በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ሁለ-ገብ የኢኮኖሚ ዕድገት ለብሄራዊ ነፃነት መከበርና ለተሟላ ሰላም መስፈን ወሳኝ ነው!

ፈቃዱ በቀለ(/)

ህዳር 26 2023

 

በአገራችንም ሆነ በአብዛኛዎቹ የአፍሪካ አገሮች ያለው ትልቁ ችግር ወደ ውስጥ ያተኮረ በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ሰፋ ያለ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ እንዲሁም የሚያማምሩ ከተማዎችና መንደሮች መገንባትና፣ እነዚህም በተለያዩ የመመላለሻ ዘዴዎች መያያዝ እንዳለባቸው ያለመረዳት ነው። አንድ ህዝብ በአስተማማኝ የኑሮ ሁኔታ ሲኖርና፣ የሰለጠነና በሁሉም አቅጣጫ በምሁራዊ ዕውቀት መንፈሱ የዳበረ ሰፋ ያለ የህብረተሰብ ክፍል ካለ አንድ አገርና ህዝብ በቀላሉ በውጭ ኃይሎች ሊታለሉና ህዝቦቻቸውም ከውጭ በሚመጣ የተበላሸ ባህል ሰለባ በመሆንና በገንዘብ በመታለል የአገራቸውን ህልውና በፍጹም አይሸጡም።  እንደሚታወቀው አብዛኛዎቹ የአፍሪካ አገሮች በባሪያ ንግድ የተነሳና፣ በኋላ ላይም በቅኝ-ግዛት አስተዳደር ውስጥ በመውደቃቸው ወደ ውስጥ ያተኮረ በስራ-ክፍፍል ላይ የተመሰረተ ማህበረሰብ እንዳይመሰርቱ ተደርገዋል። የቅኝ ግዛት አስተዳዳሪዎች አፍሪካን እናሰለጥናለን ብለው ቢሄዱም ያደረጉት ነገር እስከዚያ ጊዜ ድረሰ የነበሩትን ዕድገቶችና የታሪክ ቅርሶች እንዳሉ ነው ያወደሙባቸው። አንዳንድ በማደግ ላይ የነበሩ ከተማዎችንና ቤተመንግስቶችን እንዳለ ነው ያፈራረሱባቸው። በተጨማሪም በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ የዕድገትና የስልጣኔ ምልክቶች የነበሩ የታሪክ ቅርፆችን እየነቃቀሉ ነው ወደ አዎሮፓ ዋና ዋና ከተማዎች ማጋዝ የጀመሩት። እነዚህ  ከብረታ-ብረት፣ ከዕብነ-በረድ፣ ከተለያዩ የዲንጋይ ዐይነቶችና ከእንጨት የተሰሩ የሚያማምሩ ቅርፃ ቅርፆች በአሁኑ ወቅት በየሙዚዬሞች ውስጥ በመቀመጥ በህዝብ የሚጎበኙ ናቸው። በዚህ የተነሳና የኋላ-ኋላም ከቅኝ-ግዛት ከተላቀቁና ነፃነታቸውን ተቀዳጁ ከተባሉ በኋላ በተዘዋዋሪ የቅኝ-ግዛት እንዲሆኑ ነው የተደረገው። የተለያዩ በነፃ ገበያ ስም ሳይንሳዊ ያልሆኑና ወደ ውስጥ ህዝባዊ ሀብት ሊፈጥሩ የማይችሉ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ብለው የሚጠሯቸውን ራሳቸው ባቋቋሟቸው የዓለም አቀፍ ተቋማት ብለው በሚጠሯቸው እያስገደዱ ነው ወደ ተግባርነት እንዲመነዘሩ ለማድረግ የበቁት። የነጩ የኢሊጋርኪ መደብ በማንአለኝበት መንፈስ በመወጠር አብዛኛዎቹ የአፍሪካ አገሮች  በራሳቸው ጥረትና በምሁሮቻቸው ጥናትና ክርክር ጠንካራ ኢኮኖሚና ማህበረሰብ እንዳይገነቡ  የዕድገቱን መንገድ ለመዝጋት በቅቷል። አንዳንዶች ከዚህ ዐይነቱ የስውር ቅኝ አገዛዝ ለመላቀቅ ጥረት ሲያደርጉና አንዳንድ ዕርምጃዎች ሲወስዱ የመንግስት ግልበጣ ሊደረግባቸው ችሏል። አንዳንዶች በራሳቸው ጓዶች እንዲገደሉ ለመደረግ በቅተዋል። ይህም የሚያመለክተው በምንም ዐይነት የነጩ ኦሊጋርኪ መደብ ጥቁር አፍሪካውያን ጠንካራና የበለፀገ ማህበረሰብ እንዳይገነቡ ቀን ከሌት እንደሚሰራና፣ ካስፈለገም በተዘዋዋሪ የርስ በርስ ጦርነት በማስነሳት የኋላ-ቀርነት ዘመኑ እንዲራዘም እንደሚያደርግ ነው። ዛሬ በተለያዩ የአፍሪካ አገሮች የሚካሄዱት የርስ በስር ጦርነቶች በመሰረቱ የውክልና ጦርነቶች ሲሆኑ፣ የሚካሄዱትም የእስላም አክራሪን ኃይል ለመዋጋትና የራስን የጂኦ ፖለቲካ ጥቅም ለማስጠበቅ በሚል ስም ነው።

 

ወደ አገራችን ስንመጣ ግን አገራችን ለጥቂት ጊዜያት ካልሆነ በስተቀር የቅኝ ግዛት ሰለባ ባትሆንም ህዝባችን ብሄራዊ ነፃነቱን ለማስከበር የሚያስችለው በሳይንስና በቴክሎጂ ላይ የተመሰረተ፣ የሚያማሩ ከተማዎችና መንደሮች፣ እንዲሁም እነዚህን የሚያያዙ ልዩ ልዩ የመገናኛ ዘዴዎች ባለመዘርጋታቸው ህዝባችንና አገራችን የመከበር ዕድል በፍጹም አላገጠማቸውም። ይህንን ዐይነቱን ጉድለት የተረዳ የተገለጸለት ምሁራዊ ኃይል ብቅ ማለት ባለመቻሉና፣ ጥቂት ተማርኩ ነኝ የሚለው የአሜሪካ ርዕዮተ-ዓለም ሰለባ በመሆንና የእሱም የጥፋት ድርጊት ተላላኪ በመሆን የአገራችን ብሄራዊ ነፃነት እንዳይከበርና፣ አልፎም በመሄድ አገራችን እንድትፈራርስ የማይሰራው ሴራ የለም። ይህ ዐይነቱ የመንፈስ ድክመትና ለውጭ ኃይል መገዛትና ብሄራዊ ነፃነትን በመሸጥ አገራችን በጠንካራ መሰረት ላይ እንዳትገነባ ማድረግ ከሁሉም ብሄረሰብ በተውጣጡ ኤሊቶች የሚሳበብ ሳይሆን ከተወሰኑ ብሄረሰቦች የተውጣጡ ኤሊቶች ዋና ተግባር ሊሆን በቅቷል። በተለይም ከአደሬ ብሄረሰብ፣ ከአማራው፣ ከትግሬና ከኦሮሞ ብሄረሰብ የተውጣጡና የመማር ዕድል ያገጠማቸው ኢሊት ነን ባዮች ንቃተ-ህሊናቸው በጣም ዝቅተኛ ስለሆነ ባለፉት አርባና ሃምሳ ዓመታት በአሜሪካን የስለላ መረብ ውስጥ በመካተት የዕድገትና የብሄራዊ ነፃነት ጠንቅ በመሆን ህዝባችንና አገራችን ፍዳቸውን እያዩ እንዲኖሩና እንዲዋረዱም ለማድረግ በቅተዋል።  ያም ሆነ ይህ ይህንን ጉዳይ ዘርዘር በማድረግና በማነፃፀር  ከህብረ-ብሄር ምስረታ አኳያ የብሄራዊ ነፃነትንና  የየዜጎችን መብት መከበር ጉዳይ ጠጋ ብለን እንመልከተው።

 

