ሁሉን ንገር ትተን እኛው እንታረቅ! (በዶ/ር ተክሉ አባተ)

ethiopiaኢትዮጵያ ያለችበትን ማኅበራዊ፣ ምጣኔ ሀብታዊና ፖለቲካዊ ቀውስ ሊፈታላት የሚችለው ፍቱን መድኃኒት ብሔራዊ መግባባትና እርቅ እንደሆነ የተለያዩ አካላት እየሰበኩ ይገኛሉ። ምዕራባዊ ሀገራትና የተባበሩት መንግስታት በቀጥታና በተዘዋዋሪ እያስተጋቡት ያለው አጀንዳ የበርካታ ኢትዮጵያውያንን ትኩረት ሳይስብ አልቀረም። በተለይም የቀውሱ ሁሉ ምንጭና ዋና ተዋናይ የሆነው ሕወሓት የብሔራዊ መግባባትና እርቅ ዋና አካል እንዲሆን መወትወታቸው ግርምትን ሳይፈጥር አልቀረም። ሕወሓት በበኩሉ መግባባትና እርቅ እንደሚካሄድ አምኖና እርግጠኛ ሆኖ አደራዳሪ በመምረጥ ላይ የተጠመደ ይመስላል። የኢትዮጵያ ማኅበራዊ የመገናኛ ብዙኃንም ብሔራዊ መግባባትንና እርቅን እንደ ትልቅ አጀንዳ አድርገው ባያራግቡትም የማይናቅ ትኩረት ሰጥተውታል። አንዳንዶች ሕወሓት በብሔራዊ መግባባትና እርቅ መሳተፍ እንደሌለበት ሳይጠቁሙ አላለፉም። የሃይማኖት ተቋማት መሪዎችም ጉዳዩን ዘለግ ላለ ጊዜ ያዝ ለቀቅ ሲያደርጉት ቆይተዋል። መንግስት ደግሞ ብሔራዊ መግባባትና እርቅ የለውጡ አንዱ አካል እንደሆነና ከመጪው መስከረም ወር ጀምሮ ልዩ እንቅስቃሴ እንደሚኖር አመላክቷል። ሕወሓት የሂደቱ ተሳታፊ እንደማይሆን ሳይጠቅስ አላለፈም። ይሁንና ከሦስት ዓመት በፊት የተቋቋመው የብሔራዊ እርቅና መግባባት ኮሚሽን ምን ላይ እንደደረሰ፣ መስከረም ጀምሮ በሚቀጥለው ሂደት ያለው ሚና ምን እንደሆነ በይፋ የተጠቆመ ጉዳይ የለም። ይህ ሁሉ ተደማምሮ በሕዝቡ ዘንድ ብዥታና ጥርጣሬ ሳይፈጥር አልቀረም። በተለይም የሕወሓት እጣ ፈንታ ምን ሊሆን እንደሚችል እያነጋገረ ይገኛል። በጉዳዩ ላይ ቀጣይና የተደራጀ ውይይትና ክርክር ቢኖር ለታሰበው ብሔራዊ መግባባትና እርቅ ማዘጋጃ፣ መሠረትም ሊሆን እንደሚችል አያጠራጥርም።

ይህች ጽሑፍ ጉዳዩ የበለጠ እንዲሳለጥና በመጨረሻም የተሻለ መረዳት እንዲመጣ የበኩሏን አስተዋጽዖ ልታደርግ ትችላለች። የዛሬ ሰባት ዓመት ብሔራዊ መግባባትንና እርቅን በተመለከተ ያካሄድኩት አጭር የዳሰሳ ጥናት ነበር:: በወቅቱ በርከት ያሉ ውይይቶችና መጣጥፎች እያተኮሩበት የመጣው ጉዳይ ነበር:: የጥናቱ ዓላማዎችም ስለብሔራዊ (ኢትዮጵያዊ) መግባባትና እርቅ  በጽንሰ ሃሳብ ደረጃ ምን እንደተጻፈ መመርመር፣ ብሔራዊ መግባባትና እርቅን በተመለከተ በሚገባ ያልተብራሩ ሃሳቦችን ለይቶ ማውጣት እንዲሁም ብሔራዊ መግባባትና እርቅን በተመለከተ ወደፊት በጽንሰ ሃሳብና በተግባር ደረጃ ምን መደረግ እንዳለበት ለመጠቆም ነበር። በወቅቱ የተካሄደው ጥናት በርካታ ጉዳዮችን ያብራራና አቅጣጫ ያመላከተም ነበር:: ለውጡን ተከትሎ ደግሞ አስፈላጊነቱን ስለተገነዘብኩ ይህን ጥናታዊ ጽሑፍ የዛሬ ሦስት ዓመት እንደገና አትሜው ነበር። ጥናቱ አሁንም ወደፊትም የሚካሄዱ ብሔራዊ መግባባትንና እርቅን የሚመለከቱ ዝርዝር አጀንዳዎችን ለመለየት ሊያግዝ ይችላል:: የመነሻ ሃሳቦችን ለመለየት ይጠቅማል:: በመሆኑም የዛሬ ሰባት ዓመት የተካሄደውን ጥናት መነሻ አድርጌ በመሠረታዊና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የራሴን ምልከታ አቀርባለሁ። ይህም የተሻለ ውይይትና ክርክርም ጉዳዩ በሚመለከታቸው አካላት መካከል እንዲደረግ ሊጋብዝ ይችላል።

ብሔራዊ መግባባት ሲባል ምንን ያካትት!

