ለኢትዮጵያ ኢንቨንስትመንት ኮሚሽን ዳይሬክተር ጄኔራል ተሾመ

አቶ አበበ አበባየሁ ቸኮል የኢትዮጵያ ኢንቨንስትመንት ኮሚሽን ዳይሬክተር ጄኔራል ሆነው መሾማቸው ተሰማ፡፡ የኮሚሽኑ ሃላፊ የነበሩት አቶ ፍፁም አረጋ በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር መሆናቸውን ተከትሎ በቦታው መመደባቸው ታውቋል፡፡

የጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አቢይ አህመድ ቀኝ እጅ እንደሆኑ የሚነገርላቸው አበበ ቀደም ብሎም የኢንቨስትመንት ኮሚሽኑ ምክትል በመሆን ያገለግሉ ሲሆን፤ የጠቅላይ ሚንስትሩ የሕግ ጉዳዮች አማካሪ ነበሩ። የሕግ ባለሙያ የሆኑት አቶ አበበ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተመረቁት ወርቅ ተሸልመው ነበር፡፡

በመቀጠል ከደቡብ አፍሪካው ዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርሲቲ በአለም አቀፍ ንግድና ኢንቨስትመንት ህግ የማስተርስ ዲግሪ ያገኙ ሲሆን፣ ከብሪታንያው ደንዲ ዩኒቨርሲቲ በኢነርጂ ህግና ፖሊሲ በከፍተኛ ማዕረግ የተጨማሪ ማስተርስ ዲግሪ ለማግኘት የበቁ ናቸው፡፡ አቶ አበበ አበባዬሁ በአለም አቀፍ ንግድና ኢንቨስትመት ከ10 አመት በላይ ያካበተ ልምድ ያላቸው ከመሆናቸውም በላይ የአለም ባንክ አካል በሆነው በአለም አቀፉ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን የሰሩና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም በሕግ መምህርነት ያገለገሉ መሆናቸውን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=HxjVbnkoygk

ተጨማሪ ያንብቡ:  "መሬትህን ሊቀሙ ነው የመጡት" በሚል የቤንሻንጉል ነዋሪ ተመላሽ አማራዎችን እንዲያገል በመንግስት ተላላኪዎች እየተሰበከ ነው
Share