አይ ሀገሬ ኢትዮጵያ! ሰውን ለማዳን የማለው ሰውን ጨረሰው (እልማዝ አሰፋ-ዘረ ሰው)

የተሟላና ደስታን ባቀፈ ሕይወት ውስጥ ስንኖር የጤንነትን ዋጋ መገመት ይከብዳል፡፡ ሁላችንም ብቃት ያላቸውና ለሙያቸው ኃላፊነት የሚሰማቸውንና ገንዘብ ለመስራት ሳይሆን ሰውን ለማዳን በሕክምና ትምህርት ፍፃሜ ጊዜያቸው የወሰዱትን የሂፖክራሲያዊ መሐላ እውን የሚያደርጉ የጤና ባለሙያዎች (ሐኪሞች) ጤንነታችንን እንዲንከባከቡ ሁላችንም እንሻለን ፡፡

የሕክምና ሙያ : ከማናቻወም በትምህርት ከሚገኙትና ከሚቀሰሙት ሙያዎች የላቀና እጅግ አስፈላጊና የአገር ቀጣይነት የሚያራምድ ሙያ መሆኑን ማንም አይጠራጠርም:: ምክንያቱም አገርን እገር የሚያሰኘው የሰው ልጆች መኖር ነው:: ለአገር ብልፅግና የሕዝቧቿ ጤንነት በከፍተኛ ደረጃ መጠበቅ እስፈላጊነቱ አያጠያይቅም:: ጤናማ ሰዎች የአገር እድገትና ልማት ምንጮች ናቸው:: ለዚህም ሐኪሞች በማያጠራጥር የሂፖክራሲያዊ መሐላቸው በሚያስገድዳቸው መንገድ ሂሊናቸውን ለገንዘብ ሳይሸጡ በችሎታቸው መጠን ችሎታቸው የሚፈቅድላቸውን አገልግሎት ማበርከት ይጠበቅባቸዋል::

ሁሉንም ማወቅ ለማንኛውም ሰው የማይቻል ስለሆነ ከአጠቃላይ የሕክምና ትምህር በሗላ እያንዳንዱ ምሩቅ ሐኪም በመረጠው ልዩ ሕክምና ዘርፍ ገብቶ ልዩ ትምህርት ይወስዳል:: ለዚህም ነው : የልብ በሽታ ልዩ ሐኪም : የኩላሊት በሽታ ልዩ ሐኪም : የካንሰር ልዩ ሐኪም : የአእምሮ በሽታ ልዩ ሐኪም በሚል በተለያዪ የሰውነት አካል ክፍሎች ረገድና በአእምሮ አኳያ የልዩ ሕክምና ሙያዎች የሚኖሩት:: አንድ ሐኪም ምንም ጎበዝ ቢሆን የብዙ ልዩ ሕክምናዎች ሐኪም ለመሆን እድሜ ልኩን ቢማር የሁሉም ጠቢብ ሊሆን አይችልም:: በአለም ደረጃ ከሚሰጡት ሙያዎች የሕክምና ሙያ በእስፈላጊነቱ አንደኛ ደረጃ ይይዛል:: ምክንያቱም ሕክምና በሕይወት ከመሰንበትና ከመሞት ያለውን ምርጫ ወደ ሕይወት ቆይታ የሚያሸጋግር ሙያ ነው:: ሰዎች ከአልኖርን : አለም እኛ ሰዎች እንድምናውቃት ልትኖር አትችልም:: የሰዎችን ጤንነት መንከባከብ ዋናውና የማሉበት የሐኪሞች ተልእኮ ነው:: ለዚህም ነው በአለማችን ይህ ሙያ ተከብሮ የሚታየውና አንዳንዴ ሐኪሞች ከፈጣሪ ቀጥሎ በምድር ላይ እንደ ሁለተኛ ፈጣሪ የሚቆጠሩት::