ብሔራዊ መግባባትንና እርቅን በተመለከተ የመገናኛ ብዙኃንና ጸሐፊያን እንዲሁም ፖለቲከኞች የተለያዩ ቃላትንና ሐረጎችን ሲጠቀሙ ይስተዋላል። ብሔራዊ መግባባት ማለት ምንድን ነው? መግባባት ላይ ሊያደርሱ የሚገቡ መሠረታዊ ነጥቦች ምንድን ናቸው? እንዚህና መሳይ ጥያቄዎች በቂና አጥጋቢ መልስ ካላገኙ ሊደረግ የታሰበው ብሔራዊ መግባባትና እርቅ የተንዛዛና አሰልቺ፣ ግቡንም የማይመታ ሊሆን ይችላል። በመሆኑም መሠረታዊ ጽንሰ ሀሳቦችን ቀድሞ መለየትና ለሚመልከተው ሁሉ በጊዜ ማሳወቅ፣ ማስተማር ወሳኝ ነው። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ቀጥሎ የተዘረዘሩትን ጥቂት ዐበይት ነትቦች ግምት ውስጥ ማስገባት ሊጠቅም ይችላል።

ብሔራዊ መግባባትና እርቅ የሚያስፈልገው ሕወሓት የለኮሰውን ጦርነትና ተያያዥ ቀውሶችን ብቻ ታሳቢ በማድረግ መሆን የለበትም። ይህ ጦርነትና ቀውሱ የችግሮች ሁሉ መጨረሻ እንጅ መነሻ አይደለምና። በመሆኑም ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ከተፈለገ ላለፉት 30 ዓመታት የተደረጉ ግፎችን ሁሉ መለስ ብሎ ማየት ያስፈልጋል። እንዲሁም የታሰበው መግባባትና እርቅ በብሔራዊ ደረጃ የሚካሄድ ቢሆንም አፈጻጸሙ ግን በእያንዳንዱ ክልል፣ ዞን፣ ወረድ፣ ቀበሌ፣ መንደር፣ ብሔረሰብ፣ ሃይማኖት ተቋም፣ ፖለቲካ ፓርቲ፣ ሲቪክ ማኅበር፣ ሙያ ማኅበር፣ እድር ወዘተረፈ ደረጃ ሊካሄድ ግድ ነው። በመሆኑም ጉዳዩ የትግራይ ክልል ወይም የሕወሓት ብቻ መሆን የለበትም። በነዚህ ደረጃዎች የሚደረጉ ውይይቶች፣ ክርክሮች፣ ትምህርቶች፣ ሥልጠናዎች የሕዝቡን ዕውቀትና ግንዛቤ ለመጨመር፣ አረዳድንና አመለካከትን ለመለወጥ አንዲሁም የዕለት ከዕለት ማኅበራዊ ተስተጋብሮችን ወይም ግለሰባዊ ባህርይን ለመቀየር የታሰቡ መኖን ይኖርባቸዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ምክንያት አልባው ፅንፈኝነት - በያሬድ ኃይለ መስቀል

ብሄራዊ መግባባትና እርቅ በሚገባ ከተያዘና ከተጠናቀቀ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት የሚያስችል ጭስ አልባ ወይም አረንጓዴ አብዮት ነው። ቀጣይነት ላለው ሰላምና ጤናማ ማኅበረሰብ ለመፍጠር ያስችላል። ለቀጣዩ ትውልድ ኩራትና አንድነትን የሚያጎናጽፍ ይሆናል። ይህ ሁሉ ለውጥ ሊመጣ የሚችለው ግን ቢያንስ ቀጥለው በተዘረዘሩት ጉዳዮች ላይ ሕዝባዊ መሠረት ያለው ተግባቦት፣ መረዳት ሲኖር ብቻ ነው።

ብሔራዊ መግባባትና እርቅ መንግስት ካሰበው ለውጥ ጋር ከተጣጣመ፣ ከተገናበም መሠረታዊ ለውጥ ያመጣል

ብሔራዊ መግባባትና እርቅ ሊሰምር የሚችለው ባለፉት 30 ዓመታት ውስጥ የተደረጉ ግፎችን ሁሉ ስናካትት ነው

የክፋት ሁሉ ምንጭ ስለሆነ ሕወሓት እንደ ድርጅት ለዘላለም አሸባሪ ተብሎ መፈረጅ አለበት

ከፍተኛ የሕወሓት አመራር አባላት በሀገርና በሕዝብ ላይ የፈጸሙት ግፍ ከአእምሮ በላይ ስለሆነ ጉዳያቸው በሕግ እንዲታይ ማድረግ፣ ወደፊትም በማናቸውም የሥራ ሓላፊነት ቦታዎች እንዳይሾሙ ማድረግ

