የትምህርት ሚኒስቴር ከ12ኛ ክፍል የመልቀቂያ ውጤት እና ከዩኒቨርሲቲ መግቢያ መቁረጫ ነጥብ ጋር በተያያዘ ተጨማሪ ማብራሪያ ሰጥቷል

የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ሳሙኤል ክፍሌ (ፒ ኤች ዲ) ከ12ኛ ክፍል የፈተና ውጤት እና የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ነጥብ ጋር ተያይዞ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ሚኒስትር ዴኤታው የ12ኛ ክፍል ፈተና በሁለት ዙር እንዲሰጥ መደረጉንና በመጀመሪያው ዙር የስነ-ዜጋና ስነ ምግባር ትምህርት ከፈተናው ቀን ቀድሞ በመውጣቱና የውጤት ግሽበት በመምጣቱ እንዲሰረዝ መደረጉን ተናግረዋል።

በመጀመሪያ ዙር ፈተና ከወሰዱት ተማሪዎች ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት 50 ከመቶና በላይ ውጤት ማስመዝገባቸውን የተናገሩት ሚኒስትር ዴኤታው በመጀመሪያው ዙር ፈተና ከወሠዱት 544ሺ 682 ተማሪዎች ውስጥ 44 ከመቶዎቹ 50 ከመቶ እና ከዚያ በላይ ውጤት ማስመዝገባቸውን አብራርተዋል።

በሁለተኛው ዙር ከተፈተኑት 53ሺ 997 ተማሪዎች ውስጥ 28 ከመቶዎቹ ወደ መንግስት ዩኒቨርሲቲዎች የሚመደቡ ሲሆን ከመጀመሪያው ዙር 554 ሺ 682 ተፈታኞች ውስጥ ደግሞ 25 ከመቶዎቹ ይመደባሉ ብለዋል።

የ 10ኛ ክፍል የማትሪክ ፈተና በመቅረቱ ምክንያት በጣም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎች በዘንድሮው አመት የ12ኛ ክፍል ፈተናን ወስደዋል ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው አራት ዩኒቨርሲቲዎቻችን መቀበል በማይችሉበት ሁኔታ ከአምናው የተሻለ ቁጥር ያለው ተማሪ ወደ መንግስት ዩኒቨርሲቲዎች እንዲመደቡ መደረጉን አብራርተዋል።

በትግራይ ያሉ አራት ዩኒቨርሲቲዎች ይማሩ የነበሩ ተማሪዎች ወደ ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች መመደባቸውና ዘንድሮም ይመደቡ የነበሩ ተማሪዎች ወደ ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች እንዲመደቡ መደረጉ 48ሺ ተማሪ የቅበላ አቅም አጥተናል ብለዋል።

ነገር ግን ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመነጋገር በ43 የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች 152 ሺ 14 ተማሪዎች እንዲመደቡ መደረጉና ይህም ከአምናው የቅበላ አቅም ጋር ሲነፃፀር ከፍ ያለ መሆኑን አብራርተዋል።

ፀጥታ ችግር ያጋጠማቸው አከባቢዎች በተመለከተ የተለየ መቁረጫ ነጥብ ለመወሰን የሚያስገድድ የውጤት ትንተና ስላልተገኘ በበመደበኛው የመቁረጫ ነጥብ ተስተናግደዋል ብለዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ቦሌ ለሚ ኮብልስቶን በሚሰሩ ሰዎችና በአካባቢው ነዋሪዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት 8 ሰዎች ሞቱ

ባለፈው አመት በ47 ዩኒቨርሲቲዎች 147 ሺ ተማሪዎች ምደባ የተደረገ ሲሆን ዘንድሮ በ43 ዩኒቨርሲቲዎች 152ሺ 014 ተማሪዎች እንዲመደቡ ተደርጓል።