እንደሚታወቀው በ18ኛውና በ19ኛው ክፍለ-ዘመንም ሆነ ከዚያ ቀደም ብሎ ህብረ-ብሄሮች እንደዛሬው ዘመን በአንድ ግዛት ውስጥ ተጠቃለውና መለያ የሚሆናቸው የየራሳቸው ባንዲራ ሳይኖራቸው በነበረበት ዘመን ኃያል ነን የሚሉ መንግስታት ደካማ አገሮችን ጦራቸውን በማዝመት ነው በቀጥታ የሚወሯቸው የነበረው። በቀድሞው ዘመን አንዳንድ አገዛዞች በውጭ ኃይሎች ግዛቴ ተደፈረ፣ ተወረርኩም በማለት ህዝባቸውን በማስተባበር የወረራቸውን ኃይል መክተው ለመመለስ የሚጠቀሙበት ዘዴ በቀጥታ ከወረራቸው ኃይል ጋር በመፋለም ነው ብሄራዊ ነፃነታቸውን የሚያስከብሩት። በዚህ መልክ በቀጥታ የተወረሩ አገሮች አገዛዞች የተገለፀላቸው ከሆነ እንደገና ላለመወረር ሲሉ ቶሎ ብለው የሚወስዱት እርምጃ የተበታተነውን ህዝብና  በአንድ ማዕከላዊ አገዛዝ አልገዛም በማለት የሚያስቸግረውን የክልል አገዛዝ በመሰብሰብና በማታለል፤ እንዲያም ሲል በማሸነፍ ወደ ውስጥ ያተኮረ ሁለ-ገብ የሆነ የአገር ግንባታና ለሰፊው ህዝብ የስራ መስክ የሚከፍት ትናንሽና የማዕከለኛ ኢንዱስትሪዎችን በማቋቋም ነው አገራቸውን ዘመናዊ ለማድረግ የበቁት። ከዚህም አልፈው በመሄድ ህዝባቸውና ቀስ በቀስ እያደገ የሚመጣው የንዑስ ከበርቴው የህብረተሰብ ክፍል ብሄራዊ ስሜት እንዲያድርባቸውና አገራቸውንም በጋራ እንዲጠብቁ የሚወስዱት እርምጃ መንፈስን የሚሰበስቡና ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል የሚያስተናግዱ ከተማዎችንና መንደሮችን መገንባት ነው።  ከዚያም አልፈው በመሄድ ከተማዎችንና መንደሮችን በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች በማስተሳሰር የንግድ ልውውጥና እንቅስቃሴ እንዲዳብር ማድረግ ነው። በተጨማሪም እዚህና እዚያ ለመኖሪያ የሚሆኑ ቤቶችን መገንባት፣ የተለያዩ የትምህርት ዘርፎችንና የሙያ ማስልጠኛ ማዕከሎችን በማስፋፋትና፣  ክሊኒኮችንና የገበያ አዳራሾችን፣ እንዲሁም  ለሰፊው ህዝብ የመዝናኛ ማዕከሎችን በመገንባት አንድ ህዝብና ተከታታዩ ትውልድ ተከብረው የሚኖሩበት አገር ጥለው ያልፋሉ። ለሰፊው ህዝብ የሚጠቅሙና ግልጋሎትም የሚሰጡ የሰለጠኑ ተቋማት በመገንባት ማንኛውም ዜጋ ተጠቃሚ እንዲሆን በማድረግ ለህዝባቸው አለኝታ መሆናቸውን ያረጋግጣሉ። ተከታታይ አገዛዞችም በዚህ ዐይነቱ አገርን መገንባትና የህዝብ አገልጋይ መሆን መንፈስ ተኮትኩተው ስለሚያድጉ እነሱም በበኩላቸው አገራቸውን በተሻለ መልክ በመገንባት ለተከታታዩ አገዛዝ የሚሆን በቀላሉ ሊደፈርና በተለያዩ የውስጥ ኃይሎች በቀላሉ ሊረበሽ ወይም ሊናጋ የማይችል አገርና ማህበረሰብ ጥለው ያልፋሉ።

 

በዚህ መልክ በ19ኛው ክፍለ-ዘመን በቀጥታ በውጭ ኃይሎች ይደፈሩ የነበሩ እንደጀርመን፣ ጃፓን፣ የኋላ ኋላ ደግሞ ደቡብ ኮርያና፣ ከ1949 ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ ቻይና  እንደገና በውጭ ኃይሎች ላለመወረር ሲሉ እንደምንም ብለው በድል አድራጊነት ከወጡ በኋላ ተግባራዊ ማድረግ የጀመሩት በሁለ-ገብ የአገር ግንባታ ላይ በመሰመራት ነው አገሮቻቸውን በጠንካራ መሰረት´ ላይ ለመግንባት የቻሉት። ለዚህ ነው ጀርመን እስከ 1871 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ የውጭ ኃይሎች በመወረሯና ወደ ውስጥ ያተኮረ የአገር ግንባታ ማካሄድ ባለመቻሏ ይህንን  ድክመት የተረዱት የፕረሽያ ሞናርኪዎችና ሁለ-ገብ ዕውቀት ያላቸው ምሁራን ዋናውን ምክንያት በመፈለግና የሚያስቸግሯቸውን ኃይሎች ድል በማድረግና ሌሎችንም በማታለል በፈረንሳይ ላይ ድልን ከተቀዳጁ በኋላ በሙሉ ኃይል ወደ ውስጥ ያተኮረ ሁለ-ገብ የአገር ግንባታ ማካሄድ የጀመሩት። በተለይም ለዕውቀት ማዕከላዊ ቦታ በመስጠትና ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል የሚጠቅም ሁለ-ገብ የሆነ የትምህርት የጥገና ለውጥ በማካሄድና፣ በተለይም በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ ያተኮረ ትምህርት በማስፋፋት፣ ከዚህም በላይ ለኢንጂነሪንግና ለዕደ-ጥበብ ሙያዎች ከፍተኛ አትኩሮ በመስጠት ነው ጀርመን በአንድ ትውልድ ጊዜ ውስጥ እንግሊዝንና ፈረንሳይን ቀድማ ለመሄድ የቻለችው። ተግባራዊም በሆነው ሰፋና ጠለቅ ያለ የትምህርት የጥገና ለውጥ አማካይነት ነው ጀርመን በ20ኛው ክፍለ-ዘመን ሁለት-ሶስተኛውን የሚሆን የኖቭል ዋጋ ተሸላሚ ሳይንቲስቶችን ማፍራት የቻለችው።

 

ወደ አገራችን ስንመጣ ጣሊያን ሁለት ጊዜ ከመውረሩ በፊት ኢትዮጵያችን በተለያዩ የጎረቤት አገሮች ትደፈር ነበር። በጊዜው ህዝቡን የሚያስተባብር ማዕከላዊ ግዛት ባለመኖሩና በየክልሉም ፊዩዳላዊ አገዛዝች በመኖራቸው ይህ ዐይነቱ የውስጥ ሽኩቻ ለውጭ ኃይሎች ወረራ አመቺ ነበር። ይህንን ድክመት የተረዱት አፄ ቴዎድሮስ አሻፈረኝ የሚለውን ኃይል በሙሉ በማሸነፍ ነበር የድርጅትን አስፈላጊነት በመረዳት አገራቸውን የኢንዱስትሪ አብዮት ባለቤት ለማድረግ ከእንግሊዙ ሞናርኪ ጋር ይጻጻፉ የነበረው። በአንድ በኩል የጥገና ለውጥን አሻፈረኝ የሚለው ፊዩዳላዊ ኃይልና ሌሎች፣ በሌላው ወገን ደግሞ በእንግሊዝ መንግስት ተንኮለኛነት የተነሳ አፄ ቴዎድሮስ የተመኙትን አገርን በአስተማማኝ መሰረት የመግንባት ዕድል አላገጠማቸውም። በጊዜው አፄ ቴዎድሮስ ከእንግሊዙ ንግስት ከነበሩት ከንግስት ቪክቶሪያ ጋር ይጻጻፉ የነበረው ኢንጂነሮችን፣  የዕደ-ጥበብ ሙያተኞችን፣ የከተማ ግንባታ አዋቂዎችንና ሌሎችንም ለአገር ግንባታ ይጠቅማሉ የሚሏቸውን ሙያተኞችን እንዲልኩላቸው ነበር። ንግስት ቪክቶሪያና አገዛዛቸውም አፄ ቴዎድሮስ የጠየቁትን ሙያተኞች ከመላክ ይልቅ ሃይማኖትን የሚያስፋፉና የሚሰብኩ ቄሶችን  ነበር። በዚህ ድርጊት የተናደዱት አፄ ቴዎድሮስ የተላኩትን ቄሶችንና ሌሎችን ቀሳውስቶች በማሰር ነው ብረታ-ብረት እንዲቀጥቅጡና ልዩ ልዩ መሳሪያዎችንም እንዲሰሩ ያስገድዷቸው የነበረው።  በአፄ ቴዎድሮስ ድርጊት የተናደደችው እንግሊዝ ጦሯን በመላክ ነው አፄ ቴዎድሮስ በሰው ልጅ ከምገድል ይልቅ በማለት ራሳቸውን የገደሉት። አፄ ቴዎድሮስ ራሳቸውን ካጠፉ በኋላ አገርን በጠንካራ መሰረት ላይ መገንባቱ የታሪክ አጋጣሚ ሆኖ  የኋላ ኋላ በአፄ ምኒልክ ትከሻ ላይ ነው ሊወድቅ የቻለው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢትዮጵያን ገጽታ አደባባይ ያወጣው አውሮፕላን አብራሪ ሃይለመድህን አበራ

 

