በማንኛውም መንገድ ባህላዊ ታሪካችንን ማውደም  የዘረኞች ጎል ነው –  መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

የዛሬይቱ ኢትዮጵያ እኮ በውሥጥና በውጭ ይኼ ሁሉ ግፍ እየተፈፀመባት አልሞት ብላ የምትታገለው በባህላዊ ታሪኳ ጥንካሬ ምክንያት ጭምር ነው ።ጠላቶቿም እኮ በዚሁ በባህላዊ ታሪኳ ጥንካሬ ምክንያት ነው ከውሥጥና ከውጪ ባህሏን ለማጥፋት ጥርሳቸውን ነክሰው የተነሱባት ዛሬ ሀቀኛ ምሁር ሆኖ በኢትዮጵያ ባህላዊ ታሪክ የማይቀና ወይም የማይኮራ እንደሌለ ሁሉ ውሸታም ምሁር ሆኖ የሚያፍርበት ወይም እንዲያፍሩበት የማይጥር የለም። ለዓለም ሥልጣኔ ፈጣሪ እናት ለሆነችው አፍሪካ እኮ የኢትዮጵያ ባህላዊ ታሪክ  ነው መነሻ እምብርቷ። የጥንታዊት ኢትዮጵያን ባህላዊ ታሪክ  መካድና ማፍረሥ ማለት እኮ የመላውን ጥቁር ዓለም ዘር የታሪክ ክብርና መንፈሳዊ ኩራት እንደገና ማጨለም ማለት ነው። አፍሪካንም ለዳግመኛ ቅኝ ግዛት ማመቻቸት ማለት ነው

 ( ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድህን  ጦቢያ ቅፅ 5 ቁጥር 11 ፣ 1990 ዓ/ም )

የኢትዮጵያዊያንን በዘመን ሂደት የተጋመዱ  ና ተመሣሣይ የሆኑ  ባህሎች  እና ባህሎቻችን ያሥገኘልንን ቱሩፋት እና የዜጎቿን ትሥሥር ለማወቅ ከፈለግህ በኢትዮጵያ ክፍለ ግዛቶች በመሄድ  በሠረጉ፣በክርሥትናው፣በአረፋ ፣ በመውሊዱ ና በጠቅላላ የኃይማኖታዊ ባህላዊ  የበዓል አከባበር   ሥርዓት ላይ ተገኝ ና ሥነሥርዓቱን በአንክሮ ተመልከት ። ቋንቋው ቢለያይም ብዙሃኑ ዜጌ ባህሉ የተጋመደ ከመሆኑም በላይ የጋራ ኢትዮጵያዊ ባህል  እንዳለው ትገነዘባለህ።

ኢትዮጵያዊ ባህል ፣ ፍቅርን ህብረትን ፣ ወንድማማችነትን ፣ መተሳሰብን ፣ ተካፍሎ መብላትን ወዘተ ፤   ብቻ ሣይሆን  በአኗኗር ዘይቤው  ፣ በኪነት እና በኪነታዊ መሣሪያዎቹ   ፣ በምህንድሥነው ፣ በእደ ጥበብ ወዘተ ፤ የበለፀገና ይህንን የባህል ብልፅግና ለአፍሪካ ያወረሰ ነው።

የኢትዮጵያዊያን ባህል ከጥቁር ህዝብ ጋር ትሥሥር ያለው ፣ የተወራረሰ ነው። ኪነታዊ ባህሉ ለአፍሪካና ለጥቁር አሜሪካዊያን የተረፈ ነው። የወላይታን እና የጃማይካውያንን የሬጌ ጭፈራ ተመልከት ። ራፑ ፣ ሂፕሆፑ ፣ ዳንሱ ፣ ውዝዋዜው  ችክ ቻካው  ከእኛ የሄደ ነው። …ከዚህ ባሻገር ባህላዊ መጠጥ ና ምግቦቻችንንም በጥልቀት በመመርመር ከአፍሪካ ባህላዊ መጠጥና ምግቦች ጋር አጣምረህ ፈትሸው። …