የቀውሱ ሁሉ መሐንዲስና ሥራ አሥፈጻሚ ሕወሓት ቢሆንም በሁሉም ደረጃ ከሁሉም ብሒረሰብ ተባባሪዎችና አጋፋሪዎች እንዳሉም መቀበል

እነዚህ ባለሥልጣናት ለፈጸሙት ግፍ ወይም ወንጀል ከዚህ በፊት በይፋ ሕዝብን ይቅርታ ከጠየቁ ይቅርታው እንዲጸና ማድረግ

ይቅርታ ያልጠየቁ ካሉ ሥራቸውን አውቀው ከልብ የመነጨ ይቅርታ እንዲያቀርቡ መጋበዝ

ዘርን ወይም ብሔረሰብን ወይም ነገድን መሠረት ያደረገ ፖለቲካ ሀገራችንን በሁሉም መስክ እንዳደቀቃት ማመን

እውነተኛ፣ ሕዝባዊና ብሔራዊ መንግስት የሁሉንም ቡድኖችና ግለሰቦች መብትና ጥቅም ማስከበር እንደሚችል ማመን

በመሆኑም በብሔረሰብ ወይም በቋንቋ ላይ የተመሰረተ አስተዳደርም ሆነ የፖለቲካ አወቃቀር እንዳይኖር ማድረግ

የቀውሱ ሁሉ ሕጋዊ መሠረት ስለሆነ ሕገ መንግስቱ ዜጋን ባማከለ መልኩ መቀየር እንዳለበት ማመን

ብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማችንም የሕዝቡን ፍላጎት ባማከለ መልኩ መቀየር እንዳለበት ማመን

እስካሁን ድረስ በግፍ የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ለትውልድ መታሰብ ስላለባቸው እነሱን የሚመጥን ቤተ መዘክርና ቤተ መጽሐፍት በአዲስ አበባና በክልል ታላላቅ ከተሞች መገንባት እንዳለበት መተማመን

ብሔራዊ መግባባትና እርቅ የሚሳካው አስታራቂው አካል ፍጹም ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ተአማኒነት ሲኖረው ብቻ እንደሆነ ማመንና በዚያም መሠረት ማዋቀር

የሚታረቀው ማን ነው?

ብሔራዊ መግባባትና እርቅ የተጣሉ አካላት እንዳሉ አመላካች ቃል ነው። ከላይ እንደተጠቀሰው የታሰበው መግባባትና እርቅ በብሔራዊ ደረጃ የሚካሄድ ቢሆንም አፈጻጸሙ ግን በክልል፣ በዞን፣ በወረድ፣ በቀበሌ፣ በመንደር፣ በብሔረሰብ፣ በሃይማኖት ተቋማት፣ በፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ቢሲቪክ ማኅበራት፣ በሙያ ማኅበራት፣ በእድሮች፣ ወዘተረፈ ደረጃ ሊካሄድ ግድ ነው። በመሆኑም ብሔራዊ መግባባትና እርቅ አሁን እየተካሄ ባለው ጦርነት ላይ ወይም ከሕወሓት ጋር ብቻ የተወሰነ አይደለም። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ በአንድ ወቅት እንደተናገሩት በማጭበርበር ያልተነካካ የለም። ምንም እንኳን ሕወሓት ለተፈጸመው ግፍ ሁሉ የመጀመሪያው ተጠያቂ ቢሆንም በየደረጃው ያሉ ተቋማትም በአንድም በሌላም መንገድ የክፋቱ ተባባሪ አስፈጻሚም ሆነዋል። ከዚህ መሠረታዊ ሀሳብ ከተነሳን መግባባትና እርቅ በብሔራዊ ደረጃ ለማምጣት በየደረጃው መሠራት ያለባቸው ሥራዎች አሉ። ማለትም በየደረጃው መግባባትና እርቅ ሊደረግ ግድ ነው። ሁሉም አካላት እንደሚገባቸው ሕዝብን በታማኝነት፣ በእኩልነትና በፍትሕ፣ በጥራት፣ በንጽህና ወይም በታማኘንት፣ ሳላላገለገሉ ወይም ግፍ ሲፈጸም ዝም ብለው ስላዩ ተጠያቂ ስለሆኑ የተናጥል መግባባትና እርቅ ያስፈልጋል። ለመነሻ ያህል ቀጥሎ የተዘረዘሩትን ግምት ውስጥ ማስገባት ይቻላል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  U.S. Double-talking Human Rights in Ethiopia, Again!

መግባባትና እርቅ በሃይማኖት ተቋማት መሪዎች ውስጥ። ለምሳሌ የሲኖዶስ አባላት ለብቻቸው፣ የመጅሊስ አባላት ለብቻቸው እንደ መሪ የወደቁባቸውን ፈተናዎች በማንሳት እርስ በእርስ ከልብ ይቅር መባባል፣ ይህንም ለሕዝብ ይፋ ማድረግ። የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች የሞራል ልእልና ይዘው ገዳይና ጨቋኝ መንግስታትን መገሰጽ፣ ማስተማር ስላልቻሉ፣ ለሚመሩት አማኝም ጠበቃ ሊሆኑለት ስላልቻሉ ተጠያቂቆች ናቸው። እንዲያውም መንግስትን ተገን አድርገው የራሳቸውን ሌቦችና ዘረኞች በየእምነት ተቋማቱ በመሰግሰግ ሀብት ንብረት ዘርፈዋል፣ ሰው አስገድለዋል፣ አሰድደዋል፣ አስደብድበዋል፣ አሳስረዋል። በመሆኑም ሕዝቡ ለሃይማኖት ያለውን ክብርና ዋጋ እንዲቀንስ ክፉኛ ጥረዋል።

መግባባትና እርቅ በሃይማኖት መሪዎችና በአማኞች መካከል ። ለምሳሌ ሲኖዶስ ሕዝቡን ከሚወክሉት ጋር፣ መጅሊሱም እንዲሁ

መግባባትና እርቅ በሃይማኖት ተቋማት መሪዎች መካክል። ለምሳሌ የሲኖዶስና የመጅሊስ አመራሮች ተግባቦት ፈጥረው ይቅር ተባብለው ለሕዝብ ምሳሌ ሆነው መታየት ይኖርባቸዋል

