እግዚኦታችን አልሰምር እያለን የተቸገርነው ለምንድን ነው? – ጠገናው ጎሹ

መቸም ሃይማኖታዊ እምነትን ያህል ለስሜት እጅግ ቅርብ (very sensitive) የሆነን ጉዳይ የሂሳዊ አስተያየት ርዕሰ ጉዳይ ማድረግ ለብዙ አማኝ ወገኖች የማይመች ብቻ ሳይሆን ሃጢአትን እንደ መጋበዝ ሆኖ ሊሰማቸው እንደሚችል በሚገባ እገነዘባለሁ። የርዕሰ ጉዳዬ ይዘት (ትርጉም) ለዘመን ጠገቡ እና ከስድስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ እንኳን ለማመን ለመስማትም በሚከብድ ሁኔታ ለቀጠለው ፖለቲካ ወለድ ግዙፍና መሪር መከራና ውርደት ከዳረጉን ምክንያቶች አንዱ ይኸው ተግባር አልባ እግዚኦታችን ነውና ለሰማያዊውም ሆነ ለምድራዊው ህይወታችን ጤናማነት የሚበጀንን ሆነንና አድርገን እንገኝ ለማለት እንጅ እውነተኛው አምላክ ለበጎ ነገር የምናስበውንና የምናደርገውን ይባርክልን ዘንድ እግዚኦ ማለት  አያስፈልግም ማለት አለመሆኑ ግልፅ ይሁንልኝ።

እርግጥ ነው በገሃዱ ዓለም ለገጠመን እና እየገጠመን ላለው የመከራና የውርደት ዶፍ ዋነኛ ምክንያት (root cause) የሆነውን የእኩያን ገዥ ቡድኖች ፖለቲካ ሥርዓት በተደራጀና በተቀናጀ ሁኔታ መጋፈጥና እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን አምጠን ለመውለድ ሲሳነን የሰበብ ድሪቶ መደረቱ የሚቀናን በመሆኑ የሃይማኖታዊ እምነት ሃይለ ቃላትንም ከገሃዳዊው ግዙፍና መሪር እውነት እየሸሸን ለመደበቂያነት የመጠቀም (የማዋል) ክፉ አባዜ ከተጠናወተን አያሌ ዘመናት አስቆጥረናል።

በእጅጉ የሚሳዝነው ጉዳይ ደግሞ የሃይማኖት መሪዎችና ሊቃውንት በጎቻቸውን ከነጣቂ ተኩላ መጠበቅ እንደሚኖርባቸው እረኞች ሰብአዊ ማንነታችንና ምንነታችን በሚፈታተን ግዙፍና መሪር እውነታ ዙሪያ ከመዞር አልፈው የእኩይ ፖለቲካ ሥርዓት ዘዋሪዎችን (ጠርናፊዎችን) በግልፅና በቀጥታ ለመገሰፅ የሞራል ልዕልና ሲገዳቸው መታዘብ ነው ። ይህ ህሊናውን የማይረብሸው እውነተኛ ፍትህና ነፃነት ፈላጊ የአገሬ ሰው የሚኖር አይመስለኝም።

እናም እግዚኦታችን የሚፈለገውን ውጤት ያላስገኘልን የፈጣሪ ቁጣ ወይም ያለመታደል ሆኖብን ሳይሆን ሃይማኖታዊ እምነትን ከትክክለኛ እሴትነቱ (ትርጉሙ) እያወረድን የዘልማድ አይነት ድግግሞሽ ስላደረግነውና ይህ ደግሞ ፈጣሪ ከሌላው እንስሳ ሁሉ ለይቶ የረቂቅ አእምሮና የብቁ አካል ባለቤት አድርጎ የፈጠረበትን ዓላማ በአግባቡ ለመወጣት አለመቻላችን ነው የሚያሳየው።

“እግዚኦታችን ሠርቷል እንጅ ለምን አልሠራም?” በሚል ሊሞግቱና ሊያሳምኑ የሚፈልጉ ወገኖች ቁጥር ቀላል እንደማይሆን እረዳለሁ። ይህንን ጥያቄ ለመመለስ ከላይ የገለፅኩትን  በሌላ አገላለፅ እደግመዋለሁ። አዎ! ለዘመናት ከመጣንበትና አሁንም እጅግ አስከፊ በሆነ ሁኔታ ተዘፍቀን የምንገኝበትን እውነታ እና ከተግባር ጋር ያልተገናኘውን እግዚኦታችንን ትክክለኛና ገንቢ በሆነ ፀፀት (ቁጭት) ካላየነውና ከምር ካልመረመርነው በስተቀር መውጫ መንገድ የለንምና በየቤተ እምነቱ በምንሰግደው ስግደት፣ በየአደባባዩና  በየአዳራሹ በምናነበንበው እግዚኦታ፣ በምንዘምረው ዝማሬ፣ በምናሸበሽበው ሽብሸባ፣ በምንለብሳቸው ፀአዳ አልባሳት ፣ በምንቀኘው ቅኔ፣ በምናሿሿው ፀናፅል፣ በምንጎስመው ከበሮ፣ በምንፆመው ፆም፣ በምናዥጎደጉደው ፀሎተ ምህላ፣  ወዘተ ብቻ  ሰማያዊውንም  ሆነ ምድራዊውን ህይወት የተሳካ ማድረግ አይቻለንምና ቆም ብለን ራሳችንን  መጠየቅ ግድ ይለናል ። ከተግባር ውሎ ጋር የተቆራኘ ተማፅኖን/እግዚኦታን  ይበልጥ የመለማመድ ሃይማኖታዊ ማንነት በፈጣሪ አምሳል የተፈጠርንበትን ማንነትና ምንነት ሙሉ ያደርገዋልና።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ፓትርያርኩ ከመንግሥት ጥገኝነት ነፃ ለመኾን እንደማይችሉ ያምናሉ

