ልዕለ-ኃያልነት (ያስረካቢ፣ ተረካቢና ያረካካቢዎች ትራጄዲ!!) –   ቴዎድሮስ ጌታቸው-ድሬዳዋ   

ከ2021-2024!!
ቴዎድሮስ ጌታቸው

ባለፈው ሳምንት-ማክሰኞ ‹‹ቀዝቃዛው ርክክብ ወይስ ቀዝቃዛው ጦርነት?›› በሚል፤ ለልዕለ-ኃያልነት ርክክቡ ግብአት የሚሆኑ አንኳር መረጃዎችን ተለዋውጠን ነበር፤ ከነዚህም ውሰጥ ‹‹ዴሞክራቶቹ አይመቿትም›› በሚለው ንዑስ ርዕስ፤ የአሜሪካኖቹ ዴሞክራቶች ከእሥራኤል (ከናታንያሁ) ጋር እስከመካረር የደረሱበትን ጉዳዮች ጠቅሰን፤ ቤንጃሚን ናታንያሁ ከሩሲያ ጋር ግልፅ ግንኙነት ነገር ግን ስውር ስምምነት አድርጎ፤ ለአሜሪካን የአፀፋ መልስ መስጠቱን፤ እንዲሁም ‹‹ሁለተኛው ቀዝቃዛ ጦርነት›› ንዑስ ርዕስ ስር ደሞ፤ ቀዝቃዛውን ጦርነት አሜሪካና ሩሲያ በ2015 በሶሪያ ምድር ማስጀመራቸውንና መዘናጋት እንደማይገባን ተጨዋውተናል፤ ዛሬ በልዕለ-ኃያልነት ውስጥ ‹‹የማይዘነጉ እውነቶችን›› ጠቅሰን፤ ‹‹የተረካቢውን ማንነትና ዝግጁነት›› ገልፀን በቀጥታ ወደርክክቡ እንሄዳለን፡፡ እነሆ፤

የማይዘነጉ እውነቶች!

‹‹ተረካቢ ካለ የግድ አስረካቢ መኖር አለበት›› የሚለውን ሚዛናዊ እውነታ ጠቅሶ ለማለፍ ታስቦ እንጂ! የልዕለ-ኃያልነት አስረካቢዋ ሀገር አሜሪካን መሆኗ አይጠፋችሁም፤ ስለዚህ ዛሬ በዚህ ጉዳይ ጊዜ አናጠፋም፤ ከዚህ ይልቅ ልዕለ-ኃያልነትን ለማረካከብ ሚና ካላቸው አገራት ውስጥ አንዷ ናት ተብላ የምትታሰበው እሥራኤል፤ የማረካከብ አቅሟን እንዳንጠራጠር የሚያደርግና ግንዛቤ ሊያስጨብጠን የሚያስችል ‹‹የማይዘነጉ እውነቶችን›› ባጭሩ ላስቃኛችሁ!! የቀድሞው የአሜሪካን ፕሬዚደንት ባራክ! የ2015ቱን ከኢራን ጋር የተደረሰውን ‹‹ኑክሌር ተኮር ስምምነት››፤ ‹‹የማስፈፀምና ትእዛዝ የመስጠት ፅኑ ሥልጣን Veto-Power አለኝ›› እያለ በአሜሪካን ኮንግረስ ሲደነፋ! ቤንጃሚን ናታንያሁ ደግሞ ‹‹እንኳን በዚህ ስምምነት ላይ ልታዝ ይቅርና በአሜሪካንም አታዝም›› የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ፤ የባራክን እውቅና ሳይጠይቅ አሜሪካን ከተፍ አለ! ይህ የቤንጃሚን ናታንያሁ ተግባር! እንድን እጅግ የማይደፈር እልፍኝ ያለማንም ከልካይ በርግዶ እንደመግባት ነበር! በMarch 2, 2015 አይሁዶችንና የእሥራኤል ወዳጆችን በአሜሪካን ዋሽንግተን-ዲሲ ሰብስቦ ማነጋገር! ለናታንያሁ እንደቀላል የሚቆጠር ተግባር መሆኑን አሳይቶናል፤ ናታንያሁ! ባራክ ኦባማን ‹‹እስኪ በደንብ ይግረምህ!›› ብሎት፤ በዓለም ጉዳይ ላይ የሚወስኑ የአሜሪካን ኮንግረስ አባላትን! በነታው March 3, 2015 በአዳራሻቸው ሰብስቦ ቁጭ ብድግ ሲያደርጋቸው ስናይ! ‹‹አሜሪካን የባራክ ናት ወይስ የቤንጃሚን ናታንያሁ?›› ብለን እንድንጠይቅ ተገደናል!!