መግባባትና እርቅ በመንግስት ተቋማት መሪዎችና በገዥው ፓርቲ መካከል። ይህ የብሔራዊ መግባባትና እርቅ ትልቁን ድርሻ የሚወስደው ነው። ፓርቲዎች እንደ ብልጽግና፣ ኢሕአዴግ፣ ብአዴን፣ ኦሕዴድ፣ ደሕዴድ ራሳቸውን መርምረው የምር ተግባቦት ላይ መድረስ አለባቸው፣ ሕዝቡንም ይቅርታ መጠየቅ አለባቸው። ዞሮ ዞሮ የቀውሱን ሁሉ የአንበሳ ድርሻ የሚወስዱት እነዚህ ተቋማት ናቸውና ትልቅ ሥራ መሠራት አለበት

መግባባትና እርቅ በተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል

መግባባትና እርቅ በተቃዋሚ ፓርቲዎችና በገዥው ፓርቲ መካከል

መግባባትና እርቅ ከላይ በተጠቀሱት አካላት ሁሉ መካከል። ብሔራዊ መግባባትና እርቅ የሚባለውም ይህ የመጨረሻው ደረጃ ነው። ሁሉንም ሕዝብ ማሳተፍ ስለማይቻል በሁሉም ደረጃ ካሉ አካላት የተቻለውን ውክልና ማስገባት ይመረጣል።

አከራካሪ ነጥብ የሚሆነው የሕወሓትና የኦነግ ሸኔ በብሔራዊ መግባባትና እርቅ መሳተፍ ወይም አለመሳተፍ ነው። ሁለቱም ድርጅቶች በአሸባሪነት ስለተፈረጁ እነሱን የእርቁ አካል ማድረግ ክሕግ አኳያ አጣብቂኝ ውስጥ ሊከት ይችላል። ይሁንና እዚህ ላይ ልዩ ጥንቃቄ ልናደርግና ሰፋ አስርገን ልንመለከት ይገባል። ሁለቱ ድርጅቶች እስካሁን ድረስ ያስከተሉትን ቀውስ፣ ይህ ቀውስም የማይረሳ ጠባሳ ጥሎ እንደሚሄድ ማንም አይስተውም። ይሁንና ሁለቱን ድርጅቶች የሚወክሉ አመራሮች ላይ ብቻ ማተኮርና ተራ አባላትን በብሔራዊ ይቅርታ ማለፉ አዋጭነቱ አያጠያይቅም። በማቀድ፣ በማስፈጸም፣ ግብአት በማቅረብ፣ ሞራል በመስጠት፣ በማስገደድ፣ በማታለል፣ በመደለል፣ ከውጭ ኃይሎች ጋር በማበር ወዘተ ከፍተኛውን አስተዋጽዖ የሚያደርጉት የማእከላዊና ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ናቸው። እንዚህን አመራሮች ከብሔራዊ መግባባትና እርቅ ውጭ አድርጎ በሕግ መጠየቅ ፍትሐዊ ከመሆኑም በላይ አስተማሪነቱ የጎላ ይሆናል። በእርግጥ አንዳንድ የማእከላዊና ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በምንም መንገድ የጎላ በደል ላያደርሱ ይችሉ ይሆናል። በአንጻሩ ደግሞ አንዳንድ ተራ አባላት ከአመራሩ በላይ ግፍ አድርሰው ይሆናል። በመሆኑም  ብሔራዊ መግባባትና እርቅን የሚመራው አካል ብርቱ ጥንቃቄ እያደረገ ሊሠራ ይችላል። ባጠቃላይ ሲታይ ግን ከነዚህ የሥራ ሓላፊዎች ውጭ ያለውን ተራ አባል በይቅርታ ማለፍ ሆደ ሰፊነት ነው። ሁሉንም እንክሰስ ወይም እንሰር ከተባለ እስር ቤቶችን ስንገነባ፣ ዳኞችንና ጠበቆችን ስናሰለጥን ልንኖር ነው። በመሆኑም ብሔራዊ መግባባትና እርቁን የሚያስተባብረው አካል ፍትሕና እውነታ ላይ የተመሠረተ አሠራር ቢከተል የተመረጠ ነው።

እርቁን ማን ያስተባብረው?

