ለመሆኑ  የከሞት በኋላ ህይወት መንገዱና መግቢያው ምንድን ነው?

April 23, 2024

ጠገናው ጎሹ

ገዳይ አብይ አህመድ መመለስ ያለበት ጥያቄ
ገዳይ አብይ አህመድ መመለስ ያለበት ጥያቄ

መቸም በገዛ ራሳችን ስንፍና ለዘመናት የመጣንበትንና በአሁኑ ወቅትም በባሰ አኳኋን ተዘፍቀን የምንገኝበትን ግዙፍና መሪር ፖለቲካ ወለድ መከራና ውርደት መጋፈጥ ሲያቅተን ወይም ወኔው ሲያጥረን ነውርና ሃጢአት የሆነውን እየሸሸን ነውርና ሃጢአት ያልሆነውን ነውርና ሃጢአት ከማድረግ የአስተሳሰና የእምነት እንቆቅልሽ ለመላቅ ገና ብዙ የሚቀረን መሆኑን ስለመገነዘብ ለምን በሃይማኖት ተቋማት መሪዎችና ባለ ሌላ ማዕረግ አባላት ላይ ሂሳዊ ትችት ይሰነዘራል በሚል የእርግማንና የውግዘት ናዳ የሚያወርደው ወገን ቁጥሩ ቀላል ባይሆን አይገርመኝም።

የሃይማኖታዊ እምነት ተልእኮና ሃላፊነት በፈጣሪ በሚታገዝ ተግባራዊ የጋራ ጥረት ጤናማና ስኬታማ የሆነ ትውልዳዊ መሠረትና ቅብብሎሽ (ትስስር) እውን እንዲሆን በማድረግ የምድራዊው ህይወት ስኬት ከሞት በኋላ ተስፋ የሚደረገውን ህይወት መውረሻ እንዲሆን ማድረግ ካልሆነ ሌላ ምን?

በእውነት ስለ እውነት ከተነጋገርን የእውነተኛ ሃይማኖታዊ እምነት ምንነትና እንዴትነት የሚገለፀው እውነት፣ ፍትህ፣ ርትዕ፣ ነፃነት፣ እኩልነት፣ መተሳሰብ፣ ፍቅር፣ መታመን ፣ መተማመን፣ ወዘተ ወይም የእነዚህ ወርቃማ እሴቶች ተቃራኒ የሆኑትን መፀየፍና መታገል መሆኑንና የከሞት በኋላ ህይወት ዋስትናውም ይኸው እንደሆነ የምንግባባ ይመስለኛል። እኛ ግን ለዘመናት ከመጣንበትና ከስድስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ ለመግለፅ በሚያስቸግር ሁኔታ ተዘፍቀን ከምንገኝበት ግዙፍና መሪር እውነታ አንፃር ስንታይ እንኳንስ አርአያነት ያለው ትውልዳዊ ሃላፊነትን ልንወጣ ትውልድን ግራ ከማጋባት አዙሪት ሰብረን ለመውጣት ትርጉም ያለው ሥራ አልሠራንም።

ምንም ስፋትና ጥልቀቱ ሊለያይ ቢችልም ሁሉም ዓይነት የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች፣ አስተማሪዎች እና እንደ ድርሻቸው መጠን ተከታዮችም ከውድቀቱ አዙሪት ነፃ አይደለንም፤ ልንሆንም አንችልም።

ረቂቅ የሆነውን የፈጣሪ ባህሪ  የሚያስተምረን ከሞት በኋላ ህይወትን (life after death)ተስፋ የማድረግ እምነት እንደ ተጠበቀ ሆኖ የዘመን ጠገብ ፖለቲካ ወለድ የመከራና የውርደት ቀንበር ሰለባ የሆነውን እና ከስድስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ ለመግለፅ በሚያስቸግር ሁኔታ የግፍ ግድያ እና የአካልና የአእምሮ፣ የመፈናቀል፣ የፍፁም ርሃብ፣ የበሽታ፣ ልክ የሌለው ድንቁርና (የቁም ሞት) ሰለባ እየሆነ ያለውን ትውልድ በመታደግ ገንቢ፣ ፅዕኑና ዘላቂ የሆነ ትውልዳዊ መሠረት የመጣል እና አስፈላጊውን ክትትልና እገዛ ለማድረግ የመቻል ፈቃደኝነት፣ ዝግጁነትና ተግባራዊነት በራሱ የከሞት በኋላ ህይወት መንገድ መሆኑን ለመረዳት የዓለማዊም ሆነ የቲዎሎጅ ሊቅነትን አይጠይቅም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ማን ሆነና ጠብ አስተናባሪው! - አሁንገና ዓለማየሁ