አፄ ምኒልክ እ.አ. አ በ1896 በአደዋ  በጣሊያን ላይ ድልን ከተቀዳጁ በኋላ ተግባራዊ ማድረግ የጀመሩት እርምጃ ቢያንስ ህዝባቸውን የሚያስተሳስርላቸውንና ብሄራዊ ስሜቱ እንዲያድር የሚያደረገውን አገርን የመገንባት የመጀመሪያውን እርምጃ ነው መውሰድ የጀመሩት። ትምህርት ቤቶችን መክፈት፣ ድልድዮችን ማሰራት፣ የብሄራዊ ባንክ መክፈትና ለመገበያያ የሚሆን በሁሉም ዘንድ ተቀባይነት የሚኖረው ገንዘብ አትሞ ማሰራጨት፣ የባቡር ሃዲድ ማሰራትና የፖስታ ቤት መክፈት ለህብረ-ብሄር ምስረታ የሚያመቹb  የመጀመሪያዎች  እርምጃዎች ነበሩ። ህብረ-ብሄር ለመመስረት የሚያስችሉ በየቦታው የተሰሩና የተገነቡ ከተማዎች ስላልነበሩና፣ በተለይም ወደ ደቡቡ የኢትዮጵያ ግዛት አብዛዎችም መሬቶች ጠፍ ስለነበሩና፣ በየቦታውም የተገለጸለት ወይም የተማረ ኃይል ባለመኖሩ አፄ ምኒልክም  ሀ ብለው መጀመር ነበረባቸው። ወደ ማዕከላዊ መንግስት አካባቢም ስንመጣ በሁለ-ገብ ዕውቀት የሰለጠነ ምሁራዊ ኃይል ባለመኖሩ የአፄ ምኒልክን ፍላጎትና ምኞት በመረዳት የማህበራዊ መሰረት በመሆን ምኞታቸውን ዕውን የሚያደርግ ኃይል ሊኖር ባለመቻሉ ኢትዮጵያን ዘመናዊ የማድረጉ ጉዳይ ሙሉ በሙሉ ሊሳካ አልቻለም።  ከተማዎችንና መንደሮችን በአስተማማኝ መሰረት  ላይ መገንባት አልተቻለም። የተዘረጋው የባቡር ሃዲድ ለውጭ ገበያ እንዲያመች በመሆኑ ለውስጥ ገበያ ዕድገት የሚያመቹ ልዩ ልዩ የመገናኛ ዘዴዎች ለመገንባት ባለመቻላቸውና፣ ይህንንም ተግባራዊ የሚያደርግ በኢንጂነሪንግ ሙያ የሰለጠነ የህብረተሰብ ኃይል ባለመኖሩ ለአንድ አገር ብሄራዊ ነፃነት መከበር አስፈላጊ የሆነው የአገር ውስጥ ገበያ ዕድገት አስፈላጊው አትኩሮ ሊሰጠው በፍጹም አልተቻለም። ከዚህም ጋር ተያይዞ ለብሄራዊ ገበያና ለብሄራዊ ሀብት መፈጠር በጣም አስፈላጊ የሆነው የማሺን ኢንዱስትሪ ስለማይታወቅና በዚህም የተነሳ ተግባራዊ ለመሆን ባለመቻሉ የአገራችን ህዝብ ከእጅ ወደ አፍ አልፎ ሊሄድ በማይችል የግብርናና የዕደ-ጥበብ ሙያ ነው ይተዳደር የነበረው። ይሁንና አፄ ምኒልክ ጥለው የሄዱት መሰረት ህዝባችን ብሄራዊና አገራዊ ስሜት እንዲያድርበት ለማድረግ  በቅቷል ማለት ይቻላል።

 

አፄ ምኒልክ ከሞቱ በኋላ አገርን በፀና መሰረት ላይ ለመገንባት የጃፓናዊ ዐይነት እንቅስቃሴ ቢኖርምና ቀስ በቀስም ምሁራዊ ኃይሎች ብቅ ቢሉም በሁለተኛው የጣሊያን ወረራ ምክንያት የተነሳ በ1920ዎች የነበረው የዘመናዊነት እንቅስቃሴ ሊዳፈን ቻለ። በጊዜው የነበረው ትንሽ ምሁራዊ ኃይል በጣሊያኑ ወራሪ ኃይል ደበዛው እንዲጠፋ ለመደረግ በቃ።  ጣሊያን ድል ከሆነና አፄ ኃይለስላሴ እንደገና ስልጣናቸውን ሲረከቡ ሁሉም ነገር በሳቸው ትከሻ ላይ የወደቀ ነበር ማለት ይቻላል። ጣሊያን ህዝባችንን እንደዚያ እየጨፈጨፈ፣ በሌላ ወገን ደግሞ ሊሰራ የሚችለውን የአገራችንን ህዝብ ከጣሊያኑ ጋር በማሰማራት በአምስት ዐመት ያህል ጊዜ ውስጥ ትላልቅ ከተማዎችን ለመገንባት ችሏል። አንዳንዶች ከተማዎችም በብዙ ሺሆች የሚቆጠርን ህዝብ ለማስተናገድ የሚችሉ የተሟላ የከተማ አገነባብና ተቋማት እንደነበራቸው የማይታበል ሃቅ ነው። ጣሊያንም አገራችንን ሲወር እዚህና እዚያ ኢንዱስትሪዎችን ተክሏል፤ መንገዶችንም ገንብቷል፤ የሬዲዮ ጣቢያም አቋቁሟል። ይሁንና እንግሊዞች አፄ ኃይለስላሴን ይዘው ከመጡ በኋላ የአገዛዙን ድክመት በመመልከት ጣሊያን የተከላቸውን ኢንዱስትሪዎችና የሬዲዮ ጣቢያዎች፣ እንዲሁም የአየር ላይ ባቡር ማስኬጃ የብረት ገመዶችን እየነቀለችና እያፈራረስች ነው ወደ ሌላ የቅኝ ግዛቶቿ ማጋዝ የጀመረችው። ይህም ማለት አፄ ኃይለስላሴ ኢትዮጵያን እንደገና ዘመናዊ ለማድረግ ሲፈልጉ ሀ ብለው መነሳት ነበራባቸው። በጊዜው የአገራችንም ዋናው ድክመት የውጭ ኃይሎችን አሻጥር የሚረዳ ሰፋ ያለ ምሁራዊና ብሄራዊ ባህርይ ያለው የከበርቴ መደብ አለመኖሩ ነው።  ከ1950ዎቹ ዐመታት መጀመሪያ ጀምሮ ትምህርት ቤቶች ቢስፋፉም፤ ኢንዱስትሪዎችም ቢተከሉምና፣ ሀኪም ቢቶችም ቢስፋፉና መንገዶችም ቢሰሩ፣ በተለይም የትምህርት ቤቶች መስፋፋትና የትምህርት ስርዓቱ ለመሰረታዊና ስር-ነቀል ለሆነ ሁለ-ገብ ዕድገት የሚያመቹ አልነበረም። መንፈስን የሚገልጽና ንቃተ-ህሊናን የሚያዳብር ለመሆን ባለመቻሉ በዚህ ዐይነቱ የተኮላሸ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ ሊፈጠር የቻለው ትዕቢተኛ የሆነና ለብሄራዊ ነፃነቱ የማይቆረቆር ኤሊት ነኝ ባይ ነው። በተለይም የፍጆታ ምርትን ለማምረት ብቻ የተቋቋሙት ኢንዱስትሪዎች የተለያዩ ቀላል ምርቶችን ከማምረት አልፈው ለተሟላና ለሁለ-ገብ ዕድገት የሚያመቹ አልነበሩም። እንደሚታወቀው የኋላ ኋላ ወደ ውስጥ ያተኮረና ተከታታይነት ያለው ዕድገት የተጎናፀፉ አገሮች ስርዓት ያለው(Systematic Industrialization)  የኢንዱስትሪ ፖለቲካን የተከተሉት በማሽን ኢንዱስትሪ ላይ በማትኮርና፣ ይህንንም ከምርምርና ከዕድገት (Research and Development)  ጋር በማማያዝ ነው። በማሽን ኢንዱስትሪ መኖርና በማኑፋክቸሪንግ አማካይነት ነው የተለያዩ ምርቶችን፣ ማለትም የአጭርና የረጅም ዕድሜ ያላቸውን የምርት መሳሪያዎች ሊያመርቱና ለአምራች ኃይሉም ሊያቀርቡ የሚችሉት። በዚህም አማካይነት ብቻ ነው ግልጽነት ያለው የውስጥ ገበያ(Home Market) ሊያድግና ሊስፋፋ የሚችለው። ይህ ብቻ ሳይሆን፣ አንድ አገር በባህል፣ ማለትም በስነ-ጽሁፍ፣ በሙዚቃ፣ በስዕል፤ በሳይንሳይዊ ምርምርና በሌሎችም መጥቃ ልትሄድ የምትችለውና በማንኛውም የውጭ ኃይል ለመከበር የምትችለው ይህንን ዐይነቱን የተሟላ የዕድገት ፖሊሲ ስትከተል ብቻ ነው። ይህንን መሰረታዊ የሆነ ለተሟላና ለተስተካከለ የሁለ-ገብ ዕድገት መሰረት ሊሆን የሚችለውን የኢኮኖሚ ዕድገት ፖሊሲና ለባህላዊ ለውጥ የሚያመቸውን ሂደት የተረዳ ኃይል ሊኖር ባለመቻሉ ዛሬ የወደቅንበት የብሄራዊ ውርደትና ወደ አገር መፈራረስ አደጋ ላይ ልንደርስ በቅተናል። ዛሬም እንደትላንትናው ሁሉም በትናንሽ አስተሳሰብ በመወጠርና ልዩ ልዩ ተንኮሎችን በመፍጠር ለዕድገት የሚያመች የተሟላ ሳይንሳዊ ዕውቀት እንዳይስፋፋ የማይሸርበው ተንኮል ይህ ነው አይባልም። ለአገሩ ብሄራዊ ነፃነት ከመታገልና ለህዝቡ የሚሆን አስተማማኝ ሁኔታ ከመፍጠር ይልቅ ለነጭ የኦሊጋርኪ መደብ የበላይነት ካለደርኩ እያለ እዚህና እዚያ የሚቅበዘበዘው ኃይል ቁጥሩ ትንሽ ነው አይባልም። አብዛኛው ደግሞ በጥራዝ ነጠቅ የአካዴሚክስ ዕውቀት የተካነ በመሆኑ ከዚህ በመላቀቅ ሰፋ ያለ ምርምርና ጥናት ለማድረግ አይፈልግም። በአካዴምክስ ዕውቀት ብቻ እየኮራ አገሩ ወደ አዘቅት ውስጥ ስትወድቅ ዝም ብሎ እየተመለከተ ነው። ይህ ዐይነቱ የህብረተሰብ ኃይል በዚህች ዓለም ለምን እንደሚኖርና ተልዕኮውም ምን እንደሆነ የተረዳ ባለመሆኑ ከራሱ ጊዜያዊ ጥቅም ባሻገር ለማሰብ የሚችል አይደለም። ስለሆነ ይህ ዐይነቱ የህብረተሰብ ኃይል ለተሟላ ዕድገት እንቅፋት የሆነነ የህዝባችንን ድህነትና ኋላ-ቀርነት የሚያራዝም ነው ማለት ይቻላል።