 

ለሰማያዊውም ሆነ ለምድራዊው የህይወት ስኬታማነት የሚበጅ መፍትሄ መፍጠርና ማበጀት ካለብን የሚከተሉትን ጥያቄዎች ከምር መጋፈጥና መመለስ ይኖርብናል፦ 

·         ለመሆኑ ስንቶቻችን እንሆን በገሃዱም ሆነ በሃይማኖታዊው ዓለም ወይም በሁለቱም ተገቢና መልካም ነው ብለን የምናስበውና የምናደርገው ነገር እንደምናስበውና እንደምናደርገው መሆኑን ወይም አለመሆኑን በአግባቡ በመገምገም የመሆን ወይም ያለመሆኑ (የመሳካት ወይም ያለመሳካቱ) ምክንያት ምን እንደሆነና ማን እንደሆነ ለመረዳት ከምር የሆነ ጥረት የምናደርገው?

·         ስንቶቻችን ነን ያልተሳካው ነገረ ሥራችንን ያልተሳካበትን ምክንያት በትክክል ተረድተን የጎደለውን ለማስተካከል እና የተሳካውን ደግሞ ይበልጥ የተሳካ ለማድረግ ተገቢና ወቅታዊ ጥረት የምናደርገው?

·         ስንቶቻችን ነን ደጋግመን የወደቅንበትን መሠረታዊ ምክንያት በቅጡና በቅንነት አጢነን የራሳችንን ሃላፊነት ከመውሰድና ተገቢውን ከማድረግ ይልቅ ሁሉን ነገር የፈጣሪ ቁጣና ቅጣት እያደረግን (ድርጊት አልባ እግዚኦታ እያስተጋባን) ፈጣሪን ጨምረን የገዛ ራሳችን አስከፊ የውድቀት አካል በሚያደርግ አስቀያሚ አስተሳሰብ ውስጥ የምንቦጫረቅ?

·         ስንቶቹ የሃይማኖት መሪዎችና ሰባኪዎች ናቸው የፀሎትን (ለተደረገልን የማመስገንና መልካሙ ነገር እንዲደረግልን የመጠየቅን) ፣የፆምን (የሥጋ ፍላጎትን የመቆጣጠርና ለጤናማ ህሊና ተገዥ የማድረግን) ፣ የምህላን (እግዚኦ መሃረነ/አድነነ ብሎ የመማፀንን) ፣ የንስሃን (ከልብ ተፀፅቶ ከስህተት የመመለስን) ፣ ወዘተ ወርቃማ ሃይማኖታዊ እሴት ከተግባር አልባ መነባንብ ባለፈ በአርአያነት (ሠርቶ የማሠራት መሪነት) የሚነግሩን/የሚያስተምሩን/የሚያሳውቁን?

·         በአንድ በኩል እጆቻቸው በንፁሃን ደም ከጨቀዩ የቤተ መንግሥት ፖለቲከኞች ጋር እየተሻሹ እና በሌላ በኩል ግን ስለ ፆም፣ ስለ ፀሎት፣ ስለ ምህላ፣ ስለ ንስሃ፣ ስለ ፍቅር፣ ስለ ፍትህ እና ስለ ሰላም የሚሰብኩንን የሃይማኖት መሪዎችና ሰባኪዎች ተሳስታችኋልና ንስሃ ገብታችሁ በአርአያነት አደባባይ ላይ ተገኙ ብሎ እቅጩን መንገርና መነጋገር ለምንና እንዴት ተሳነንበእውን በዚህስ የሚቀየም እውነተኛ አምላክ አለ እንዴ?

·         ለመግለፅ የሚያስቸግር ፖለቲካ ወለድ የመከራና የውርደት ዶፍ እያወረዱ እግዚኦ ከሚያሰኙን ወንጀለኛ ፖለቲከኞች ጋር እየተሻሹ “እግዚኦ በሉ” ማለት ምን የሚሉት የሃይማኖት መሪነትና ሰባኪነት ነው?

·         የሩብ ምዕተ ዓመቱ ህወሃት መራሽ ፖለቲካ ወልዶ ያሳደገው የጎሳ አጥንት ስሌት አገዛዝና ከአስድስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ በተረኛ ኦሮሙማዊያን/ብልፅግናዊያን ጠርናፊነት ተሰምቶና ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ የመከራና የውርደት ዶፍ ማውረዱን በቀጠለበት በዚህ ወቅት የሃይማኖታዊ እምነት መሪነት ሃላፊነታቸውን ውድቀት አምነው በመቀበል ክፉ ገዥዎችን በአግባቡ ለመገሰፅ የሞራል ከፍታ የተሳናቸውን የሃይማኖት መሪዎች፣ ሊቃውንትና ሰባኪዎች በአግባቡ ተጠየቁ ማለት ለምንና እንዴት ሃጢአትና ድፍረት ይሆናል?

