የጦርነቱ ሁኔታ ዘገባ: የወያኔ ፍጻሜ መጀመሪያ ማሳያ – ግርማ ካሳ

11/11/2021

የኢትዮጵያ መንግስት የተናጥል የተኩስ አቁም አውጆ፣ የአገር መከላከያ ጦር ከትግራይ ክልል እንዲወጣ ማድረጉን ተከትሎ ፣ ሕወሃትን ተኩስ አቁማ አስቸኳይ የሰብአዊ ድጋፍ የሚያስፈልገው የትግራይ ህዝብ ድጋፍ እንዲያገኝ ሁኔታዎች ይመቻቻሉ፣ ያሉ የፖለቲካ ችግሮችን በውይይት ለመፍታት በሮችን ይከፍታሉ ተብሎ ነበር የሚጠበቀው፡፡

ሆኖም ግን ሕወሃት የትግራይ ህዝብ መከራ እንደገና እንዲባባስ በማድረግ፣ በአማራና አፋር ክልሎች ወረራ በመፈጸም፣ የሰባአዊ ቀውሶች ከትግራይ ውጭም እንዲዛመት አድርገዋል::

ህውሃቶች በመቶ ሺሆች የሚቆጠሩ ታጣቂዎችን በማሰማራት በከባባድ መሳሪያዎች ታግዘው በሁሉም አቃጣጫ ነው ዉጊያ የከፈቱት:: ከትግራይ ተነስተው እስከ ሰሜን ሸዋ ይፋት ድረስ ዘልቀው ሄደዋል፡፡ በተለያዩ የወሎ ወረዳዎች እየተዋጉ ነው፡፡

የወያኔዎች ሸዋ መድረስንና በአብዛኛው ወሎ ውስጥ መገኘትን አንዳንዶች እንደ ጥንካሬ ሊያዩት ይችላሉ፡፡ ሆኖም ከደጀናቸው ከትግራይ እየራቁ በሄዱ ቁጥር መጨረሻቸው መልካም እንደማይሆን ለመገመት አርቆ ማሰብ አይጠቅም፡፡

የወገን ጦር ወደ ትግራይ የሚወስዱ መንገዶችን እየቆረጠባቸው ነው:: በሸዋ በወሎ የተበተኑት ወያኔዎች ከማለቅ ወይንም እጅ ከመስጠት ውጭ ሌላ አማራጭ አይኖራቸውም፡፡

ከትግራይ ክልል ወደ አዋሳኝ ኤርትራ፣ አፋር፣ ጎንደርና ወሎ የሚወስዱ መንገዶች ወደ 15 ይጠጋሉ፡፡ እስቲ እነዚህ መንገዶች ምን ደረጃ ላይ እንዳሉ እንቃኛቸው

1ኛ ወደ ኤርትራ የሚወስዱ መንገዶች

አራት ከትግራይ ወደ ኤርትራ የሚወስዱ መንገዶች ናቸው፡፡ በአዲግራት ፣ ሰንዓፈ በኩል፣ በጾሮና በኩል፣ በአድዋ ራማ በኩል፣ በሽራሮ፣ ባድመ ሸንበቆ በኩል፡፡

እነዚህ መንገዶች፣ በተለይም ከአስመራ የሚመጡት፣ ከሕወሃት የጠብጫሪነትና የአሸባሪነት ባህሪ የተነሳ ጥቅም ላይ ሊዉሉ አልቻሉም እንጂ፣ በረሃብና በችግር ላይ የሚገኘው የትግራይ ህዝብ ፈጣን ድጋፍና እርዳታ እንዲያገኝ ለማድረግ በጣም አመች ነበሩ፡፡

