November 15, 2024
የትውልደ ትውልድ ውድቀታችንን ግልፅነትን በተላበሰ፣ ቀጥተኛ በሆነና ወደ ተሻለ ሁለንተናዊ ግሥጋሴ በሚወስድ ይዘትና አቀራረብ ለመናገርና ለመነነጋገር ያለመቻላችን ድክመት ያስከተለብን አስከፊ ውጤት ዘርፈ ብዙ ነው።
በዚህ ረገድ መከረኛው ህዝብ በእኩያን ገዥ ቡድኖች የግፍ አሟሟትና የቁም ሙትነት ሰለባ ሆኖ በቀጠለበት በዚህ እጅግ አስጨናቂና አስፈሪ ወቅት ሃይማኖትን ያህል ታላቅ ጉዳይ እና ሊከበር የሚገባው ኪነ ጥበብን ያህል ሙያ በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ የወንጀለኛ ፖለቲካ ሥርዓት ሰለባዎች (መሣሪያዎች – ሽፋን ሰጭዎች) የመሆናቸውን ግዙፍና መሪር ሃቅ ለመጥቀስ ስገደድ እያዘንኩ ነው።
በወጣትነቱ የጀመረው የድምፃዊነት ሙያ አድናቆትንና ታዋቂነትን ያስገኘለት ዳዊት ፅጌ የአሁኑ እሁድ እለት በአብዛኛው የሸፍጠኛ፣ የሴረኛና የጨካኝ ገዥ ቡድኖች ርካሽ የፖለቲካ ተውኔት በሚካሄድበትና ሚሊኒየም ብለው በሰየሙት አዳራሽ የሙዚቃ ድግሥ (ኮንሰርት) እንዳዘጋጀ ወይም እንደተዘጋጀለት የሃፍረትና የውርደት መረጃ/ዜና መስማት በማይሰለቻቸው ጆሮዎቻችን እየሰማን ነው።
በመሠረቱ አለመታደል ሆኖብን ሳይሆን በገንዛ ራችን አስከፊና ተደጋጋሚ የውድቀት አባዜ ምክንያት እሰየው የሚያሰኝ ሁኔታ ለመፍጠር ባለመቻላችን ነው እንጅ ብንችል ኖሮ እንኳንስ እንደ ዳዊት አይነት ተስጥኦውና ክህሎቱ ያላቸው ግለሰቦች ሌሎችም እንችላለን/ እንሞክራለን ለሚሉ ሁኔታዎች እየተመቻቹላቸው ቢዘፍኑ ወይም ቢተውኑ የሚቃወም ባለ ጤናማ አእምሮ ህሊና የአገሬ ሰው የሚኖር አይመስለኝም። ለዘመናት የመጣንበትና አሁንም ለማመን በሚያስቸግር መከራና ውርደት ውስጥ የመሆናችን ግዙፍና መሪር እውነታ ግን ተቀባይነት ካለው እንዲህ አይነት እውነታ ውጭ ነው።
በመሆኑ እንደ ዳዊት ፅጌ አይነቶች ድምፃዊያን ወይም የሌላ አይነት ኪነ ጥበብ ባለሙያዎች አዲስ አበባን ጨምሮ በአገሪቱ ውስጥ ምንም እንዳልተፈጠረ በመቁጠር ወይም ከህሊና በላይ የሆነውን የአገራችን መከራና ውርደት “መከራና ደስታ አብረው የኖሩ ናቸው” የሚል እጅግ ደምሳሳና ግልብ ትርጉም በመስጠት ወይም እጅግ አሳፋሪ በሆነ ግብዝነት ወይም የህዝብ እውቅና እና አድናቆት ማግኘት ማለት ሁሉን ማወቅ አድርጎ በመውሰድ ከንቱ ግብዝነት ፣ወዘተ የሚያዘጋጁት የአዳራሽ ውስጥ መውረግረግና ሽር ጉድ በህዝብ መከራ ላይ የመሳለቅ ክፉ ተግባር እንጅ ሌላ ትርጉም አይኖረውም።
