ከፈረሱ ጋሪው – አበበ ገላው

አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ አሸባሪው ህወሃት በከፈተበት የጭካኔና የጥፋት ጦርነት ሳቢያ በቀጥታና በተዘዋዋሪ መንገዶች ከፍተኛ ጉዳቶች ደርሶበታል። በዚህ ፋሺስታዊ ጦርነት ምክንያት የአማራ፣ የአፋርና የትግራይ ክልሎች መጠነ ሰፊ ውድመት፣ ረሃብ፣ ሞትና መፈናቀል ደርሶባቸዋል። በተለይ በአማራ ክልል ህወሃት ሂሳብ አወራርዳለሁ በሚል ሰይጣናዊ ስሌት ሆን ብሎ ከፍተኛ ዝርፊያ፣ የዘር ማጥፋት እንዲሁም ዘግናኝ በሆነ ሁኔታ አረጋዊያን፣ ሴቶችና ህጻናት በጅምላ እዲደፈሩ አድርጓል። በጠቃላይ የኢትዮጵያ ህዝብ በዚህ ጦርነት ምክትያት ከደረሰበት ሞትና ውድመት በተጨማሪ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ድቀት የገጠመው ሲሆን በዚህም ሳቢያ ህዝቡ ለከፍተኛ የኑሮ ውድነት ተጋልጧል።

ከህወሃት ታሪክና ሰይጣናዊ እኩይነት አንጻር አሸባሪው ቡድን ተሸንፏል፣ ጦርነቱ በድል ተጠናቋል በሚል በመንግስት በኩል እየተቀነቀነ ያለው የተሳሳተ አጀንዳ አደገኛና ህዝብን ለሌላ ዙር ጥፋትና ውድመት ሊያጋልጠው የሚችል አካሄድ ነው። ሰሞኑንም በዚሁ በተሳሳተ ግምገማ ላይ ተመስርቶ የህወሃት ዋና የጥፋት ስትራቴጂስት የሆነው ስብሃት ነጋን ጨምሮ አደገኛ የሆኑ የአሸባሪው ድርጅት አመራሮች ያለምንም ቅድመ ሁኔታና ህጋዊ አግባብ መለቀቃቸው ፍትህ ፈላጊውን ህዝብ ማስደንገጡና ማስቆጣቱ የአደባባይ ሚስጢር ነው።

አሁን ደግሞ ይባስ ተብሎ የድህረ ጦርነት የግምገማ ሰንድ በገዢው ፓርቲ ለውይይት ለህዝብ መቅረቡ በኢትዮጵያ ህዝብ ዘንድ የተፈጠረውን ግራ መጋባትና ብዥታ ይበልጡንው አባብሶታል። ህዝቡ፣ ሰራዊቱ፣ ሚሊሻው፣ ወዶ ዘማቹና መሪዎቹ በአንድ ልብ ሙሉ ትኩረታቸውን በህወሃት ላይ ተጀምሮ የነበረው የመልሶ ማጥቃት ላይ ከማተኮር ይልቅ የድህረ ግጭት (postconflict) ግምገማና ውይይት እንዲጀመር ማድረግ ህዝብን ለመከፋፈልና ለጥርጣሬ ለጠላት ደግሞ ምቹ ቀዳዳ የሚያሰፉ አጋጣሚና እድል እየፈጠረለት ይገኛል።

በተለይ የአማራና የአፋር ክልልሎች አሁንም ለድጋሚ ዙር የህወሃት ወረራና ጥፋት ተጋላጮች መሆናቸው የቀጠለ ሲሆን በሰሜን ወሎና በሰሜን ጎንደር እንዲሁም በአፋር አንዳንድ አካባቢዎች ላይ ጥቃት መክፈቱና ተለቀው የነበሩ ቦታዎችን መልሶ መያዙ እየተሰማ ነው። ተወደደም ተጠላም ህወሃት ሙሉ ለሙሉ እስካልተሸነፈና ትጥቅ እስካልፈታ ድረስ በእነዚህ ክልሎች ላይ የህወሃት ጥፋትና ጥቃት እያባራም። ህወሃት ለሌላ ዙር ጥፋት መጠነ ሰፊ ምልመላና ስልጠና በማድረግ ላይ ባለበት በዚህ ጊዜ የሚያመለከተው ወደ ድህረ ጦርነት ምዕራፍ ገና ያልተቃረብን መሆኑን ነው። በመሆኑም ገዢው ፓርቲ ህዝብን በየጊዜው ከሚከፋፍሉና ብዥታ ከሚፈጥሩ ድርጊቶች መቆጠብ ይገባዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያቶ ኤርምያስ ለገሰና የመሰሎቹ ቅጥፈት፣ እውን አማራ ዘረኛ ነው?

የመንግስት፣ የሰራዊቱ፣ የክልል ልዩ ሚሊሻና እንደ ፋኖ ያሉ ህዝባዊ ሰራዊቶች ትኩረት ሙሉ በሙሉ የህወሃትን ጥቃት መክቶ በድል ማጠናቀቅ ላይ ማተኮር ይገባዋል። ስለዚህም ገና ጦርነት ሳይጠናቀቅ ስለ ትጥቅ ማስፈታት (postconflict demobilization) መወያየት አግባብነት የለውም።

እነ ስብሃት ነጋን በተመለከተም መንግስት የወሰደው እርምጃ ፍትህ የተጠማውን ህዝብ ስሜትና ፍላጎት የሚጻረር ህዝብና መንግስትን በከፍተኛ ደረጃ የሚያቃቅር እርምጃ መሆኑን ከግንዛቤ በማስገባት ውሳኔውን እንዲቀለበስ ቢደረግ የተሻለ እንደሚሆን አምናለሁ። እንዲህ አይነቱ ከፋፋይ አጀንዳ ህዝብ ላይ ያለ ጊዜው መወርወርም ያለውን አሉታዊ ተጽእኖ በመረዳት ገዢው ፓርቲ ሙሉ ትኩረቱን የተጀመረውን የአገርን ህልውና የመታደግ ዘመቻ በአንድነት አጠናክሮ በአስተማማኝ ድል ለማጠናቀቅ ህዝብን ከመከፋፈልና ለውዥንብር ከመዳረግ መቆጠብ ይገባዋል።

ጦርነቱ ሳይቋጭ የተንጋደደና የተዛባ የድህረ ጦርነት ትንተናና ውይይት ማካሄድም ከፈረሱ ጋሪው እንደሚባለው ስለሆነ እንዲቆም ይደረግ። በጦርነቱ በቀጥታ ተጎጂ የሆኑ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎቻችንን መልሶ ማቋቋምና የወደሙትን ትምህርት ቤቶች፣ የጤና ተቋማትና የመሰረተ ልማት አውታሮችን ጠግኖ ተጎጂዎችንም ክሶ ወደ ተረጋጋ ህይወታቸው እንዲመለሱ ጥረት ቢደረግ የበለጠ ውጤታማ ስራ መስራት እንደሚቻል መገመት አያዳግትም።

2 Comments

  1. አቤ፣ ይቺን አጋጣሚ ተጠቅመሽ ያስኮረፍሺውን ግንፍል ቲፎዞ ለመታረቅ ነው?

  2. ዶር አብይና ለማ መገርሳ ጴንጤ ሁነው ከጁንታው ጋር እጅና ጓንት ሁነው ከስሩ የራስቸውን ጊዜ ሲያገኙ ከስብሀት የባሱ አውሬዎች ሊሆኑ እንደሚችሉ የሚያሳይ ክስተት ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share