ኢትዮጵያዊ ባህላችን ፣ አውሮፖና እስያ ገና ሣይነቁ ና በወጉ  እንደ ሰው መኖር ሳይጀምሩ  … እንጊሊዝ ና ፈረንሳይ ገና አሜሪካ ያሏትን የቀይ ህንዶች አገር በወረራ ይዘው እርሥ በእርሥ ለአመታት በሰው አገር መሬት ተዋግተው በመሸናነፍ ኢንጊሊዞች የአገሪቱ መሪዎች ሲሆኑ እና አሸናፊዎቹ  ከባህል አንዱ የሆነውን ቋንቋቸውን በሰፊው አሜሪካ ላይ ያነገሱት ትላንትና ነው ። አገር አሳሹ ክርስቶፎር ኮለምበሥ በ1492 ዓ:ም  እኤአ አሜሪካንን እንዳገኛት ይታወቃል ። እንደ አገር ግን ከ1600 እአአ ነው ። እናም ሥሟን ከሰጧት  እንኳ ገና 529 ዓመቷ ነው ። እንደ አገር የቆመችው ግን በ1783 ዓ/ም  እኤአ ነው። በጀነራል ጆርጅ ዋሽንግተን አማካኝነት። 238 ዓመቷ ነው ፤ ህጋዊ  አገር ከሆነች ። እኛ ከአሜሪካ   በሺ ዓመት  ቀድመን ቋንቋ የነበረን ፣ የቱባ ባህል ባለቤቶች  ከመሆናችንም በላይ ግዛታችን እጅግ ሰፊና በሥልጣኔ እጅግ የላቅን  ነበርን ።በሥልጣኔ የመጠቅን    ሥልጣኒያችን ፣ ለአውሮፖና እስያ ሥልጣኔ የተረፈ እንደነበር ፣  የአውሮፓ ፀሐፍት  በታሪክ መፅሐፍቶቻቸው መሥክረዋል።

ዳሩ ምን ያደርጋል ፣ይኽቻ ታላቅ አገር፣ ይኽቺ ሀብታም ና መፅዎች የሆነች አገር ዛሬ ተመፅዎች ና በድህነት ና በእርስ ፣ በእርስ መጠፋፋት  የምትታወቅ አገር ሆናለች ።እንዲህ ተዋራጅ የሆነችሁ ህዝቧ በደሙ ውሥጥ ጥላቻ ብቻ የሚዘዋወርበት ሤጣን ሆኖ አይደለም ። እንደውም በተቃራኒው በደሙ ውሥጥ ፍቅር የሚዘዋወርበት ፃድቅ ህዝብ ነበር ። ጥላቻን በመሥበክ የጥቂቱን ዜጋ ህሊና የበረዙት ፣  ከኢትዮጵያ መንግሥት ሺ ዓመት በኋላ  ለመሠልጠን የቻሉት  ፣ የአውሮፖ ና የአሜሪካ መንግሥታት ፣ ትላልቅ መርከብ ና ገዳይ የጦር መሣሪያ በመሥራት ፣  በእምነት ሥም የተጋመደበትን  ቱባ ባህሉን በመበተን እና ህብረቱን በማፍረሥ በጎሣው ና በቋንቋው እንዲያሥብ ሥላደረጉት ነው ።

ባርያ ፈንጋዮቹ የአውሮፓ ና የአሜሪካ ቱጃሮች ፣ አፍሪካውያንን በባርነት እንዴት እንዳጋዙ ና ኢትዮጵያዊያንን በመሣሪያ እየደለሉ ፣ አንዱን መሥፍን በማቅረብ ሌላውን በማራቅ ፣ መሣሪያ እየሰጡ እንዴት እንዳፋጁን ፤ ከታላቁ የጥቁር ህዝብ ድል ከአድዋ በኋላ ፣ አምሥት ዓመት ሙሉ ተዘጋጅተው ማጨው ላይ ፣ እንዴት ባለ ጨካኝነት በአውሮፕላን ከሰማይ መርዝ እየረጩ እና የመረዝ ጋዝ እያፈነዱ ፣ከቃላት በላይ በሆነ ጭካኔ ፣ፍፁም ፋሺሥታዊ በሆነ በዘግናኝ ድርጊት ታጅበው  ፣ ኢትዮጵያን ለመግዛት እንደሞከሩ ታሪክ በሚገባ ዘግቦታል ።

(…አፍሪካውያን ሠልጥነናል በሚሉ ሤጣኖች ፤ የሞራል ልዕልና በሌላቸው የአሜሪካና የአውሮፓ ገዢ መደቦች ፣እጅና እግራቸው ተጠፍሮ ፣ መለመላቸውን ፣ እንደ ዕቃ እየደራረቡ ፣ በሚዘገንን ሁኔታ ፣  በመርከቦቻቸው  ጭነው  በባርነት እያሰቃዩ ለመግዛት ፣ ጉልበታቸውን ለመበዝበዝ ፣   ወደአሜሪካ  ፣ ስፔን ፣ ፖርቹጋል እና ቤልጄም እንደወሰዳቸው የሚያሳይ መረጃ   በታሪክ ተፅፎ ፣ በፊልም ተሰርቶ እናገኛለን ። )