 

ያም ሆነ ይህ በአፄው ዘመን አንዳንድ ለውጦች ቢታዩም በተለይም የሰፊውን ህዝብ ፍላጎት ለሟሟላት የሚችሉ ባለመሆናቸውና፣ ከዚህም በላይ በየቦታው የመስፋፋት ኃይላቸው ደካማ በመሆኑ የተነሳ ወደ ውስጥ ያተኮረ  ኢኮኖሚያዊ ግንባታ ማካሄድ አልተቻለም። በአፄ ኃይለስላሴ ዘመንም ህዝቡን የሚያስተሳስረው ትንናንሽና ትላልቅ መንደሮችና ከተማዎች ስርዓት ባለው መልክ ባለመገንባታቸውና፣ ከተማዎችን በአማረ መልክ የመገንባት አስፈላጊነት የተረዳ ኃይል ባለመኖሩና፣ በተለይም ሰፊው ህዝብ ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ ለመጓዝ እንዲችል የባቡር ሃዲዶች ባለመዘርጋታቸው የተነሳ በበቁሎና በእግሩ የሚጓዘው የህብረተሰብ ክፍል ቁጥሩ ትንሽ አልነበረም። የእርሻ መስኩም በተለያየ ደረጃ ዘመናዊና ምርታማ እንዲሆን በጊዜው አስፈላጊው የጥገና ለውጥ ስራዎች ባለመሰራታቸው ህዝባችን በተደጋጋሚ ለሚከሰት ረሃብ ይጋለጥ ነበር። አፄውና አገዛዛቸው በጊዜው የነበረውንና የሰፈነውን ሰላምና፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ የነበረውን በጊዜው ለሁለ-ገብ ዕድገት የሚያመቸውን ሁኔታ ባለመረዳትና አስፈላጊውን እርምጃ ተግባራዊ ለማድረግ በላመቻላቸው ህዝባችንና አገራችን በቀላሉ ሊደፈሩበት የሚችሉበትን ሁኔታ ሳያውቁት አመቻችተው ሂደዋል ማለት ይቻላል። በአፄው ዘመን እዚያው በዚያው ኋላ-ቀርነትና የተኮላሸ የዘመናዊነት ዕርምጃዎች አንድ ላይ ይጓዙ ስለነበር፣ በተለይም የተማረው ኃይል በግልጽ የሚመራበት መመሪያ አልነበረውም። ቤተ-መጻህፍትና ሌሎች የዕውቀት ማዕከሎች በየቦታው ባለመስፋፋታቸው የተነሳ በወጣትነት ጊዜው ለጭንቅላት ዕድገትና ለፈጠራ ስራ የሚጠቅሙ ዕውቀቶችን ለመቅሰም የሚችለው ወጣት ጊዜውን ባልባሌ ቦታዎች ነበር የሚያባክነው ማለት ይቻላል።

 

ይህንን ዐይነት ያልተሟላ ዕድገትና፣ ህዝባችንን በድህነትና በተደጋጋሚ ረሃብ የሚያሰቃየውን ሁኔታ ለማሰወገድ በአብዮት ወቅት አንዳንድ የጥገና ለውጦች ቢካሄዱም በጊዜው በነበረው የርስ በርስ መሻኮት የተነሳና፣ በተለይም ስልጣንን የጨበጠው ደርግ የሚባለው ከወታደሩ የተውጣጣ ያልተገለጸለትና በምሁራዊ ዕውቀት ጭንቅላቱ ያልታነፀ የወታደር ስብስብ በጊዜው የሚታዩ ችግሮችን በፖለቲካ ዘዴ ከመፍታት ይልቅ ወደ አመፅ ነው ያመራው። ሌሎች ታጋይ ነን ይሉ የነበሩ ኃይሎችም በጊዜው የነበረውን ድክመት በመረዳት ሁኔታውን ለማርገብ ዘዴ ከመፈለግ ይልቅ በተቀጣጠለው እሳት ላይ የባሰውን ቤንዚን ማርከፍከፍ ነው የጀመሩት። ይህ ዐይነቱ በብስለትና በምሁራዊ ዕውቀት የማይመራ ፖለቲካ የሚሉት ፈሊጥ ቀስ በቀስ የደርግን አገዛዝ ´ከሰረሰረ በኋላ አገርን ለመከፋፈልና ለማዳከም ለሚችሉ በጣም አደገኛ ኃይሎች ነው ሁኔታውን አመቻችቶ ጥሎ የሄደው።  የደርግንና የተቀረውን የሚሊተሪና የስለላ ኃይል የዕውቀት ደረጃ ስንመለከት ደግሞ አብዛኛዎቹ በአሜሪካን ጭንቅላትን በሚያደነዝዝ “የሚሊተሪ ሳይንስ” ብለው በሚጠሩት የሰለጠኑ ናቸው። የቢሮክራሲውና የቴክኖክራሲውም አሰለጣጠን አገርን በተሟላ መንገድ ላይ እንዲገነባ በሚያደርግ ዕውቀት ላይ የተመሰረተ ባለመሆኑ በቀላሉ ለአሜሪካኖች የሚያጎበድድና አገርንም የሚሸጥ ነበር። በሌላ ወገን ግን ብሄራዊ ነፃነታቸውን ያስከበሩና ጠንካራ ኢኮኖሚን በመገንባት ህዝባቸውን ከድህነት በማላቀቅ በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ተወዳዳሪ የሁኑ አገሮችን የመንግስታት አወቃቀር ስንመለከት አንዳቸውም መንግስታት ውጭ ሰልጠነውና የአሜሪካንን ርዕዮተ-ዓለምን በሚያራምዱና አገራቸውን በሚያደኸዩ አጎብዳጅ ኃይሎች አልተሰገሰጉም። እንደነዚህ ዐይነት ኃይሎች ካሉም በፍጥነት ነው እርምጃ የሚወሰድባቸው። ወደ አገራችን ስንመጣ ግን ለአሜሪካን የስለላ ድርጅት መስራትና አገርን ማፈራረስ እንደትልቅ ነገር ነው የሚታየው። እንደዚህ ዐይነቱም ሰው  ነው በጣም  የሚከበረው። ይህም የሚያረጋግጠው የአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ኤሊት ጭንቅላትና የአንዳንድ የታወቁ ሰዎች ተከታዮቻቸው ጭንቅላት የቱን ያህል ጨቅላ እንደሆነ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሁለት ሀገር ስደተኛው - ጋዜጠኛ። (ሥርጉተ ሥላሴ)

 

