የትግራይ እና አፋር ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ላይ በአዲስ መልክ ባገረሸው ጦርነት ከአፋር 5 ወረዳዎች 200 ሺህ ሰዎች ገደማ መፈናቀላቸውን ክልሉ ዐስታወቀ። የአፋር ክልል አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መሃመድ ሁሴን ለዶይቼ ቬለ (DW) እንደተናገሩት በተቀሰቀሰው በከባድ ጦር መሣሪያ የታገዘ ጦርነት በርካቶች በየመንገዱ ወድቀዋል።
የአገር መከላከያ ሰራዊት በስፍራው እንዳልነበረና የአፋር ክልል ሃይሎች የመከላከል ስራ እየሰሩ ነው የሚሉት አቶ መሃመድ አህመድ ጦርነቱ እየተደረገበት የሚገኘው ይህ መንገድ መዳረሻው የጂቡቲ እና ሰመራ አካፋ ወደ ሆነው ሰርዶ እንደሚወስድ ነግረውናል፡፡ እንደ ባለስልጣኑ ገለጻ በአዲስ መልክ ጦርነት በተከፈተባቸው የአፋር ከተሞች ውድመትና ዝርፊያም ተፈጽሟል፡፡
የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ ሁሴን በበኩላቸው ለዶይቼ ቬለ እንደነገሩት አሁን ላይ ለመድረስ አስቸጋሪ ባሉት እንደ አዲስ በተቀሰቀሰው የጦርነቱ ስፍራ ወደ 200 ሺህ ሰዎች ተፈናቅለዋል፡፡
ጦርነት በሚካሄድበት ስፍራ የሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦትን ማድረስ እንዳልተቻለ የገለጹት አቶ መሃመድ ሁሴን አከባቢው ላይ ኮሚቴ ተዋቅሮ ክትትል ግን እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ በከባድ መሳሪያ የተጠቁ ሰላማዊ ዜጎችን በተወሰነ መልኩ ወደ ህክምና ማእከላት መውሰድ መቻሉንም በማከል፡፡ ወደ ትግራይ የሚወሰደውን የእርዳታ ቁሳቁስ ለማጓጓዝ ብቸኛ መንገድ የሆነው ጦርነቱ የተስፋፋበት የአብዓላ ሰመራ ኮሪደር የተዘጋው በህወሓት ጸብ አጫርነት እንደሆነ በመንግስት በኩል ሲነሳ፤ ህወሓት በፊናው ተፈጽሞብኛል ያለውን ከበባ በመስበር የርዳታ ቁሳቁሶችን ማስገባ መንገድ ፍላጋ ላይ እንደሆነ ማንሳቱ ይታወሳል፡፡
ሥዩም ጌቱ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
እሸቴ በቀለ
DW