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከቅኝ አገዛዝ እስከ ኒዮሊብራሊዝም ፣ - ከደረጀ ተፈራ፣

የአውሮፓ ና የአሜሪካ ገዢ መደቦች ፣ ቀሥ በቀሥ ከህብረት ይልቅ ግለኝነትን የሚያነብር  ከሞራል ና ከእምነት የሚፃረረ   ባህላቸውን ቀደም ሲል በራሳቸው ሚሺነሪዎች  ና በትምህርት መፀሐፋቸው በኩል ፣ ዛሬ ደግሞ በዲጂታል ቴክኖሎጂው ና በዓለም አቀፉ የኢንተርኔት መረብ  በኩል ፣ በጎጂ ባህል ሥርጪት ክፍላቸው በኩል ፤  አወቅን ፣ አወቅን በሚሉ  ምሁራን ና  ” ከራሥ በላይ ነፋስ ” በሚሉ ፖለቲከኞቻቸው አማካኝነት ፣ እርኩሰቶቻቸውን  በወጣቶቻችን ልብ ወስጥ በመዝራት ፣  ግብረ ገብ የሌለው ፣ በሱስ የደነዘዘ ፣  ጥቂት የማይባል በከተማ የሚኖር ጎልማሳና ወጣት እንዲፈጠር አድርገዋል ።

( በጣም በሚገርም መልኩ በሁሉም የመንግሥት ተቋማት፣በልማት ድርጅቶች እንዲሁም በተከበረው ና ጠንካራ ዲሲፕሊን በሚጠይቀው መከላከያ ጭምር  በጫት ሱስ የተዘፈቁ ፣ ያለጫት ደማቸው የማይዘዋወር ፣  በሱሱ የተነሳም ” የጀዘቡ ” እና ለሙሥና ተጋላጭ የሆኑ ግለሰቦች የበዙት ባለፉት 27 ዓመታት ነው ። ከእነዚህ …  ውሥጥ ጥቂቶቹ  በኃላፊነት ደረጃ ህዝብና አገርን ያገላግላሉ ተብሎ ፣ በክልል ና በፌደራል ደረጃ ሥልጣን የተሰጣቸው እንደሆኑ ሥናውቅ ደግሞ “መገረማችን ” እጅግ ይብሳል። …)

በጣም በሚያሳዝን መልኩ ፣  አኩሪ ባህላችንን በመበረዝ ሥልጡን ከተባሉቱ ሆኖም የሤጣንን ሥራ ከሚተገብሩት ፣ አንዳንድ የምዕራብ ቱጃር መር ተቋማት በባሰ መልኩ    ፣  ህሊና ቢሥ የሆኑ ፖለቲከኞቻችን  እና ለሆዳቸው ያደሩ  ምሁራን  አገር በታኝ  ሚና ተጫውተዋል።  ህሊና ቢስ ፖለቲከኞች ና ሞራለ ቢስ ምሁራን  የጠቅላላ ዕውቀት ደሃ የሆነውን ዜጋ በቆዳ ማዋደድ ፖለቲካ  ተጠርንፈው  ዛሬም እንደ ጋሪ ፈረሥ ግራ ና ቀኙን እንዳያይ አድርገውታል ።የእነሱ መጠቃሚያ እና መክበሪያ የሆነውን መሬት የአንተ ነው  በማለት ና የአንተው ሰዎች ነን ፤ እምናሥተዳድርህ በማለት ፤ በቋንቋው እያወሩት እንደ ጆርጅ ኦርዊል ድርሰት  “የእንሥሣ ጉባኤ  ” ትርክት የብዝበዛቸው መንገድ ጠራጊ እያደረጉት ነው።