በአሁኑ ጊዜ የውጭ ድርጅቶች፣ የተባበሩት መንግስታት ወደ ትግራይ እርዳታ እያደረሱ ያሉት ከጅቡቲ ወደብ ፣ በአፋር ክልል፣ በአላማጣ፣ መኾኔ ፣ ሕዋኔ አድርገው ነው፡፡ ከደቡባዊ ትግራይ ሕዋኔ ከተማ ለመድረስ 670 ኪሎሚተሮች ይጓዛሉ፡፡ ወደ 11 ሰዓታት ገደማ፡፡ ለእርዳታ ስራ ምጽዋን መጠቀም ቢቻል ኖሮ፣ አዲግራት ለመግባት ወደ 3 ሰዓት ተኩል ብቻ ተጉዘው 280 ኪሎሚተሮች ብቻ ነበር ማቋረጥ የሚያስፈልጋቸው፡፡

የኤርትራ መንግስት ሰብዓዊ ድጋፍ በምጽዋ በኩል እንዳያልፍ አልከለከለም፡፡ ሆኖም የተባበሩት መንግስታት ሃላፊዎችና እነ አሜሪካ ፣ እርዳታ አልደረሰም ወዘተእያሉ ፣ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጫና ከሚያሳድሩና ክስ ከሚመሰርቱ፣ በርግጥም ለሰብዓዊነት የሚቆረቆሩ ከሆኑ፣ በሕወሃት ላይ ጫና አሳድረው፣ ለእርዳታ የቀለለውን የምጽዋን መስመር መጠቀም ይችሉ ነበር፡፡ ግን አላደረጉትም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዜግነትን መቀየር በተመለከተ አንዳንድ ነጥቦች - ባይሳ ዋቅ-ወያ1

እንግዲህ እዚህ ጋር ልብ እንበል፤ ለከፍተኛ የሰብአዊ ቀውስ የተጋለጠው የትግራይ ሕዝብ፣ በሚቀለው መስመር፣ የተቀላጠፈ እርዳታ ማግኘት ያልቻለው፣ በዋናነትና ቆመንልሃል የሚሉት ሕወሃቶች ፍቃደኛ ስላልሆኑ ብቻ ነው፡፡

2ኛ ወደ አፋር የሚወስዱ መንገዶች

በምስራቅ ትግራይ ከመቀሌና ከውቅሮ በአራትን መስመር ወደ አፋር ክልል ዞን ሁለት ወደ ምትገኘው በርሃሌ ከተማ የሚወስዱ መንገዶች አሉ፡፡ በነዚህ መንገዶች የወይኔ ታጣቂዎች በርሃሌን ከማጥቃት ውጭ ወደ ሌለ አካባቢዎች የሚወስዳቸው መንገድ አይደለም፡፡

3ኛ በተከዜ ወንዝ የሚያልፉ መንገዶች

ወደ ሌሎች ከትግራይ የሚያስወጡ መንገዶች ስንሄድ ተከዜን ተሻግረው ሶስት መንገዶችን እናገኛለን፡፡

አንደኛው ከሽሬ ተነስቶ በአዲ ገብሩ አልፎ ወደ ሰሜን ጎንደር፣ ወደ ማይጠምሪ የሚወስደው መንገድ ነው፡፡ በዚህ መንገድ የወያኔ ታጣቂዎች እስከ ደባርቅና ዳባት ወረዳዎች ደርሰው ነበር፡፡ ሆኖም የወገን ጦር ከፍተኛ ሽንፈት አከናንቧቸው፣ አዲ አርቃይና ከአዲአርቃይ በስተሰሜን ባለው የጠለምት አካባቢ ብቻ በአሁኑ ወቅት እንዲወሰኑ አድርጓቸዋል፡፡

ሁለተኛው ከትግራይ ተከዜ ተሻግሮ ፣ ከሽሬ፣ በደደቢት አድርጎ ፣ የአቶ መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን የትውልድ ቦታ ወደ ሆነው ፣ ወያኔዎች አዲ ረመጽ ይሉት ወደነበረው፣ ወፍ አርግፍ ከተማ የሚወስደው መንገድ ነው፡፡