ተጨማሪ ያንብቡ:  አዲስ ዓመት - በነተበ ሥርዓት

·         ሸፍጠኛና ጨካኝ ገዥዎችን በግልፅና በአግባቡ ለመገሰፅ በቃላት መረጣ የሚጨነቁ የሃይማኖት መሪዎች ክርስቶስ የህይወት መስዋእትነት ለመክፈል የሚያስችለውን መሪር ተግባር እያሰበና ለዚያም እየተዘጋጀ ስለ ፆመው ዓቢይ ፆም ባስተላለፉት መልእክታቸው መከረኛውንና የዋሁን አማኝ  “ባለመፆምህና እግዚኦ ባለማለት ነው መከራህ የበዛው” ሲሉት “ምነው ከምትነግሩን (ከምትሰብኩን) ሆናችሁና አድርጋችሁ ብታሳዩኝ (show me, do not just tell me)” ቢባሉ ድፍረት ይሆናል እንዴ?

 

·         የቤተ ክርስትያኗ የሃይማኖት “አባቶች” ወይም “አባላት”ነን ያሉ እጅግ ጨካኝ ወገኖች  የሃጢአት ማምረቻ፣ ማከፋፈያ ፣ ገዳይና አስገዳይ የሆነውን የቤተ መንግሥት ፖለቲካ ጠርናፊ (አብይ አህመድን) በቅኔ እያንቆለጳጰሱ እና በመስቀሉ እያማተቡ ሲያሞካሹት “የመከረኛ ንፁሃን ነፍሶች ይጮሃሉና ነውር ነው” ለማለት ያልደፈረ የሃይማኖት መሪ ስለ ምን አይነት ፆም፣ ፀሎት፣ ምህላና ፅድቅ እየነገረን እንደሆነ ለመረዳት አይከብድም እንዴ?

 

·          መከረኛው (ጦም አዳሪውና የገዥዎች ግፍ ሰለባ የሆነው) የአገሬ ህዝብ ከሌላው የዓለም ህዝብ በተለየ ሃጢአተኛ ይመስል ፖለቲካ ወለድ መከራና ውርደት ሰለባ የሆነው በሃጢአቱ ብዛት እንደሆነ መስበክ ምን የሚሉት የሃይማኖት መሪነትና ሊቅነት ነው?

 

·         የገዛ ራሳችንን እጅግ አስቀያሚ የውድቀት አዙሪት በነፃነት ጥረንና ግረን እንኖር ዘንድ በራሱ አምሳል በፈጠረን እውነተኛ አምላክ ማላከክ ምን የሚሉት የሃይማኖት አባትነትና ሰባኪነት ነው?

 

·         መከረኛውን ህዝብ ለጦርነት፣ ለርሃብና ለበሽታ የዳረጉት ሴረኛና ጨካኝ ገዥዎች መሆናቸው እየታወቀ ለይቶ መገሰፅ ሲገባ በደምሳሳው አካላት ወይም ወገኖች ወይም ሁሉም ተፋላሚዎች ፣ ወዘተ በሚል የሰለቸ መግለጫ ማሰራጨትን እንደ ታላቅ ሃይማኖታዊ መሪነት ተልእኮ መቁጠር እንኳንስ ሰማያዊ ምድራዊ ወንዝን እንዴት ሊያሻግር ይችላል?

 

“ፆም ስለሆነ የህልውና፣ የነፃነትና የፍትህ ተጋድሎ ማድረጉን አቁሙና የገዳዮችና የአስገዳዮች መጫወቻ ሁኑ” የሚል አይነት እጅግ የወረደና አዋራጅ ሰባኪነትን እንኳን ለመቀበል ለመስማት አይከብድም/አያምም እንዴ?  እንዲህ አይነቱን ሰንካላ ምክንያት ባርኮ የሚቀበል እውነተኛ ፈጣሪስ አለ እንዴ? በጨካኝ ገዥ ቡድኖች ጨካኝ ሰይፍ እንደ ጎርፍ የሚወርደውን የንፁሃን ደም ከመታደግ የበለጠ ምን አይነት የፅድቅ  አርበኝነት አለና ነው “ለፆም ስትል እጅህን አጣጥፈህ ተቀመጥና የሬሳ ክምርህን ‘በክብር’ ወደ አፈር ለመመለስ ተዘጋጅ፤ እናም ትፀድቃለህ” ማለት ምን የሚሉት ሃይማኖታዊ ሰብእና ነው?