ታዲያስ ኢትዮጵያ ውስጥ ይህ የተከበረና የተደነቀ ሙያ በሙያቶኞቹ ይከበራል? ይህን ስል ምን ማለቴ ነው? ይህንን ለመመለስ የሕክምናን ሙያ ተልእኮ እንደገን መመልከት አስፈላጊ ይሆናል:: በጥቂት ቃላት ባስቀምጥ የሕክምና ዋንኛውና ታላቁ ተልእኮ ለሰዎች በሕይወት የመቀጠልን ተስፋ መስጠት ነው:: ሂፖክራትስ እንዳለው ለሞት የሚያበቁና የማይድኑ በሽታዎች እንኳ ሳይቀሩ ሕክምና አገልግሎት ለወደፊቱ የበለጠ ውጤታማ ሕክምና ለማግኘት ተስፋ እንደሚሰጥ ቃል በመግባት : ሕክምና አንዳንድ ጊዜ በመፈወስ : ብዙ ጊዜ በመንከባከብና : ሁል ጊዜም መጽናናትን በመስጠት ተልእኮውን ይቀጥላል ፡፡

ይህ ተልእኮ እንዲቀጥል: ሐኪሞች በሕክምና ትምህርት በምርምርና በሕክምና እንክብካቤ የላቀ ችሎታ እንዲያዳብሩ እየተደረገ ሙያቸው የሚያድግበት መንገዶች እየተፈጠሩና : ሙያቸውን የሚያግዙ ሳይንቲስቶችን በማስተማርና በማነሳሳት የሰው ኃይልን አዳብሮ : ርህራሄ የተሞላው : ባህልን የተከተለ ስሜታዊ እንክብካቤ በመስጠት የሰውን ስቃይ ለማቃለል; በሕክምና ሙያና በደጋፊ ባዮሜድካል ምርምሮችና ጥናቶች የተገኙትን ሳይንስን የተከተሉ ፈጠራዎችን በማሳደግ በመንግስት አመራር አማካይነት ብሔራዊ የጤና አጠባበቅ ስርዓትን ማራመድ ያስፈልጋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: እህቴን ሔፕታይተስ ከውጭ ጉዞዋ ያስቀራት ይሆን?

ከትምህርትና ከስልጠና በሗላ ይህ ሙያ የሚጠይቀውን መስፈርቶች ባለሙያተኛው ማሟላቱን የሚከታተል አካል በማንኛውም አገር የመንግስታዊ አስተዳደር ተደራጅቶ ይቀመጣል:: ሰዎች የሕክምና ትምህርታቸውን ሲያጠናቀቁ ትምህርት ቤቱ የሚሰጠውን ፈተና አልፈው ዲግሪያቸውን ከተቀበሉ በሗላ ወደ ሙያው ስራ ዘርፍ ከመግባታቸው በፊት ይህ አካል ለሙያው ብቁነታቸውን ለማረጋገጥ በታላላቅ ያደጉና የበለፀጉ አገሮች የሙያ ችሎታቸውን የሚያረጋግጥ የፅሁፍና የቃል ፈተና ይሰጣቸዋል:: ይህንን ፈተና ያላለፈ የሕክምና ትምህርት ምሩቅ እንኳን በሽተኛ በግል ሊያይና ሊያክም ቀርቶ ሐኪም ተብሎ አይጠራም:: በሰለጠኑት አገራት የሕክምና ትምህርት ምሩቅ መሆንና በሙያው ብቁነት እውቅና አግኝቶ መስራት የተለያዩ ናቸው:: ግን ይህ የሙያ ብቁነት መሳፍርት በኢትዮጵያ ውስጥ የለም:: ይህ አስፈላጊ መሳፍርት ባለመኖሩና ሐኪሞች ለስህተታቸው ሕጋዊ ተጠያቂነት ስለሌባቸው በሕክምና ብልሹነት (medical malpractice) የሚሞቱት ኢትዮጵያውያን ቁጥር ቤቱ ይቁጠረው::

የዚች ፅሁፍ አብዛኛ አንባቢዎች በዳያስፖራም ሆኑ በአገር ቤት ውስጥ የሐኪሞች ሰለባ የሆኑ ዘመዶች ጏደኞች ወይም የሚያውቋቸው ሰዎች አያጡም:: በማያስፈልግ ቀዶ ሕክምና ወይም ከቀዶ ሕክምና በሗላ አስፈላጊ ጥንቃቄና ክትትል ጉድለት : በተሳሳተ የበሽታ ምርመራ : ቀኑ ባለፈበት መድሃኒት ወይም የተሳሳተ መድሃኒት በመስጠት በሽተኛውን ክማዳን የገደሉ ሐኪሞች ስንት ናቸው? አግባብ ሕክምናና እንክብካቤ ተደርጎላቸው ከበሽታው ባለመዳን ሕይወታችው የሚያልፍ አሉ:: ይህን ማንም ሊቆጣጠር አይችልም:: ግን በሐኪሞች እንዝላልነት የሚሞተው ልብ ይሰብራል::

