May 12, 2024
19 mins read

ትላንት ጥሩ ተሰራ ተብሎ ዛሬ ስህተት ሲፈጸም ዝም ማለት አይቻልም

441515707 10231919618644097 1307513304590501476 n

ግርማ ካሳ

441515707 10231919618644097 1307513304590501476 n(የመቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤና እስክንድር ነጋ እንቅስቃሴን በተመለከተ)

ከሰባት ወራት በፊት በፊት፣ በጎጃም ያሉ አብዛኞቹ የፋኖ አደረጃጀት መሪዎች፣ መሃል ጎጃም እምብርት ፣ ፈረስ ቤት ከተማ ላይ በመሰባሰብ የጎጃም እዝን መመስረታቸው የሚታወቅ ነው፡፡ በወቅቱ ዕዙ በእስክንድር ነገ የሚመራው፣ የአማራ ህዝባዊ ግንባርና እነ አርበኛ ዘመነ ካሴና አስረስ ማሩ ያሉበት የአማራ ህዝባዊ ኃይል፣ ተነጋገረው፣ አንድ ወጥ የፖለቲካ አመራር የሚሰጥ ኮሚቴ እንዲያቋቋሙ፣ ፖለቲካውን እንዲመሩ ከመጠየቅም አልፎም የነርሱ አመራር እንደሚቀበል በይፋ አሳውቆ ነበር፡፡

በተመሳሳይ ጊዜ በፋዎች ዘንድ፣ አንድ ወጥ የፖለቲካ አመራር እንዲኖር ለማድረግና ለማገዝ ጋዜጠኛ ሃብታሙ አያሌውን ጨምሮ፣ በተለይም በአማራ ህዝባዊ ግንባር የዳያስፖራ ደጋፊዎች ባደረጉት ግፊት፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና  አርበኛ ዘመነ ካሴ ከሌሎች አንዳንድ የፋኖ መሪዎች ጋር በመሆን፣ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት የሚል ስብስብ ለመፍጠር ከመግባባት ደረሱ፡፡ የአማራ ህዝባዊ ግንባር ሲባል የነበረውም መክሰሙ ተገለጸ፡፡ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት ከተመሰረተ በኋላ፣ ጤናማና አስፈላጊ አጀንዳና ግብ ይዞ የተነሳ ቢሆንም፣ በተለያዩ ምክንያቶች ረጅም ርቀት ሊሄድ አልቻለም፡፡

አርበኛ ዘመነ ካሴ ከነእስክንድር ተለይቶ ፣ ከነ አስረስ ማሩ ጋር በመሆን በአማራ ህዝባዊ ኃይል ስር የበለጠ መንቀሳቀስ ጀመረ፡፡ ( አርበኛ ዘመነ ካሴ ለምን ተለየ ? በነ እስክንድር ነጋ ላይ ክህደት ፈጿምል ወይ ? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎች ይነሳሉ፡፡ ያ የነርሱ ጉዳይ ነው) የአማራ ህዝባዊ ኃይል በአንድ በኩል የጎጃም እዝ በሌላ በኩል ሁለት አደረጃጀት ሆነው በራሳቸው መንገድ መጓዝ ጀመሩ፡፡ ከፍተኛ ጥረትና ውይይቶች ከተደረጉ በኋላ የአማራ ሕዝባዊ ኃይል የጎጅም እዝ አንድ በመሆን፣ የአማራ ፋኖ በጎጃም ተቋቋመ፡፡ በጎጃም ያሉ ፋኖዎች በአንድ ወታደራዊና ፖለቲካዊ አደረጃጀት ውስጥ ሆኑ፡፡

በዚህ ወቅት እስክንድር ነጋ ከጎጃም ለቆ ወደ ሸዋ አመራ፡፡ ለምን ? የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ የጎጃም ዕዝን ምስረታ ተከትሎም፣ በሸዋ፣ በወሎና በጎንደር ሁለት ሁለት እዞች ተቋቋሙ፡፡ እንደ ጎጃም የወሎ ሁለት እዞች አንድ ሲሆኑ፣ በጎንደርና በሸዋ ያሉ ሁለት ዕዞች አንድ ለመሆን በንግግር ላይ ናቸው፡፡

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ፋኖውች አንድ እንዲሆኑ ራእይ ይዞ የተንቀሳቀሰ ሰው ነው፡፡ እርሱ ባሰበበት መንገድ፣ በአማራ ህዝባዊ ግንባር ሆነ በአማራ ሕዝባዊ ሰራዊት በኩል ባይሆንም, ራእዩ ተገባራዊ ወደ መሆን እየመጣ ነው፡፡ ያ ሊያስደስተው ነው የሚገባው፡፡