የሰው ልጅ ከሌሎች እንስሳት ተለይቶ ከማሰቢያ ረቂቅ አእምሮና ከብቁ አካል ጋር ከተፈጠረባቸው ዓላማዎች (ምክንያቶች) አንዱ ትናንት የመጣበትን ፍኖተ ህይወት (የአስተሳሰብና  የተግባር ሂደት)  ቆም እያለ ከምር በመመርመር አወንታዊ ጎኖችን ይበልጥ በማጎልበት (በማጠናከር) እና አሉታዊ ጎኖችን ደግሞ ወደ አወንታዊነት በመለወጥ የተሻለ ነገንና  በእጅጉ የተሻለ ከነገ ወዲያን እውን ለማድረግ የሚጥር መሆኑን ለመረዳት የሊቅነት ወይም የሊቀ ሊቃውንትነት እውቀትን አይጠይቅም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የበሻሻው ተወካይ ''--አገር ለማፍረስ ከፈልግን ማን ሊከለክለን---የሚያቆመንስ ምን ኃይል አለ?--''

ይህ መሠረታዊ እሳቤ ደግሞ ከዓለማዊው ብቻ ሳይሆን ከሃይማኖታዊ (ከመንፈሳዊ) እምነትና ተግባር ጋር በጥብቅ የተያያዘ (የተቆራኘ) ነው። ለምን? ቢባል የየራሳቸው የሆነና አንዱ የሌላውኛውን መሠረታዊ ተልእኮ፣ ዓላማና አሠራር መስመርን አልፎ አላሰፈላጊ ጣልቃ ገብነት ማድረግ የለበትም የሚለው መርህና ህግ እንደ ተጠበቀ ሆኖ ሁለቱም ከሰው ልጅ (ከማህበረሰብ) ሁለንተናዊ መስተጋብር ውጭ የሚታሰቡ አይደለምና ነው።

አዎ! ከሞት በኋላ ተስፋ የምናደርገው ህይወት የሚወሰነው በዚሁ ሁለገብ በሆነው ማህበረሰባዊ መስተጋብር ምንነት፣ለምንነት፣ እንዴትነት፣ እና ከየት ወደ የትነት እንጅ በአየር ላይ በሚንሳፈፍ አንዳች አይነት የማይጨበጥ መንፈስ ወይም ተአምር አይደለም። ይህንን ደግሞ አምላክ በክርስቶስ አማካኝነት ሥጋ ለብሶ በመወለድ፣ በማስተማር፣ በጥምቀት አማካኝነት ራሱን ገልጦ በማሳየት፣ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ በመሞት (ለእውነት፣ ለፍትህ ፣ ለፍቅርና ለሰላም ዋጋ በመክፈል) እና በመጨረሻም ሞትን አሸንፎ በመነሳት (የእውነትን፣ የፍትህን፣ የፍቅርንና የሰላምን አሸናፊነት በማረጋገጥ) አሳይቶናል።

በእውነት ስለ እውነት ከተነጋገርን አሁን ለምንገኝበት በእጅጉ ግዙፍና አስከፊ ለሆነ ሁለንተናዊ መከራና ውርደት የተዳረግነው ድንገተኛና ማስቀረት የማንችለው ፈተና ሆኖብን አይደለም። አለመታደል ወይም ከሌላው ህዝበ አዳምና ሔዋን በተለየ ሃጢአተኞች በመሆናችን ፈጣሪ በማያቋርጥ ቅጣት ሊቀጣን ስለ ፈለገም አይደለም።

አዎ እውነት ነው በማነኛውም የፖለቲካ ማህበረሰብ የእድገት ሂደት ሊያጋጥሙ የሚችሉ ጉልህ ስህተቶች እኛንም ያጋጠሙን የመሆኑ እውነትነት እንደ ተጠበቀ ሆኖ የረጅም ጊዜ አኩሪ የአገርነትና የሃይማኖት ታሪክ ባለቤቶች መሆናችንን ለማስተባበልና ለማጣጣል የሚፈልጉት የውጭ ትምክህተኛ ሃይሎች ብቻ ሳይሆኑ በዋናነት በገዛ ውድቀታችን ምክንያት ወደ የጎሳና የመንደር ማህበረሰብነት ያወረዱን  ገዥ ቡድኖችና ግብረ በላዎቻቸው ናቸው።

ከዚህ ሁሉ የሚከፋው ግን የንፁሃን የምድራዊውም ሆነ የሰማያዊ ህይወት የተሳካ ይሆን ዘንድ (የሰማያዊ ህይወት የሚወሰነው በምድራዊ ሥራ በመሆኑ ሁለቱ የሚነጣጠሉ አለመሆናቸው ሳይረሳ) ተልእኮና ሃላፊነት የተጣለባቸው የሃይማኖት ተቋማት በደካማ መሪዎች ምክንያት የፖለቲካ ወለድ ወንጀል ሰለባ የመሆናቸው መሪር እውነት ነው።

ከዚህ በእጅጉ ከተመሰቃቀለና አስከፊ ከሆነ ፖለቲካ ወለድ አዙሪት መውጫው መንገድ አንድና አንድ ብቻ ነው። ህልውና ፣ ነፃነት፣ ፍትህ፣ እኩልነት፣ መተሳሰብ፣ ሰላም፣ እና የጋራ ሥልጣኔና እድገት ለሚረጋገጥባት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እውን መሆን እልህ አስጨራሽ ተጋድሎ በማካሄድ ላይ ለሚገኙ ወገኖች ሁለገብ ድጋፍ ከማድረግ ውጭ የሚኖረው አማራጭ የመቃብር ውስጥ እና የቁም ሙትትነት መቀበል ነው።

ምርጫችን የመጀመሪያው እንደሚሆን ያለኝን ተስፋ እየገለፅሁ አበቃሁ!