የሃይማኖት መሪዎችና ሰባኪዎች የሰማእትነት ዋጋ ሊያስከፍል እስከሚችል የአርበኝነት አቋምና ቁመና ሊደርሱ/ሊበቁ ይችላሉ ብለን ስንጠብቅ ይባስ ወደ ቁልቁለት የመውረዳቸውን አስከፊ ሁኔታ እየታዘብን ባለንበት በዚህ ወቅት እንደ ዳዊት ፅጌ አይነት ገና በወጣትነታቸው ባሳዩት የኪነ ጥበብ ዘርፍ አካል በሆነው የሙዚቃ ተሰጥኦና ክህሎት ከህዝብ የተቸራቸውን ከበሬታና አድናቆት በሚያጎሳቁል/ዋጋ በሚያሳጣ ሁኔታ የሙዚቃ ፌስታ (ኮንሰርት) ሊያካሂዱ መሆናቸውን መስማት ህሊናውን የማያቆስለው ነፃነትና ፍትህ ፈላጊ ወገን የሚኖር አይመስለኝም።
አዎ! በሴረኛና ጭካኝ ገዥ ቡድኖች ምክንያት ንፁሃን ወገኖቹ በግፍ ደም እየጨቀዩ ባሉበት፣ ማቆሚያ ባጣ የደም እንባ በመጣጠብ ላይ በሚገኙበት፣ ፈፀሞ እረፍት የማይሰጥ የቁም ሰቆቃ ሰለባዎች በሆኑበት ፣ እጅግ አስፈሪ በሆነ ተስፋ የማጣት መሪር እውነታ ውስጥ በሚገኙበት ፣ ወዘተ ግዙፍና አስከፊ እውነታ ወቅት እንኳን ታላቅ ኮንሰርት አዘጋጅቶ ታደሙልኝ ለማለት ሃሳቡን ለማሰብም በእጅጉ ይከብዳል።
እናም ለዚህ ነው ምነው እነዚህ ወገኖችን ነውር ነው ብሎ የሚመክር ወላጅ፣ ዘመድ፣ ጓደኛ፣ የእድሜና የተሞክሮ ባለፀጋ ሽማግሌ ፣ እንጥፍጣፊም ቢሆን የእረኝነት ሃላፊነት ያለበት የሃይማኖት አባት/መሪ/ሰባኪ/ሊቅ/ሊቀ ሊቃውንት የለም እንዴ? ብሎ መጠየቅ አስፈላጊ የሚሆነው።
ከፋኖዎች የተላለፈው የወንድምነት መልእክት የፖለቲካ ብቻ ሳይሆን የሞራል/የህሊና፣ የመልካም ሰብእና፣ የሥነ ምግባር፣ የትክክለኛ ኪነ ጥበብ ባለሙያነት ፣ የመንፈስ ልእልና ፣ ወዘተ ጉዳይ ነውና ከምር ሊወሰድ ይገባል የሚል ፅዕኑ እምነት አለኝ ።
“ወጣ ወጣና እንደ ሸንበቆ ተንከባለለ እንደ መውቀጫ“ “የቄስ ሚስት አወቅሽ አወቅሽ ቢሏት መጽሐፍ አጠበች“ ፣ ” እዩኝ እዩኝ ያለ ደብቁኝ ደብቁኝ ይላል“ “ትንሽ (ቁንፅል) እውቀት አደገኛ ነው“ ወዘተ የሚሉ አባባሎችን በጥሞና ማጤን ይጠቅማል። ለምን? ቢባል በአያሌ ንፁሃን ደምና የቁም ሰቆቃ ዙሪያውን በተጥለቀለቀ አዳራሽ ውስጥ በተዘጋጀ ብልጭልጭ መድረክ ላይ መውረግረግና ማስጨብጨብ እውነተኛው ታሪክ ፈፅሞ ይቅር የማይለውና በኪነ ጥበብ ስም የሚፈፀም እኩይ ተግባር ነውና የሚሻለውና ከሰው ተርታ የሚያውለው ከህሊና ጋር ተማክሮ ከይቅርታ ጋር ሰርዠዋለሁ ማለቱ ነው።