በዕዞች አመሰራረትና እንቅስቃሴና ሂደት ውስጥ ፣ እስክንድር ነጋ የሚመራው የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት ምን ያህል አዎንታዊ ሚና እንዳለው የማውቀው ነገር የለም፡፡ ሆኖም የተመሰረቱ የፋኖ የጠቅላይ ግዛቶ ዕዞችን የማዳከምና የመከፋፈል አፍራሽና አሉታዊ ስራዎች፣ በዚህ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት ስም ግን እየታዘብን ነው፡፡ ከቀናት በፊት መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ “በጎጃም የአማራ ህዝባዊ ስራዊት ተቋቁሟል” የሚል መግለጫ ወጥቷል፡፡ ይህም ብዙዎችን እያስደነገጠና እያስቆጣ ያለ አሳዛኝና አሳፋሪ ክስተት ሆኗል፡፡

ከሶስት አመታት በፊት መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ፣ ከዘመነ ካሴ ቀጥሎ የአማራ ሕዝባዊ ኃይል ምክትል ሊቀመንበር የነበረ ሰው ነው፡፡ የህወሃት ሁለተኛው ዙር ጦርነት ሲጠናቀቅ ፣ አገዛዙ ዘመነ ካሴን ወደ ወህኒ ወስደ፡፡ ከ15 ሺህ በላይ ፋኖዎችን፣ ብዙዎቹ የጎጃም ፋኖዎችን ፣ አሰረ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መቶ አለቃው ድምጹ አልተሰማም፡፡ የደቡብ አፍሪካው ስምምነት የተባለው ተፈረመ፣ አገዛዙም አፍጦና አግጦ የጥጋብና የጀብደኝነት ጦርነቱን ሚያዚያ 20 ቀን 2015 ዓ/ም በአማራ ክፍለ ሃገር ላይ ከፈተ፡፡ በተለይም የጎጃም እዝ ከተቋቋመ በኋላ እንዳለ ምስራቅ እዝን በማምጣት፣ እጅግ በጣም ክፍተኛ ውጊያዎች በጎጃም ምድር ተደረጉ፡፡ በሻለቃ ዝናቡ የሚመራው የጎጃም ዕዝ፣ በነጀለራን መሐመድ ተሰማ ከሚመራው ጦር ጋር ለወራት መሬት አንቀጥቅጥ ውጊያዎችን አደረገ፡፡ የአገዛዙ ጦር አከርካሪውን ሰባበረ፡፡ በዚህ ሁሉ ጊዜ መቶ አለቃ ማስረሻ ስጤ ብዙ ድምጹ አልተሰማም፡፡

ታዲያ አሁን ከየት መጥቶ ነው፣ “የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት የጎጃም እዝ ተቋቁሟል” በሚል ፣ አንድ የሆነውን የጎጃም ፋኖዎች አደረጃጀት የተጻረረ፣ በጎጃም ሌላ እዝ በመመስረት፣ የጎጃም ፋኖዎች ለመከፋፈል የመሞከር ስራ የሚሰራው ?

እንግዲህ ለዚህ ወንድማችን ግልጽ መልእክት አለኝ፡፡ ማስረሻ ሰጤ ጎጃምን ከመከፋፈል ተግባሩ መቆጠብ አለበት እላለሁ፡፡ ለህዝብ፣ ለጎጃም፣ ለአማራ ማህበረሰብ፣ ለአገር፣ ለኢትዮጵያ የቆመ ከሆነ፣ የኦሮሞ ብልጽግናን አጀንዳ ሳይሆን ማስጠበቅ ያለበት የህዝብን አጀንዳ ነው፡፡ በግለሰብ ደረጃ ከዘመነ ካሴ ወይንም አስረስ ማሬ ወይንም ሌሎች ሰዎች ጋር ችግር ካለበት፣ ጉዳዩ የግለሰብ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ መሆኑን መረዳት አለበት፡፡ ተለይቶ የራሱን ኃይል ለማቋቋም በሚያደርገው ነገር ግን፣ ከዘመነ ካሴ ወይንም አስረስ ማሩ ጋር ሳይሆን ከህዝብ ጋር ነው የሚጋጨው፡፡ በአስቸኳይ ከዚህ ድርጊቱ ተቆጥቦ፣ አዛዋለሁ የሚለውን ኃይል በአማራ ፋኖ ጎጃም እዝ ወታደራዊ ኮምንድ ስር ማስደረግ አለበት፡፡ ያ ካልሆነ ግን የርሱ ኃይል እንደ ብልጽግና ወይንም ብአዴን፣ ጸረ ህዝብና ጸረ ፋኖ ኃይል ተደርጎ እንደሚቆጠር ማወቅ አለበት፡፡ በጎጃም ከአማራ ፋኖ ጎጃም እዝ ውጭ ሌላ ምንም አይነት የተደራጀ የፋኖ አደረጃጀት መኖር የለበትም፡፡

መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ ይሄንን አፍራሽ ተግባራት ሲያደርግ፣ የእስክንድር ነጋ ሚና ምንድን ነው ? የሚለው መነሳት ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ እስክንድር ነጋ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት መሪ ነው፡፡ ማስረሻ ሰጤ ጎጃም የጎጃም ፋኖዎችን እየከፋፈለ ያለው በአማራ ሕዝባዊ ሰራዊት ስም ነው፡፡ በነማስረሻ ሰጤ በኩል እስክንድር ነጋ በርግጥም ሸዋ ላይ ተቀምጦ የጎጃም ፋኖዎች እንዲከፋፈሉ እያደረገ ነውን ? ለዚህ በአሰቸኳይ ምላሽ መስጠት አለበት፡፡

በጎጃም ብቻ አይደለም፣ በሸዋም እነ አቶ አሰግድ መኮንንና እነ ሻለቃ መከታው የሚመሯቸውና አንድ ለመሆን እየተወያዩ ያሉ ዕዞች ሳያውቁ፣ በድብቅ፣ እስክንድር ነጋና የአማራ ሕዝባዊ ሰራዊት በሸዋ ሌላ ሶስተኛ የፋኖ አደረጃጀት ለመፍጠር እየሰሩ ነው ወይ ? በወሎ የነበሩ ሁለት ዕዞች አንድ ሆነዋል፡፡ በጎንደር ያሉ ደግሞ አንድ ለመሆን ተስማምተው አንድ ለመሆን ጫፍ ደርሰዋል፡፡ ታዲያ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት አንድ ለመሆን እየተደረገ ባለው ጥረት ላይ ቀዝቃዛ ውሃ በመቸለስ ለምን አፍራሽ ተግባራትን ይፈጽማል ? ለነዚህ ጥያቄዎች እስክንድር ነጋ ግልጽ ምላሽ መስጠት አለበት፡፡ ግልጽ ምላሽ መስጠት ብቻ ሳይሆን በአስሸኳይ ከግትርነቱ ወጥቶ፣ የህዝብን ትግል በአሁኑ ወቅት እየመሩ ካሉ የአማራ ፋኖ እዞች ጋር በመተባበር መስራት መጀመር አለበት ባይ ነኝ፡፡

በዚህ ዙሪያ በአክብሮት የሚከተሉትን እንዲያደርግ ምክር እሰጣለሁ፡

1ኛ በአሁኑ ወቅት ስድስት የአማራ ፋኖ እዞች ነው ያሉት፡፡ በቅርቡም የጎንደርና የሸዋ እዞች አንድ ሲሆኑ፣ የዕዞቹ ቁጥር ወደ አራት ይወርዳል ተብሎ ነው የሚጠበቀው፡፡ አራቱ ዕዞች ደግሞ አንድ የአማራ ክፍለ ሃገር ኮማንድ ያቋቁማሉ፡፡ በመሆኑም እስክንድር ነገ በይፋ፣ በጠቅላይ ግዛቶቹ ላሉ ለአማራ ፋኖ ዕዞች እውቅና ይስጥ፡፡ አንድ በመሆን ላይ ያሉ ዕዞች በቶሎ ውህደታቸውን እንዲያጠናቅቁ፣ ትልቅ የአማራ ኮማንድ እንዲቋቋምም የርሱ እገዛ ያድርግ፡፡ እንጂ በተናጥል፤ የተወሰኑት በመያዝ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት የሚል ጨዋታውን ማቆም አለበት፡

2ኛ በይፋ በአማራ ህዝባዊ ሰራዊት ስር የተደራጁ፣ የፋኖ አደረጃጀቶች፣ እነ ማስረሻ ሰጤ የሚመሩትን ጨምሮ፣ በጠቅላይ ግዛት እዞች ስር እንዲሆኑ መመሪያ ይስጥ፡፡ እነ ማስረሽ ሰጤ ወደ ጎጃም እዝ፣ ወሎ ያሉት ጥቂት የአማራ ህዝባዊ ሰራዊቱ ሰዎች በነኮሎኔል ፋንታሁንና ምሬ ወዳጆ ወደ ሚመራው የወሎ እዝ፣ በጎንደር ያሉም በቅርቡ አንድ ለመሆን በተስማሙት በጎንደር እዞች ስር ይጠቃለሉ፡፡