ሶስተኛው ከሽሬ በሽራሮ አድርጎ ተከዜን በመሻገር ወደ አዲ ጎሹ የሚወስደው መንገድ ነው፡፡

በደደቢት ወፍ አርግፍ፣ በሽራሮ አዲ ጎሾ መንገዶችን በመያዝ ፣ ወያኔዎች ወልቃይት ጠገዴን ለመቆጣጠር ፣ በሱዳን በኩል ኮሪዶር ለማግኘት፣ ከሃያ ጊዜ በላይ ዉጊያ ከፍተው፣ ሁሉንም ጊዜ እጅግ በጣም ብዙ የትግራይ ወጣቶችን ገብረው ተሸንፈው ተመልሰዋል፡፡

በመሆኑም ወደ ኤርትራ፣ ተከዜን ተሻግረው ወደ ወልቃይትና ሰሜን ጎንደር የሚወስዱት በድምሩ ሰባት መንገዶች በመጠቀም ወያኔዎች ማለፍም፣ መውጣትም አይችሉም፡፡ የተዘጉ መንገዶች ናቸው፡፡

4ኛ ወደ ወሎና ዋገመራ የሚወስዱ መንገዶች

በወሎና በዋገመራ በኩል ወደ ትግራይ የሚወስዱ አራት ሌሎች መንገዶች አሉ፡፡ በነዚህ መንገዶች ወያኔዎች ታጣቂዎቻቸውን ከትግራይ ወደ ወሎ በስፋት ያሰማሩባቸው የነበሩ መንገዶች ናቸው፡፡ ከትግራይ ውጭ የዘረፉትን በእነዚህ መንገዶች ነው ሲያመላልሱ የነበሩት፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያውያን አድዋ ላይ ያሸነፉት የአለምን ህግ ነበር - ይርጋ ገላው

አንደኛው መንገድ በመቀሌ ፣ ሕዋኔ፣ መኾኔ፣ አላማጣ፣ ቆቦ አድርጎ፣ በሃራ ገበያ በኩል ወደ ጭፍራ አፋር ክልል፣ በወልዲያ በኩል ወደ ደሴ የሚወስደው መንገድ ነው፡፡

ሁለተኛው መንገድ በመቀሌ ፣ ኮረም፣ አላማጣ፣ ቆቦ አድርጎ፣ እንደ አንደኛው መስመር በሃራ ገበያ በኩል ወደ ጭፍራ አፋር ክልል፣ በወልዲያ በኩል ወደ ደሴ የሚወስደው መንገድ ነው፡፡

አሁን ባለው ሁኔታ ወያኔ እነዚህን ሁለት መስመሮች የመጠቀም እድሉ የመነመነ ብቻ ሳይሆን ሙሉ ለሙሉ የተዘጋ ነው፡፡ ይሄም ለአራት ወር ገደማ ወያኔን በሽምቅ ውጊያ ሲታገሉ በቆዩ ፋኖዎችና የቆቦ ወረዳ ሚሊሺያዎች አስደማሚ የጀግንነት ስራ ምክንያት ነው፡፡

ፋኖዎቹ ሲጀምሩ የዞብል ተራራና አካባቢውን ነበር የያዙት፡፡ ቀስ በቀስ ብዙ ወጣት እየተቀላቀላቸው ፣ አድማሳቸውን እያሰፉ በአሁኑ ወቅት የቆቦ ፣ የሮቢት፣ የጎብዬ ከተሞችንም ጨምሮ፣ የቆቦ ወረዳን ሙሉ ለሙሉ ነጻ ያወጡበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ በዚያ አካባቢ ወያኔዎች መቆጣጠር ስላልቻሉ፣ ተገድለዋል፣ ወይንም ለቀው፣ ሸሽተው ወጥተዋል፡፡

ያ ብቻ አይደለም፣ ወያኔዎች ተጨማሪ ወታደሮች ከመቀሌ፣ የዘረፊትን ወደ መቀሌ ማመላለስ የማይችሉበት ሁኔታ እንዲፈጠር ተደርጓል፡፡