ስለኢትዮጽያ ሐኪሞች የሚደንቀው : የሚከፍቱት ኪሊኒኮች ስም ነው:: ይህች ፀሐፊ በዲያስፖራ ብዙ ቆይታ አድርጋ ለጉብኝት ኢትዮጵያ ሄዳ ያስተዋለችው አብዛኛው ቦታ የኪሊኒኮች ስም ከፍተኛ ኪሊኒክነው:: ወንድሜ ታሞ መርካቶ እስላም መስጊድ ፊትለፊት ከሱቆች መሃከል ተሸንቅሮ የነበረ አንድ ኪሊኒክ ለመጎብኘት እድል ገጠመኝ:: ስንገባ ወደ30 የሚሆኑ ከሕፃን ልጆች እስከ እርጉዝ ሴቶች በሽተኞች ነበሩ:: ተረኛው የነበረው ሐኪም (ከኪሊኒኩ ባለቤቶቹ አንዱ ነው ተብዬ ተነግሪአለሁ) ልዩ የሰለጠነበት ሙያው ራዲዮሎጂ ነው:: ይህንንም የታዘብኩት የተማርኩትና ኑሮዬን የመራሁበት የነርስ ሙያ ስለነበረ ከወንድሜ ጋር ሐኪሙጋ አስፈቅጄ በመግባቴ ነው:: ያኔ ነው ደረቱ ላይ የነበረውን የስም አርማ አይቼ የተረዳሁት:: በተጨማሪም በስሙ አርማ አማካኝንት ይህ ሐኪም በእዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ሕክምና ትምህርት ቤት የራድዮሎጂ ዲፓርትመንት ረዳት ፕሮፌሰር መሆኑን አስተዋልኩኝ:: ይህ እውነት ይሁን ሰዎችን መሳቢያ ሰውየውና ፈጣሪው እውነቱን የሚያውቁት:: በጣም ያሳዘነኝ ነገር ወንድሜ የሽንት የደምና የሰገራ ናሙና ስጥ ተብሎ መጀመሪያ ደም ለመስጠት ላብራትዎሪ ክፍል ውስጥ ስንገባ ቴክንሽያኑ ከማይክሮስኮፑና ከላብ ናሙናዎቹ ጎን በትንሽ ኤሌክትሪክ ምድጃ ሻይ እያፈላ ነበር:: የላቡ ንፅህና ያሳፍራል:: ናሙናዎቹ ለብክለት (CONTAMINATION) እጅግ የተጋለጡ ነበር:: እንኳ ሳያበቃ ሽንት ቤቱ ሞልቶ የአጎራባች ቤትን አጥለቅልቆ ባለቤቱ እየጮኸ መጥቶ : እስከ

ተጨማሪ ያንብቡ:  ደም ብዛት የያዘህ ጨው አብዝተህ በመመገብህ ነው ተባልኩ፤ እውነት ይሆን?

መቼ ድረስ ነው በዚህ ክሊኒክ መፀዳጀያ ግንፈላ ቤቴ የሚጥለቀለቀው በማለት ትልቅ ሁከታ ፈጠረ:: ይህ የሚያሳየው የመንግስት ቁጥጥር አለመኖሩን ነው:: እውነት መንግስት በዚህ የስራ ንግድ ላይ ሕጋዊ ፈቃድ የሚሰጥ ቢሆን ይህ ቤት ክሊኒክ መሆን ቀርቶ ለጥጃ ማሰሪያም ሊሆን እይገባውም:: ምንም እንኳ ራዲዮሎጅስት መሰረታዊ የሕክምና ትምህርት ቢኖረውም በሌላ አገር እንደ አጠቃላይ የሕክምና ባለሙያ (GENERAL PRACTITIONER) ሊሰራ አይፈቀድለትም:: እንግዳ መቀበያው ተጨማሪ አገልግሎቱ የመድሃኒት መሸጫነቱ ነው:: ያስተዋልኩት ለሁሉም ያዝ የነበረው መድኃኒት አንድ አይነት አንታይባዮቲክ ነበር:: ሕፃን ይሁን እርጉዝ : ልቤን ይበል : ኩላሊት : ደምግፊት ይሁን ስኳር በሽታ በዚያን እለት እስክንወጣ ድረስ ይታዘዝ የነበረው መድሃኒት አንድ አይነት ነበር:: ይህ እንግዳህ አዲስ አበባ ውስጥ ነው:: እስቲ እስቡት በየገጠሩ ያለው ሕዝብ በሐኪሞች የሚደርስበት የሕክምና ብልሽት::