ቤንጃሚን ናታንያሁ ወደታላቋ ብሪታንያ ጎራ ብሎ የፈፀመውን በምልሰት ስንመለከት፤ የእሥራኤልን ‹‹ሥውር ገናናነት›› ለዓለም ያወጀበት ነበር፤ እስኪ በጥቂቱ ላስታውሳችሁ! እንግሊዝ ከተቀሩት ኃያላን ሀገራት ጎን ሆና July 14, 2015 ከኢራን ጋር በጋራ የደረሰችብትን ስምምነት ተግባራዊ ለማድረግ ሽር ጉድ በምትልበት ጊዜ፤ ናታንያሁ በSeptember, 2015 ከተፍ ብሎ ‹‹እስኪ ተረጋጊ ምንድነው እንዲ ጥድፍ-ጥድፍ ማለት!›› ይላታል፤ ‹‹ወር! ምንድነው የምረጋጋው ስምምነት-ስምምነት ነው በቃ!››፤ ናታንያሁ ለስለስ አርጎ ‹‹እንደዚኮ አይደለም እንግልጣን! እሥራኤል አንቺ የማታውቂውን ቴክኒዮሎጂ ትሰጥሻለች››፤ እንግሊዝ ‹‹እስኪ I swear  በለኝ!›› ናታንያሁ ‹‹I swear! እንግልጣን ሙች! በምትኩ ግን ኢሄ የኢራን ስምምነት ይፈፀም የምትይውን ተይ! ሃዬ?›› እንግሊዝ ‹‹ሃዬ!››፤ ቤንጃሚን ናታንያሁ ከታላቋ ብሪታንያ ጋር የነበረውን ጉዳይ በዚህ መልኩ በቀላሉ ነው የጨረሰው!! እነዚህን እውነቶች ስንመለከት ‹‹እሥራኤል በዓለም-አቀፍ እንቅስቃሴ ውስጥ ሚና የላትም›› ብሎ ማሰብ ስህተት ይሆናል፤ በመሆኑም ‹‹የዓለም ልዕለ-ኃያልነት ርክክብ›› ላይ በሚኖር አስተዋፅኦ ውስጥ! እሥራኤልን ልንዘነጋት አይቻለንም፡፡ እንቀጥል!

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያ - ትናንት እና ዛሬ !

የልዕለ-ኃያልነት ተረካቢው ማንነው?

ቻይና?

እስኪ ‹‹የሕዝባዊት ቻይና ሪፐብሊክ›› ልዕለ-ኃያልነትን ለመረከብ ያላትን አቅም እንፈትሽ! ፍተሻውን አከናውነን ተገቢ ግምት ላይ የምንደርሰው! ቻይና ያላትን የኢኮኖሚ አቅም ለሕዝብ ቁጥሯ እያካፈልን በምናገኘው ውጤት! ወይም ያላትን የሚሊታሪ ብዛት፣ የታጠቀችውን ጦር-መሣሪያ አሊያም ለሚሊታሪዋ የምትበጅተውን በጀት ገምግመን በምንደርስበት ውጤት አይደለም! ኸረ ምንበወጣችሁ!! ፍተሻውን የምናደርገው የአሜሪካን ፕሬዚደንት ባራክን እና የቻይናውን ፕሬዚደንት ዢን አንድ መድረክ ላይ በማገናኘት ነው፤ እስኪ እናገናኛቸው! September 22, 2015 ዢ ጂን ፒንግ አሜሪካንን እንዲጎበኝ ከባራክ በቀረበለት ግብዣ መሠረት፤ ባራክ በሲያትል አስጀምሮት አሜሪካንን እያዞረ አስጎበኘው! ዢ ከጎበኛቸው በርካታ ቦታዎች ውስጥ የጦር-መሣሪያ ቴክኒዮሎጂ ማዕከሎችን ይጨምራል፤ September 25 ላይ ጥቂት ዕረፍት ከወሳሰዱ በዃላ ባራክና ዢ በቴሌቪዥን መስኮት ቀጥታ ሥርጭት ብቅ አሉ! Press-Conference መሆኑ ነው፤ የአሜሪካን ፕሬዚደንት ባራክ ካደረጋቸው ረጅም ንግግሮቹ ውስጥ፤ ከዢ ጋር ያደረገውን ስምምነት እንዲህ ሲል ይገልፃል! ‹‹አሜሪካን በቻይና ውስጥ የሚገኘውን አስከፊ ድህነት ለመቅረፍ ትሠራለች››፤ ባራክ የቻይናው መሪ ዢ ባለበት ለጋዜጠኞች በሚሰጥ የመሪዎች መግለጫ ላይ፤ ይህን የመሰለውን የአሜሪካን-ቻይና ስምምነት ለዓለም ሀገራትና ሕዝብ ሲናገር! ‹ዢ› በዓለም ሕዝብ ፊት ‹‹ዓይኑን እያቁለጨለጨ›› እውነታውን ከመቀበል ውጪ አማራጭ አልነበረውም!! ቻይናን በፖለቲካ መነፅር ለማየት ስንሞክር ደሞ! አሁንም በአፈና ላይ የተመሠረተ ‹‹የአንድ ፓርቲ አምባገነናዊ ሥርዓት›› ውስጥ የምትገኝ፤ ከታይዋን ጋር ያላት ‹‹የአንድ ቻይና መርህ›› እልባት ያላገኘ፤ ነገ ፍፃሜ ማግኘቱ ‹‹አይቀሬ›› በሆነው በሆንግኮንግ /Ambrella Movement/ እና ከሌሎች ግዛቶቿ በሚነሳው የዴሞክራሲ ጥያቄ! ውስጥ-ውስጡን እየተናጠች የምትገኝ፤ ‹‹ግዙፍ የሚመስል ኢኮኖሚ›› ያላት አገር ነች!! ስለዚህ ልዕለ-ኃያልነትን ለመረከብ ቅርብ የሆነ ሀገር ብንፈልግ ይሻላል!!