ህወሃት ወይም ወያኔ የሚባለው አገዛዝ በአሜሪካንና በእንግሊዝ ኢምፔሪያሊስት ኃይሎችና በሰለላ ድርጅቶቻቸው ተደግፎና ተረድቶ ስልጣንን ሲጨብጥ ሆን ብሎ የጀመረው ስራ አገርን በፍጥነት ማዳከምና ብሄራዊ ነፃነቷ እንዲደፈር ማድረግ ነው። በመጀመሪያ ደረጃ የጎሳ ፌዴራሊዝም ብሎ የሚጠራውንና የሚያቆላብሰውን አገርን የሚሰነጣጥቅውንና  የህዝቡን ብሄራዊ ስሜት የሚያዳክመውን ነው ተግባራዊ ያደረገው። ከዚህም በላይ ይህ ዐይነቱ ሂደት ጠንካራ ህብረ-ብሄር እንዳይመሰረት የሚያደርግ አደገኛ አካሄድ ነው። ተፈጥሮአዊ ከሆነው የህብረ-ብሄር ምስረታ አንፃርም ስንመረምረው የኋሊት ጉዞ የሆነና የህብረ-ብሄርንና የተፈጥሮ ህግን የሚጥስ ኢ-ሳይንሳዊ አካሄድ ነው።  በመሰረቱ የጎሳ ፌዴራሊዝም  ለብሄረሰቦች ዕውነተኛ ነፃነትን ያጎናፀፈና የፈጠራ ኃይላቸው እንዲዳብር ያደረገ ሳይሆን ለራሱ ለወያኔ የከፋፍለህ ግዛው ፖሊስና በየአካባቢው የሚገኙ የጥሬ-ሀብቶችን እንዲበዘብዝ የሚያመቹ ናቸው። ህወሃት ወይም ወያኔ በዓለም ኮሙኒቲውና ተላላኪዎቻቸው በሆኑት፣ በዓለም የገንዘብ ድርጅትና(IMF) በዓለም ባንክ(World Bank)በመመከርና በመገፋት ተግባራዊ ያደረገው የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚክ ፖሊሲ በመሰረቱ ለትናንሽና ለማዕከለኛ ኢንዱስትሪዎች መስፋፋትና፣ እንዲሁም ደግሞ ለሳይንስና ለቴክኖሎጂ ዕድገት የሚያመች አልነበረም። ይህ ዐይነቱ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ብለው አቆላብጠው የሚጠሩት በመሰረቱ የአንድን አገር የጥሬ ሀብት መበዝበዢያ ዘዴ ነው። ከዚህም በላይ በአየር ላይ የሚንሳፈፍ የሚመስለው የህብረተሰብ ክፍል በመፈጠር አንድን አገር የብልግና ኢንዱስትሪ የሚስፋፋባት መድረክ ማድረግ ነው። ሰፊው ህዝብ ሊኖርባቸው የሚችሉ እዚህና እዚያ የተለያየ ደረጃ ያላቸውን ቤቶች ከመስራትና  ሰው መሆኑን እንዲገነዘብና የኑሮንም ትርጉም እንዲረዳው ከማድረግ ይልቅ የአምስትና የሰባት ኮከብ ትላልቅ ሆቴልቤቶች በመስራት ነው ሰፊውን ህዝብ ደግሞ ወደ ድህነት ዓለም ውስጥ እንዲጣል ለማድረግ የበቁት። በዚህ መልክ ወያኔ የሚባለው አገር አውዳሚ፣ ባህልን ከስካሽ የሆነ ኃይል ከኢምፔሪያሊስት ኃይሎች ጋር በማበርና ትዕዛዝ በመቀበል የህዝባችን መብትና የብሄራዊ ነፃነታችን ጠንቅ በመሆን አገራችንን ለማዋረድ በቅቷል፤ የህዝባችንንም ሞራልና መንፈሱን በከፍተኛ ደረጃ አዳክሟል። ከዚህም በላይ በምንም መልኩ ለህዝባችንና ለብሄራዊ ነፃነታችን ደንታ የማይሰጠው ለውጭ ኃይሎች ተላላኪ የሆነ  የህብረተሰብ ኃይል እንዲፈጠር በማድረግ በከፍተኛ ፍጠነት ብሄራዊ ነፃነታችንና የአገራችን ልዑላዊነት እንዲደፈሩ አድርጓል። በተለይም የወጣቱ መንፈስ እንዲዳከምና ግብረ-ሰዶማዊነት እንዲስፋፋ አመቺ ሁኔታ መፍጠሩ ብሄራዊ ነፃነታችን ከፍተኛ ፈተና ውስጥ እንዲወድቅ አድርጎታል።  ወያኔ በዚህ ዐይነቱ የጨለመና የጠበበ አስተሳሰቡ ብቻ ሳይረካ እንደ ሱዳን ለመሳሰሉ ጎጠኛና በኋላ-ቀር አስተዳደር ለሚመሩ አገራችን ምድር ሰተት ብለው እንዲገቡ በማድረግ በብዙ ኪሎ ካሬሜትር የሚቆጠር መሬት እንዲወሩና ኗሪው የገበሬው ህዝባችን ላይ ጦርነትን እንዲከፍት ለማሰደረግ በቅቷል። ወያኔ በቂም በቀልና በዝቅተኛ መንፈስ በመታገዝ የወሰዳቸው ዕርምጃዎች በሙሉ ዛሬ እንደምናየው አገራችንን ለከፍተኛ አደጋ ጋርጧት ነው ያለፈው። በዓለም የገንዘብ ድርጅትና በዓለም ባንክ እየተመከረ ተግባራዊ ያደረገው የነፃ ገበያ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ብለው የሚጠሩት አገራችንን የዕዳ ተሸካሚ ነው ያደረጋት። ኢ-ሳይንሳዊ በሆነው የኢኮኖሚ ፖሊሲ የተነሳና ወደ ውጭ የሚላከውም ምርት በእርሻ ላይ ብቻ ያተኮረ ሰለሆነ አገዛዙ የግዴታ ከውጭ ገንዘብ መበደር ነበረበት። ዕዳውን ለመክፈል ሲል ደግሞ ወደ ውስጥ ያተኮረ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ከማካሄድ ይልቅ በተወሰኑ የእርሻ ምርት ውጤቶች ላይ ብቻ ነው እንዲያተኩር የተደገደደው። በዚህም ምክንያት የተነሳ የዕዳው መጠን ከጊዜ ወደ ጊዜ መቆለሉ ብቻ ሳይሆን፣ የውጭ ንግድ ሚዛኑም በከፍተኛ ደረጃ ሊናጋ ችሏል። ይህም ማለት አገራችን ወደ ውጭ ከምትልከው ምርት ይልቅ ወደ ውስጥ የምታስተገባው ዕቃዎች በከፍተኛ ደረጃ የዕጥፍ ዕጥፍ ጨምረዋል። የሚገቡትም ዕቃዎች የቅንጦት ሲሆኑ፣ እነዚህም የውጭ ምንዛሪን በከፍተኛ ደረጃ የሚጋሩ ናቸው። በዚህ ዐይነቱ የተዛባና ህዝባችንን የሚያደኸይና ብሄራዊ ነፃነታችንን የሚያስደፍር የኢኮኖሚ ፖሊሲ አማካይነት የወንበዴዎች ስብስብ የሆነውና የውጭ ኃይሎችን አገርን የማፈራረስ ተግባር የሚፈጽመው ወያኔ በመባል የሚታወቀው ሰይጣናዊ ኃይል አገራችን በቀላሉ ልትወጣ የማትችለው ማጥ ውስጥ ነው ጥሎልን የሄደው ማለት ይቻላል።

 

ከወያኔ መውደቅ በኋላ በወያኔ ሰይጣናዊ መንፈስ የታነፀው በአቢይ አህመድ የሚመራው የኦሮሞ ኤሊት ነን ባይ የመንግስትን መኪና የመቆጣጠር ዕድል ነው ያጋጠመው። አብይ አህመድ ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ እያለ ህዝቡን ካሳሳተና ልቡን ከበላው በኋላ የራሱን ሰዎች በመሰብሰብ ነው ይኸው እንደምናየው በተለይም ከአለፈው አራት ዓመት ተኩል ጀምሮ አገራችንን በሁሉም አቅጣጫ ለማዳከመና ለመበታተን የሚሰራው። ከበስተጀርባው ሆነው የሚጠመዝዙትና አገራችን እንድትፈራርስ የሚያደርጉት የውጭ ኃይሎች ዋናው ዓላማም ወደፊት ሊወዳደርን ይችላል ብለው የሚጠረጥሩትን አገሮች ማፈራረስና ህዝቦችን ከወደቁበት እንዳይነሱ ማድረግ ነው። አቢይ አህመድ ከወያኔዎች ጋር በማበር በተለይም በህዝባችን ላይ የከፈተው የውክልና ጦርነት በመሰረቱ የአሜሪካኖችና የእንግሊዞች፣ እንዲሁም የተቀረው የምዕራቢ ካፒታሊስት አገሮች  ዕቅድ ነው። እንደሚታወቀው እነዚህ ኢምፔሪያሊስት ኃይሎች ሞራልና ስነ-ምግባር፣ እንዲሁም ዕውነተኛ ባህል ምን እንደሆን የማይገባቸው  ስለሆነና፣ ጠንካራ ሃይማኖትና የሚያስተሳስረውን ልዩ ልዩ ባህሎች ለማረራረስ የማይሰሩት ተንኮል የለም። ከዚህም ባሻገር ዱርዬ ኃይሎችን በመኮትኮትና በማሰማራት ነው በቀላሉ ለማስተዳደር የማይቻልበትን ሁኔታ የሚፈጥሩት። ይህንንም እርኩስ ስራ በተለያዩ የደቡብና የማዕከለኛ የአሜሪካ አገሮች ተግባራዊ በማድረግ መንግስታት ራሳቸው የማፊያዊ ተግባር እንዲያካሂዱ አመቺ ሁኔታን ሊፈ›ጥሩ ችለዋል። ባጭሩ በተለያዩ የላቲንና የማዕከለኛ አገሮች ፋሽሽት መሰልና ኋላ-ቀር የሆኑ አገዛዞችና የመንግስት መክኒናዎች በመፈጠር የአሜሪካን የጥሬ-ሀብት አውጭ ኩባንያዎች እንደፈለጉ በመግባትና በመውጣት ጥሬ-ሀብቶችን ይዘርፋሉ። የነበሩ ባህላዊ የሰው በሰው ግኑኝነቶችን እያፈራረሱና አካባቢውን በተለያዩ ኬሚካሎች እየመረዙ ነው።  በዚህም የተነሳ ምስኪንና ያልተማረው ሰፊው ህዝብ አቅመ-ቢስ በመሆን እንደ ሰው እንዳይቆጠር ለመደረግ በቅቷል። የስለላ ድርጅቶቻቸውም ዋና ተግባር ይህንን ሰይጣናዊ ስራ መስራትና አገሮችን በሁሉም አቅጣጭ በመወጠር የመጨረሻ መጨረሻ የጦርነት አውድማ ማድረግ ነው።  በዚህም ምክንያት የተነሳ የየአገሮችን ታሪክና ከትውልድ ወደ ትውልድ የተላለፈ ባህል በማጥፋት እንደነዚህ ዐይነት ምሁራዊ ብቃት የሌላቸውን፣ ብሄራዊ ነፃነት ማለት ምን እንደሆነ የማይገባቸውን መንፈሰ-ደካማ ወይም መንፈስ-አልባ ኃይሎችን በመጠቀም የብዙ ሺህና የብዙ መቶ ዓመታት ባህሎችና እሴቶች ያላቸውን አገሮች እንዳለ እንዲፈራርሱ ያደርጋሉ። ሰለሆነም መንፈሱ በጣም ደካማ የሆነ፣ አገርና ህብረተሰብ እንዴት እንደተመሰረቱ የማይገባውን እንደ አቢይ አህመድና ግብረአበሮቹን የመሳሰሉትን በመጠቀም አገራችን ከድጡ ወደ ማጡ እንድትገባ እያደረጉ ነው። አብይ አህመድ ስልጣንን ከጨበጠ ጀምሮ በመሰረቱ ከወያኔ የተለየ የኢኮኖሚ ፖሊሲ መከተል አልቻለም። ራሱና በዙሪያው የተሰበሰቡት ኃይሎችና አማካሪዎችም በአገራችን ምድር ተግባራዊ የሚሆነውን የኢኮኖሚ ፖሊሲ የሚያውቁ አይደለም። ከቢሮዎቻቸው ወጥተው የተለያዩ ቦታዎችን እየተዘዋወሩ ስለማያዩና ቢያዩም እንኳ ደንታ ስለማይሰጣቸው ለእነሱ የኢኮኖሚ ዕድገት ሆቴልቤቶችን በመገንባት፣ የገበያ አዳራሾችን በማስፋፋትና ከውጭ የቅንጦት ዕቃዎችንና መኪናዎችን በማስመጣት የሚገለጽ ነው የሚመስላቸው።  ህዝባችን ከድህነት ይላቀቅ አይላቀቅ ደንታቸው አይደለም።