 

 

4 Comments

  1. ወንድም ጠገናው፦
    እግዚዎታችን ያልሰመረልን ክልብና በሀቅ ታስቦበት ያልቀረበ የሰነፍ እግዚዎታ ስለሆነ ነው። እግዚዎ ስንል፣ የራሳችንን ድርሻ ሳንሠራ፣ በተሰጠን ራስ መፍትሔ ሳንፈልግ፣ እንደ እንሣት በቀላሉም ያገኘነውን እየጎሰጎስን፣ ሲደክመን እንደ እንስሣቱ እየተጋደን፣ በነጋታውም ለገጠመን ችግር አንድም መፍትሔ ሳንፈልግ፣ ነጋ ጠባ “እግዚዎ” መፍትሐኤ አምጣልን በሚል የእንስሣ አከል ባሕርይ በመለከፋችንና፣ መንግሥትም ተመሳሳይ ባሕርይ ስላለው ነው። የመንግሥትም ሆነ የ”ሊቃውንቱ” አሠራር ሣይንሳዊ ሳይሆን ሙሉ በሙሉ ልማዳዊ ነው። እንደዚህ ባይሆን ኖሮማ፣ የትምሕርት ሥርዓቱ ሲበሰበስ፣ ኢኮኖሚው ቅጥ ሲያጣ፣ የኑሮ ውድነቱና የዋጋ ግሽበቱ ጣራ ሲነኩ፣ የጤና አገልግሎቱ ሲዳቀቅ፣ የግብርና ማሣሪያችን የዛሬ 2500 ዓመት ያመጡልን ሲሆን፣ ድሕነት በአገራችን ሲነግስ፣ ድሀ ዜጎች እርስ በእርስ ሲናከሱ፣ “ሊቃውንቱ”ና መንግሥት መፍትሔ ይዘው ብቅ ይሉ ነበር። ዶክቶሬት ለአገር ችግር መፍትሔ ሊያስገኝ ካልቻለ ፋይዳው የት ላይ ነው? ለምንስ የድሀ ታክስ ይባክናል ? ትምሕርት ለአገር ዕድገትና ለብልጽግና ካልረዳ፣ የዩኒቬርሲቲ ምሩቅ መጻፍና ማንበብ ካልቻለና ቀጣሪ ካጣ፣ ብሎኬት በየመንደሩ እየከመሩ ዩኒቬርሲቲ፣ 2ኛ ደረጃ፣ የሙያ ት/ቤት አንደኛ ደረጃ ት/ቤት ገነባን እያልን ራስን ከማታለል “አቃተኝ” ብሎ ለሚችል ሥራውን መተው ይገባል። ዲሞክራሲያዊ ሥር ዓት ቢኖረን ኖሮማ ሕዝብ በሕጋዊ መንገድ ይባረር ነበር። ምርጫው ወይ የዕድገት መሣሪያ የሚሆን ት/ቤት መገንባት፣ አለዚያም ት/ቤትን የመሀይም መፈልፈያ ፋብሪካ ከማድረግ መዝጋትና ባጀቱን ወደ ግብርና ማዞር ነው፣ ባይዮን ወገኖቻችን በልተው ሊያድሩ ይችላሉ። ዛሬ ላይ ይህ ማታለል የሚደረገው እጅግ በተማሩ መሪዎች ነው።

    ታዲያ በጥንቃቄ አስበን ለአገራችን ሰላምና ዕድገት እናምጣ ካልን፣ 1ኛ/ ዛሬ ያለው የሁለት ጠመንጃ ነካሽ ቡድን ሕገ መንግሥት 9 ጎሣ አንግሦ የቀሩትን 74 የ9ኙ ተገዢ ስለሚያደርግ፣ 2ኛ/ ዛሬ ያለው መንግሥታዊ ሥርዓት ፌደራል ሳይሆን አምባ ገነን፣ ጎሠኛና አሐዳዊ በመሆኑ፣ 3ኛ/ ሶስቱን የመንግሥት ዘርፎች የእርስ በእርስ ቁጥጥር እንዲያደርጉ ባግባቡ ባለማዋቀሩ፣ 4ኛ/ አያሌ አንቀጾች ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓትና ለአገር ግንባታ ስለማይበጁ፣ 5ኛ/ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ሊገነባ ስለማይችል፣ 6ኛ/ሽማምንቱ ሕግ ማክበርም ሆነ ማስከበር የሚባል ያልፈጠረባቸው በግልጽ ሕግና ሥርዓት የሚቀጡ፣ ከሥልጣን የሚባረሩና ለፍርድ እንዲቀርቡም ባለማድረጋችን፣ ሕገ መንግሥቱ በ1987 በኦነግ፣ ሕወሐትና በምርኮኞቻቸው ጭብጨባ ብቻ መደንገጉ አክትሞ፣ ሁሉም ወገኖቻችን ተወካዮቻቸውን መርጠው ለሕገ መንግሥት አርቃቂ ጉባዔ ልከው፣ በጋራ ውይይት ተረቅቆ በአገር አቀፍ ፓርላማና በክፍለ ሀገራትም ዲሞክራሲያዊ ፓርላማዎች መጽደቅ አለበት ። እዚህ ላይ የልሂቃን ድርሻ ረቂቅ ሕገ መንግሥት አዘጋጅቶ ለጋራ ውይይት በ’ዘሀበሻ” ላይ ቢቀርብ፣ ነገ የሕገ መንግሥት ጉባዔ ሲመሠረት በመጠኑ የበሰለ ረቂቅ ሕገ መንግሥት ይዞ የተፋጠነ ሥራ ሊሠራ ይችላል። የተለመደው እርስ በእርስ መወቃቀስ፣ መተቻቸትና ትረካ፣ ለግል ስሜት እርካታ ካልሆነ በስተቀር፣ ለምንጓጓለት የአገር ሰላምና ግንባታ ሂደት ብዙ ፋይዳ አይኖረውም። በዚህ ረገድ የአሜሪካው እምቢልታ የጀመረው የሚመሰገን ነው።

