በሥልጣን ላይ አይሎ ያለው፤ የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ነው። ይህ ድርጅት፤ እንደጠፍጣፊው እንደ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ሁሉ፤ ብቻውን መግዛት ነው የሚፈልገው። እንደጠፍጣፊው እንደ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ሁሉ፤ ኢትዮጵያን በራሱ አምሳል ነው ማድረግ የሚፈልገው። እንደጠፍጣፊው እንደ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ሁሉ፤ በራሱ መንገድ ነው መግዛት የሚፈልገው። በርግጥ ይሄም ሌሎች እስኪያይሉ ድረስ ነው። ይሄ ድርጅት፤ እንደጠፍጣፊው እንደ “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ሁሉ፤ ስሙን በየጊዜው እንዳመቸው ይቀይራል። አሁን ብልፅግና ብሏል። ነገ ደግሞ ሌላ ስም ይይዛል። የሚወስነው፤ የሚወስደው ዕርምጃና ስኬቱ ነው። ገዥዎች ዋና የአስተዳደር መሳሪያቸው፤ ለመግዛት የሚያመቻቸውን ትርክት መፍጠር ነው። ለአሁኑ ገዥዎች መሠረታዊ ትርክታቸው፤ “እኛ የአገሪቱን ሲሶ የሚበልጥ የሰው ቁጥር አለን!”። “ትልቁ የአገሪቱ ሕዝብ ቁጥር የኛ ነው!” እናም “ትልቁን ቁጥር እስከያዝን ድረስ፤ ሁሌም ገዥዎች እኛ መሆን አለብን!” የሚለው ነው። “አዲስ አበባ የኛ ናት!” ይቀጥላሉ። ቁጥራቸውና የአዲስ አበባ የነሱ መሆን የራሱ የሆነ ታሪክ ስላለው፤ ለሌላ ጊዜ እተወዋለሁ። ብቻ፤ ይህ ከዴሞክራሲ ጋር ያለውን ግጭት እንድትመለከቱት እፈልጋለሁ። ክልል እስካለና ውከላው በሕዝብ ቁጥር እስከሆነ ድረስ፤ በቀላሉ ዴሞክራሲያዊ አሠራር ደህና ሰንብች! መቼም ቢሆን የአኝዋክ ተወላጅ ጠቅላይ ሚኒስትር፣ የሶማሊ የመከላከያ ሚኒስትር፣ የአፋር የገንዘብ ሚኒስትር! ሕልም ነው።

በማጠቃለያ፤ ዴሞክራሲና የክልል አስተዳደር ተቃራኒ ናቸው። ኢትዮጵያዊነትና የክልል አስተዳደር ተቃራኒ ናቸው። ክልሎች ወደ አገርነት፤ ኢትዮጵያ ወደ መፍረስ ብቻ ነው ግስጋሴያቸው። የደቡብ ክልልን የፈጠረው “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ለራሱ ዓላማ ነበር። የዚያ ዘውግ አቀንቃኞች፤ አሁን የበለጠ መበጣጠሱን የኔ ብለው ይዘውታል። የኦሮሞ ብልፅግና አማራውን እዲስ አበባ እንዳይገባ፤ በደብረብርሃን መስመር ዘግተውታል። እዲስ አበባን እያተራመሰ ነው። “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” የፖለቲካ አስተሳሰቡና የአስተዳደር መመሪያው እንጂ፤ መሪዎቹ ትግሬዎች መሆናቸው አይደለም ለዚህ ያበቃን! እናም፤ የክልል አስተዳደር፣ የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር ሕገ-መንግሥት፣ ከትግሬዎች ነጻ አውጪ ግንባር ጋር አብረው ካለተደመሰሱ፤ ያገራችን አደጋ ወደ መጨረሻ ግቡ ይነጉዳል። ኢትዮጵያዊነት እንዲጠፋ ተዘምቶበት፤ ኢትዮጵያ የምትባል አገር አትኖርም፤ ኢትዮያዊያን እስካልተነሱ ድረስ!!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  [የሚኒሶታውን ደብረሰላም መድሃኔዓለም ቤ/ክ ጉዳይ ለምትከታተሉ ሁሉ] ቅጥፈታቸው ሲጋለጥ

 

2 Comments

  1. ( ውድ አዘጋጅ
    ይሄውልህ ፍጽሓ አጥላው የላከልኝ መልስ )
    ክልልማ መፍትሔ ነው!
    ክልል በረት በየፈርጁ የታጠረ
    ከሌለማ ያስቸግራል
    ለመለየት አንዱን ካንዱ
    የታሰረን ካልታሰረ።
    ፈረስ በቅሎ ፍየል በጉን
    ከጥቁሩ ግራጫውን
    ላም በሬውን፣ አህያውን፣
    ተጠቂውን አስጠቂውን፤
    ለመነጠል ለማስገባት በየቢጤው
    ክልልማ መፍትሔ ነው
    አስፈላጊ ጠቃሚ ነው።
    ፍሥሓ አጥላው
    ነሐሴ ፮ ቀን ፳ ፻ ፲ ፬ ዓ. ም.
    8/12/2022

  2. ( ውድ አዘጋጅ ይሄውልህ ፍጽሓ አጥላው የላከልኝ መልስ )

    ክልልማ መፍትሔ ነው!
    ክልል በረት በየፈርጁ የታጠረ
    ከሌለማ ያስቸግራል
    ለመለየት አንዱን ካንዱ
    የታሰረን ካልታሰረ።
    ፈረስ በቅሎ ፍየል በጉን
    ከጥቁሩ ግራጫውን
    ላም በሬውን፣ አህያውን፣
    ተጠቂውን አስጠቂውን፤
    ለመነጠል ለማስገባት በየቢጤው
    ክልልማ መፍትሔ ነው
    አስፈላጊ ጠቃሚ ነው።

    ፍሥሓ አጥላው
    ሐሴ ፮ ቀን ፳ ፻ ፲ ፬ ዓ. ም. 8/12/2022

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share