3ኛ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት መክሰሙን ይፋ ያድርግ፡፡ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት የተቋቋመው ፋኖዎችን አንድ ለማድረግ ነበር፡፡ አሁን ፋኖዎቹ በራሳቸው መንገድ አንድ እየሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት የሚባለው አስፈላጊ አይደለም፡፡

4ኛ ዘመነ ካሴ በአማራ ፋኖ ጎጃም ዕዝ ውስጥ የፖለቲካ ስራ ሃላፊነት ወስዶ የድርሻዉን እየተወጣ ነው፡፡ እስክንድር ነጋም ልክ እንደዘመነ ካሴ፣ የሸዋ ፣ ወይንም ጎንደር ወይንም ወሎ ዕዞች ውስጥ በመታቀፍ ፣ የድርሻዉን ለማበርከት ይዘጋጅ፡፡ ትልቅ ተወዳጅነትና ተቀባይነት ነው ያለው፡፡ ከፋኖ ዕዞች በተጻራሪ ከቆመ ግን ለርሱ ትልቅ የፖለቲካ ኪሳራ ነው የሚሆንበት፡፡ ከዕዞቹ ጋር ከሰራ ግን እንደገና በፖለቲካ ማንሰራራት ይችላል፡፡

5ኛ ከእስክንድር ነጋ ጋር የሚሰሩ፣ የቀድሞ የአማራ ህዝባዊ ግንባር አሁን የአማራ ህዝባዊ ሰራዊት ሰዎችና የሜዲያ ሰዎች አሉ፡፡ በውጭ አገር፡፡ በፋኖዎች ስም የተሰበሰበ ወደ ሚሊዮን ዶላር (ከመቶ ሚሊዮን ብር በላይ) በእጃቸው አለ፡፡ ለነ ማስረሻ ሰጤም ድጋፍ እያደረጉ ያሉትን እነዚሁ ናቸው የሚል ተቃውሞ የሚሰማው፡፡ ለፋኖዎች ጥንካሬ፣ ለፋኖዎች ድጋፍ ህዝብ ያዋጣው የህዝብ ገንዘብ፣ ፋኖዎችን ለመከፋፈል መዋል በጭራሽ የለበትም፡፡ በመሆኑም እስክንድር ነጋ፣ በፋኖ ስም የተሰበሰበውን ገንዘብ በሙሉ፣ ለአማራ ፋኖ ዕዞች እንዲተላለፉ መመሪያ መስጠት አለበት፡፡

6ኛ አንድ ብቃት ያለው መሪ አንደኛ ችግሮች ከመከሰታቸው በፊት፣ ምልክቶች እንዳየ አስቀድሞ ይጠነቀቃል፡፡ ሁለተኛ ችግሮች ሲከሰቱ ደግሞ ወዲያው መፍትሄ ይፈልጋል፡፡ ሶስተኛ እርሱ ለመከፋፈለና ለልዩነት ምክንያት አይሆንም፡፡ የተከፋፈሉትን የተለያዩትን ያሰባስባል እንጂ፡፡ እስክንድር ነገ በነዚህ በሶስቱም መስፈርቶች ሚዛን ሊደፋ አልቻለም፡፡

በተለየም ሶስተኛውን ምክኑታ አስመልክቶ፣ እስክንድር ነጋ ቆም ብሎ ማሰብ አለበት፡፡ በርሱ ምክንያት፣ በርሱ ስም፣ በሶሻል ሜዲያ፣ በየትዊተርና ቲክቶኩ ፣ በአንድ ላይ መቆም ያለባቸው ወገኖች፣ እየተጋጩ ነው፡፡ እስክንድርን ለምን ተናገራችሁ ፣ አልተናገራችሁ በሚል እየተወዛገቡ ነው፡፡ እየተወዛገብን ነው፡፡ እስክንድር ነጋ “በኔ ስም ይህ መሆን የለበትም” ብሎ ይሄን ነገር ማስቆም ነበረበት፡፡ እስክንድር ነጋ በተለይም በዳያስፖራ ለመከፍፈል ምክን ያት በመሆኑ በግሌ በጣም ያዘንኩበት ነገር ነው፡፡ አሁን ጊዜው አልረፈደምና ይሄንን ነገር ያስቁም፡፡