ሶስተኛው መንገድ ከአቢ አዲ፣ ተንቤን በሰቆጣ አድርጎ ወደ ላሊበላ የሚወስደው መንገድ ነው፡፡ ይህን መንገድ ወያኔዎች፣ ሌላው በስፋት ታጣቂዎቻቸውን ለማመላለስ የሚጠቀሙበት መስመር ነበር፡፡ ወያኔዎች አብዛኛውን የዋገምራ ዞን ወረዳዎች ተቆጣጥረው፣ ከአምደ ወርቅ ወደ እብናት የሚወሰደውን መንገድ በመያዝ ፣ ቀላል የማይባል የሰራዊት ቁጥር አሰልፈው በአዲስ ዘመን በኩል ጎንደር ወይም ባህር ዳርን ለመያዝ ሞክረው ነበር፡፡

ሆኖም በወልቃይትና በጠለምት ግንባሮች እንደታየው፣ ከፍተኛ ውድመትና ኪሳራ ደርሶባቸው፣ እጅግ በጣም ብዙ የትግራይ ወጣቶችን ገብረው፣ ከአብዛኛው የዋገመራ ወረዳዎች ለቀው እንዲወጡ ተደርገዋል፡፡ በዋገመራ ካሉ ወረዳዎች ከአበርገሌ ወረዳና ኮረምን ከሚያዋስኑ የሰቆጣ የገጠር ወረዳዎች ውጭ የዋገመራ ዞን በወገን ቁጥጥር ስር ነው ያለው፡፡ የሰቆጣ ከተማም እንደዚሁ፡፡

ስለዚህ ከተንቤን በሰቆጣ በኩል ያለው መስመር ለወያኔ ሙሉ ለሙሉ የተዘጋ ሆኗል፡፡ በአጭሩ አነጋገር ወደ ወሎ፣ ሸዋ ወዘተ የተበተኑት የወያኔ ታጣቂዎች እንደገና ወደ በቆቦ አልፎ ወደ ትግራይ ለመመለስ የሚያስችላቸው እድል መንምኗል፡፡

በአሁኑ ወቅት ወያኔዎች ከትግራይ ለመውጣትና ለመግባት፣ ወደትግራይ ማናቸውንም ነገር ለማስገባትና ለማስወጣት የቀራቸው ሁለት መንገድ ብቻ ነው፡፡ እነርሱም ከላሊበላ በስተደቡብ፣ በኩልመስክ፣ ሙጃ ፣ አሞራ ገደል፣ ዋጃ አድርጎ በአለማጣ በኩል ወደ ትግራይ የሚወስደው መንገድ አንደኛው ሲሆን፣ የጊዳንና ጉባ ላፍቶ ወረዳዎችን አልፎ ከላሊበላ በስተሰሜን፣ ከሰቆጣ በስተደቡብ፣ በአስከተማ፣ ጭላርዋ፣ አዲዋሾ መንገድ አድርጎ ወደ ኮረም የሚወስደው መንገድ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  "እኛ ና እነሱ" የወቅቱ " የዘረኝነት መደብ " መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

በቆቦ ወረዳ ፋኖዎችና ሚሊሺያዎች ተደራጅተው፣ ወረዳዉን ነጻ የማውጣታቸው ዜና በጊዳንና ጉባ ላፍቶ ወረዳዎች በወያኔ ላይ የሽምቅ ውጊያዎች እንዲቀጣጠሉ አድርጓል፡፡ በቅርብ ጊዜውም ጊዳንና ጉባ ላፎት ወረዳዎች እንደ ቆቦና አብዛኛው የዋገመራ ወረዳዎች፣ በወገን የሕዝባዊ ሰራዊት ነጻ የመውጣት እድላቸው እጅግ በጣም የሰፋ ነው፡፡

ያ ሲሆን ወያኔ አንድ መንገድ ብቻ ይቀራታል ማለት ነው፡፡ እርሱም ከላሊበላ በስተሰሜን፣ ከሰቆጣ በስተደቡብ ወደ ኮረም የሚወስደው መነገድ፡፡

እጅግ በጣም ከፍተኛ የወገን ጦር ክምችት፣ ከጋሸና በስተምእራብ 10 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው የአርቢት ከታማ ላይ አለ፡፡ ይህ ጦር እንዲንቀሳቀስ ት እዝዝ ቢሰጥና ጋሸናን መቆጣጠር ቢቻል የቀረችዋም አንዱ መንገድ ሙሉ ለሙሉ ትቆረጣለች፡፡

