በትግራይ እና አፋር አዋሳኝ የተቀሰቀሰው ጦርነት እና መዘዙ

የትግራይ እና አፋር ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ላይ በአዲስ መልክ ባገረሸው ጦርነት ከአፋር 5 ወረዳዎች 200 ሺህ ሰዎች ገደማ መፈናቀላቸውን ክልሉ ዐስታወቀ። የአፋር ክልል አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መሃመድ ሁሴን ለዶይቼ ቬለ (DW) እንደተናገሩት በተቀሰቀሰው በከባድ ጦር መሣሪያ የታገዘ ጦርነት በርካቶች በየመንገዱ ወድቀዋል።

ሰሞኑን የትግራይ እና አፋር ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ላይ በአዲስ መልክ ባገረሸው ጦርነት ከአፋር አምስት ወረዳዎች 200 ሺህ ሰዎች ገደማ መፈናቀላቸውን ክልሉ ዐስታወቀ። የአፋር ክልል አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መሃመድ ሁሴን ለዶይቼ ቬለ (DW) እንደተናገሩት በተቀሰቀሰው በከባድ ጦር መሣሪያ የታገዘ ጦርነት በርካቶች በየመንገዱ ወድቀዋል። የተወሰኑትንም ወደ ህክምና ማድረስ ተችሏል። ባለስልጣናትና የዐይን እማኞች እንደሚሉት የሕወሓት ኃይሎች ወረራ ፈጽመዋል ባሉት የአፋር ዞን 2 ወረዳዎች ከፍተኛ ውድመትና ቀውስም ተከስቷል። በበረሃሌ በኩል የአፋር ተዋጊዎች የሕወሓት ኃይልን ተከላክለው በብርቱ ጉዳት እንዳደረሱበትም ተናግረዋል።

መምህር መሐመድ ኑር ዑስማን በአፋር ዞን ሁለት ኢሬብቲ ከተማ ትምህርት ቤት በርዕሰ መምህርነት ያገለግላሉ፡፡ መምህሩ እንደሚሉት በዓብዓላ የከባድ ጦር መሣሪያ ተኩስ በትግራይ በኩል መከፈቱን ተከትሎ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ ወደዚች እሪብቲ ከተማ በመፈናቀላቸው ለመጠለያ እንዲሁን ትምህርት ቤት ከተዘጋም ሁለት ወር ገደማ እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ አሁን ደግሞ እሪብቲን ጨምሮ በአራት የአፋር ወረዳዎች ጦርነቱ በመስፋቱ መኖሪያ ከተማቸውን ለቀው ወደ አፍዴራ አቅራቢያ መሰደዳቸውን በመግለጽ ስላከባቢው አሁናዊ ሁኔታ አስተያየታቸውን አጋርተውናል፡፡

እንደ የአፋር ክልል ባለስልጣናት ከትግራይ ክልል ዋና ከተማ መቀሌ 40 ኪ.ሜ. ገደማ በቅርብ ርቀት ላይ እንደምትገኝ በሚነገረው የአፋር ክልል ዞን 2 አብዓላ ከተማ የከባድ መሳሪያ ድብደባ መፈጸም የጀመረው የፌዴራል መንግስት ሰራዊቱ ወደ ትግራይ ከሚያደርገው ግስጋሴ ታቅቦ ባለበት እንዲቆይ ውሳኔ ባሳለፈበት ማግስት ነው፡፡ በአፋር ክልል ረዳት የመንግስት ተጠሪ መሃመድ አህመድ በተለይም ለዶይቼ ቬለ እንደተናገሩት ጥር 15 ቀን 2014 ዓ.ም. እሁድ ሌሊት በትግራይ ኃሎች ተከፍቷል ባሉት ድንገተኛ ጥቃት ደግሞ ጦርነቱ በአፋር ዞን ሁለት ወደ አራት ወረዳዎች ሰፍቷል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  “አብረን ወደ ፊት እንሄዳለን፤ አብረን የጀግንነት ሥራ እንሠራለን” ኮሎኔል አለበል አማረ

የአገር መከላከያ ሰራዊት በስፍራው እንዳልነበረና የአፋር ክልል ሃይሎች የመከላከል ስራ እየሰሩ ነው የሚሉት አቶ መሃመድ አህመድ ጦርነቱ እየተደረገበት የሚገኘው ይህ መንገድ መዳረሻው የጂቡቲ እና ሰመራ አካፋ ወደ ሆነው ሰርዶ እንደሚወስድ ነግረውናል፡፡ እንደ ባለስልጣኑ ገለጻ በአዲስ መልክ ጦርነት በተከፈተባቸው የአፋር ከተሞች ውድመትና ዝርፊያም ተፈጽሟል፡፡
የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ ሁሴን በበኩላቸው ለዶይቼ ቬለ እንደነገሩት አሁን ላይ ለመድረስ አስቸጋሪ ባሉት እንደ አዲስ በተቀሰቀሰው የጦርነቱ ስፍራ ወደ 200 ሺህ ሰዎች ተፈናቅለዋል፡፡

ጦርነት በሚካሄድበት ስፍራ የሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦትን ማድረስ እንዳልተቻለ የገለጹት አቶ መሃመድ ሁሴን አከባቢው ላይ ኮሚቴ ተዋቅሮ ክትትል ግን እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ በከባድ መሳሪያ የተጠቁ ሰላማዊ ዜጎችን በተወሰነ መልኩ ወደ ህክምና ማእከላት መውሰድ መቻሉንም በማከል፡፡ ወደ ትግራይ የሚወሰደውን የእርዳታ ቁሳቁስ ለማጓጓዝ ብቸኛ መንገድ የሆነው ጦርነቱ የተስፋፋበት የአብዓላ ሰመራ ኮሪደር የተዘጋው በህወሓት ጸብ አጫርነት እንደሆነ በመንግስት በኩል ሲነሳ፤ ህወሓት በፊናው ተፈጽሞብኛል ያለውን ከበባ በመስበር የርዳታ ቁሳቁሶችን ማስገባ መንገድ ፍላጋ ላይ እንደሆነ ማንሳቱ ይታወሳል፡፡

ሥዩም ጌቱ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
እሸቴ በቀለ

DW

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share