ከላይ በመግቢያዬ በጠቀስኩት ጥናት ውስጥ የተካተቱ ብሔራዊ መግባባትና እርቅን ሊያስተባብሩ የሚችሉ አካላት ተለይተዋል። እርቁን መጀመርና ማስተባበር ያለበት መንግስት እንደሆነ ያተቱ አሉ:: ፍላጎትና ዝግጁነት ካለው መንግስት ካለበት ብሔራዊ ሓላፊነትና ካለው አቅም አኳያ ይህን የማስተባበር ሥራ ቢወስድ እንደማይከብደው ይገመታል:: እርቁን መምራት ያለባቸው  ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ናቸው የሚሉም አሉ:: ይህ አማራጭ ከፖለቲካው ሜዳ በመንግስት እየተገፉ ያሉት ሓይሎች ሂደቱን እንዲመሩት ያመቻቻል:: መንግስትና ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ዋና የእርቁ አካል ስለሆኑና በዳይና ተበዳይም ስለሆኑ ነጻና ገለልተኛ ኢትዮጵያውያንን ያቀፈ አስታራቂ ግብረ ኃይል የእርቁን ሂደት መምራት አለበት የሚሉም አሉ:: ከነዚህ አማራጮች ለየት ያሉም አሉ:: ሁሉን አቀፍ የምክክር ጉባዔ እንዲጠራ ያሳሰቡም አሉ:: መገናኛ ብዙኅን አስተዋጽዖ ማድረግ እንደሚችሉ ቢጠቀስም ሂደቱን ማን እንደሚመራውና እንደሚጀምረው ግን ግልጽ አይደለም:: እንዲሁም ወጣቱ ትውልድ ወደብሔራዊ እርቅ የሚያደርሰውን ውይይትና ምክክር በበላይነትና በባለቤትነት መምራት እንዳለበት ያሳሰቡም አሉ:: የተማረው ወጣቱ ትውልድ የትናንቱ ትውልድ ከሚዳክርበት የግራና የቀኝ የፖለቲካ አመለካከት ነጻ ሆኖ የእርቁን ሂደት ቢመራው እጅግ እንደሚሻል ተጠቁሟል:: ምዕራባዉያን ደግሞ  ራሳቸው የሚመሩት ዝቅ ሲል ደግሞ የአፍሪካ ኅብረት የሚመራው አካል እንዲቋቋም  በገደምዳሜ እየተናገሩ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰው ሆይ! - በላይነህ አባተ

ይሁንና ለውጡን ተከትሎ መንግስት ያቋቋመው የብሔራዊ መግባባትና እርቅ ኮሚሽን እንዳለ ይታወቃል። ከአመሰራረቱ ጀምሮ አሠራሩም ግልጽነት ስላልነበረው እንዲሁም በብዙ ድካም የሚታሙ ግለሰቦች የተካተቱበት ስለሆነ ብዙ ሰዎች በጥርጣሬ ይመለከቱታል። ከዚህ በላይ ደግሞ ይህ አካል ከተቋቋመ ዓመታት ቢቆጠሩም ይህ ነው የሚባል ሪፖርትም ሆነ ተስፋ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ሊሰጥ አልቻለም። ይህ በዚህ እንዳለ ይህ አካል ከመስከረም ጀምሮ ሊካሄድ ለታሰበው ብሔራዊ መግባባትና እርቅ አስተባባሪ ከሆነ የአሰበውን ያህል ለውጥ ሊያመጣ አይችል ይሆናል። በመሆኑም ይህ አካል ተበትኖ እንደገና መደራጀት አለበት ወይም አሠራሩንና ቅቡልነቱን አስቀድሞ ሊያስመሰክር ይገባል። ቅቡልነት የሚመጣው ደግሞ ግለሰቦች ባላቸው የሞራልና የምግባር ልእልና ነው። ብዙዎች አባላት በተለያዩ ጉዳዮች ተዋንያን ስለነበሩ መግባባትና እርቅ ሊያመጡ የሚችሉት መጀመሪያ ራሳቸው ተግባብተውና እርቅ አውርደው ለሕዝብ ሲያሰሙ ብቻ ነው። ለሕዝብ ይፋ መሆን ያለበት የመጀመሪያው መግባባትና እርቅ መሆን ያለበትም ከዚህ ኮሚሽን አባላት ነው። ይህ ሲሆን ብቻ ነው ለቆሙለት ከባድ ሓላፊነት እንደሚመጥኑ የሚታወቀው። እንዲሁም የኮሚሽኑ አባላት በአስተሳሰባቸው፣ በሞራል፣ በምግባር፣ በተግባቦት፣ በአካታችነት፣ በፍትሕ፣ በሐቀኝነት ወዘተ አርአያ መሆን የሚችሉ መሆን አለባቸው። የኢትዮጵያን አንድነትና ሰላም አብዝተው የሚፈልጉ ለእሱም መሳካት ሳይታክቱ የሚጥሩ መሆን ይገባቸዋል። ከሕዝብ ድጋፍና ተቀባይነት ለማግኘት እቅዳቸውንና ሥራ አፈጻጸማቸውን በየጊዜው ግልጽ ማድረግ ይኖርባቸዋል።

ዋናው መሰመር ያለበት ጉዳይ ብሔራዊ መግባባትና እርቅ መታቀድ፣ መፈጸም፣ ሪፖርት መደረግ ያለበት በኢትዮጵያውያን ብቻ መሆን ይገባዋል። የማንም ሀገር ልምድም ሆነ እገዛ አያስፈገንም። ኢትዮጵያ ከሦስት ሺህ ዓመታት በላይ የቆየች ሀገር ነች እያልን፣ የአይሑድ፣ የክርስትናና የእስልምና ሃይማኖቶች መናኸሪያ ነች እያልን፣ ከ95% በላይ ፈጣሪን አማኝ ሕዝብ አላት እያልን፣ የተራቀቁ የሽምግልናና የእርቅ ሥርዓታት አሉን እያልን የውጭ ሀገራት ወይም ግለሰቦች በብሔራዊ መግባባትና እርቅ ሂደት ዋና ተዋናይ እንዲሆኑ መፍቀድ እጅግ ያስተቻል። ብዙ ጣጣም ይዞ ሊመጣ ይችላል። የደቡብ አፍሪካም ሆነ የሩዋንዳ፣የኮሎምቢያም ሆነ የቺሊ፣ የካናዳም ሆነ የደቡብ ኮሪያ ልምድም ተሞክሮም አያስፈልገንም። በመሆኑም አስታራቂዎችም፣ ታራቂዎችም፣ ፍትሕ ሰጭዎችም እኛው መሆን አለብን። ወደራሳችን ወደ ሀብቶቻችን እንመልከት። ጥቃቅን ጉዳዮችን ወደጎን ትተን መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ ብቻ እናተኩረ። ንዋይ ደበበ እንዳለው ሁሉን ነገር ትተን እኛው እንታረቅ! ይህ ከሆነ ለማኅበራዊ፣ ለባህላዊና ሃይማኖታዊ  እሴቶቻችን ክብርና ዋጋ እንሰጣለን። ይህንም ለቀጣዩ ትውልድ እናወርሳለን። ሰላምና አንድነት ለዘላለም በኢትዮጵያ ይሰፍናሉ። የዘመኑ አርበኝነትም ይህ ነው።

