በሀድያ ዞን በአየር መዛባት ምክንያት ከ300 በላይ ቤቶች ተቃጠሉ (ሪፖርተር ጋዜጣ)

‹‹ሰሞኑን ዝናብ በመዝነቡ ችግሩ ተቀርፏል›› የዞኑ የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት መምርያ ኃላፊ

በደቡብ ክልል ሀድያ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች የኤልኒኖ ክስተት በሆነው የአየር መዛባት ምክንያት፣ በድንገት በሚፈጠር ቃጠሎ ከ300 በላይ የሚሆኑ ቤቶች መውደማቸው ተጠቆመ፡፡

በተለይ ጊቤ፣ ሰሮ፣ ገምቦራና ሸሸጐ ወረዳዎች ላይ በተደጋጋሚ ባልታሰበ ቀንና ሰዓት በተፈጠረ ድንገተኛ የእሳት ቃጠሎ፣ የበርካታ ቤተሰቦች ቤቶች በመቃጠላቸው ለከፋ ጉዳት መዳረጋቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በነዋሪዎቹ መኖሪያ ቤቶች ላይ የደረሰው የእሳት ቃጠሎ ጉዳት በአካባቢው ከተፈጠረው ድርቅ ጋር ተያይዞ ችግራቸውን እንዳባባሰባቸው የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ የክልሉ መንግሥት ከዞኑና ከወረዳ ኃላፊዎች ጋር በመተባበር ዕርዳታ ባያደርግላቸው የከፋ ችግር ይደርስባቸው እንደነበር አስረድተዋል፡፡

ለጊዜው መጠለያ አጥተው ከአካባቢያቸው ርቀው በመጓዝ ጊዜያዊ መጠለያ ለመጠቀም መሞከራቸውን የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ የክልሉ መንግሥት አስፈላጊውን ዕርዳታ እያደረገላቸው ቢሆንም፣ ቤታቸውን ግን መልሶ መገንባት እንዲችሉ ዕርዳታ እንዲያደርግላቸው ጠይቀዋል፡፡

በዞኑ የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት መምርያ ኃላፊ አቶ ተሻለ ዮሐንስ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የአየር መዛባቱ በአገር የመጣ ስለሆነ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ በሀድያ ለየት የሚያደርገው ድንገተኛ እሳት እየተነሳ የነዋሪዎች ቤቶች መቃጠላቸው ነው፡፡ ያንን ያህል የተጋነነ ጉዳት ባይደርስም የተወሰነ እውነታ መኖሩን አረጋግጠዋል፡፡
እንደ አቶ ተሻለ ገለጻ፣ ካለፈው ሁለት ሳምንት ጀምሮ ዝናብ በመዝነቡ ምክንያት ችግሩ ተቀርፏል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የአካባቢው አርሶ አደሮች 70 በመቶ ለሚሆነው የበልግ አዝመራ፣ መሬታቸውን በዘር ለመሸፈን በመሥራት ላይ መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡

የዝናቡ አጀማመር የተስተካከለ መሆኑንና መንግሥትም ለነዋሪዎቹ ዘር እያቀረበላቸው መሆኑን የጠቆሙት የመምርያ ኃላፊው፣ የአየሩ ሁኔታ ከተስተካከለና ዝናቡም በዚሁ ከቀጠለ ጥሩ የግብርና ወቅት ሊሆን እንደሚችል ግምታቸውን ተናግረዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሃይ ባይ ያጡት ደላሎች!  - አሸናፊ በሪሁን ከ seefar

በተጠቀሱት ወረዳዎች ላይ ደረሰ በተባለው የድንገተኛ እሳት ቃጠሎ አደጋ የሰው ሕይወት ባይጠፋምና በአካባቢው የተፈጠረውን የድርቅ ጉዳት ቢያባብሰውም፣ የክልሉ መንግሥት አስፈላጊውን ዕርዳታ እያቀረበና እያከፋፈለ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለ137 ሺሕ ሰዎች ዕለታዊ ዕርዳታ የሚደረግ መሆኑን፣ 104 ሺሕ ሰዎች ደግሞ በሴፍቲኔት ታቅፈው ዕርዳታውን እያገኙ እንደሆነ አቶ ተሻለ አክለዋል፡፡ በ1999 ዓ.ም. በተደረገው የሕዝብና የቤቶች ቆጠራ በሀድያ ዞን 1.5 ሚሊዮን ሕዝብ እንደሚኖር ተገልጿል፡፡ አሥር ወረዳዎችና በሁለት ከተማ አስተዳደሮች (ሆሳዕናና ሾኔ) እንዳሉትም ይታወቃል፡፡

በዞኑ በተደጋጋሚ ከአየር መዛባት ጋር በሚከሰት የእሳት ቃጠሎ ጋር በተገናኘ ከሁለት ዓመት በፊት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጥናት ያካሄደ ቢሆንም፣ መወሰድ ስላለበት ዕርምጃ ወይም መደረግ ስላለበት ቅድመ ዝግጅት የተባለ ነገር እንደሌለ ታውቋል፡፡

1 Comment

  1. ye Ayer mezabat aydelen !!!!

    weyane botawin le sikuwar ersha selemefelgew

    tedebqew

    ye weyane dehninetoch nachew yemeyaqatlut !!!

    ::

Comments are closed.

Share