አዲሳባ ገንፍል!

addis ababa zehabesha
addis ababa zehabesha

እስከ መቼ ጥደው ያንፈቀፍቁሃል፣
ስንት ዘመን ቀቅለው ንፍርቅ ያረጉሃል፣
አዲሳባ ገንፍል እሳት በዝቶብሃል!

ተቤትህ አውጥተው መንገድ ጥለውሃል፣
የግዛትን ቀንበር በጫንቃህ ጭነዋል፣
ሲፈልጉ እንደ በግ ጎትተው ያስሩሃል፣
ሰውነትን ገፈው ግዑዝ አርገውሃል!
በራራ አዲሳባ ምንድን ይሰማሃል?

እንደ በሬ አፍነው አፍህን ዘግተዋል፣
ደንቆሮም ሊያደርጉህ ጆሮህን ደፍነዋል፣
አውረው ሊሸጡህ ዓይንህን ጋርደዋል፣
መብትህን ተገፈህ ስንት ዘመን ያልፋል?

ወገንህን ሕዝብህን በድሮን ፈጅተዋል፣
ለድሮኑ መግዣም ብር ያስገብሩሃል፣
እግርህን በእጆችህ ቁረጠው ይሉሃል፣
እንዲያው አዲሳባ ምንድን ይሻልሃል?

በቋንቋ ወረንጦ ሲነቅሱህ ኖረዋል፣
ጠርገው ሊያስወጡህም ቁማር ቆምረዋል፣
ፈተና የሚባል መጥረጊያ ሰርተዋል፣
አወይ አዲሳባ ምንድን ይበጅሃል?

ፈረስ ሲለጉሙት በኮቴው ያደማል፣
ዶሮ ለእርድ ሲጎተት በጥፍሩ ይጭራል፣
በሬ ለእርድ ሲጠለፍ በቀንዱ ይዋጋል፣
ያንተ ዝምታ ግን እግዚኦ! እግዚኦ! ያሰኛል!

ግለት ሲያሰቃየው ፈንድሻ ይንጣጣል፣
በከሰል ሲፈላ ቡና ቡልቅ ይላል፣
እሳት ሲበዛበት ሽሮ ተክ ተክ ይላል፣
አንተ ተቃጥለህም ድምጥን ዋጥ አርገሃል፡፡

በእሳት ሲፍለቀለቅ ውሀም ይፎክራል፣
ወደ ታች ነጥሮም እሳቱን ያጠፋል፣

ይበቃል! ይበቃል! አንድ በአንድ መቃጠል፣
ይበቃል! ይበቃል! በጅሎች መቀቀል፣
እሳቱን ለማጥፋት አዲሳባ ገንፍል!

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)
ታህሳስ ሁለት ሺ አስራ ስድስት ዓ.ም.

ተጨማሪ ያንብቡ:  አባይ ፈላ ጉዱ - በላቸው ገላሁን

1 Comment

  1. ትክክል ነው፡፡ በቋፍያለው አዲስ አበቤ ገንፍሎ መውታት አለበት፡፤ ያለቀቅ አልቆ የተረፈው ነጻነቱን ያረጋግታል፡፡ ከዘለአለም ማንቋረር ይድናል፡፡
    የአብይ አህመድን ቀደዳ ማዳመት አያስፈልግም፡፤ ከአብይ አህመድየሰለቼ መበጥረቅ ውስጥ ያሳቀችኝን አንዲት ነገር ግን ሹክ ልበላችሁ፡፡
    ፋኖ በርታ!!! በአማራ ክልል ውስጥ ከሚገኙት 167 ወረዳወችና 3429 ቀበሌወች ውስጥ 80 ከመቶው በፋኖ ቁጥጥር ስር ለመሆናቸው፡፡ ማረጋገቻው የአብይ አህመድ ሹመኞች በቦታውወቹ ላይ አለመገነታቸው ነው፡፤ ህዝቡ ይህንን ያውቃል፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ አብይ አህመድ መቀደድ ልማዱ ስለሆነ በክልሉ ውስጥ ሁሉም ወረዳወችና ቀበሌወች በመንግስት ቁጥጥር ስር ናቸው እያለ ያናፋል፡፡ ወንድ ከሆነ በቦታወቹ ላይ ሆኖ ማረጋገጫውን ያቅርብ፡፡ ወራዳ፡፡በቦታው ያለው ህዝብኮ ራሱ ይታዘበዋል፡፡ አይ ሀፍረተቢስነት!!!!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share