 

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

ገንቢ አስተያየት ካላችሁ በteklu.abate@gmail.com ላኩልኝ።

3 Comments

  1. ወያኔ በገባው ቃል መሰረት ሂሳብ እያወራረደ ነው። አሁን ከወያኔ ወረራ ነጻ ሆኑ በተባሉት ቦታዎች በአፋርና በአማራ ህዝብ ላይ የፈጸመው ዘግናኝ በታሪክ ከናዚ ጀርመኖች ድርጊት ጋር የሚነጻጸር ነው። አንዲት የገጠር ሴት ወያኔን እንዲህ ስትል ተገልጣቸዋለች። ወያኔ ማለት አረመኔ፤ ጨካኝ ከሰው ዘር መመደብ የማይቻሉ ፍጥሮች ናቸው። ሌላው ራሱን የጠመጠመ ቄስ ነህ ወይ ተብሎ ሲጠየቅ አይ ለጸሃዪ ነው ቄስ አደለሁም ካለ በህውላ ያየውን ሲነገር ቤት እያንኳኩ ሰውን በተለይም ወጣቱን አውጥተው ካሰለፉ በህዋላ ረሸኗቸው። እንቅበር ስንል አይሆንም በማለት ነዳጅ አርከፍክፈው አቃጠሏቸው በማለት እንባ እያፈሰሰ ምሬቱን ገልጿል።
    ዶ/ሩ ከላይ ስለ ሰላምና እርቅ ያወራሉ። ምን አይነት ሰላምና እርቅ ነው ከአውሬ ጋር ሰው እንዲኖር የሚያመቻቸው? ወይስ ጸሃፊው የወያኔ የ 27 ዓመት ሴራና አሁን የሚያደርጉት እኩይና ዘግናኝ ድርጊት ግልጽ አልተረዳውም?
    ትላንት ንፋስ እንደ መታው ድቄት ተበተኑ፤ ቀበርናቸው፤ አበቃላቸው እያሉ ባለስልጣኖች ሲደነፉ እኔ ተው ጉራ ትንፉ፤ ወያኔ ማለት ድመት ማለት ነው። ዘጠኝ ነፍስ አላቸው በማለት በዚሁ ድህረ ገጽ ላይ የጻፍኩትን ወደ ኋላ ተመልሶ ማንበብ በቂ ይመስለኛል። የአሁኑ ጉራም ከዚያው የቀጠለ ነው። ቀጠቀጥናቸው፤ ፈረጠጡ፤ ተበተኑ፤ ተሽመደመድ፤ ተቆርጦ የቀረውን እያጸዳን ነው ወዘተ የሚለው ወሬ ሁሉ ግብስብስ ነው። ወያኔ ታንክ፤ ከባድ መሳሪያ፤ የአየር መቃወሚያ ይዞ ነው አፋርና የአማራን ክልል በማተራመስ ላይ ያለው። የተበተነ እና የተደቆሰ ሃይል ይህን የማድረግ አቅም አይኖረውም። የወያኔን ወታደራዊ ስልትና ጉልበት አለማድነቅ አይቻልም። የሚፈጽሙትን ግፍና በደል እንዳለ ሆኖ ሙሉ ትጥቅ ባለው መንግስት ነኝ በሚል ሰራዊት ላይ ጥቃት ፈጽሞ ዳግመኛ እንዳይነሱ አረገን ደቆስናቸው ተብለን እንደገና ነፍስ ዘርተው ዛሬ የሚፈጽሙትን ወታደራዊ እንቅስቃሴ ልብ ላለ ሰው አስገራሚ ድርጊት ነው። በጭልጋ፤ በወለጋ፤ በአማራና አፋር ክልል በሌሎችም የሃገሪቱ ክፍሎች ሰውን ከሰው የሚያተራምስቱት እነዚህ የሞት መልዕክተኞች ማቆሚያቸው የት እንደሆነ ገና የታወቀ ነገር የለም። ነጩና አረቡ አለም ስለ ትግራይ ህዝብ መራብና መከራ ሲዘግብ ወያኔ ባደረሰው ዘግናኝ ግፍ ስለወደመው ንብረትና የሰው ሞት ብሎም መፈናቀል ትንፍሽ አይሉም። በአውሮፓና በሰሜን አሜሪካ የትግራይ ተወላጅ የሆኑ በአሸንዳ በአል ሰበብ ሲዘፍኑና ሲዘሉ ማየት መፈጠርን ያስጠላል? ለመሆኑ እነዚህ ሰዎች የትግራይ ህዝብ በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ይረዳሉን? ቀሪዎቹ ምንም ባልተረድት ነገር ወያኔና ወረራውን ደግፈው ጀኖሳይደ በትግራይ ህዝብ ተፈጸመ በማለት በየመንግስታቱ መ/ቤት በመሰለፍ ሲያላዝኑ ማየት የዘረኝነታቸው በሽታ ጣራ ላይ እንደ ደረሰ አመላካች ነው። እንግዲህ ይህ በዚህ እንዳለ ነው ሁሉን ነገር ትተን እናው እርቅ እናውርድ የሚባለው። የእርቅ የመጀመሪያው መስፈርት ሰላምን መናፍቅ ነው። ወያኔ ባሩድ ካላሸተተ፤ በሰው ደም እጅ ካልተጨማለቀ እንደማይኖር ያውቃል። ወያኔ በስልጣን ላይ እያለ በምንም ሂሳብ ሰላም ሊሰፍን አይችልም። ዞረው ተመልሰው ያው ሂሳብ ማወራረድን ይቀጥላሉ እንጂ። ወያኔን ከስልጣን ማውረድ የሚችለውና የሚገባው የትግራይ ህዝብ ነው። ሌላው ሁሉ ተቀጥላና ድጋፍ ሰጪ ሃይል ቢሆን እንጂ እዚህ ግባ የሚባል አስተዋጾ ማድረግ አይችልም።
    እየሞቱ በሚሸለልበት ሃገር፤ እንስሳትን ሳይቀር በጥይት የሚቦዳድስ የሰው አራዊትና በሃሽሽ የሰከረ ትውልድ እንዴት ተደርጎ ነው ለሽምግልና መቀመጥ የሚቻለው? በጭልጋ፤ በደብረዘቢጥ፤ በቆላ ወገራ በላሊበላና ዙሪያዋ በአፋር በራሄሌና አካባቢው ዛሬ ማን ነው አርሶ አደሩን በማሸበርና በመግደል ላይ ያለው? ወያኔ አይደለምን? በሜዳ ላይ ጉራው ማለትና ተግባር ይለያያሉ። እንዲያው በፈጠራችሁ ተደመሰሱ፤ ተያዙ፤ ፈረጠጡ አትበሉን። ሰልችቶናል። ወሬአችሁን በጓዳችሁ አድርጉት። ስንት ሰፊ ሥፍራ በወያኔ ተይዞ እንደፈለጉ እያደረጉት ደመሰስናቸው፤ በቅርብ ቀን ለህዝባችን የድል ወሬ እናሰማለን ገለ መሌ መባሉ ፍሬ ቢስ ነው። የትግራይ ህዝብ እፎይ እንዲል፤ ቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ በሰላም አብሮ መኖር እንዲችል ወያኔ ሃርነት ትግራይ ከስልጣን ወርዶ የትግራይ ህዝብ በፈለገው መንገድ መሪዎቹን ይምረጥ። ከኢትዮጵያ ጋርም አብሬ መኖር አልፈልግም ካሉ ይገንጠሉ። ግን የመገንጠሉ ሃሳብ የወያኔ እንጂ የትግራይ ህዝብ አለመሆኑ የታወቀ ነው። ወያኔ አጣብቂኝ ውስጥ ገብቷል። ጭራሽ ጭራቅ መሆኑን ለአፋርና ለአማራ ህዝብ በ 27 ዓመት አገዛዙ ካሳየው በላይ አሳይቷል። ሰው ከህጻን እስከ አዛውንት አክ እንትፍ ብሏቸዋል። በጦር ግንባር ያሉ የትግራይ ልጆች በየጊዜው መሞታቸው ደግሞ ለትግራይ ህዝብ መነሳሳትና አመጽ ዋና መሳሪያ ነው። ለምን ብሎ መጠየቅ ከቻለ። ስለሆነም እርቅ እናርግ መባሉ የበሽታ እንጂ የጤና አይደለም። ይህ ሁሉ ጥፋት ከመድረሱ በፊት ደብረጽዪንን የለመኑት እናቶች እንባ አይታይህም እንዴ? ስንት ጊዜ ነው ዶ/ር አብይ የሰላሙን ጥሪ ያራዘመው? ይህ ሁሉ ግን ለወያኔ ጉልበትና ጊዜ መግዣ ሆነው እንጂ እውነትን እንዲረዳ አልጠቀመውም። ፈረንሳዪች፤ እንግሊዞችና አሜሪካኖች ከጀርመን ገስታፓ ጋር ለሰላም አልተቀመጡም። ለፍርድ አቀረቧቸው እንጂ። ወያኔ ከጀርመኑ ገስታፓ ይከፋል። እርቅ በእሳት መካከል መጀመር አንድ ሌላውን እንዲገፋው ይረዳል እንጂ ጠቃሚነት የለውም። ጦርነቱ መቀጠል አለበት። ወያኔ በቃኝ ብሎ እጅ እስኪያነሳ ወይም የትግራይ ህዝብ ከህዋላ እስኪወጋው ድረስ ትግሉ መቀጠል አለበት። የአሜሪካ አስታራቂ ሃሳብም ለተንኮል እንጂ ለሰላም አለመሆኑን ሁሉ ሊገነዘበው ይገባል። በቃኝ!

  2. ከወያኔ ጋር ምንም ዓይነት ድርድር መደረግ የለበትም ከነሱ ጋር እርቅና ሰላም ማምጣት አይቻልም ምክንያቱም እነሱ ሰላምን አይፈልጉም ቢፈልጉም በጦርነቱ ገፍተው የበላይነት በመያዝ የቀድሞ ስፍራቸውን በማረጋገጥ ነው፡፡ስለዚህ ከወያኔ ጋር የሰላም ድርድር እንኳን ቢደረግም የጥግራይን ህዝብ ፍላጎት ሊያሟሉ ከሚችሉ የጥገራይ ልጆችና እነኝህን በደም የተጨማለቁ የወያኔ መሪዎችን ለኢትየጵያ ፍርድ ቤቶች አሳልፈው ከሚሰጡ እውነተኛ የትግራይ ህዝብ ወኪሎች ጋር መሆን የለበትም አለበለዚያ ድመት መንኩሳም አይጥ መብላትዋን አትረሳም እነደይሆን እርቁ፡፡
    ወያኔነ መሪዎቹ ለፍርድ መቅረብ አለባቸው የወያኔ ሀብት በጦረነቱ በግፍ ደማቸው ለፈሰሰና ሀብት ንብረታቸው ለተዘረፈ ዜጎቸ ካሳነት መዋል አለበት፡፡ ቀጣዩ ዘመን ወያኔን በፖለቲካው በአጸደ ነፍስ የማኛይበት የህዝባችን ሰላም የተረጋገጠበት መሆን አለበት ይህ የሚሆነው ወያኔና መሪዎቹ በህዝብ ክንድ ደቀው ሲሸነፉ ብቻ ነውአለበለዚያ ሰላምን እነደጓጓን እንቀራለን በጥባጭ እያለ ማ ነጹሀ ውሀ ይጠጣል፡፡

  3. ከወያኔ ጋር ምንም ዓይነት ድርድር መደረግ የለበትም ከነሱ ጋር እርቅና
    ሰላም ማምጣት አይቻልም ምክንያቱም እነሱ ሰላምን አይፈልጉም
    ቢፈልጉም በጦርነቱ ገፍተው የበላይነት በመያዝ የቀድሞ ስፍራቸውን
    በማረጋገጥ ነው፡፡ስለዚህ ከወያኔ ጋር የሰላም ድርድር እንኳን
    ቢደረግም የጥግራይን ህዝብ ፍላጎት ሊያሟሉ ከሚችሉ የጥገራይ
    ልጆችና እነኝህን በደም የተጨማለቁ የወያኔ መሪዎችን ለኢትየጵያ
    ፍርድ ቤቶች አሳልፈው ከሚሰጡ እውነተኛ የትግራይ ህዝብ ወኪሎች
    ጋር መሆን አለበት አለበለዚያ ድመት መንኩሳም አይጥ መብላትዋን
    አትረሳም እነደይሆን እርቁ፡፡
    ወያኔነ መሪዎቹ ለፍርድ መቅረብ አለባቸው የወያኔ ሀብት በጦረነቱ
    በግፍ ደማቸው ለፈሰሰና ሀብት ንብረታቸው ለተዘረፈ ዜጎቸ ካሳነት
    መዋል አለበት፡፡ ቀጣዩ ዘመን ወያኔን በፖለቲካው በአጸደ ነፍስ
    የማኛይበት የህዝባችን ሰላም የተረጋገጠበት መሆን አለበት ይህ
    የሚሆነው ወያኔና መሪዎቹ በህዝብ ክንድ ደቀው ሲሸነፉ ብቻ
    ነውአለበለዚያ ሰላምን እነደጓጓን እንቀራለን በጥባጭ እያለ ማ ነጹሀ
    ውሀ ይጠጣል፡፡
    ኢትዮጵያ የተራዘመ ጦርነት የሚሸከም ኢኮኖሚየላትም ይህ
    ይታወቃል ወ|ያኔንም መልሶ የሚያዝል ጀርባ የላትም መፍትሄው
    በተቀናጀ ትግል ጦረነቱን ማሳጠርና ወያኔን እስከወዲያኛው መቅበር
    በተቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ መካከል (የትግራይንእውነተኛ ልጆች
    ጨምሮ) እርቅና ሰላም ማውረድ ከመካከላችን መረጃ ለጠላት መላስ
    አሳልፈው በመስጠት ጦርነቱ እንዲራዘም የሚሰሩ ከአመራሩ ስፍራሊነሱ ይገባል ፡ ከሀዲዎቸን መመንጠርና ውስጣችንን ማጥራት
    ያስፈልጋለ፡፡
    የብአዴን ቆሻሻ መሪዎች የባንዳነት ታሪክ ጦርነቱን ለመምራት
    የሚያስችል ቁመናና ወኔ የላቸውም ጠፈጥፎ በፈጠራቸው መለስ
    ዜናዊ የሚያመልኩ ለሆዳቸው ያደሩ ቅንጣት ታክል የኢትዮጵያዊነትና
    የአማራነት ስሜት የሌለባቸው ስለሆኑ በነሱ የሚመራ ጦርነት
    የህዝብን ህይወት፤ሀብትና ንብረት ለአደጋ ከማጋለጥ ውጭ ውጤቱ
    በዜሮ የተባዛ ነው፡፡
    ትናንት ከወያኔ ጋር ሆነው ህዝብ ሲያሰፈጁ የነበሩ ይቅርታ ያልጠየቁና
    በዚያው ስህተትና እብሪት የቀጠሉ የብአዴን ሰዎች ዛሬ ለድል ያበቁናል
    የሚል እምነተ የለንም ስለዚህ ያለነሱ ድል እነኣደርጋለን በትንታግ
    ተዋጊዎቻችን፡
    ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share