 

ባጭሩ የአቢይ አህመድ አገዛዝ ከወያኔ የወንበዴዎች አገዛዝ ፈጥኖ በመሄድ አገራችንን በሁሉም አቅጣጫ እያዳከመና ለመበታተን ደፋ ቀና እያለ ነው። የአገራችን ዳር ድንበር እጅግ ወደ ኋላ በቀሩ አገዛዞች እየተጣሰ ነው። አንዳንድ አካባቢዎች እየተወረሩና ህዝባችንም እየተፈናቀለ ይገኛል። አብይ አህመድና አገዛዙ የቅኝ ግዛት አስተዳደር እንኳ የማያደርገውን የወንጀል ስራ በመስራት ህዝባችን እፎይ ብሎ እንዳይኖር እያደረገው ነው። በተለይም ከሰድስት ወር በላይ ጀምሮ በአማራው ክልል የሚያደረገው ወረራና ጦርነት በዚያ አካባቢ የሚኖረውን ህዝባችንን እፎይ ብሎ እንዳይኖር አድርጎታል። በሰላም የእርሻ ተግባሩን እንዳያካሄድ አሰናክሎታል። በየቦታው የምርት እንቅስቃሴ እየተዳከመ ነው። የምርት እንቅስቃሴ ከተዳከመ ደገሞ የገበያ እንቅስቃሴም ይዳከማል። በዚህ መልክ በአማራው ክልል አካባቢውን ለማልማት፣ በኢኮኖሚ ለማሳደግና ህዝቡንም ከድህነት ለማላቀቅ የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል ማለት ይቻላል።

 

በዛሬው ወቅት ህዝባችንን የሚወክል አገዛዝና መንግስት የለም ብሎ መናገር  ይቻላል። አገዛዙ፣ በተለይም ጠቅላይ ሚነስተር ተብዬው የህግ የበላይነትን የሚያውቅ አይደለም። በሶስቱ ኦርጋኖች መሀከል ያለው የስራ ክፍፍል ተግባራዊ ሲሆን አይታይም። ኤክስኪዩቲቩ የህግ አውጭው ተጠያቂ መሆን ሲገባው ጠቅላላው የአጋዝዙ አካሎችና የመንግስቱ መኪናዎች፣ ማለትም ወታደሩ፣ የፀጥታው ኃይል፣ ፖሊስና ፍርድቤቶች የአቢይ የግል ሀብት ይመስሉ እንደፈለገው የሚጠመዝዛቸው ናቸው። ጋዜጠኞችና የፖለቲካ አክቲቪስቶች ምንም ዐይነት ወንጀል ሳይሰሩ በአብይ ቀጭን ትዕዛዝ ወደ እስር ቤት ውስጥ በመወርወር እንዲሰቃዩ እየተደረገ ነው። ሌሎች ደግሞ እየታፈኑ በመወሰድ በመታጎሪያ ቦታዎች እየታጎሩ  እየተሰቃዩ ነው። ከዚህ ሁኔታ ስንነሳ በአገራችን ምድር ህዝባችንን የሚወክል አገዛዝና መንግስት የለም ብሎ መቶ በመቶ መናገር ይቻላል። የሚያሳዝነው ደግሞ በአቢይ አካባቢ የተሰባሰቡ ኃይሎች ንቃተ-ህሊናቸው የደከመ በመሆኑ አቢይ እንደፈለገው ሲዘላብድ ከመሳቅና ከማጨብጨብ በስተቀር በድፍረት በቃህ ብሎ የሚናገር አንድም ኃይል ያለመኖሩ ነው። አንዳንዶች የዶክትሬት ዲግሪ ቢጨብጡም የአቢይ ተገዢና ተላላኪ በመሆን አገራችን በፍጥነት ስትፈራርስ፣ ህዝባችን ደክሞ ፍዳውን ሲያይ ዝም ብለው እየተመለከቱ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  "ከሰው ያቀያይማል"??? - ጠገናው ጎሹ

 

ነገሩን ለማሳጠር የአንድ አገር ልዑላዊነትና ብሄራዊ ነፃነት የሚደፈሩትና አንድም ህዝብ የሚናቀው እንደዚህ ዐይነት አገዛዝ ስልጣን ላይ ሲኖር ብቻ ነው። እንደሚታወቀው የአፄው ኃይለስላሴም ሆነ የደርግ አገዛዝ እስከዚህ ድረስ ገፍተው በመሄድ የአገር ልዑላዊነት እንዲፈራርስ የሰሩት ወንጀል አልነበረም። ይሁንና ባለማወቅ ከፍተኛ ስህተቶች ሊሰሩ ችለዋል። ትላልቅ መሬቶች “ለወዳጅ አገሮች” የኤምባሲ መስሪያዎች በመሰጠት ብሄራዊ ነፃነት የሚያስደፍር ስራ በተለይም አዲስ አበባ በሚገኘው የአሜሪካን ኤምባሲ ውስጥ ሲሰራ ´እንደነበር የሚታወቅ ጉዳይ ነው። ለዚህ ደግሞ አብዛኛው የወታደር ኃይል በአሜሪካ የስለላ ድርጅትና የሚሊታሪ ሰዎች የሰለጠነ በመሆኑ አገርንና ብሄራዊ ነፃነት እንዴት እንደሚናዱ የገባው አልነበረም። አብዛኛውም ምሁራዊ ኃይሉ በጣም ደካማ ስለነበረ ከራሱ ባሻገር ዘልቆ በመሄድ በሁሉም አቅጣጭ የማየትና የማሰብ ኃይል አልነበረውም። በጠቅላላው የሚሊታሪውና የሲቪሉ ቢሮክራሲ፣ እንዲሁም የፀጥታ ኃይል የሚባለው ብሄራዊ ስሜትን በሚያዳብር፣ መንፈስን በሚያጠነክር ምሁራዊ ዕውቀት የሰለጠኑ ባለመሆናቸው ከውጭ የሚመጣውንና የሚሸረበውን ተንኮል በቀላሉ የመረዳት ኃይል አልነበራቸውም። ለዚህ ነው ደርግ ወደ መውደቂያው አካባቢ አብዛኛዎቹ የስለላውን መረበ በመበጣጠስ ለወያኔ ሰተት ብሎ እንዲገባ አመቺ ሁኔታን የፈጠሩለት።  አሜሪካኖችም ለሚሊታሪው፣ ለፀጥታው ኃይልና ለሲቪሉ ቢሮክራሲ ይሏቸው የነበረው እናንተ ደርግን ጣልሉንና ኢትዮጵያን እንደ ደቡብ ኮሪያ እናደርግላችኋለን እያሉ ነበር የሚያታልሏቸው።

 

ባጭሩ በዛሬው ዘመን የአንድ አገር ብሄራዊ ነፃነትና ልዑላዊነት የሚደፈሩት እንደድሮው በቀጥታ ወረራ አይደለም። ልፍስፍስና ብሄራዊ ክብር የማይሰማቸውን፣ በተለይም ደግሞ ጠለቅ ባለ ምሁራዊ ዕውቀት ጭንቅላታቸው ያልተገነባ ኃይሎችን ስልጣን ላይ በማውጣትና ህዝብን የሚያደኸይና አገርን የሚያዳክም የኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ እንዲሆን በማድረግ ነው። ከዚህም በላይ በአገራችን ምድር የሊበራል ዲሞክራሲንና የግለሰብአዊ ነፃነት የሚያስከብረውን የከበርቴውን ዲሞክራሲና ለህግ የበላይነት ተጠያቂ የሚያደርገውን ስርዓት ተግባራዊ ከማድረግ ይልቅ ህዝብን የሚከፋፍል የጎሳ ፌዴራሊዝም ተግባራዊ በማድረግ ነው። ይህ ዐይነቱ ሂደት ደግሞ አንድ ልጅ ተፀንሶ፣ ተረግዞ፣ ተወልዶና ለአቅመ-አዳም  ከደረስ በኋላ እንደገና ወደ እናትህ ማህፀን ውስጥ  ተመልሰህ ግባ ብሎ እንደመምከር የሚቆጠር ነው። በራሳቸው የከበርቴው ዲሞክራሲና በአገር ግንባታ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በሌሎች አገሮችም በምንም መልኩ ተግባራዊ ያልሆነ የጎሳ ፌዴራሊዝም የሚሉት ፀረ-ተፈጥሮና የህብረተሰብ ህግ ፀር የሆነውን ነው በአገራችን ምድር ተግባራዊ  እንዲሆን አገዛዙን የመከሩትና ያስገደዱት። በዚህ ዐይነቱ እርኩስ ስራና የታሪክ ወንጀል ሰለጠንኩኝ የሚለው የአሜሪካንና የእንግሊዝ ኤሊት ከተጠያቂነት የሚያልፍ አይደለም። ባለፉት ሰላሳ ሶስት ዓመታት ህዝባችን ፍዳውን የሚያየው በዚህ መልክ በተቀነባበረ ሰይጣናዊ ስራ ነው።