እነርሱ አራት ጊዜ እየበሉ እርሱ አንዴ መብላት አቅቶት ፤ እነሱ በጣት በሚቆጠሩ ዓመታት ቪላ ሰርተው ፣ መኪና ገዝተው እሥከ ቤተሰባቸው ሲንደላቀቁ እርሱ ፣ የጭራሮ በሩን በቆርቆሮ መቀየር እያቃተው ለአንተ ብልፅግና ነው ፤ የምንታገለው ሲሉ ተንሽ እንኳን ህሊና ያለው ምን ይለናል በማለት አይሸማቀቁም። ይግረማችሁ ብለው በንቃተ ህሊናው አሥገዳጅነት እነሱ ሳይሆኑ ቋንቋውን የማይናገረው አብሮት የሚኖረው ፣ውህድ ዜጋ  እንደ አደኸየው ይተረኩለታል ።     ተደጋጋሚ በሚነግሩት  የሐሰት ትርክትም ወደአውሬነት ሲቀየር ያሥተውላሉ ። የዛን ጊዜ  ፣ሐሺሽ ገዝተው የበለጠ እንዲጦዝ በማድረግ በፈጠራ ለተቀነባበረው  በቀል ያሰልፉታል  ።

እናም ጥቂት ሣንቲም ሰጥተው” ይህንን የብልፅግናህን ጠላት ሂድ ዝረፈው ፤ ግደለው ፤ መኖሪያውንም ውረስ ።ወይም አውድም ። ” በማለት ትእዛዝ ይሰጡታል  ። ደሃ ምን ምርጫ አለው ። በዚኽም በዜያም ያው ሞት ነውና የከበበው ፣ በድርጊቱ ባያምንበትም ህይወቱን ለማቆየት የእነሱ እኩይ ሃሳብን ይፈፅማል። …

ይኽ ነው ፤ እንግዲህ የእኛ አገር የፖለቲከኞቻችን የአሥጠሊ ፓለቲካዊ ጫወታ ጎል። የእነሱ ና የጥቅም ሸሪኮቻቸው ቅንጦት እንዳይቋረጥ ፣ በዜጎች ደካማ ንቃተ ህሊና እና የዳቦ ጥያቄ ያለመመለሥ ተጠቅመው ለአገር አፍራሽ ድርጊት     መጠቀሚያ የሚያደርጓቸው   ። ከድህነታቸው ና ከዕውቀት እንዳይፋቱ በማድረግ በእነሱ አማካኝነት  ብዝበዛቸውን የሚያፋጥኑት ።እነሱ ግን በአውሮፓና አሜሪካ ቤት መገዝት ዶላር ማከማቸት ። ብዝበዛው ሙሉ ፣ ለሙሉ ሲቋረጥ “ላሽ ።” ማለትን ያውቁበታል ።

እሥከዛው ግን ፣ የአንተ ጎሣ ና ዘር ወዘተ ። የበለጠ ተጠቃሚ መሆን አለበት በሚል ፣ የሥግብግቦችና የሆዳሞች ጫወታን ያሥቀጥላሉ።  ለሁሉም የሚበቃ ዳቦ አገሪቱ ሳታጣ ፣ በዜጎች መካከል፣ የሌለ የቋንቋ አጥር በማጠር ፣ እጥረት እና ችጋራምነትን በተከታታይ  በመፍጠር ዜጎች  እርሥ በእርሱ እንዲገዳደሉ ያደርጋሉ ።

ይህ ፣ ከአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች የተማሩት እና የወረሱት ከይሲ  የጅብ አሥተሳሰብ ነው። ይህንን የከይሲዎች ፀያፍ ውርስ   በአእምሮአቸው አሥርፀው ፣ ትላንት ሲፈፅሙት የነበረው  ፣ የጭካኔ ተግባር ፣እንሆ   ዛሬም አላባራም ።

ኢትዮጵያውያን የጥንቱን የአባቶቻቸውን ተቻችሎ የመኖር ፣የፍቅርና የመከባበር  አኩሪ ባህል በመንገዘብ   ቋንቋ ሳይሆኑ ሰው መሆናቸውን የሚያውቁበት ንቃተ ህሊና ላይ ካልደረሱም የእነዚህ ከይሲዎች እኩይ ተግባር  ከቶም  አያባራም።

ያለማባራቱንም የምንረዳው እንሆ ዛሬም ሽብር ፈጣሪዎቹ ” አማራና ኦሮሞ ” እያሉ ፣ ድራማ በመሥራት  እዚሁ ” ከመዲናችን አፍንጫ ሥር ” ወሎና ከሚሴ “ እያሉ  ፣ ንፁሐን ወገኖቻችን ህይወታቸውን እና ንብረታቸውን እንዲያጡ ማድረጋቸውን ሥነመለከት ና ስንሰማ ነው ።  ሽብር ፈጣሪዎቹ በከተማ የሚኖሩ ወገኖቻችንን  የግጭቱ ሰለባ ማድረጋቸው የሚያመለክተው   ደግሞ የአሸባሪዎች መቀመጫ አዲስ አበባ እንደሆነ እንድንጠረጠር ያሥገድደናል   ። …