ሩሲያ?

‹‹የሩሲያ ፌዴሬሽን ልዕለ-ኃያልነትን ለመረከብ ያላት ዝግጁነት ምን ይመስላል?›› የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ፤ ወደአውሮፓ ሕብረት ጎራ እንድትሉ ጋብዣችሁ በቀላሉ አስቃኛችዃለሁ! ሩሲያ በ2014 የዩክሬይን ግዛት የነበረችውን ‹‹ክሬሚያ›› ወደግዛቷ መጨመሯን ተከትሎ፤ በምሥራቁም በምዕራቡም ዛቻና ማስጠንቀቂያዎች የታከሉበት ውዥንብሮች ተፈጥረው ነበር፤ የአውሮፓ ሕብረት ‹‹ክሬሚያን በተግባር የማስመለሱን ሥራ›› ለአሜሪካን፣ ለታላቋ ብሪታኒያና ለNATO በመስጠት፤ በሩሲያ ላይ የንግድና ሌሎች ማዕቀቦችን መጣል መርጧል! በዚህ ጊዜ የሩሲያ የአፀፋ-ምላሽ ፈጥኖ ታይቷል፤ ወደአውሮፓ የሚሄደውን የጋዝ ማስተላለፊያ ቱቦዎችን በመዝጋት! ሩሲያ በጊዜው የወሰደችው እርምጃ ቆንጠጥ ካደረጋቸው አገራት ውስጥ፤ ‹‹ግዛቴ ተወሰደብኝ›› ብላ ምሬት ላይ የነበረችውን ዩክሬይንን ይጨምር ነበር! አውሮፓውያኑን ይህ የሩሲያ ቁንጥጫ ህመሙ ዘልቆ እንዲሰማቸው ካደረጋቸው ምክንያት አንዱ፤ ሰኔና ሰኞ የገጠመበት በመሆኑ ነው፤ ምን ልላችሁ ፈልጌ ነው! በጊዜው በአውሮፓ የክረምት ወራት በመሆኑ፤ ያለሩሲያ ጋዝ ብርዱን ማስታገስም ሆነ ምግብ አብስሎ የሆድ ጥያቄ መመለስም የማይቻል ነበር፤ ስለዚህ የአውሮፓ ሕብረት ሩሲያ ላይ ማዕቀብ በጣለበት እግሩ ተመልሶ አንድ ነገር ማድረግ ነበረበት! ያም ማዕቀቡን ባስቸኳይ አንስቶ በሩሲያ ጋዝ ሰውነታቸውን እያሟሟቁና በረዶ የሠራውን ምግባቸውን እያሞቁ ቀጣዩን ማሰላሰል!!