 

ለህዝባችን ደህንነትና ለአገራችን ክብርና ብሄራዊ ነፃነት እንታገላለን የሚሉ የተለያዩ ኃይሎች ከዚህ ዐይነቱ አገርን የማፈራረስ ሴራ ብዙ´ የሚማሩትና የሚወያዩበትም አያሌ ነጥቦች እንዳሉ መታወቅ አለበት። ወደ ኋላ ተመልሶ ታሪካችን እንደዚህ ነበር በማለት በተለይም ወጣቱን ትውልድ ከማዘናጋት ይልቅ ከላይ በተዘረዘሩት ነጥቦች ላይ በሰፊው በዙምም ሆነ ግልጽ በሆነ በሰሚናር መልክ መወያየትና ማጥናት ያስፈልጋል። ለዚህም ወጣቱን ትውልድ ለማንቃት የሚችሉ  የሰለጠኑ ሰዎች እሉ። እነሱን እየጋበዙ ዘመናዊ የአገር ግንባታ ትምህርት እንዲሰጡ ማድረግ የጊዜው አንገብጋቢ አጀንዳ መሆን አለበት። ይህን ከማድረግ ይልቅ አብዛኛው በአንዳንድ እንታወቃለን በሚሉ፣ ይሁንና ደግሞ ንቃተ-ህሊናቸው ባልዳበሩ ወይም በጣም ዝቅተኛ በሆኑ ሰዎች እየታለሉና እነሱን እያሞገሱ መሰራት የሚገባቸው ነገሮች እንዳይሰሩ እንቅፋት በመሆን ላይ ናቸው። እነዚህ ታወቅን የሚሉ ሰዎች ከመኩራራት በስተቀር ወጣቱ መንፈሱ እንዲጎለምስ የሚወስዱት እርምጃ የለም፤ ለ፣አስተም፣አርም የሚችሉ አይደሉም። ያላቸውም አስተሳሰብን በጣም ወደ ኋላ የቀረ በመሆኑ ለተሟላ ዕድገትና ለሰለጠን ኑሮ ከፍተኛ እንቅፋት የሚሆኑ ናቸው። ለወጣቱም የተለያዩ ለመንፈስ መዳበርና ለአገር ግንባታም የሚያመቹ ዕውቀቶችን እንዲያጠና የተለያዩ የመጽሀፍ ዐይነቶችን እንዲያደነብ ሲጠቁሙና ሲመክሩ በፍጹም አይታይም። አብዛኛዎችም የአሜሪካ አፍቃሪዎችና የምዕራቡን ካፒታሊስት አገሮች አትንካብን የሚሉ ስለሆነ እነዚህ ዐይነት ሰዎች በቀጥታ አገራችንና ህዝባችን በድህነት ዓለም ውስጥ ለዝንተ-ዓለም እየተሰቃዩ እንዲኖሩ ነው የሚያደርጉት። ዋናው ተልዕኮአቸውም  አገራችንና ህዝባችን የሳይንስና የቴክኖሎጂ ባለቤት እንዳይሆኑ ማድረግ ነው። የሰለጠነና ፈጣሪ የሚያደርግ ባህል እንዳያዳብሩና ለነጩ ኦሊጋሪክ መደብ ተገዢ ሆነው እንዲቀሩ ማድረግ ነው ዋናው ተግባራቸው። ሌሎችም በአንዳንድ ጋዜጠኛ ነን ባዮች የሚጋበዙ ምሁራን ነን ባዮች ዋና ተግባራቸው ህዝባችን በዘለዓለማዊ ድህነት ውስጥ እንዲኖር ማድረግና አገራችን ተዳክማ እንድትቀር ማድረግ ነው። ከእነዚህ በዕድሜያቸው ከገፉ ምሁራን ነን ከሚሉ ሰዎች የሚጠበቅ አንዳችም ሳይንሳዊ ዕውቀት ስለሌለ እነዚህን እየጋበዙ ወጣቱን ማደንቆር መቅረት ያለበት ጉዳይ ነው። ጋዜጠኛ ነን የሚሉትም በተቻለ መጠን አዕምሮን ከሚገነባና የአስተሳሰብ አድማስን ከሚያሰፋ ትክክለኛ ዕውቀት ጋር መተዋወቅ አለባቸው። እንደከታተልኩትና እንደምከታተለውም  ክሆነ የጋዜጠኛ ስም አንግበው አንዳንድ ሰዎችን እየጋበዙ የሚጠይቁ ኢትዮጵያውያኖች ምን እንደሚጠይቁ የሚያውቁ አይደሉም። በተለያየ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ብለው በሚጠሩት መሀከል ያለውን ልዩነት ለመረዳት የማይችሉ ናቸው። አብዛኛዎቹ ጋዜጠኛ ነን ብለው ራሳቸውን ቢጠሩም በመሰረቱ የጋዜጠኝነት ሙያ ከአንዳች ሌላ ዕውቀት ጋር መያያዝ እንዳለበት የተገነዘቡ አይደለም።  በዚህም ምክንያት የተነሳ ጋዜጠኛ ነን የሚሉና ታዋቂ የሚባሉ ግለሰቦችን የሚጋዙ  ከፍተኛ የታሪክ ወንጀል እየሰሩ ነው።

 

በአገራችንም ሆነ ውጭው ዓለም በሚኖረው ኢትዮጵያዊ ዘንድ ያለው ትልቁ ችግር ዘመናዊነት የሚባለውን ነገርና፣ የዘመናዊነትን የተለያዩ ሂደቶችና ደረጃዎች ጋር አለመተዋወቅ ነው። ዛሬ የምንጠቀምባቸው ቴክኖሎጂዎች፣ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ዕድገቶች፣ የከተማዎች ዕድገትና፣ በተለይም በአውሮፓ ምድር ባለፉት ሰባ ዓመታት የህዝቡ ኑሮ መሻሻል  ለአብዛኛዎቻችን ከሰማይ ዱብ ብለው የወረዱ የሚመስለን እንጂ ይህ ዐይነቱ ዕድገት በጣም ጥቂት በሆኑና በተገለጸላቸው ኃይሎች እንደ መነሻ መሰረት የተጣሉ አለመሆናቸው ነው። የግሪኩን ስልጣኔ ወደ ጎን ትተን ከአስራአራተኛው ክፍለ-ዘመን ጀምሮ የተፈ›ጠረውን አዲስ ሁኔታና ጥያቄን የማቅረብና የመመራመር ጉዳይ ስንመለከት ይህ ዐይነቱ ጭንቅላትን የማስጨነቅ ሁኔታ ባይፈጠር ኑሮ የዛሬው በሳይንስና በቴክኖሎጂ የሚገለጸው ዓለም ባልተፈጠረ ነበር። እንደ ኮፐርኒከስ፣ ጋሊሊዮ፣ ሬኔ ዲካ፣ ፍራንሲስ ቤከን፣ ላይብኒዝና ኒውተን፤ እንዲሁም የኋላ ኋላ ሌሎች ዕውቀቶችን  ያዳበሩ ሳንስቶችና ፈላስፋዎች ባይፈጠሩና የሰውንም ልጅ ከነበረበት የጨለማ አኗኗር ለማውጣት በየቀኑ በቆራጥነት ባይሰሩ ኖሩ ሁላችንም በጨለማ ዓለም ውስጥ ተዳፍነን በቀረን ነበር። ልክ እንደኛው አገር የአውሮፓውም ህዝብ በዲስፖታዊ አገዛዞች ፍዳውን እያየ እንዲኖር በተገደደ ነበር።  ስለሆነም  ለአገራችን ዕድገትና ብሄራዊ ነፃነት መከበር መታገል አለብን የምንል ከሆነ ዛሬ ካለንበት በጣም ደካማ ሁኔታ በመላቀቅ የነገሮችን ሂደት በሰፊው ማጥናት አለብን። ጊዜያዊ በሆኑ ብልጭልጭ ነገሮች በመታለል ጊዚያችንን አናባክን።  ለአገር መከበር፣ ለህዝብ ነፃነት ዋና መፍትሄው  ሳይንሳዊ ዕውቀት ሰለሆነ በዚህ ላይ መረባረቡ የጊዜው አንገብጋቢ ጥያቄ ነው።  በተለይም ደግሞ ስራዎች በሙሉ ፕሮፌሽናል በሆነና በድርጅት መልክ ቢሰሩ ትግሉ ጥራት ይኖረዋል። ፕሮፌሽናል ባልሆነ መልክ የሚሰሩ ስራዎች በሙሉ ወደ ትክክለኛው ነፃነት ሊያመራን በፍጹም አይችሉም። በመሀከላችን ያለው ትልቁ ችግር በጣም ሰነፎች ስለሆነ በተከታታይነትና በጥረት መንፈሳችንን ለመገንባት ምንም ጥረት ለማድረግ የማንችልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል። ጊዜው የስማርት ፎንና የሶሻል ሚዲያ ዘመን ስለሆነ አብዛኛው ጊዜውን የሚያባክነው ከዚህ ዐይነቱ ዘመናዊ ቲክኖሎጂ ጋር ነው። ሌላው አስቸጋሪው ነገር ደግሞ ተጣጥረው ለማስተማር የሚፈልጉ  ግለሰቦችን  ለመርዳት  ያለው ፍላጎት  በጣም ደካማ  መሆኑ ነው።  ታዲያ በማን ኃይልና በምን ዐይነት ዘዴ ነው አንድን አገር ታላቅና የተከበረች አገር ማድረግ የሚቻለው? እስቲ ምስጢሩን ንገሩኝ። ለማንኛውም እንደዚህ ዐይነት ምሁራ´ዊ ጥናት በተከታታይ እንዲወጣ የምትፈልጉ ሰዎች የዚህን ጸሀፊ ድረ-ገጽ በማገላበጥና በማጥናት አስፈላጊውን ዕርዳታ ማድረግ በጣም ተገቢ ነው። የተጻፉ መጽሀፎችንም በመግዛትና በማንበብ መንፈስን ማበረታት ይቻላል።  ካለበለዚያ በተከታታይ ጽሁፎችን ማውጣትና መጽሀፎችን መጻፍ በፍጹም አይቻልም።  መልካም ግንዛቤ!!