  2. ማንኛውም ሃይማኖት የሰው ልጅ ማታለያ የጥቂቶች መጠቀሚያ መሳሪያ ነው። በተለይ በሃበሻዋ ምድር ድርጊትና ቃል አልገናኝ ካሉ ዘመናት ቆጥረናል። በዚህም የተነሳ አንድ ሌላውን አልሰማ ብሎ ይኸው ዝንተ ዓለም ስንገዳደል እንገኛለን። ህዝባችን ከዘመን ዘመን የሽሽትና የመከራ ኑሮ እየኖረ ክራራይሶ ማለቱ ግብዝነት ነው። ተጾመ፤ ተጸለ፤ ተሰበከ ለውጥ የለም። እንዲያውም የሰው ክፋት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከፋና እየዘመነ በመሄድ ዛሬ የሩቅና የቅርብ ኪስ አውላቂዎች ተላላ የእምነት ሰዎችን ምን ያህል እንደሚዘርፏቸው በየወቅቱ እየሰማን ነው። የቆቅ ኑሮ ለሚኖረው ህዝብ ነው የራሳቸውን የምድር ኑሮ አሳምረው ከምሲን ነገር ለነገ የሌላቸው ዛሬ ላይ እጃቸው ላይ ያለውን ሽርፍራፊ ሳንቲም የሚነጥቁ ጭልፊቶች በእምነት ስም ህዝባችን የሚመዘብሩት።
    ባጭሩ የኢትዮጵያ ህዝብ እግዚኦታ አያስፈልገውም። ጊዜውን በማያድን ጸበል፤ ለማይረባ የዘይት ቢልቃጥ ያለ የሌለውን ከማባክን ይልቅ ራሱን መጠየቅ ያለበት ይህ ፈጣሪ የሚባለው የት እንዳለ ለማወቅ በጋራ ማፈላለግ ተገቢ ይመስለኛል። የነፍሰ ጡር ሆድ ቀዶ ጽንስ የሚያወጣ፤ ሰውን ዘቅዝቆ የሚሰቅል፤ በእግረኛ ላይ ሆን ብሎ መኪና የሚነዳ፡ ሴቶችን በጉልበትና በማታለል የሚደፍሩ ወስላቶችና ደም አፍሳሾች ለምን በምድሪት እንዳቆጠቆጡ ራስን መጠየቅ መልካም ነው። የሰማዪን ጉዳይ እዚያ ስንደርስ እንጠያየቅበታለን። በምድር ላይ ላለው ግፍና መከራ የሌሎችን እንባና ሰቆቃ እያዪ በሚስቁ የጊዜው ታጣቂዎችን ነው መጠየቅና መሞገት ያለብን። የችግራችን ሁሉ መፍትሄ በእጃችን ነው። የችግሩም ፈጣሪዎች እኛ ነን። የቆመን እያፈረሱ፤ ሰውን እያታለሉና በብሄርና በቋንቋ መንዝሮ ኡኡታ ማሰማቱ ገልቱነት ነው። የሰው ልጅ የሚመዘነው በሰውነቱ ነው። እኛ ባመነጨነው መከራና ሰቆቃ ፈጣሪ ምን አድርግ ነው የምንለው? ፈጣሪ የምናስብበት አእምሮ ሰቶናል። እልፍ ቤት እያቃጥልንና ገበሬው አርሶ እንዳይበላና እንዳያበላን ከቀየው እያፈናቀልን ረሃብ ገባ፤ በሽታ ተዛመተ የምንል ጉዶች! በብሄር ነጻነት ሰክረን ነጻ እናወጣሃለን የምንለውን ህዝብ እንደ ድፎ ዳቦ ከላይም ከታችም በእሳት እንዲጠበስ የምናደርግ ሙታኖች። ዘፈናችን በለው ያዘው ጥለፈው፤ ገዳይና ተገዳይ በወረፋ የሚሸኙበት የኢትዮጵያ ምድር የሰው ደም የማይጠግብ የመሸራደድ ፓለቲካ ከዘመን ዘመን የሚቆላለፍባት መዓት የማይለያት ሃገር ናት። እግዚኦታ እውነቱን ያጨልማል እንጂ ደምቆ እንዲታይ አያደርገውም። 3 ሺህ ዓመት ተለምኖና ተጸልዪ የተገኘው ትርፍ ምንድን ነው? መልሱ ምንም። ከክፋት ወደ ክፋት መሸጋገር ብቻ! ስለዚህ ወንድማችን ለምን ጸሎታችን አልሰመረም ላለው ጉዳይ የሚሰማ የለም። አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም። በዚህም በዚያም ሃገር በቀልና ባህር የተሻገረ እምነትን ግሳንግስ እየተጋቱ ራስን እንደማየት ለሆነው ሁሉ በፈጣሪ ላይ ማሳበቡ ተንጋሎ መትፋት ነው። ፈጣሪ 6 ሚሊዪን አይሁዶች በናዚ ጀርመኒ ሲርመጠመጡ የት ነበር?ጣሊያን መጻፍና ማንበብ በማይችሉ የሃገሬ ሰዎች ላይ በመርዝ ጢስ ሲፈጅ፤ 45 ቀን ሙሉ በጾምና በጽሎት ላይ የነበሩት አቡነ ጳውሎስን (የእስር ቤቱ ሃበሳ – አቶ አበራ ጀምበሬ እንደዘገቡት) ለምን ከደርግ የጥይት ሩምታ አላተረፋቸውም? ነጮቹ እንደሚሉት Living is easy eyes closed. ምንም አልጠይቅም፤ በደመ ነፍስ እስከኖርኩ ድረስ ለራሴ ብቻ ኑሬ ልለፍ ለምንል ግን የሃበሻዋ መሬት ለም መሬት ናትና ይመቻቹሁ። ለነቃ ሰው ግን ያለንበት ዘመን ራስን የሚያስፈትሽ፤ የአለም የፓለቲካ አሰላለፍን የሚመዝን፡ የጠባብ ብሄርተኞችን ቀረርቶና ድንፋታ አክ እንትፍ የሚያስብል መሆን አለበት። ሌላው ሁሉ የልጆች ጫወታ ያደረ እንጀራ ቁርስርስ አይነት ነው። ከዚህ በታች ባለው የግል ግጥም እሰናበታለሁ።
    ተው እግዚኦ ማለት ይቅርብን ልመና
    በዘመናት መሃል ተስለው አልቀሰው መንነው ተሰደው
    ዞረው ተመልሰው ባሉበት የሄድ ከጊዜ ጋር አብረው
    በመንበርህ አለህ በማለት ጠይቀው
    መልስ ስያገኙ ስለታቸው ሳይደርስ
    ስንቶች አንቀላፉ አይኖቻቸው ሳይደርቅ።

  3. ወንድም ጠገናውና ተስፋ፦
    አስቦ፣ አቅዶና ዋጋ ከፍሎ ችግርንን ለመቋቋም ከመሥራት ይልቅ ማለቃቀስ፣ መንጫጫት፣ ማጉረምረም፣ ማኩረፍ፣ መተቸትና መሰል ተግባራት ለሕልውና ትግሉ ፋይዳ ቢስ ናቸው። በምሥራቅ ሽኔ፣ በሰሜን ወያኔና ሳምሪ፣ በምዕራብ ሰው በላ የጉሙዝ ሽፍታ፣ ሱዳንና ሸኔ፣ በደቡብ በኦሮሞ አክራሪ ብሔርተኛና ሽኔ የተከበበ አማራ ክልል፣ በአያሌ ክልሎች እንደሰውና ዜጋ የመኖር መብት የላችሁም እየተባለ አማራ ሲታረድና ሲፈናቀል፣ መንግሥት መብት አስከብሮ ለአማራ ሕልውና ቀጣይነት ግድ ከሌለው፣ ለራስ ሕልውና መከበርና ራስን ማስከበር፣ ብሎም በአባቶቻችን እንደታየው ኢትዮጵያን መጠበቅ የሚቻለው በጠላት ላይ አጸፋዊ እርምጃ በመውሰድ ነው። አውሮጳ ናዚ ጀርመን ወርሮ ሲገድል፣ ሲያፈናቅልና ሌሎችን መንግሥታት ሲያሳድድ አጸፋዊ እርምጃ ባይወስዱ ኖሮ፣ ቁጭ ብለው ብቻ ቢጽልዩና ደም ቢያነቡ የዛሬዋ አውሮጳ አትኖርም ነበር። የተጠና ተግባር ድርሻን በማለቃቀስ መተካት ለሕልውና አደጋ ነው።

    ታዲያ ሁሉም ነፍጥ እንዲይዝ አይጠበቅም። ምሁር ወይም ሊቅ ነኝ የሚለው በአዕምሮውና ከት/ቤትና ምርምር ባካበተው ክህሎት መሰልፍ አለበት ። መሰዳደብና መወቃቀሱን ለድኩማን ትቶ፣ ምን ባደርግ ለሕልውና ትግሉ እረዳለሁ ብሎ፣ ፋኖ የሌለውን እንዴት ማሟላት እችላለሁ ብሎ ድርሻውን ማዋጣት አለበት ። ፋኖ የደረጀ ቤተ መጻሕፍት፣ ተሰባስቦ ስለ ፖለቲካ ሥርዓት መወያያ ጊዜ፣ የበሳል ጥናትና ምርምር ከባቢም ሆነ ጊዜ የለውም፣ ያለው በሰው በላ ትግል ላይ ነው። የትግሉ የመጀመሪያ ደረጃና የትግሉ ጊዜያዊ መቋጫ የሽግግር መንግሥት በአማራ ክልል ማቋቋም ነው፤ ለእዚያም ማቋቋሚያ ስልጡን ሥርዓት ሊኖረው ይገባል። የሽግግር ጉባዔ፣ የተለያዩ የሽግግር ኮሚቴዎች፣ የሽግግር አደረጃጀትና የሁሉም ማጠቃለያ የሽግግር መንግሥት መመሥረት ያሻል።

    የሽግግሩ መንግሥቱ ዛሬ ካለው ዝቃጭ የክልል መንግሥት በዲሞክራሲያዊነቱ፣ በሰባዊነቱ፣ በልማት አያያዙ፣ ወዘተ፣ የላቀ መሆኑን ማረጋገጥ ይገባል፤ አለዚያ የተከፈለው መስዋዕት ዋጋ ያጣል። ከሽሽግግር መንግሥት ወደ ቋሚ የተመረጠ መንግሥት መሸጋገሪያ አስተማማኝ ሥርዓትም መታቀድ አለበት ። ይህ ሁሉ ጥረት ዓላማው አንድም ለክልሉ የተሻለ መንግሥትና ሕይወት ለማምጣት፣ ሁለተኛም ለኢትዮጵያ ምሣሌ የሚሆን ሥርዓት ለመፍጠርና ወደምንመኛት ሙሉ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ከሌሎች ወገኖቻችን ጋር በሕብረት ሰመሸጋገር ነው። ክልሉ የአማራ ብልፅግና ሽታ ካለው፣ የተከፈለው መስዋዕት ታጥቦ ጭቃ ይሆናል። ታዲያ ጠገናውና ተስፋ በተጨባጭ ሊረዱ የሚችሉት ይህን ከነፍጥ ውጭ የሆነ ሥራ ለማሳካት፣ ሁሉም ኢትዮጵያውያን በእኩልነት፣ በመከባበርና በወንድማማችነት ሊያስተሳስር የሚችል በተስፋ የሚጠብቁት ሕገ መንግሥት በማርቀቅና ለአገራዊ ውይይት በማቅረብ፣ ለሽግግር ሥርዓት የሚበጅ ረቂቅ በማዘጋጀት ሰላም፣ አንድነትና ብልፅግና ለማምጣት ድርሻን በመወጣት ለጋራ ስኬት አስተዋጾ ማድረግ ይጠበቃል። ለዚያ ያብቃን ! መወቃቀሱና በሃይማኖት ላይ መፈላሰፉ የትም አያደርስም።

    • ቅማልን የት ትሄጃለሽ ቢሏት መተማ። ትደርሻለሽ ልብማ አለች ይባላል። ይመችህ ወንድሜ እኔ የዲሞክራሲ ነገር ሰልችቶኛል። ዲሞክራሲ ብሎ ነገር የለም። ለዚህም ይመስለኛል ፈላስፋው ፕሌቶ ዲሞክራሲን የጠላው። ጉዳዪ የአለቃ ልውውጥ በመሆኑ! አንተ የምታልማት ሃገር ለእኔ ጭራሽ አትታየኝም። የሚታየኝ የከፋ ጊዜ ብቻ ነው። የፈጠራ ወሬው የሚያናፍሰውን ሳይሆን በምድሪቱ ላይ ያለውም እውነታ የሚያመላክተው ምጽአትን ነው። ኢትዮጵያ ያበቃላት ወያኔና ሻቢያ የሃገር አለቆች ከሆኑ በህዋላ ነው። ሰው በዘሩና በቋንቋው በክልል ፓለቲካ ተወጥሮ ሃገር ገለ መሌ ማለት በሽታን ማራባት ነው። የሃበሻ ፓለቲካ ክፋት በሰውና በእንስሳት ላይ ብቻ ሳይሆን በፊደላትም ላይ የሚተኩስ የእብድ ፓለቲካ ነው። ያለፈ የአውሮፓን ፍትጊያ ከሃበሻው ዝንተ ዓለም መገዳደል ጋር ማገናዘብም የሰውን ሥነ ልቦና ካለመረዳት የመጣ ነው። ጭራሽ አንገናኝም። ባጭሩ የሃይማኖት ወይም የፓለቲካ ፍልስፍና ሳይሆን የእኔ ሃሳብ በፈጣሪና በሰይጣን ማላከኩን ትተን እራሳችን እንይ ነው። ሃይማኖት የመመዝበሪያ መሳሪያ ለመሆኑ አይንን ከፍቶ ማየት ነው። ስለዚህ ሃገራችን ፈጣሪ ረሳት፤ ጸሎታችን አልተሰማም። ምህላችን ባዶ ቀረ ከማለት ተፈጥሮ ያደለንን ጭንቅላት በመጠቀም ለምን 3 ሺህ ዓመት ሙሉ ህዝባችን በረሃብና በቸንፈር፤ ሰው ሰራሽ መከራ ባስከተለው ሰቆቃና መከራ ውስጥ ይዋኛል ብሎ መጠየቅ ማለፊያ ይመስለኛል። ሌላው ሁሉ የስማ በለው ወሬና የማይዳሰስ ጉዳይ ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share