አዎ! በእውነት ስለ እውነት ከተነጋገርን ሃይማኖታዊ እምነትን የልዕለ ሃይልነትን ትርጉም የሚያጎናፅፈው  እና ትውልድን እንዲታደግ የሚያደርገው ቃል እና ተግባር  ሲዋሃዱ ብቻ ነው።

ባለጌ ፣ ሴረኛ፣ ሸፍጠኛና ጨካኝ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ገዥ ቡድኖች የመከራና የውርደት ዶፍ እየወረዱበት ባለ እንደኛ አይነቱ አገር ሲሆን ”በፈጣሪ አምሳል የተፈጠረውን ከክፉና ከክፉዎች ሁሉ ነቅተን እንጠብቀው ዘንድ ከፈጣሪ በአደራ የተሰጠንን ህዝባችንን ልቀቁት” በሚል ግልፅና ቀጥተኛ የሃይማኖት አርበኝነት ስሜት  ፣ ይህ እንኳ ባይሆን ቢያንስ ግልፅና ፅዕኑ በሆነ ቁመና እና አቋም ቁጣንና ተግሳፅን ለማሰማት የሞራል ልዕልና የሚገደው የሃይማኖት መሪና አስተማሪ ስለ የትኛው የከሞት በኋላ ህይወት መውረሻ መንገድ እንደሚሰብክ ለመረዳት ያስቸግራል።

ከሞት በኋላ ተስፋ የምናደርገው ህይወት እናምናለን እና እግዚኦ በማለት ብቻ የሚወረስ ዓለም  ሳይሆን ትውልድን በመታደግና መልካም የሆነና ገዥዎች በተፈራረቁ ቁጥር የማይናወጥ ትውልዳዊ ድልድይ በመዝርጋት ብቻ እንደሆነ በግልፅና በቀጥታ መንገርና መነጋገር ካልቻልን ትውልዳዊ የውድቀት አዙሪቱ መቀጠል ብቻ ሳይሆን እንዳልነበርን ሊያደርገንም  ይችላል። ፈጣሪ በሰጠን አእምሮና አካል ተጠቅመን ከገዛ ራሳችን ልክ የሌለው ውድቀት ሰብረን ለመውጣት ሳንችል ቀርተን እንዳልነበርን የሚያደርግ ፈተና ቢገጥመን “የፈጣሪ መልካም ፈቃድ ባይሆን ነው” የሚል የሰበብ ድሪቶ መደረት በፍፁም የእውነተኛ አማኝነት ምንነትና እንዴትነት አይደለም።

በገዛ ምድሩ (አገሩ) ገፅ ላይ እና ከርስ ውስጥ ያሉ ልዩ ልዩ ሃብቶችን እየተጠቀመ እና ለዚህም ፈጣሪውን  እያመሰገነ በነፃነት፣ በፍትሀዊነት፣ በእኩልነት፣ በመከባበር፣ በመተሳሰብ፣በሰላም ፣ በፍቅር፣ በፍስሃ/በደስታ ፣ወዘተ ይኖር ዘንድ  ከረቂቅ አእምሮና ብቁ አካል ጋር  በአምሳሉ የተፈጠረን ትውልድ  ህገ መንግሥታዊ በሆነ የጎሳ አጥንት ስሌት ፣ የጥላቻ፣ የመለያየት፣ የመናቆር፣ የመጠፋፋት፣ ወዘተ ፖለቲካ ደዌ መርዘው እጅግ ውድ የሆነውን የዛሬና የነገ እጣ ፈንታውን በእጅጉ ሲያበላሹበት ከተለመደው ድርጊት አልባ ስብከት አልፎ የማይቆጣና  አስፈላጊ ከሆነም ዋጋ ለመክፈል ፈቃደኛና  ዝግጁ ያልሆነ የሃይማኖት አባትና አስተማሪ ስለ የትኛው ከሞት በኋላ ህይወት እንደሚሰብከን አላውቅም።

ፈጣሪውን እያመሰገነ ጥሮና ግሮ በነፃነት፣ በፍትህ፣ በእኩልነት፣ በፍቅር ፣ በሰላም፣ በመተሳሰብ፣ በመተባበር፣ በደስታ ይኖር ዘንድ በፈጣሪ አምሳል የተፈጠረን ትውልድ (ሰብአዊ ፍጡር) ከመታደግ የበለጠ ከሞት በኋላ ህይወት መውረሻ መንገድ የትኛው ነው?