ሌላው ‹‹የBre-Exit ጣጣ›› ነው! የቀድሞው የአሜሪካን ፕሬዚደንት ባራክ፤ የታላቋ ብሪታንያ ከአውሮፓ ሕብረት የመውጣት እንቅስቃሴ እንዲቆም፤ የቻለውን ያህል ጥሯል-ግሯል ግን ምን ዋጋ አለው! የሆነው ነገር ሆኗል! የባራክ ጓደኛ የሆነው የብሪታኒያው ጠቅላይ ሚኒስት ካሜሮንም! በዚህ ምክንያት ከመሪነት ራሱን አግልሏል፡፡ ፕሬዚደንት ባራክን የተካው ፕሬዚደንት ትረምፕ በበኩሉ! የብሪታኒያ ከአውሮፓ ሕብረት መውጣትን አጥብቆ የሚደግፍ ሆኖ ታይቷል፤ ትረምፕ በአሜሪካን ፕሬዚደንት ሆኖ መከሰት የእሥራኤልና የሩሲያ እጅ እንዳለበት ባለፈው ተጨዋውተናል፤ ይህ የትረምፕ አቋም የሩሲያና እሥራኤል እጅ ብሪታንያ ድረስ እንደዘለቀ ማሳያ ነው!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከምርጫው በፊት ልናደርገው የሚገባ ሌላ ምርጫ (ገዛኸኝ አበበ ከኖርዌይ ሌና)

በቅርቡ ማለትም ከ2014 ጀምሮ ሲፈራ-ሲቸር መጥቶ እየተሻሻለና እስከ-ፊታችን July 31, 2021 እየተራዘመ የመጣው፤ የአውሮፓ ሕብረት በሩሲያ የጣለው ማዕቀብ እና እግድ፤ በሩሲያ ጉዳት አላስከተለም ወይም ሕመም የለውም ማለት አይቻልም! ነገር ግን ሩሲያም በምላሹ የሕብረቱ አባል ሀገራት ላይ በተናጥል፤ እንዲሁም የሕብረቱን ኮሚሽነር፣ ምክትል ፕሬዚደነቱንና ሌሎች ባለሥልጣኖችን እየለየች! የምትጥለው ማዕቀብ እና እግድ! ቆንጠጥ ሲያደርጋቸውና አንዳንዴም ሲያነጫንጫቸው እየታዘብን እንገኛለን!! /ምንጭ፡- politico.eu June 14, 2021/

ሩሲያ የዓለም ልዕለ-ኃያልነትን ለመረከብ ያላትን አቋም ስንፈትሽ፤ አቋማ ያልተሟላ መሆኑን የሚያሳየን፤ በተደጋጋሚ የተጣለባት የአሜሪካን ማዕቀብ ነው! በቅርቡ ማለት ‹‹በሳይበር ጥቃት አመካኝታ›› አሜሪካን የጣለችባት ማዕቀብ ደግሞ፤ ሩሲያን ‹‹ቻይኒቲ ድረሽ!›› የሚለውን የድንጋጤ ድምፅ እንድታሰማ የተገደደችበትና የአፀፋ ምላሽ ለመስጠት የቻይናን አጋርነት በእጅጉ እንድትፈልገው ያስገደዳት ነበር! ቻይናም አላሳፈረቻትም!! ከላይ የቻይናን አቅም ስንፈትሽ ልዕለ-ኃያልነትን ለመረከብ ካላት አቅም አንፃር ብቻ የተፈተሸ እንጂ፤ በዓለም ያላትን ከፍተኛ ሚና መካዳችን አይደለም፡፡

የNATO ጣጣ ለሩሲያ በለስ!

ሩሲያ ልዕለ-ኃያልነትን ለመረከብ ቅርብ መሆኗን የሚገልፅልን መረጃ በቅርቡ ተገኝቷል፤ ይህን መረጃ የምናገኘው ‹‹በNATO ጣጣ ውስጥ ነው››፤ ምን ማለቴ ነው! ሰሞኑን የNATO አባል አገራት የአሜሪካው ፕሬዚደንት ጆ. ባይደን በተገኘበት ውይይት አድርገው ነበር፤ ውይይቱ /ግምገማው/ በዋናነት ያተኮረው ‹‹አሜሪካን NATOን አስከትላ ከቻይና ጋር ጦርነት ብትገጥም ወይም ስትገጥም፤ ውጤቱ ምን ይሆናል?›› የሚል ነው!! ልብ በሉ ይህ ግምገማ የተካሄደው ቻይና ልታዳምጥ በምትችልበት ሁኔታ ነው፤ የዚህ ግምገማ ሀሳብ አመንጪ ደግሞ ባይደን ነበር! በዚህ ተግባሩ ‹‹ባይደን አሜሪካንን ወዴት እየወሰዳት ነው?›› ብለን እንድንጠይቅ አስገድዶናል፤ ደግነቱ ይህን የባይደን አጥፊ ሀሳብ የሚያለዝብ ሦስት ጠንካራ ተቃውሞ ከNATO አባል ሀገራት መሰማቱ ነው! አንደኛው ተቃውሞ የተነሳው ኖርዌያዊ በሆነው የNATO ፀሐፊ Jens Stoltenberg የተነሳው ነው፤ የስቶልቴንበርግ ሀሳብ ‹‹ወደጦርነት ከመገባቱ በፊት ቻይናን አስቀርቦ በኑክሌር ጉዳይ ላይ ማነጋገር የተሻለ ነው›› የሚል ነው፤ ሁለተኛው ተቃውሞ የቀረበው በፈረንሳዩ ፕሬዚደንት Emmanuel Macron ነው! ማክሮን ‹‹ጠላት ማን ነው?›› /Who is The Enemy?/ በማለት ጆ. ባይደንን በማፋጠጥ ጀምሮ፤ ‹‹NATO በአባል አገራቱ በሚቃጣ ጥቃት ላይ ነው ማተኮር ያለበት!›› ሲል ባይደንን ኩም ያደረገ መደምደሚያ ሰጥቷል! ሶስተኛው ባይደን ላይ የተነሳው ተቃውሞ በምሥራቅ አውሮፓ ተወካዮች የቀረበ ሲሆን፤ ሁሉንም ውል! አድርጎ ያሳየ ነው!! ‹‹አሜሪካን NATOን ይዛ ቻይና ላይ ጦርነት የምትሰብቅ ከሆነ! ምሥራቅ አውሮፓ ክፍት ይሆናል፡፡›› የሚል ተቃውሞ ነበር፤ ይህ ተቃውሞ! ‹‹ባይደን አደብ ግዛ›› የሚል ማስጠንቀቂያ ያዘለ ይመስላል!! ምሥራቅ አውሮፓ ሀገራቱ ‹‹አለበለዛ!›› ብለው ከቀጠሉ! ‹‹NATOንና አሜሪካንን ከመተማመን ከሩሲያ ጋር መስማማት እንመርጣለን፤ ድሮምኮ ከሩሲያ ጋር የምታጣሉን እናንተው አሜሪካኖች ናችሁ!!›› ወደሚለው ሀሳብ ሊመራቸው ይችላል፡፡ ሩሲያ ልዕለ-ኃያልነትን ለመረከብ እድል አላት የምንለው በነዚህ ተጨባጭ እውነታዎች ተመርኩዘን ነው፡፡ /ምንጭ፡- politico.eu June 14, 2021/ እንቀጥል!

ተጨማሪ ያንብቡ:  የደቡብ አፍሪካው ድርድር የጨረባ ተዝካር - ድራንዝ ጳውሎስ (ከባህር ዳር)

የልዕለ-ኃያልነት አረካካቢዎች እነማን ናቸው?