ተጨማሪ ያንብቡ:  አብይ አህመድ ኢትዮጵያዊ ብሄርተኛ ወይንስ የኦነግ ምርኮኛ? ......ከጥሩነህ

በታላቅ ምሥጢር ና በህቡ   አፍንጫችን ሥር ሆነው የሚከውኑት  ፣ የግፈኞች ተግባር የሚመሰክረውም  ፣ ዛሬም የኢትዮጵያን አኩሪ ባህል የማጥፋትና ለእጅ አዙር ቅኝ ገዢነት የማመቻመች ሥራን በተከታታይነት እየፈፀሙ ና እያስፈፀሙ ያሉት ፣ ህሊና ቢሥ የሆኑ  በንዳዎች ፤ ሆድ አደር ፖለቲከኞች ፤  ከይሲዎቹ ቅጥረኞቻቸው ና  አሸባሪዎች  በጣምራ በመሆን እንደሆኑ ተመሣሣይ የጭካኔ ተግባራቸው ይመሠክራል ።  የኢትዮጵያ ጠላቶችም  ይህንን እኩይ ተግባር በፋይናሥና በምክር ፣ በሥልጠና ፣በሥንቅና ትጥቅ  ይደግፉታል።

በኢኮኖሚ የደቀቀ ፤ መሠረታዊ ፍላጎቶቹ ያልተሟላለት ፤ እጅ ወደ አፉ እለት ፣ እለት ፣ የሚወሥደው የቸገረው፤… ቁርሥ የማያውቅ ፤ ምሳውን በቁራሽ እንጀራና በአንድ ጥፊ ወጥ ( እሱም ከሥንት አንዴ ቢገኝ ነው ) ቀምሶ እራቱን አሥቦ የሚያድር በበዛበት አገር ፣ እንዲሁም በጫትና በጋንጃ የደነዘዘ ቀላል የማይባል ወጣት በየከተሞቹ በሚርመሠመሥባት አገር ፤ ጥቂት የደላቸውና ፣ ገንዘባቸውን የሚጥሉበት ያጡ ፣ ( አንዳንድ ቢሊየነሮች በህግ ጥላ ሥር ቢሆኑም የገንዘብ ምንጫቸው በሦሥተኛ ወገን እንደሚንቀሳቀሥ ማሰብ ብልህነት ይመሥለኛል …) ይህንን ምሥኪን ወጣት ና ጎልማሳ በእጦቱ በመጠቀም ለጥፋት ቢዳርጉት ምን የገርማል ?

ይህ እጦት ያሥጨነቀው ፣ ለመኖር መብላት እንደሚያሥፈልገው አሥራጂ የማይፈልግ  እና በመሞት እና በመኖር መካከል ያለ … በጫት ፣ በሃሺሽና በመጠጥ የደነበዘ ወጣትን ለእኩይ አላማቸው ቢያሰልፉትና አንገት ቢያሳርዱት ምን ይገርማል ???

አገርን ለማፈራረሥ በህቡ እየወጠኑ እቅዳቸውን በተለያየ የሽብር አጀንዳ ተግባራዊ ለማደረግ ሌት ተቀን ያለማሠለሥ ላለፉት 60 ዓመታት ያለእረፍት የሠሩ የጥፋት ኃይሎች ፣የበግ ለምድ የለበሰ ተኩላ በመሆን በቋንቋው ሥም በሐሰት ጠዝጥዘው ለእኩይ አላማቸው ፣ በረብጣ ብር በመደለለ በጥፋት መንገድ ቢያሠልፉት እምብዛም አያሥደንቅም ።    ( ሦሪያ ና ሊቢያ ለብዝበዛቸው እንዲያመቻቸው  የመንግሥትን ማዋቅር በማፈራረሥ ወጣቱን እና ጎልማሳውን ለጥፋት አላማቸው ያሰለፉበትን መንገድ ዞር ብሎ መቃኘት ፣ ከአበራሽ ጠባሳ ለመማር ዝግጁነታችንን ያጠናክርልናል ።ሣይቀጣጠል በቅጠል ።ይሏል ይኸው ነው  ። )

እነዚህን የጠላት የጥፋት  መንገዶች ተገንዝበን  ከአገራችን ፈፅመው እንዲወገዱ ፣ ህዝብን በማሥተባበር ና የቀደመው ፍቅሩን ና የመቻቻል ባህሉን እንዲያጎለብት   ካላደረግን ዛሬ የምናሥተውለው  ግጭት ነገ ከነገወዲያ ፣ አገርን እሥከማውደም እንደሚደርስ  ከወዲሁ መገንዘብ አለብን ።