 

fekadubekele@gmx.de

www.fekadubekele.com

 

5 Comments

  1. ውድ ዶ/ር ፍቃዱ
    እንደተለመደው እጅግ በሳል ሃገራዊና አለምአቀፋዊ ጉዳይችን ስላካፍልከን ላመሰግንህ እወዳለሁ::ሰሞኑን በሃገር ቤት የማከብረው ፕሮፌሰር ዝናቡ ከሌሎቹ ጋር ትምህርታዊ ገለጻ መስጠቱን ወዳጆቼ ከሃገር ቤት አሳውቀውኛል::
    የእኔ ምኞትና ጸሎት እንዲህ ህዝባችንን የምትጠቅሙ በሳል ምሁራንን የሃገራችን ተቁዋማት ተጠቅመውባችሁ ሃገራችን ከገባችበት የመክሸፍ አዙሪት ትወጣ ዘንድ ነው::የእናት ሆድ ዥንጉርጉር እንዲሉ ሌሎቹ ደግሞ ተምረው እንዳልተማረ እድሜ ጨምረው እንደልጅ ህዝባችንን ሃገራችንን ቁልቁል ከመንዳት ይታቀቡ ዘንድ ህሊና ያለው ሁሉ ተገቢ ተሳትፎ እንዲያደርግ ሃገርና ህዝብ ጎጂ ትርክቶችን እምቢ ይል ዘንድ መክራለሁ::
    ፓስተር ኤዲ መካሻ

  2. ዶ/ር ፈቃኡ፦

    ከአድዋ ጦርነት በፊት ጎረቤት አገሮች አልነበሩንም። እኛው (የተማርነው) ያደኸየናት አገራችን አትከበርም እንጂ በ19ኛውና በ20ኛው
    ዘመንማ እኔ ወደ አሜሪካ ለከፍተኛ ትምህርት በ1950ዎች ስሄድ በጀርመንና በሎንዶን ሳልፍ፣ ቪዛ አስፈላጊ አልነበረም። ኢትዮጵያዊነት በቂ ነበር። በአሜሪካም ሆነ በአፍሪቃ አገሮች የገጠሙኝን ብነግርህ፣ ኢትዮጵያ እጅግ የተከበረች አገር ነበረች ። ለአንድ ቀን እንኳ ኢትዮጵያዊ ለመምሰል ለፈለገ አፍሪቃዊ የአገር ልብሴንም በ1950 ግድም አውሰኝ ስላለ ሰጥቻላእሁ። በአንድ ወቅትም አንድ ትልቅ የምሁራን ስብሰባ ላይ አንድ የእንግሊዝ ዩኒቬርሲቲ ፕሮቮስት ያልሆነ አስተያየት በንግግሩ ላይ ጨምሮ ” ለምን እንደዚህ አልህ ?” ብየ በመጠየቄ፣ የሻይ እረፍት ላይ እኔን ፈልጎ መጥቶ፣ ” አገርህ የት ነው ? ” ብሎ ጠይቆኝ ” ኢትዮጵያ ።” ስለው ” I thought so !” ብሎ ወደ ጓደኞቹ ተመለሰ። የቀለለችው አንተና እኔ ዶክቶርና ፕሮፊሶር ከሆንን ወዲህ ነው።

  3. Well, what the Dr is saying is clear and big enough to any person with basic knowledge leave alone well-educated !!! I have to say that though is clear and big , it is the right thing to teach and remind ourselves aggressively and progressively!!! It is from this point of view that I sincerely appreciate the article !!!
    Leaving this as it is, we are unfortunately missing one and one factor in the very idea of creating and using products of science and technology and be parts of the civilized world. That factor is the very tragic absence of any opportunity of being free society and free thinker and inventor. because of the very tragic and deadly political discourse for so long and nowadays getting much more horrible .

    I do not understand you intellectuals talk or write about other great things without informing this generation about the very reason why we keep being victims of ignorance , absolute poverty and beggars of others !

    Is this not a tragic paradox of our intellectuals ? Absolutely it is !

  4. የተከበሩ ዶ/ር አየነው እጅጉ፣

    በመጀመሪያ ለሰጡኝ አስተያየት በጣም አመሰግንዎታለሁ። እርስዎና እኔ የዶክትሬት ዲግሪ ወይም የፕሮፌሰር ማዕረግ ከያዝን በኋላ ነው ነገሩ የተበላሸው የሚለው አነጋገር በመሰረቱ አንድ ሰው የዶክትሪት ዲግሪ ስለያዘ አገር አያፈርስም፤ አገርንንም አያዋርድም። አንድ ሰው የተሟላ ፍርድ ሊሰጥ የሚችለው ዛሬ አገራችን ላለችበት ሁኔታ ምክንያቱን በደንብ ካጠና በኋላ ነው። ዋናውን ምክንያት ለማጥናት የኢምፔሪካል ጥናት በማካሄድ የሚገኝ አይደለም። በአገራችን ምድርም ሆነ በሌላ ኋላ ቀር በሚባሉ አገሮች የሚከሰተው ችግር ዋናው ምክንያት የጭንቅላት በሚገባ አለመዳበር ነው። ዛሬ በምርምር እንደተደረሰበት ተራ የአካዴሚክስ ዕውቀት የአንድን ህብረተሰብ ችግር ለመረዳትና መፍትሄም ለመስጠት ስለማይችል እንዲያውም ችግሩን የበለጠ እንደሚያባብሰውና መፍትሄ ለማግኘት እንደማይቻል ነው። በትክክል እንደሚያውቁት በአገራችን የአስኳላ ትምህርት ሲገባ በደንብ ተጠንቶና ተመርምሮ ባለመሆኑ ትምህርታችንን ጨርሰን ስንወጣ በህብረተሰባችንን ውስጥ የሚላወሱትን ችግሮች ለመረዳትና መፍትሄም ለመስጠት አይቻልም። ሌላው ንገ ደግሞ ደጋግሜ ለማስረዳት እንደሞከርኩት ውጤታማ የሆኑ አገሮች የየአገሮቻቸውን የመንግስት መኪና በውጭ ኃይሎች እንደማያዋቅሩ ነው። ወደኛ አገር ስንመጣ የመንግስቱ መኪናና በቢሮክራሲው ውስጥ ተመልምለው የገቡት አብዛኛዎቹ ውጭ አገር የተማሩና ከአሜሪካን የስለላ ድርጅት ጋር የሚሰሩ ነበሩ። አሁንም የሚሰሩ አሉ። በተለይም አብዮቱ ሲፈነዳ እነዚህ ሰዎችና ተራማጅ ነን የሚለው ክፍል የአሜሪካን ተላላኪ በመሆን በአገራችን ምድር ከፍተኛ ችግር እንዲፈጠር ለማድረግ በቅተዋል። ባጭሩ የተፈጠረው ችግር የእኛ የኢትዮጵያኖች ባህርይ በሚገባ ባለመዋቀሩና ክሪቲካል በሆነ መልክ እንዳናስብ በመደረጉ ብቻ ነው። አብዛኛዎቻችንም ጭንቅላትን የሚያዳብሩ ልዩ ልዩ መጽሀፎችን ስለማናነብ ባለን ብቻ እየተኩራራን ይኸው ለዛሬዪቱ ኢትዮጵያ በዚህ ዐይነት ሁኔታ ውስጥ መውደቅ ዋናው ምክንያት ልንሆን በቅቷል። ሁኔታውን ስመለከት የአገራችን ሁኔታ ለብዙ ዓመታት በዚህ እንደሚቀጥል ነው። እያንዳንዳችን የችግሩን መንስዔ ለመረዳት ጥረት ስለማናደርግ፣ እንዲያውም አንዳንዶች ጥረት ሲያደርጉ ስለሚሾፍ የአገራችን ችግር ተድበስብሶ እንዲቀር ለመደረግ በቅቷል። ስለዚህ ያለን አማራጭ መጸለይ ብቻ ነው።
    ከመልካም ምስጋና ጋር

    ፈቃዱ በቀለ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share