አገሩና ወገኑ ፈፅሞ ማወዳደሪያ የሌለው ፖለቲካ ወለድ የመከራና የወርደት ዶፍ ሰለባ መሆኑ አስቆጥቶት መሪር ጩኸቱን ለዓለም ሊያሰማ አደባባይ ከሚወጣ የዲያስፖራ ወገኑ ጎን ቆሞ ክፉዎችንና ድርጊታቸውን ለመገሰፅና ለማውገዝ የሞራል ግዴታ የማይሰማው የቲወሎጅ ምሁር (ዶ/ር) ፣ የአገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና መሰል የቤተ ክርስቲያን ወይም የቤተ ፀሎት ወይም የመስጊድ አገልጋይ ነኝ ባይ ስለ የትኛው የከሞት በኋላ ህይወት መውረሻ መንገድ ነው የሚሰብከን?

ተጨማሪ ያንብቡ:  "አንድ ሄክታር መሬት በ1 ፓኮ ሲጋራ ዋጋ መቸብቸብ ራዕይ ነው?" - የተስፋዬ ገ/አብ ቃለ ምልልስ

አገር ቤትስ ቢሆን “የበጎቻችን (የወገኖቻችን)  ፍፃሜ ያልተገኘለት የግፍ ግድያ  እና የቁም ሰቆቃ ይብቃ” ለማለት ወኔው የከዳው የሃይማኖት መሪ፣ አስተማሪ፣ ባለ ሌላ ማእረግ አገልጋይና አማኝ በንፁሃን ደምና የቁም ሞት  ጩኸት በተከበበ ቤተ ክርስቲያን፣ መስጊድ፣ ቤተ ፀሎት፣ አዳራሽና አደባባይ እየታደመና አሸብራቂ በሆኑ ዝግጅቶች ራሱን እየደለለ የትኛውን የከሞት በኋላ ህይወት መንገድ ነው ተስፋ የሚያደርገው?

የራሱን ተዋንያን አሰልጥኖና አሰማርቶ ሁለንተናዊ የህይወት ምስቅልቅል ያስከተለበትን የጨካኝ ፖለቲካ ነጋዴዎች ሥርዓት አስወግዶ የሚበጀውን ሥርዓት እውን ለማድረግ ሲያቅተው ናላው የዞረን የአገሬ ሰው “የአያሌ አጋንንት ማደሪያ ሆነሃል/ሻል” በሚል ይበልጥ አቅሉን/ሏን (አእምሮውን/ዋን) እያሳተ “መንፈስ ቅዱስ አድሮብኝ ነው” በሚል የሚነግድ መምህር ወይም አባ ተብየ ስለ ከሞት በኋላ  ህይወት ሲሰብከን  መታዘብ ባያስገርም እንኳ አያሳዝንም?

እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት የሰብእና ቀውስ የተጠናወተው ሰው የገዳይና አስገዳይ ገዥ ቡድኖች አማካሪና ግብረ በላ በመሆን ሃይማኖትን ጨምሮ በእጅጉ ሲያጎሳቁልና ሲያዋርድ ቢያንስ ነውር ነው ብሎ ከምር ከመቆጣትና ከመገሰፅ ይልቅ ይባስ ብሎ የእርሱን (የዳንኤልን) ተላላኪነትና መልእክት የሚቀበል ፓትርያርክ ወይም ሊቀ ጳጳስ  ወይም ጳጳስ ስለ የትኛው ከሞት በኋላ ህይወት እንደሚሰብከን ለመረዳት አይቸግርም እንዴ ?

እናም ከዚህ አይነት ዘመን ጠገብ፣ ሁለንተናዊና አስከፊ የውድቀት አዙሪት ብቸኛው መውጫው መንገድ ለዘመናት ሥር የሰደደውንና እጅግ አደገኛ ሆኖ የቀጠለውን የፖለቲካ ሥርዓት (ካንሰር) አስወግዶ በዴሞክራሲያዊ ሽግግር  እውነተኛና ዘላቂ ወደ ሆነ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት  መሸጋገር  ነው። ለዚህ ደግሞ የአማራ ፋኖ እና ሁሉም  እውነተኛ ነፃነት፣ ፍትህ፣ ሰላምና የጋራ እድገት  ፈላጊ ወገኖች እያካሄዱት ያሉት ተጋድሎ ግቡን ይመታ ዘንድ አስፈላጊውንና ገንቢውን ሂሳዊ ድጋፍ በማድረግ የመከራና የውርደት ዘመንን የማሳጠሩ ጉዳይ ለነገ የሚባል መሆን የለበትም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የ4ኛ ዓመት ተማሪዎች በግድ ዩኒቨርሲቲው እንዲለቁ ተደረገ

ያም ሲሆን ሃይማኖታዊ እምነት ከርካሽና አደገኛ የፖለቲካ ሰለባነት ነፃ ወጥቶ የምድራዊው ህይወት መፅናኛ እና  ተስፋ የምናደርገው የከሞት በኋላ ህይወት መውረሻ መንገድ የሚሆነው።  

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share