ከዛሬ ነባራዊ ሁኔታ ነገሮችን ሥንቃኝ ፣ዛሬ በከሚሴ እና በወሎ መካከል  ልዩነትን ለመፍጠር የተነሳ አጋጪ ቡድን ነገ ፊንፊኔ እና አዲስ አበባ በማለት ” የደርቢ” የጥፋት ግጥሚያ ሊያሳየን ይችላል ።ከተከፈላቸው ለማውደም ና ለመግደል ዝግጁ  በሆኑ ህሊና ቢሦች ” ይህ እውን ሊሆን ከቶም  አይቻልም ። ”  ማለት አንችልም ።  በየአካባቢው ለህግ የተገዛ ፣ ህግ የሚያሥከብር በወጉ የተደራጀ ፣ የህግ አሥከባሪ ተቋም እሥከሌለ ጊዜ ድረሥ የተረጋጋ ሰላም እንዴት በየቀበሌዎቻችን ሊኖር ይችላል ? …

አገረ መንግሥቱ በየጊዜው የሚያወጣቸውን ፣ የሠላምና የፀጥታ ደንቦችን ና መመሪያዎችን  ህግ ብቻ ሣይሆን የወንጀል ህጉን የተገነዘበ የፖሊሥ አባል  እንዲሁም ለህግ ተገዢ የሆነ  የጎሣና የቋንቋ ውግንና የሌለው የሲቪል ሠርቪስ ሰራተኛ በመላ አገሪቱ እሥከሌለ ድረሥ ግጭቶች አያባሩም ።

( በመጋቢት 24ቱ የምክር ቤት ውሎቸው ጠ/ሚ አብይ አህመድ ለምክር ቤት አባለት ጥያቄ በሰጡት መልሥ ውሥጥ ይህ ጉዳይ ተገቢ ምላሽ የተሰጠበት እና የክልል ልዩ ኃይልን በተመለከተ የሰጡት ማብራርያ ደጋግመን ሃሳብ ያዋጣንበት በመሆን ፣ የማሥተካከያ ጅምሩን አደንቃለሁ። ከሌሎች ጊዜዎች በተለየ ሰከን ባለ መልሳቸው ሥለ ህዳሴ የኃይል ማመንጫ ግድብ የመለሱት  በጥልቅ አምክንዮ የተደገፈ ምላሽም የግብፅ ና የሱዳን መንግሥታትን ቆም ብለው በማሰብ ሥህተቶቻቸውን እንዲያርሙ የሚያደርግ ነው።)

በአገራችን ቀበሌዎች በሟላ ፣  የተሟላ ህግ አሥከባሪ ተቋም እሥከሌለ  ጊዜ ድረሥም   ቀምቶ ፣ ዘርፎ ነጥቆ ፣ ገድሎ ለመብላት በሥመ ነፃ አውጪ ማንም ተደራጅቶ ቢሰማራ ምን ያሥገርማል ?

( ነፃ አውጪ ፖርቲ በተፈቀደበት አገር።ማለቴ ነው። ህዝብ በባርነት ውሥጥ ሳይሆን ፣ ባህሉ፣ደምና ሥጋው ከሌላው ዜጋ ባህል ፣ደምና ሥጋ  ተወራርሶ ባለበት አገር ውሥጥ ማን ከማን ነው ነፃ የሚወጣው  ? በእኔ አገማገም ፣ በነፃ አውጪ ሥም የተደራጁ ቡድኖች በሙሉ በሂትለር እና በሞሶሎኒ አእምሮ የሚያሥቡ ናቸው። ከራሳቸው ዘር ውጫ ፣ሌላው ሰው ሰው የማይመሥላቸው  አውሬዎች በትግራይ ና በምእራብ ወለጋ መፈጠራቸው እጅግ የሚያሳዝን ነው ። ምንም እንኳን ሁላችንም ተፈጥሯዊ ሞትን ለመሞት  ና ወደ አፈር ለመመለሥ የሞት ሠልፍ ውሥጥ ሆነን እየኖርን መሆኑ  ቢታወቅም ፤ ይህንን ጉድ ሳያዩና ሳይሰሙ ለክብሯ ና ለነፃነቷ  የሞቱት አገር ወዳድ ጀግኖቹ ኢትዮጵያዊያን  “እንኳን በዚህ ዘመን አልኖሩ ።”  ያሰኛል ።  …)

ተጨማሪ ያንብቡ:  የደብረ ብርሃኑ ስብሰባ ብልጽግና በሰሜን ሸዋ ዞን ጨርሶ እንዳበቃለትና እንደተንኮታኮተ የሚያስተምር ነበር

ደሞሥ፣  የሚላሥ የሚቀመሥ የሌለው በሦሥተኛ ድህነት የተፈረጀ ፣ በምግብ ለሥራ ወሥፋቱን የሚያሥታግሥ ፣ ዛሬ ያ እርዳታ ሲቀር ወዴት እንዲሄድ ይፈለጋል  ? ወትሮሥ ቢሆን ሰርቶ መብላት እየቻለ  ተመፅዋች ሆኖ እንዲኖር የተፈረደበት ፣ እርዳታው ድንገት ሲቋረጥ ፣ ህይወቱን ለማቆየት ሳይወድ በግድ ለሤጣናት ተልዕኮ ራሱን የመሰዋት በግ አድርጎ ማቅረቡ  ምን ያሥገርማል ?

የሚያሥገርመው የፈቀደውን በውድ ፣ እንቢ ያለውን በግድ ( በአፈሳ ) ፤እንዲሁም  ሌላው የቋንቋው ና የጎሣው ሰው   እንዲበረግግ ፊት ለፊቱ ወንድምና እህቱን ፣የጠላት ተባባሪ ብሎ  በመግደል ፣በማሸበር   ያለአንዳች ማቅማማት ነፍጥ አንግቶ ጫካ እንዲገባ የሚያደርገው ህሊና ቢሱ ነው ። ዛሬም የቀድሞዎቹ  ቅኝ  ገዢዎች አይነት ህሊና ቢስ ቅጥረኞች  በ21ኛው ክ/ዘ  በሰሜን እና በምዕራብ የአገራችን ክፍል እንደ አሸን ፈልተዋል።

ይኽ እውነት ነው ፣ በሰው ደም የሰከሩ አውሬዎችን ያበዛው ።  በአገራችን ፣  የጭካኔ ድርጊቶቹ ተከታታይ እና  እዛ ሲባሉ እዚህ ሆነው እንዲገኙ ያሥቻለው ።  ይህ ሤጣናዊ  ድርጊት ደግሞ በአገራችን ጉዳይ ውሥጥ ለጥቅማቸው ሲሉ በግልፅና በሥውር  ጣልቃ የሚገቡ እንዳሉ የሚያሳብቅ ነው ። …

ከዚህ እውነት አንፃር የአገራችንን ሠላም ማጣት መንሥኤ  ካየነው ፣  በሰሜን ኢትዮጵያ ያለው የወርቅ ክምችት አሜሪካንን ” ጦር ይዤ ካልገባው … ” ቢያሰኛት  አይገርመንም ። ሁሌም የቱጃሮቹ መንግሥታት የግላቸውን ጥቅም እንጂ የአፍሪካ ህዝቦችን ብልፅግና እንደማይፈልጉ የታወቀ ነው ። ከዚህ ሃቅ በመነሳትም ፣ ቀይ ባህርን ለመቆጣጠር ፣ እንዳይችሉ ቃኘው እሥቴሽንን የከለከላቸውን ፣ በዘር እና በጎሣ አሥተዳደር የማያምነውን ኢሳያስን የአሜሪካ ቱጃሮች እንደ ጠላት ቢቆጥሩት የሚገረም ይኖራል ብዬ አላሥብም ።

ኢምፔሪያሊዝም ጥቅም ካላገኘ በሥተቀር የአፍሪካ መሪዎችን ለመደገፍ ፈፅሞ አይፈልግም ። የዘወትር መመሪያው ” ትንሽ ሰጥተህ የእጥፍ እጥፍ ተቀበል ።” ነውና  ፤ ብዝበዛን እንጂ ፣ እኩል ተጠቃሚነትን  ፈፅሞ አይፈቅድም ።

ኢምፔሪያሊዝም ፣ በተለይ ለአፍሪካ ህዝብ ያለው ንቀት እጅግ ከፍተኛ ነው ። በኃይማኖት ሥም ሳይቀር የሚሸቅጥ የሴጣን ተላላኪ ነው ። ድርጊቱን በአንክሮ ሥትመለከቱ በፈጣሪ እንኳን የሚያላግጥ መሆኑንን ትገነዘባላችሁ ። ሞልቶ በተረፈው ሀብቱ አፍሪካውያን የሚሰሩበትን ፋብሪካ ከመገንባት ይልቅ ፣” መዓት ሥራ አሥፈቺ   የአምልኮ ቤተክርሥቲያኖችን (churches ) ” እንደ አሸን እንዲፈሉ ያደርጋል ። በአንዳንዶቹ ቸርቾችም ” መና ከሰማይ እናወርዳለን  ። የሚሉ  ፣ በአንድ ቀን ቢሊዮነር እናደርጋችኋለን  ።  በነገው እለት በለፎቅ ትሆኛለሽ ። ትሆናለህ ።  “በማለት በቀን  ዐይናችሁ እያየ በምኞት ቅቤ እንድትጠጡ የሚያደርጉ ፣ ቀባጣሪ ና ቀጣፊ ነብያትን በእምነት ነፃነት ሥም  በሥውር ያበረታታሉ ።

ከጅምሩ ከገነት ሰው  ሲባረር ፣  በወዙ ጥሮ ግሮ እንዲበላ መታዘዙን እንዲዘነጋ በማድረግ ንቃተ ህሊናው የወረደውን ዜጋ ሁሉ የህልም እንጀራ እየበላ እንዲኖርም እያደረጉት ነው።

ነብያት ና ፓሥተሮች ህዝብን እንዲያደናግሩ ያደርጋሉ። ወዳጄ አትደናገር ። ሢጀመር ፈጣሪ አብ ወልድ መንፈሥ ቅዱሥ ጥረህ ግረህ ብላ ብሎ ነው ወደዚህ ምድር የማጣህ ። እናም በሥራ ትበለፅጋለህ  እንጂ ወደሰማይ በማንጋጠጥ መና አይወርድልህም ።

ይህንን እውነት በቅጡ  ተገንዝበን  እንደ ” ቱጀር መሮቹ ” አገሮች በሥራ ለማደግ  ፣ የህግ የበላይነትን አክበረን ፣ መላውን የአገራችንን ክፍል እንደራሳችን ቆጥረን በሥራ ለመበልፀግ በትጋት እንዳንሰራ ግን ራሳቸው የማያራምዱትን የቋንቋና የጎሣ ፖለቲካ የአገራችን ዋናው መመሪያ በማድረግ “አጋጭቶ ገዢ ” ይፈጥሩልናል።

እኛም የእነሱን ሥውር ሴራ ለመገንዘብ ያለን ንቃተ ህሊና እና የኢኮኖሚ አቅም ስለማይፈቅድልን  ዘወትር ቆዳችንን በማዋደድ ለመኖር እንገደዳለን። ሊሂቃኑም ምንም ሳይሰሩ በጎሣቸው ሥም የሚያከብሩበትን አጋጣሚ ሥለሚወዱት ”   ላም አለህ በሰማይ …” እያሉ  በመግባባዬ ቋንቋው በበሬ ወለደ ፕሮፖጋንዳ ያሥሩታል ።አሥረውና  አሣውረውንም ፣ በሥማችን እየማሉ ፣ የእኛን ድርሻ ሁሉ በማጋበሥ  የግል ሀብታቸውን ያካብታሉ ።

ለመሆኑ መቼ ነው ኢትይጵያ ለኢትዮጵያዊያን ሁሉ የምትሆነው ?  ዛሬም ፣ በአገር መከላከያ ሠራዊታችን ጥቃት ደርሶ ፣ ግልፅና  አጣዳፊ  አደጋ ተደቅኖብን ሳለ ፣ የጥቁር ህዝብ በሙሉ ኩራት የሆነውን ፣ ባህላዊ ታሪካችንን ዘንግተን ፤  ወያኔ ከፀረ ኢትዮጵያ ሃይሎች ጋር ተባብሮ  በቸከለው የጎሣ ና የቋንቋ ችካል ከድህነት ጋር አቀናጅቶ አሥሮን  መራመድ እንደከለከለን እያወቅን ፣ ለምንድነው የተቸከልንበትን ችካል ነቅለን በማሶገድ ፣ እርምጃችንን ማፋጠን ያቃተን ? ?  ….

 

 

 

 

 

1 Comment

  1. Lem Ethiopia was started by the late President of Ethiopia his Excellency Girma Wolde-Giorgis. Lem Ethiopia’s work ethics and superb farming practice in conjunction with the ample rain Ethiopia is having whenever Ethiopia needs itI don’t see any reason why Ethiopia will not become the bread basket of Africa in very few years from now.

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share