2 Comments

  1. ማትሪክ ውጤት አሁንም ተዛብቷል የሚባለው መረጃው እውነት ከሆነነ በአዲስ አባባ ትምህርት ቤቶች ጭምር ተገኘ የተባለው ውጤት ጨምሮ ይህቺ ናት ጨዋታ ዕየተባለ ነው፡፡ ከድጡ ወደ ማጡ እየሆነ የዚህች አገር ጉዳይ፡፡ የባሳ አታምጣ ይላሉ እናትና አባቶቻችን የከፋ ቀን ሲመጣ፡፡ ምንድነው እየተሰራ ያለው፡፡ በቀድሞ ጊዜ ከደርግ አገዛዝ ጊዜ ጀምሮ አንዴ ፈተና ሲሰረቅና ስንት ለፍቶ ማትሪክ የደረሰ ወጣት ህይወቱ ሲበላሽ በዛህ በተቀነባበረና ሆን ተብሎ በተደረገ ዘረፋ ስንቱ ሌባና ዱርዬ የማይገባውን ውጤት እያገኘ ግማሹ ዩኑቨርሲቲ እየገባ ፍሬሽማን ላይ ተጫረ፣ ሌላው ሌባ ውጪ እስኮላር በመሄድ ቢያንስ ህይወቱን ቀይሮ ስንት ጎበዝ ተማሪ ግን ቦዘኔና በሽተኛ ሆነ፡፡
    በኃላ ደግሞ ወያኔ የሚባል አስተዳደር ሲመጣ የማትሪክ ዝርፍያው፣ ሰረቃው እና ሙሰኝነቱ በተቀነባበረ ሁኔታ ቀጥሎ ስንቱ የማይገባውን ውጤት እና ዩኒቨርሲቲ ምደባ ሲያገኝ ምስኪኑ 12 ዓመት እና ከዛ በላይ የደከመበት ውጤት መና ቀርቶ ለማንም ፓርቲ አባል ውጤት እየተሰጠና በዩኒቨርሲቲ ውስጥ የፖለቲካ ስራ ብቻ ስለሚሰሩ ስለትምህርቱ A ፊደል በደንብ ሳያውቁ ጥሩ ውጤት እየተሰጣቸው ሰርተፊኬትና ዲግሪ ታደላቸው፡፡ ከዛም በሚፈለግ የመንግስት ተቋምና ድርጅት እየተመደቡ ዘራፊ ሆነው ዛሪ ይህቺ አገር ውድቀት ላይ ትገኛለች፡፡ በሌላ መልኩ ስንት ሲለፋ የነበረ የደሃ ልጅ ተማሪ ዕድሉ እየተደናቀፈ ያልሆነ ቦታ ወድቆ ቀረ፡፡ አሁን ደግሞ ሌላ ድራማ እየታየ ነው፡፡ እህህህ እስከመቼ ……….. አለች ዘፋኟ፡፡ ይህቺ አገርስ ወዴት እየሄደች ነው፡፡ ይህ ወጣት ከደርግ ጊዜ ጀምሮ አንዴ በውትድርና ጦርነት ከዛም ውጤት በሌለው በባድማ ጦርነት እና ከዛም በቅርቡ ከትህነግ ጋር በነበረ ጦርነትና ሌሎችም ችግሮች መከራውን ያየ ወጣት መቼ ነው በዚህች አገር ፍትሃዊነት ማየት የሚችለው??????????????????????????? አሁን የሚታየው የማትሪክ ውጤት ድራማ ደግሞ ከዚህ በፊቱ በላቀ ሁኔታ የተሰራ ከባድ ድራማ ነው፡፡ እስቲ ማንኛውም የየትኛውም ክልል ወላጆች ያሳደገው ልጅ ውጤት ያለአግባብ ሲዘረፍበት ምን ነው የሚሰማወ??? አረ ሻጥሩ እስከመቼ ነው የሚቀጥለው??? ይህ የአንድ አገር አመራር በከፍተኛ ሁኔታ እንደወደቀ የሚያሳይበት ነው፡፡ ሆን ተብሎ የሚፈለግ ክልል ብቻ ማሳለፍ ከጀርባው የተጠነሰሰ ከባድ ሴራ እንዳለም አመላካች ነው፡፡ ይህ ውጤት ተሰርዞ ድጋሚ እንዲጣራ ካልተደረገና አስፈላጊ ከሆነም ፈተናው ድጋሚ ተሰጥቶ በገለለተኛ አካል ፈተናው እንዲታረም እና ውጤቱ እንዲገለፅ ካልተደረገ አገሪቷ ወደ ከባድ ቀውስ ያመራተል፡፡
    አሁን የተሾሙት ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ምን እያደረጉ ነው ለመሆኑ በሳቸው ጊዜ ይህ ድርጊት እየተደረገ ከሚመለከቱ አሁኑኑ ስራቸውን በመልቀቅ ከውጪ ለውጥ እንዲመጣ መጣር ተገቢ ይመስላል፡፡ አለዚያ ጉልቻ ቢቀያየር ለዚህ እውነተኛ ህዝብና ታታሪ ተማሪ ምን ፋይዳ መጣለት፡፡ አረ ወዴት ነው እየተሔደ ያለው ??????????

  2. ሚኒስቴር ደኤታ ብርሃኑ እንዳቦካው እሱ ይጨርሰው አትግባበት አማራን በአማራ ማስመታት ታክቲካቸው ሁኗል ነቃ በሉ እነሱ መግለጫ ይስጡበት። አማራ ክልል ወጣቶች ጦርነት ላይ ነበሩ ትምህርት ቤቶች ፈርሰዋል እስከ አሁን ዉጊያ ላይ ናቸው ሲሉት ማርክ ካልተሰጠኝ ብሎ መጮህ ምን ማለት ነው ብሎ አጣምሞ ተርጉሞታል ሽመልስን ለማስደሰት አብይን ለማስደሰት የማይሄድበት እርቀት አይኖርም።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share