እስክንድር ነጋ ለትግሉ ብዙ ያበረከተ ሰው ነው፡፡ ብዙዎቻችን ለርሱ ትልቅ ክብርና አክብሮት ነው ያለን፡፡ ከአሁን ለአሁን ትላንትና ጥሩ ሰራ ሰርቷል ተብሎ ግን ዛሬ ትልቅ ችግር ሲፈጠር ዝም ማለት አይቻልም፡፡ ዝም ማለት ትግሉን መጉዳት ነው፡፡ ጉዳዩ የእስክንድር ጉዳይ አይደለም፡፡ ጉዳዩ የህዝብ ጉዳይ ነው፡፡ ጉዱዩ የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ እስክንድር ነጋ ለትግሉ እንቅፋት መሆኑን ካላቆመ በግልጽ ሊነገረውና በቃ ሊባል ይገባዋል፡፡

በዚህ አጋጣሚ እንክንድርን የምትቀርቡት፣ አሁንም ከርሱ ጋር ግንኙነት ያላችሁ ሰዎች ምከሩት፡፡ የሚሰማ ከሆነ፡፡

1 Comment

  1. ግርማ ካሳ ከትግሉ፣ከአማራው ግፍ አንጻርና ከትግል ልምድህና ጥናትህ ወስደኸው ከሆነ አላውቅም። የእስክንድር ነገ ጥንቃቀቄ ያስፈልገዋል ነገሮች በሞራል እሳቤ ሲታዩ ያሳዝናል። ለፋኖ መብራት የለኮሰ እሱ መሆኑም ትዝ ይለኛል ዘመነ ካሴም በወቅቱ እቡይ ሁኖ ስለ እስክንድር የተናገረውም ትዝ ይለኛል ከጎጃም ምድር መልቀቁም ያ ሊሆን ይችላል። እስክንድር ስልጣን ፈልጎ የአማራውን ትግል ለማዳከም ለማኮሰስ አስቦ የሚሰራም አይደለም። እነ ማስረሻ ሰጤም ትላንት የግምባር ስጋ ሁነው የተለበለቡትን መርሳት አያስፈልግም። ትግሉ እያየለ ሲሄድ መግቢያ ያጣውና መተዳደሪያውን በህዝብ መዋጮ ያደረገው ግንቦት ፯ና በሚዲያ ስም የሚንከወከው ሆድ አደሮችም ነገሮችን በማሳከር ተጠምደዋል። በመናገራቸው ብቻ እራሳቸውን አዋቂ ያደረጉ ግልቦችም አቅማቸው በማይፈቅደው ነገር እሽክርክሪት ውስጥ ገብተው አገር ባያምሱ መልካም ነው። ካልሆነ አገር ከሚያምሱ ስሙኒ ስሙኒ በወር እያዋጣን ብንሰጣቸው አገር ሰላም ያገኛል እኛም አንጎዳም። እስክንድርንም ሆነ ማስረሻ ሰጤን የሚገባቸውን ክብር ሰጥተን የትግሉ አካል ማድረግ ይገባል። ዘመነ ካሴም ይሄ እኔ የሚለውን ትቶ እኛ ቢል መልካም ነው ጥብቅ ትእዛዝ ሰጥቻለሁ መመሪያ አውርጃለሁ የሚለው ቋንቋ ነገ ወደ ረሽኛለሁ ይሸጋገራል። መሪነቱን ወናፎች ሳይሆን ትሁቶች፣አርበኞች፣አርቆ አሳቢዎች እንጅ አስገድደው እውቅና ስጡኝ ባሉት ባይያዝ መልካም ይሆናል። ካሁኑ ፋኖ ውስጥ ዘመነ ካሴ እንዳለው ማለት ተጀምራል። ለማጠቃለል ክብር ያላቸው ዜጎች የአማራው መከራ መከራቸው የሆኑ ልጅ ተድላ ፣አቻምየለህ ታምሩ፣ፕሮፌሰር ሐብታሙን የመሳሰሉ በውስጥ መስመር ተገናኝተው መልክ ቢያስይዙት መልካም ይሆናል። በዚህ ሂደት ክልፍልፎች ብልጣብልጦች ገንዘብ ወዳዶች አክቲቪስትና ጋዜጠኞች ነን ባዮች እንዲህ አይነቱን ችግሮች ገንዘብ ማመንጫ ለሆነላቸው በሩን ጠርቅሞ መዝጋት መልካም ይሆናል። ሰርተው ይብሉ ይለምዱታል።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

67788889
Previous Story

እውን የወልቃይትና የራያ ጉዳይ የህግ መንግሥት ተብየው  ጉዳይ ነው?

190193
Next Story

አብይ ከፋኖ ጥይት ለጥቂት አመለጠ | ሰራዊቱ ጎጃም ላይ ተከበበ | ባለሀብቱ ጅቡቲ ላይ ተያዘ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop