ብፁዕ አባታችን አቡነ ሉቃስ ይፍቱን!

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)

የሉቃስ ወንጌል 12፡4 “ለእናንተም ለወዳጆቼ እላችኋለሁ፤ ሥጋን የሚገድሉትን በኋላም አንድ የሚበልጥ ስንኳ ሊያደርጉ የሚችሉትን አትፍሩ፡፡ እኔ ግን የምትፈሩትን አሳያችኋለሁ ከገደለ በኋላ ወደ ገሀነብ ለመጣል ስልጣን ያለውን ፍሩ፡፡” ይላል፡፡

መጣፉ “ሥራ የሌለው እምነት የሞተ ነው!” የሚለውን ተከትለው በዚህ ዓመት እምነታቸውን በግብር በማሳየት ላይ ያሉትና የቅዱስ ሉቃስን ሥም የወረሱት አቡነ ሉቃስ ከላይ በቅዱስ ሉቃስ ቁልጭ ብሎ የተቀመጠውን የመጣፍ ቃል በተግባር እያሳዩ ነው፡፡ አቡነ ሉቃስ ሥጋን የሚገድሉትን ንቀው ከገደለ በኋላ ገሀነብ ሊከት የሚችለውን አንዱን አምላክ ወይም ክርስቶስን እየፈሩ ነው፡፡ ሳጥናኤልን የፈራ ክርስቶስን የናቀ ነው፡፡ ክርስቶስን የፈራ ደሞ ሳጥናኤልን የናቀ ነው፡፡ ከሳጥናኤል ጋር ቆሞ ወይም ለሳጥናኤል ተላላኪ ሽማግሌ ወይም ግብር ገባሪ ሆኖ ክርስቶስን እወዳለሁ ማለት ሰው ከመግድልም የከፋ ኃጥያት ነው፡፡

“ጽንሱ ሲያድግ ነፍጠኛ ይሆናል” በሚል እርኩስ መንፈስ ሰክሮ የእርጉዝ ሆድ ቀዶ ጽንስ የሚገድል በደፈናው የሚታወቀው ሳጥናኤል ሳይሆን በሐሺሺ ጥንብዝ ብሎ የሰከረው ቀንዳም ሳጥናኤል ነው፡፡ አማራን በርሃብ እንጨርሰው በሚል ለፍቶና ማስኖ ያዘመረውን አዝመራና ክምር በእሳት የሚያቃጥል፣ ከብቶቹን በጥይት የሚገድል ባለ ቃልቻው ሳጥናኤል ነው፡፡ በሕዝብ ግብር በተገዛ ድሮን ሕዝብን የሚጨፈጭፍ ጭራቅ ቀንዳሙ ሳጥናኤል ነው፡፡ ሰውን በዘሩ እየለየ የሚጨፈጭፍ፣ ቤቱንና የእምነት ቦታውን የሚያቃጥል፣ የሚያሰድድ፣ የሥራና የትምህርት እድል የሚከለክል ከርስቶስን ከተራራ ላይ ሰቅሎ ሊፈትነው ተሞከረውም የከፋው ባለዛሩ ሰይጣን ነው፡፡

ከሰላሳ ዓመታት በላይ በተለይም ካለፉት አምስት ዓመታት ጀምሮ በኢትዮጵያ ላይ የወደቀባት ሳጥናኤል እነዚህን ፋሽሽቱ ጣሊያን እንኳን ያለደረጋቸውን ወንጀሎች የፈጠመ ነው፡፡ አቡነ ሉቃስ ድል የነሱት ይኸንን ሰይጣን ነው፡፡ አቡነ ሉቃስ ይኸንን መፈራት የሌለበትን ቀንዳም ሰይጣን በመስቀላቸው ደልዘው መፈራት ካለበት ከክርስቶስ ጉያ እንደገቡ የሰሩት ሥራ ምስክር ነው፡፡ እንደ አለመታደል ሌሎች ጳጳሳት ግን አሁንም ከዚህ ሰይጣን ጉያ ተለጥፈው ይኸንኑ ሰይጣን አንዴ ተቃውሞውን በማርገብ ሌላ ጊዜም “ሽማግሌ” በመሆን እያገለገሉት ነው፡፡ የክርስቶስን መስቀል ጨብጦ እንደዚህ ዓይነቱን ቀንዳም ሰይጣን ማገልገል የኃጥያቶች ሁሉ ቁንጮ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከዘረኛው ሰርዓት የሚጠቀሙ ኢህአዴግ ምን ያድርግህ? ሲሉ እንደ ሀገር ክህደት የሚቆጠር ወንጀል ነው! - በቶማስ ሰብሰቤ

“ሥጋን የሚገድሉትን በኋላም አንድ የሚበልጥ ስንኳ ሊያደርጉ የሚችሉትን አትፍሩ፡፡” የሚለው ትእዛዝ ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት በኢትዮጵያ እንደዚህ ዓይነት ሰይጣን እንደሚመጣ የተነበየ ይመስላል፡፡ “በኋላም አንድ ስንኳ የሚበልጥ ስንኳ ሊያደርጉ የሚችሉትን…” የሚለው ሐረግ ላይ ብናተኩር በኢትዮጵያ ላይ በገዥ መልክ የሰነፈነው ሰይጣን ሥጋ ከመግደል እንኳ የሚበልጥ አሰቃቂ ወንጀል ሰርቷል፡፡ የአማራ ዘር ለማጥፋት ሴቱንም ወንዱንም አምክኗል፡፡ ሰው ከገደለ በኋላ ዘቅዝቆ ሰቅሏል፣ አንገቱን ቆርጧል፣ በእሳት አቃጥሏል፣ በግንዲደር እየዛቀ ተአፈር ጨምሯል፣ መሬት ለመሬት ጎትቷል፣ ወደ ገደልም ወርውሯል፡፡ ይኸ ሰይጣን ዛሬ እመነታቸውን በሥራቸው ባስመሰከሩት አቡነ ሉቃስ በግልፅ ተገስጿል፡፡

ከመጽሐፈ መነኮሳት አንዱ የሆነው ማር ይስሐቅ ገፅ 106 ላይ “አቡነ” ኤርምያስ ስሙን የዘረፉትን ቅዱስ ኤርምያስን ከጠቀሰ በኋላ “ እግዚአብሔር ሳንፈራ ሳንበርድ ጸላታችንን (ሳጥናኤልን ማለቱ ነው) እንገጥመው ዘንድ ያዝዛልና” ብሎ “ሳይቀድምህ ቅደመው…ትወጋው ዘንድ መር ብለህ ቁንጮውን ያዘው”* እያለ ያዝዛል፡፡ ምንኩስናቸው የሚያዝዛቸው አቡነ ሉቃስ መስቀላቸውን ይዘው ሳይፈሩ ይኸንን ቀንዳም ሳጥናኤልን ገጥመውታል፡፡ የሳጥናኤልን ሥራ የሚጠላ ሰው ሁሉ ከአቡነ ሉቃስ ጀርባ ሊሰለፍ ይገባል፡፡ ሳጥናኤልን ማገልገል ብቻ ሳይሆን ሳጣናኤልን በመፋለም ላይ ካሉት አባቶች ጀርባ አለመቆምም በሰማይ ቤት በመለኮት፤ በምድር በታሪክና በትውልድ ሲያቃጥል ይኖራል፡፡

አቡነ ሉቃስ ሆይ፡- የኢትዮጵያ ሕዝብ ለአያሌ ዘመናት በእውነተኛ አባት ጥማት መንፈሱ እንደ በጋ ምድር ተሰንጥቆ ኖሯል፡፡ በምድር ጠብ የሚል የእውነተኛ አባት ዝናብ ጠፍቶ በሰማይ ያሉትን እነ አቡነ ጴጥሮስን፣ አቡነ ሚካኤልና መላከ ብርሃን አድማሱ ጀምበሬን እያነሳ ጉረሮን ለማርጠብ ጥሯል፡፡ በመጨረሻም አቡነ ሉቃስ የሚባል ዝናብ ወርዶ በውስጥም በውጪም ያለው ኢትዮጵያዊ በዋንጫ እየገደበ እየጠጣው ይገኛል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰሜን ወሎን ወደ“ደቡብ ትግራይ” ደቡብ ወሎን ደግሞ ወደ “ሰሜን ኦርምያ” የማጠቃለሉ ቅዠት (እውነቱ ቢሆን)

የእኒያ በአድዋ ታቦታቸውን ተሸክመው ጣሊያንን ያርበደበዱት ካህናት አምላክ፣ የእኒያ ምድሪቱም ሕዝቡም ለሳጣናኤል እንዳይገዙ ገዝተው ሰማእት የሆኑት የአቡነ ጴጥሮስ አምላክ፣ የእኒያ ከደብረ ሊባኖስ ገዳም ወጥተው ጣልያንን በሚኒሽር ያርበደበዱት እንደነ አባ ገብረየሱስ ያሉ መነኮሳት አምላክ፣ የእኒያ በአምስቱ ዘመን ፋኖዎችን እያደራጁ የእምነት ቦታቸውን ከመርከስ፣ ሕዝቡን ከባርነት ያወጡት የእነ መላከ ብርሃኑ አድማሱ ጀምበሬ አምላክ ዛሬም “የእርጉዝ ሆድ ለሚቀድ ሳጥናኢል አትገዙ!” ብሎ የሚገዝት አባት ስለሰጠን ለዘላለም ይመሰገናል፡፡ በአንጻሩ ሳጥናኤል አገሪቱን ሲያረክስና የደም አበላ ሲያደርግ ከሳጥናኤል ጋር የቆምን አለዚያም ያላዬ ያልሰማ መስለን እንደ ቅንቡርስ በልተን ለመሞት የቆረጥን ሆድ አምላኪዎች ብዙ ስላልን በያዙት መስቀል ጭንቅላታችንን ወቅረው ይኸንን የሆድ ቃልቻ አስጎርተው እንዲያስወጡልን ለምነናል፡፡

እምነትን ከሥራ ያዋሃዱ አባቶች ተጠምተን “ይፍቱን” እንኳ ሳንል ብዙ ዓመታት አሳልፈናል፡፡ እግዚአብሔር ምስጋና ይግባውና ዛሬ አባት ስላገኘን አቡነ ሉቃስ ይፍቱን ብለናል፡፡

እግዚአብሔር ሆይ! ኢትዮጵያን ከሳጥናኤል አላቀህ እንደ በፊቱ “የተናገርኩት ከሚጠፋ የወለድኩት ይጥፋ” በሚሉ ሽማግሌዎችና እምነትን ከሥራ በሚያዋህዱ የሃማኖት አባቶች ዳግም ትሞላት ዘንድ፣ እነ አቡነ ሉቃስም በእምነታቸው ጸንተው የበለጠ ብርታትን ያገኙ ዘንድ ጸሎታችንን ቀጥለናል፡፡ አሜን፡፡

 

*መጻሕፍተ መነኮሳት ማር ይስሐቅ ገጽ 106  ብርሃንና ሰላም እትም 1929 ዓ.ም

 

ታህሳስ ሁለት ሺ አስራ ስድስት ዓ.ም.

 

 

https://youtu.be/RlwtciRfhGs?si=fR66u2i5Vo6uryye

4 Comments

  1. ዳንኤል ክስረት ተባርሮም ክፉ ምግባሩ አልተወውም ማለት ነው? ጴንጤ ነው ወይስ ሱልሟል?

  2. እውነተኛ አባቶች ቢገኙ ይፍቱን ማለቱ ተገቢ ነው። ነገር ግን አቡነ ሉቃስ በቀድሞ ስም አብ ወልዴ በዋሺንግቶን ሲያትል ገብሬል ቤተ ክርስቲያን ንብረቱ በኔ ስም ካልሆነ ብለው ከአገልጋይ ከህናት፣ ዲያቆናት ፣ምዕመናን እና ጳጳሳት ጋር ተጣልተው የማይነጋገሩ ለራሳቸው እግዚአብሔር ፍታኛ የማይሉ ሰው በተገኘው አጋጣሚ ለኢትዮጵያ ገዳማት የበላይ አስተዳዳሩ የተሾሙ የአሜሪካ ዜጋ የሆኑ ሰው አጋጣውን በመጠቀም ሁለት ታቦት አቁሞ በጳጳስ ደርጃ ሳይሆን የመጨረሻ የተራውች ተራ የማይናገሩትን ስድብ፣ሰርቶ አዳሪ ወታደሩንም ሳይቀር ዘርህ ይጥፋ፣ጠንቋይ፣ ዘርህ ይበተን፣አድማ በታኝ አንተን መድኃኔዓለም ይበትንህ፣ ዘርህም ይጥፋ፤አመድ ትቢያ ሁን፣ የምተተኩስ ወታደር አይምሮህ ይሰወር፣ ወፍረሃል፣ሠብተሃል፣የበለሃው ጮማ ይበቃሃል፣ አፈር ብላ፣የወፈርክ ጋንድያ የመሳስሉትን በአውደ ምህረት ላይ ተሳዳቢ እና ረጋሚ እጂግ በጣም የወረደ መነኩሴ እንዴት ይፍቱኝ ይባላል? ወፈጥ ድንጋይ ወፈጥ ተብሎ ቢጠራ በፈቃዱ ቦታውን ስለማይለቅ በስልት እና በዜዴ ቦታውን እንዲለቅ ይድረጋል እንጂ በመስደብ ቦታውን አይለቅም ።እንድዚያም ሁሉ ጳጳሱ የደረደሩት ስድብ የአቢይን አስተዳደር ፈቀቅ አያደርግም ምክንያቱም የድንጋይ መንገሥት ነውና።ሁለት ታቦት አቁማ የስድብ ናዳ ማውረድ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በጣም ዝቅ አደረገ አማኞችንም አንገት አስደፊ ሆነ። በመሆኑም አቡነ ሉቃስ ይፍቱኝ ሳይሆን አስኪማውን አውልቀው በስድብ በረጋሚነት ኮሚሳርነታቸው እንዲቀጥሉ ይመከሩ።

    • አምባው በቀለ ከብዙ ጊዜ ጀምሮ ብዥታ ፈጥረህብን ነበር ዛሬ ጋንኤል ክስረት መሆንህን ደረሰንበት፡፡ በየጊዜው ያለ እረፍት የአንድነት ሃይሉን ስትናደፍ ነበር ዛሬ ግን ገሃድ ወጣህ፡፡ ምን ስድብህን ብታፋፋም ስለ አንተ አጀንዳ ይዞ ኦሮሙማ ተወያይቶበታል አይወዱህም አያምኑህም ታማኝነትህን ለማሳየት በጭንቅላትህ እንደ አርጋው በዳሶ ብትደንስም ስራህን ከቁም አይጽፉትም አንተም አልቆብሃል የጽሞና ጊዜ ውሰድ እጅ እጅ ብለሃል፡፡

    • አምባዉ በቀለ
      ሰለተጨፈጨፉት ህፃናት ሳተነፍሰ አባን ለማሳጣት ይጠቅመኛል ያልከውን ብቻ መርጠህ የጋኔል ክበፈትን ቆዳ ለብሰህ መጠህ።

      1. አብይ ድነጋይ ነው የምትለው ወሸት ነዉ። አባ እንዳሉት ሰይጣን ነው
      2. በዘዴ ማሰወገድ ብለሀ ከደሰኮርከዉ። ዘዴውን ታወቅ እሰቲ አምጣው። የማትናገረዉ ሆድሀ አንቆህ ነው?
      3. የዜግነት ጉዳይ ሰላነሳሀው? አንተሰ የየት አገር ዜጋ ነህ? አሜሪካኑ አባ ማትያሰ ሲሾሙ ይህንን አንስተሃል ወይሰ አሁን ጋኔል ክብረት ስትሆን ታየህ?
      4.አይሰማሙም ሰሰላልከው። ከሆዳም ካህናትና ካንተ አይነቱ ባንዳ ጋር እንዴት ይሰማሙ?
      5. ሰረዊቱን ሰደቡ ሰልከው። አንተ እምትቆረቆረው ለሚጨፈጭፋት ህዝብ ሳይሆን ለጨፍጫፊዉ ነው

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share