ሰዎች በተማሩበት ሙያ ገቢ አያግኙበት የሚልም አመለካከት በማንኛችንም ጤናማ አእምሮ ውስጥ ሊታሰብ አይገባም:: ግን የእገርን ማሳ በአገር በሬእነደሚለው የግል ሐኪሞች ለሚሰጡት የሕክምና አገልግሎት የሚደረገው ክፍያ ከሕዝቡ ገቢ ጋር መመጣጠን ተገቢ ነው:: በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ለኢትዮጵያ ሕክምና አገልግሎት የአሜሪካንን ክፍያ መጠን መጠየቅ የጠያቂውን ሕሊና ያስገምታል:: ከላይ እንደጠቀስኩት የአንድ አገርን ህልውና ከሚያስጠብቁትና አገርን ከሚያስቀጥሉ ዋንኛዎች ስራዎች አንዱ የሕክምና አገልግሎት ነው:: ይህ አገልግሎት የሕዝብን ጤንነት በማስጠበቅ አገርን ያስቀጥላል:: ለዚህም ነው ሐኪሞች ዝና ባይከተላቸውም : ዝነኞች ባይሆኑም ከሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎች በበለጠ የሚሞገሱትና የሚዘከሩት:: ይህንን ክብር ማጣትና ማሳጣት የሚችሉት ሐኪሞች በትምህርታቸው መጨረሻ የሰጡትን የሂፖክራሲያዊ መሐላ ስተው ሰውን በማከም ከበሽታው ከማዳን ይልቅ ትኩረታቸውን በክፍያ መልክ በሚመጣው ገንዘብ ሀብታም ለመሆን ብቻ ጥረት ካደረጉ ነው:: ሰባዊነት የሕክምና አገልግሎት ምልክት መሆኑን በዚህ ሙያ ላይ የተካተተ ማንኛውም ሰው ግንዛቤ ማድረግ ይኖርበታል::

የኢትዮጵያ የሕክምና አገልግሎት ብዙ ጉድለቶችና እጥረቶች አሉት:: ግን እነዚህ ጉድለቶችና እጥረቶች የሕክምና ብልሽትና (MEDICAL MALPRACTICE) የስግብግብነት ምክንያቶች ሊሆኑ አይገባም:: በተለይ በቅርቡ ሃሌሉያ የተባለ ሆስፓታል የኮቪድን ወረርሽኝ ሕክምና በተመለከተ ይጠይቅ ስለነበረው ዋጋ ስሰማ ስንቱ ኢትዮጵያዊ ነው ለሁለት ወር ሕክምና 1 ሚሊዮን ብር መክፈል የሚችለው? የገረመኝ በሆስፒታሉ ላይ የቀረበውን ወቀሳና ሂስ ለማስተባበል የቀረቡት የሆስፒታሉ ባለቤቶችና የአስተዳደር ክፍል ኃላፊዎች ክፍያው ተገቢ ለማስመሰል የሰጡት ገለፃ ተቀባይ ለመሆን አላሳመነም:: በተለይ የሆስፒታሉ ሴት ባለቤት በሃዘኔታ ከንፈራችንን እንድንመጥላቸው ሂሳቡ 600 ሺህ ብር ሲደርስ ከዚያ በሗላ አናስብም ማለታቸው የጥርጣሬ ሳቅ መሳቅ ችያለሁ:: ስንቱ ኢትዮጵያዊ ነው እንኳን 600 ሺህ ብር በአንዴ ሊያወጣ ይቅርና በሕይወቱ ሙሉ ይህንን ያህል መጠን ሀብት መሰብሰብ የሚችለው? በእርግጥ ሆስፒታሎችና ሌሎችም የሕክምና ተቋሞች ወጭ አለባቸው:: ለዚህም ገቢ ያስፈልጋል:: ግን 1 ሚሊዮን ብር ክፍያ ለአንድ በሽተኛ የሁለት ወራት ሕክምና ከአገሪቱ የኢኮኖሚ ደረጃ ጋር አይመጣጠንም:: ወደፊት አገራችን በልማት ስታድግና ሕዝቦቿ ሲበለፅጉ ይህንን መሳይ ክፍያ መጠየቅ ይቻላል:: እስከዚያ ድረስ ሐኪሞቻችን ሙያቸው የስግብግብነት ተምሳሌት እንዳይሆንና እነሱም የሰጡትን የሂፖክራሲያዊ መሐላ እንዳያጏድሉ ትልቅ ጥንቃቄ ማድረግ ይገደዳሉ::

