ጎበዝ አሁን ያለውን ሁኔታ የአገር ሕልውናና ሉዓላዊነትን ማስጠበቅና ማስቀጠል መሆኑን ማጤን የግድ ነው! – አበባየሁ አሉላ

 ይህንን የሕወኃት ጦርነት አገዛዙን የመከላከል አድርጎ ከአገር ሕልውና መለየት ከቶውንም ስህተት ነው!

ዕውነት ነው አሁን ያለንበት ወቅት ሳይጋነን የታሪክ ድግግሞሽ ነው! ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይን ወይንም አብዬታዊውን መሪ ኘሬዝደንት መንግሥቱን አገረ መንግሥት ለማስወገድና ሕወኃት የተባለ ፀረ ኢትዬጵያና ጎሰኛ መንግሥት በኢትዬጵያ መንበር ለመመለስ የሚደረግ ደባ መሆኑን ከቶውንም ልንዘናጋ አይገባም! ለኢትዬጵያና ኢትዬጵያዊናነት ማበብና መቀጠል ብሎም ፍታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ዕውን መሆን ከቶውንም አይደለም አሜሪካኖች ወይም በጥቅሉ ምዕራባዊያ ለማምጣት በቅንጅት እየሰሩ ያሉት!! ይልቁንም 1991 ዓይነት የለንደኑ ድርድር ኢትዬጵያን የሚለው ኃይል ብረቱን መሬት ላይ እንዲያስቀምጥ በማድረግ ሕወኃትን በመንበሩ ድጋሚ ለመመለስ ነው!

አሜሪካና ኃያላኑ እንደሶሪያ፣ ኢራቅ፣ ሊቢያ የመን ወዘተ መንግሥት አስወግዶ warlords እንደተኩና በቀውስ ውስጥ አገራትን መንግሥት አልባ እንዳደረጉ ሁሉ ገናናዋን ኢትዬጵያ አገራችንን በመበተን ለእነርሱ የተመቸ አርተፍሻል ሳታላይት አገዛዝ በሕዝብ ጫንቃ ላይ ለመጫን መሆኑን ሁላችንንም ልብ ልንል ይገባል!

ችግር አለን አዎን! በአገዛዙ ያልተቀናጀ የጦርነት አመራርና በውስጡ ባሉ አሻጥሮች ወገን ይህንን ጎሰኛ የኢትዬጵያ ፀር ድባቅ መትቶ ማባረር ሳይሆን እንዳይመለስና ውጋት እንዳይሆንብን በገባበት መቅበር ሲቻል ዕልፎች እየተዋደቁ ብዙ የሕይወት ዋጋ እየተከፈለበት ነው!

ስለሆነም አሁንም ሕዝብም መንግሥትም በአንድ ተናበው ይህንን ጦርነት በኢትዬጵያና በአማራው ወገናችን አሸናፊነት መደምደምና መለስ ብለን በቅንነት ኢትዬጵያና ኢትዬጵያዊነትን በማስቀደም የጠራ የጋራ ምክክርና ውይይት ማድረግ ይገባናል!

አሁን ፋታ በማይሰጥ የጦርነት እሳት ውስጥ ፍልስፍናው ብዙም ለውጤት አያበቃንምና አንድነታችን በውስጥም በውጪም የጠነከረና የተናበበ መሆን የግድ ነው! ይህ ሳይሆን ከቀረ ደግሞ በአስገዳጅነት መደራደር ቢኖር እንኳን በአጭር ጊዜ የበላይነት ካልኖረን በእነሱ ጥያቄ ምላሽ እንወጠራለን ስለሆነም ጦርነቱ በተቀናጀ መልኩ አሁን ካለበት የመከላከል (መነሳት መውደቅ) ወደ ማጥቃት መሸጋገር በአስቸኳይ አለበት!

ተጨማሪ ያንብቡ:  አካፋን አካፋ ብሎ ለመጥራት የመቸገር የፖለቲካ ባህል – ጠገናው ጎሹ

ጎበዝ ጦርነቱን አቅሎ ከቶውንም ማየት አይገባንም ከሕወኃት የጦርነት ስልት አኳያ ወደ ኃላ መለስ ብሎ ማየት ተገቢ ነው ይህ በሽምቅ ተዋጊነት ( Corella fight ) በ ( Conventional war ) የጦር ስልት መካከል ያለ የጦርነተት አውድ ነው! በዓማችን የትም የተደረጉ የሽምጥ ውጊያዎች እጅግ ፈታኝና ብዙ ዋጋ ያስከፍላሉ! ሕወኃት ሲመቸው ይዋጋል በለስ ካልቀናው አጠገብ ያለ ተራራና ሸንተረር ውስጥ እንደ ዚንጄሮ ይወጣና ስልታዊ ሥፍራ ይዞ በሜዳ ላይ ለጥቃት የሚመጣውን ኃይል በመስኮት ቀዳዳ ይረፈርፋል! በአየር የሚደረግ ድብደባ እምብርቱን ለማግኘት ስለሚያዳግት ጥይት ጨራሽ ነው! ዘልቆ ሰብሮ በተመሳሰይ መግጠም እንደገለፅኩት ብዙ ዋጋ አስከፋይ ነው! በዚህ መልክ የኢትዬጵያ ሠራዊትና የአማራ ፋኖና የአፋር ልዩ ኃይል እየተዋጋም ነው።

