“አባይ ይገደብ፤ ኢህአዴግም ይገደብ፤ አባይ ይቀየስ ኢህአዴግም ይቀየስ!” – ከአቤ ቶኪቻው

አቶ በረከት

“የዘመናት ብሶት የወለደው ጀግናው የኢህአዴግ ሰራዊት ከዚህ በፊት ደርግ ሲጠቀምበት የነበረውን የሬድዮ ጣቢያ ለሰፊው ህዝብ ጥቅም ተቆጣጥሮታል፡፡ ጉንቦት ሃያ ሺ ዘጠኝ መቶ ሰማኒያ ሶስት አመተ መህረት!” አለ ታጋዩ…

“የዘመናት ብሶት የወለደው ጀግናው የኢህአዴግ ሰራዊት ከዚህ በፊት ደርግ ሲጠቀምበት የነበረውን የሬድዮ ጣቢያ አሁን ደግሞ ለራሱ ጥቅም ተቆጣጥሮታል፡፡ ቆጣጥሮታልም፤ ግንቦት ሃያ ሺ ዘጠኝ መቶ ሰማኒያ ሶስት አመተ መህረት!” አልኩ እኔ…

“ኢህአዴግ ደርግን ደመሰሰ እና ሌላ ቀዳበት” አለ ልጅ ያሬድ! ”ኢህአዴግ ደርግን ደምስሶ በደርግ ዜማ ሌላ ቀዳበት” አልኩ እኔ

ዛሬ ግንቦት ሃያ ነው፡፡

አነዛ ፀጉራቸውን አሳድገው አዲሳባ የገቡ ሰዎች ዲሞክራሲን እና መልካም አስተዳደር ያሳድጉልናል… ብሎ ተስፋ የጣለባቸው ሁሉ በቴስታ ብለው ከጣሉት እነሆ ሃያ ሁለት አመት እንደዋዛ ሆናቸው፡፡

መልካም አስተዳደሯንም ለራሳቸው እያደሯት፤ ዴሞክራሲዋንም ራሳቸው እየኮመኮሟት ህብረተሰቡን እንቁልጭልጭ አሉት፡፡

ዛሬ የግንቦት ሃያ በዓል ሲከበር የአባይ ወንዝን የማስቀየስ ስራ ይሰራል ተብሏል፡፡ ወንዙ ተቀይሶ ምን ላይ ሊሆን ነው… እንዴት ነው ነገሩ በሳፋ ነው እንዴ ግድቡ የሚሰራው… ብዬ ልጠይቅ ወይስ አልጠይቅ…!

አስታውሳለሁ፤ “አባይ ይገደብ በቃ” ብለው ጠቅላዩ የወሰኑት ከሁለት አመት በፊት “በቃ” በሚል ሀይለ ቃል …ኢህአዴግ ይበቃዋል ግንቦት ሃያን ዘንድሮ ለመጨረሻ ጊዜ እናከብራለን ከዛም ለድጋፍ ሰልፍ ወጥተን በዛው እንቀራለን፡፡ ኢህአዴግ እስካልወረደ ድረስም እቤታችን አንገባም…. የሚል እንቅስቃሴ በፌስ ቡክ በኩል ተጀምሮ የነበረ ጊዜ ነው፡፡

በዚህ በ”በቃ” ጦስ እነ ርዮት አለሙ እነ ውብሸት ታዬ እነ አቶ ዘሪሁን ገብረ እግዚአብሄር እነ ሂሩት ክፍሌ ወድያው ለእስር ሲዳረጉ ቀስ በቀስ ደግሞ ሌሎችም ለቃሊቲ እና ለቂሊጦ ተዳርገዋል፡፡ (በተለይ የነዚህ ወዳጆቼን ፍርድ ሂደት ስከታተል ነበር እና አጋነንክ ቢሉኝም ባይሉኝም የአቃቤ ህግ ማስረጃ “በቃ የሚለውን የፌስ ቡክ እና የአደባባይ እንቅስቃሴ ትኩር ብላችሁ አይታችኋል” የሚል ነበር)

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢዜማ የሚወዳደረው አሜሪካና ካናዳ ነው እንዴ? - ሰርፀ ደስታ

እንቅስቃሴው በፌስ ቡክ ተጀምሮ በየአደባባዩም “በቃ” የሚል ሃይለቃል በመፃፍ ተሟሙቆ የቀጠለ ነበር፡፡ በርካቶችም ግንቦት ሃያ መስቀል አደባባይ የሚፈጠረውን ተዓምር እያሰቡ አንድም ደስታ አንድም ፍርሃት ሲፈራረቅባቸው አንደነበር ትዝ ይለኛል፡፡

ይሄኔ አቶ መለስ ፈርሸው ዘየዱ፤ (ሁል ጊዜ ቁጭ ብለው አሰቡ… እያልንኮ ፍራሽ የሌላቸው አስመሰልናቸው… “ፈርቸው” ማለት ፍራሽ ዘርግተው እጅግ በተመስጦ ማሰብ ማለት ነው…) አስበው አስበውም፤ “ለምን አባይን አንገድበውም…” አሉ እርሳቸው ብለው እምቢ… እንዴት… ለምን… በምን… አይባልምና እሺ እሺ ተብሎ ተጀመረ፡፡ የዛን ጊዜውን ግንቦት ሃያም መንግስታችን ለአባይ ግድብ ድጋፍ ሰልፍ ውጡልኝ፡፡ አለ… በዛውም የህዝቡ የተቃውሞ ሃሳብ ተገደበ፡፡

የአቶ መለስን ብልጠት በመኮረጅ ፈተናዎች ይታለፋሉ ብለው የሚያምኑት አቶ በረከት ደግሞ ዛሬ እነሆ በግንቦት ሃያው አባይ ወንዝን የማስቀየስ ስራ እነደሚሰራ በቴሌቪዥናቸው ብቅ ብለው ነገሩን፡፡

ጥሩ ኮርጀዋል…! አኮራረጃቸው ስም ሁሉ ሳይቀር እንደሚቀዳ አይነት ኮራጅ ነው፡፡

ህዝቡ ይህንን ዜና ሲሰማ ምን አላቸው… የሚለውን ቤት ለቤት ሄደን መጠየቅ ብንችል ጥሩ ነበር፡፡ መጠየቅ ባንችል ግን መጠርጠር እንችላለን እና አንዲህ እንጠረጥራለን፤

“አባይ ይገደብ፤ ኢህአዴግም ይገደብ፤ አባይ ይቀየስ ኢህአዴግም ይቀየስ!” ሳይላቸው አይቀርም፡፡

 

 

1 Comment

  1. I think people can organize in whatever way they want. But their support base depend on their mission and their view about others. I don’t like I’m the only victim mentality. THere are dozens of ethnic based parties out there. We support or reject them based on how they articulate their mission. OLF was Oromo based party we (at least non-Oromos) reject it because it have ‘we are the only victim’ mentality and its mission was to divide the country in to pieces. ONC is Oromo based party, we support it because they struugle for all Ethiopians in general and Oromosin particular. So I don’t mind if Amaras form their parties as far as their struugle is not for superioity of their ethnic group but the crown of human right anfd freedom for all because HUMANITY BEFORE ETHNICITY and NO ONE IS FREE UNLESS WE ALL ARE FREE. That is why I support from the bottom of my heart people like OBANG METHO even though I’a shewa Amara. We should know that no one have better or more right than anyother in any part of the country. Only qulification and attitude matters not ethnicity.

Comments are closed.

Share