እንግዲህ ይህ አንዲት ነገር ቁልጭ አድርጎ ነው የሚያሳየን፡፡ የወያኔ ፍጻሜ መዳረሱን፡፡ ወያኔዎች ታች ሸዋ ድረስ በመዝለቅ የተለያዩ የሽብር ተግባራትን እየፈጸሙ ቢሆንም፣ ትግራይ ካለው የሕወሃት የጦር አመራሮችና እዝ ሙሉ ለሙሉ እየተቆረጡ ነው፡፡ እነ ጀነራል ጽዳቃን ገብረትንሳኤ ወደ መሃል አገር ያሰማሩትን ጦር የሚያጠናክሩበት ሁኔታ የላቸውም፡፡

ተስፋቸው የነበረው 1ኛ በጭፍራ በኩል ወይንም ከባቲ በኩል ሚሌ ከተማን በመያዝ የአዲስ አበባ ጅቡቲ መስመርን በመዝጋት አዲስ አበባን በማነቅና ትልቅ ቀውስ በመፍጠር የጠየቁትን መንግስት እንዲቀበል ማስገደድ ነበር፡፡ 2ኛው በኦሮሞ ብሄረሰብ ዞን ለሁለት አመት ያለምንም ችግር ሲሰለጥንና ሲደራጅ ከነበረው የኦነግ ጦር ጋር በመተባበር፣ ሸዋን ሰብሮ ሸገር መግባት ነበር፡፡

ጉዳቶች ያደረሱ ቢሆንም፣ የአየር ኃይል ድጋፍ ተጨምሮበት በሚሌ መስመር አፋሮችን፣ በሸዋ መስመር የሸዋ ፋኖዎችና ሚሊሺያዎችን እንዲሁም የመከላከያ ሰራዊት አባላትን አልፈው መሄድ አልቻሉም፡፡

በዚህም ምክንያት ነው ደሴን ሲቆጣጠሩ፣ ከዚህ በኋላ ድርድር ብሎ ነገር የለምያለውን የጀነራል ጻድቃን ንግግር በመቀየር ፣ ጌታችው ረዳ ለመደራደር ዝግጁ ነን እስከማለት የጀመረው፡፡

4 Comments

  1. እናመሰግናለን ግርማ ካሳ ጊዜህን ወስደህ ቅልብጭ ያለች ወታደራዊ ማብራርያ የሰጠኸን እንደ ሁል ጊዜው ምስጋና ይገባሀል።

  2. ግርማ አመሰግናለሁ ሰለ ሀገርህ እና ሰለ ድሆች መልካሙን ሰታሰብ ዘመናትን በእሰር አሳልፈሀል…አሁን ይህን ብታደርግ ብዙ አይደንቅም…

  3. ውድ ግርማ ካሳ፣
    አሁን ገና በቊምነገር የተሞላ ጽሑፍ ጻፍክ። መንግሥትም እንኳ ያላደረገው ነው! ኢሳት ቅብጥርሶን ተዋቸው፤ እዚህ ዓይነቱ ጋ የሉበትም።
    ጊዜ ወስደህ በጥንቃቄ በካርታ አስደግፈህ ያቀረብከው ቊልጭ ያለ ዘገባ ህወሓት እና ግብረ አበሮቹ ለሚነዙት ውዥንብር መቅሠፍት ነው።
    የየመንደራችንን ወሬ ትተን ለአገራችን በቻልነው ሁሉ የምንሳተፍበት ሰዓት ላይ ነንና በርታልን!

  4. አለም ግርማ ካሳን እንደኛው ነው በግል የምታዉቀው? ግርማ ካሳ ቁም ነገር ያልሆነ ጽሁፍ ሲያወጣ አላየሁትም ለድካሙ እውቅና ብትሰጠው መልካም ነበር ኢትዮጵያ ማለት ብልጽግና ፓርቲ ማለት አይደለም ከዚሀ በጣም ከፍ ይላል።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share