ሕወኃት አቅሙን ያጠናክርና አሳቻ ጊዜ ወስዶ የለቀቀውን ተመልሶ በተደጋጋሚ ሙከራ በማሰላቸት እየያዘ እየገፋ መሬቱን ያሰፋል! ላሊበላን ብቻ ብንወስድ አራቴ ይዞ አራቴ ተመልሷል! ይህንን ለጦር ጠበብቶች ልተወው ።

ጎበዝ በገደልነው ልክ ብቻ አይደለም የጦርነት አሸናፊነት የሚመዘነው ” የጠላትን አቅም ማመናመኑ እንደተጠበቀ ሆኖ በምንቆጣጠረውና መልሰን በምንይዘው መሬትም ጭምር ነው ብቻ ነው ” እነርሱ እየገፉ ወደ ሸዋ እየተቃረቡ እኛ ስለገደልነው ጀሌ ብናወራ በጦርነት ትርጉም ብቻውን አሸናፊ ከቶውንም አያደርገንም! በአገዛዙ እጀ አጭርነትና አለመቀናጀት ጦርነቱ ጊዜ እየወሰደ በመሄድ ነው ሰው ሽብር ውስጥ ገብቶ መጡ ሲባል መመከትንና ድልን ሳይሆን ሽንፈትን በመጠበቅ መኖሪያው ቀየውን እየለቀቀ በቀላሉ ለእነርሱ ጥቂት ኃይል እየሰጠ የሚኮበልለው!

ስለሆነም ” ኢትዬጵያን ማንም አይደፍራትም ” በሚል ስሜትን ከፍ በሚያደርግ መፈክር ብቻ ወደ ሽንፈት እንዳንሄድ ጦርነቱ ተቀናጅቶ በአንድ ዕዝ የአገር መከላከያው ፣ ክልሎች ኃይል ፣ በአፋሩ ፣ የአማራ ፋኖና ልዩ ኃይል ወዘተ በአማራው ክልልና አመራርና በአገር መከላከያው በተቀናጀ የጦር እቅድና አመራር ጊዜ ሳይወስድ ጦርነቱ በድል ይደምደም!

ተጨማሪ ያንብቡ:  አባይ ለሕዝብ ወይስ አባይ ለኢሕአዴግ ? - ግርማ ካሳ

ሌሎቻችን በቀጥታ በዱር በገደሉ ለመዋደቅና የዜግነት ግዴታችንን ለመወጣትና ለመሳተፍ ሁኔታው ባይፈቅደልንም ከማሕበራዊ ሚዲያ ወከባ ወጥተን ከዚያ በዘለለ በሁሉም ግንባሮች ፋታ አጥቶ እየተዋደቀ ያሉ የቁርጥ ቀን ጀግኖችንና በሳቢያው እየተፈናቀሉ ወደ ሰባት ሚሊዬን የደረሱ የሚላስ የሚቀመስ ያጡና ዓለምም ጆሮ ዳባ ብሎ የተዋቸውን ወገኖች በአንድ ቅንጅት በመርዳትና ደጀን ሆነን መደገፍ የየግልና የጋራ አሻራችንን ማሳረፍ ለድሉ አንድና አንድ መፍትሔ ነው!

ይህንን ሳናደርግ ቀርተንና የጦርነትን ፊልም ማየት ዓይነት አቃቅር በማውጣት ብቻ ያለተግባራዊ ምላሽ አገራችን ለዳግም ሕወኃት ብናሳልፍ የታሪክ ተጠያቂዎች ብቻ መሆን ሳይሆን ከሕሊናችን ውስጥ በማይወጣ ደዌ ውስጥ እንደምንቀር ልብ ልንል ይገባል እላለሁ።

አበባየሁ አሉላ
ዋሽንግተን ዲሲ

1 Comment

  1. ግርማ ካሳ ተሳስተህ መሰለኝ ካርታህን አስተካክለው ትግሬ የዋህ ነው ግርማ ካሳ ስሎታል ግዛት እስከዚህ ነው ይላል ወደፊት።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share