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: የሚያሳፍሩ 6 ታላላቅ የጤና ችግሮች እና ቀላል መፍትሄዎቻቸው

በዚህ አጋጣሚ በውጭ በዲያስፖራው የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ሐኪሞች ቀኝ እጃቸውን አንስተው የማሉበትን የሂፖክራሲያዊ መሐላ በማሟላት የበጎፈቃደኝነት ሕክምና አገልግሎት በኢትዮጵያ ውስጥ በመስጠት የሕክምናን ችግር በትንሹም ቢሆን ሊቀርፉት ይችላሉ:: “ከልብ ካለቀሱ እንባ አይገድምእንደሚለው በእርግጥ እናገልግል ካሉ እነዚህ በዲያስፖራ የሚገኙ ሐኪሞች ከትርፍ ጊዜያቸው ቆጠብ አድርገው ሕዝባችንን በጥቂቱ ማገልገል የሰባዊነት ምልክት ይሆናል:: የተቀረነው ኢትዮጵያዊያን ገንዘብና ቁሳቁስ በማሰባሰብ ልንተባበርቸው እንችላለን የሚል እምነት አለኝ::

አገር ቤት ውስጥ ለሚገኙት ሐኪሞች ይህ ክሴ ሁሉንም አይመለከትም:: ብዙሐን ሐኪሞች ስነ ምግባርና ንፁህ ሕሊና ያላቸው እንደሆኑ ፍፁም አልጠራጠርም:: ግን ከደረቅ እንጨት የተጠጋ እርጥብ ዛፍ አብሮ ይቃጠልእንደሚባለው በጥቂት ስግብግብ ሐኪሞች ጥፋት መላው የሕክምና ቤተሰብ ስም በመጥፎ መነሳቱ አይቀርም:: መፍትሔው የሙያውን መልካም ስም በመልካም ድርጊት ማስጠበቅ የሙያው ዘርፍ አባላት ግዴታ መሆን አለበት:: ንፅህና የጎደለው ክሊኒክ ውስጥ በሽተኛ ማስተናገድ : የተሳሳተ ምርመራ ማድረግ : ለብክለት (CONTAMINATION) የተጋለጠ ላብራቶሪ ውስጥ የደም : የሽንትና የሰገራ ናሙናዎች ምርምር ማካሄድ : የተሳሳተ ወይም ቀኑ ያለፈበት (EXPIRED) መድኃኒት መስጠት : የተሳሳተ ቀዶ ጥገና ማድረግ : ተገቢ ክትትል አለማድረግና በሽተኛን ማንቋሸሽ የአብዛኛዎች ክሊኒኮች መገለጫዎች መሆናቸውን በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ሐኪሞች መገንዘብ ይገባቸዋል:: የመድኃኒት እጥረቶች : የምርመራ መሳሪያዎች እንደልብ አለመገኘትና : ሕጋዊ ቁጥጥር አለመኖር ለሕክምና ብልሽት (MEDICAL MALPRACTICE) ምክንያቶች ሊሆኑ አይገባም:: መሆንም አይችሉም:: ማንኛውም ሐኪምና ረዳቶቹ እያንዳንዱን በሽተኛ የገንዘብ ምንጭ ብቻ ሳይሆን : እኔ ብሆን : እናቴ ብትሆን : አባቴ ቢሆን : ባለቤቴ ብትሆን ቢሆን : ልጄ ብትሆን ቢሆን ወዘተ በማለት ልናይ ይገባናል:: ሰውን በሰባዊነት አይቶ የሚያክም ሐኪም በእርግጥም የገባበትን የሂፖክራሲያዊ መሐላ አሟልቷል ሊባል ይቻላል::

ሰውን ለማዳን የማለው ሐኪም : ሰውን አዳነው ለማለት ያብቃን::

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share