ይህን ንዑስ ርዕስ ‹‹እንደቀጭን መጠቅለያ›› ተጠቅመን፤ ላለፉት ሶስት ተከታታይ ሳምንታት ለቀረቡት ፅሁፎች መቋጫ እናደርገዋለን፤ አረካካቢዎች ተብለው በዋናነት የሚጠቀሱት ‹‹በልዕለ-ኃያሏ አሜሪካን ተጠቅተናል፣ ግፍ ተፈፅሞብናል፣ ተዋርደናል፣ ተዋክበናል›› የሚሉ ሀገራት! ማለትም እንደኪዩባ፣ ሠሜን ኮሪያ፣ ኢራን፣ ሶሪያ፣ ቪዬትናምን የመሳሰሉት ሀገራት፤ ለማረካከቡ የሚቀድማቸው የለም ተብሎ ይታሰባል፤ ሌሎቹ ‹‹አሜሪካን ልዕለ-ኃያልነቷን ተማምና መረን ለቃለች›› የሚሉ ሀገራት፤ እንደፊሊፒንስ፣ ፓኪስታን፣ ኢራቅ፣ ሜክሲኮን የመሳሰሉ አገራት ሲከተሉ፤ ሌሎች ደግሞ ‹‹አሜሪካን እንግዲ ሥራሽ ያውጣሽ›› የሚሏት እንደሕንድ፣ ብራዚልና ደቡብ አፍሪካ የመሳሰሉ ሀገራት እንደሚሆኑ ይታሰባል፤ የመጨረሻዎቹ ሀገራት ጉዳይ ግን ትንሽ! ከበድ ሳይል አይቀርም! ምክንያቱም እነኚህ ሀገራት ‹‹እንዲህ ያለው የአሜሪካን ልዕለ-ኃያልነት መቆም ነው ያለበት! ይበቃል!!›› የሚሉ ናቸው፤ ቻይና፣ እሥራኤል፣ ቱርክና ተመሳሳይ ሀሳብ ያላቸው ሀገራት እንደሚሆኑ ይገመታል!! እነጃፓን፣ አርጀንቲና ብራዚልስ? ካላችሁኝ!  የዓለም ልዕለ-ኃያልነትን ፍፃሜ ካዩ በዃላ ‹‹እናዝናለን አሜሪካን!!›› የሚሉ ይመስለኛል፡፡ ጤና ይስጥልኝ፡፡

ልዩ ማስታወሻ!!

የተከበራችሁ አንባቢያን፣ የተከበራችሁ የZehabesha ድረ-ገፅ ቤተሰቦችና ጎብኚዎች እንዲሁም ተቋማት፤ በሀገራችን ላይ ያንዣበበውን ዓለም-አቀፍና የሀገር-ውስጥ ጫናን፤ ሁሉም በየፊናው ለመፍታት ይታትራል፤ የዓለም-አቀፉን ጫና ለመቋቋም ሁላችንም በየፊናችን የሄድንበትን በምሳሌነት ብንወስድ፤ ፀሐፊ ብርሃኑ ማዲንጎ ‹‹ቁጣችንን ለዘብ አድርገን ከአሜሪካ ጋር የገባንበትን ነገር እናስተካክለው›› የሚል ቅን መልዕክት አስተላልፏል በMay 31, 2021 Zehabesha Tube-official ላይ ያስተላለፈው መልዕክት ጠቃሚ ስለሚሆን ተመልከቱት፤ በሌላ በኩል አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ‹‹በሀገር ሉዓላዊነት ላይ አንደራደርም፤ አሜሪካን ይህን አደረገች ብለን ደግሞ ሌላ አጋር ለመፈለግ አንቻኮልም›› የሚለውን ጠቃሚና ዲፕሎማሲያዊ የመንግስት አቋም ያንፀባርቃሉ፤ እንደኔ አይነቱ የፖለቲካ ተመልካች ደግሞ! ከዚህ ጋር በአራት ተከታታይ ፅሑፎች እንደተመለከታችሁት፤ ወደፅንፈኛ ፀሐፊነት ወስዶኝ የአሜሪካን ውድቀት የሚገኝበትን መረጃ እንሆ በረከት እላለሁ፡፡ መታወቅ ያለበት ግን የአንዲት እናት ሀገር! እና የአንድ ዓላማ እኩል ባልደረቦች! ፍላጎታችንም ተመሳሳይ መሆኑን ነው፤ ደጀኔ አሰፋ ከአፍሪካ ቀንድ እስከ አውሮፓ! ከመካከለኛ ምሥራቅ እስከ ሰሜን አሜሪካና ሩቅ-ምሥራቅ በመረጃ እየተንከራተተ፤ ጠቃሚ መልዕክት የሚያጎርሰን! ኡስታዝ ጀማልና መሀመድ አል-አሩሲን የመሰሉ የኢትዮጵያ ጀግኖቻችን፤ አረቦቹ ለቀጣይ ድርጊት የሚያነሳሱበትን የቃላት ኑክሌራቸውን ድባቅ እየመቱ! የሚያከሽፉትና መልሰው የሚያጠቁት፤ መነሻችንም መድረሻችንም ላደረግነው ለእናት ሀገራችን ህልውና መጠበቅ ነው፡፡ ሀገር ለመታደግ በየፊናው ለታተራችሁ ሁሉ! እናት ሀገር ኢትዮጵያ ውለታችሁን ትክፈላችሁ፡፡

ሠላም ለኢትዮጵያ ሠላም ለአፍሪካ

ቴዎድሮስ ጌታቸው

/የፖለቲካ ተመልካች/

ድሬዳዋ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share