October 16, 2023
17 mins read

መተቻቸታችን ለመማማር ቢሆን ኖሮ የት በደረስን ነበር!

October 15, 2023

T.G

ይህንን አስተያየት የምሰነዝረው በ10/14/23 “ክርስቶሳዊ ያልሆነ ክርስቶሳዊነት ” በሚል ርዕስ በሰጠሁት አስተያየት ላይ የራሳቸውን አጭር አስተያየት በሰጡ አንባቢ መነሻነት ነው።

በመጀመሪያ ለአስተያየት ሰጭው በተረዳኸው/ሽው እና ባመንክበት/ባመንሽበት መጠንና አይነት ለሰነዘርከው/ሽው አስተያየት አመሰግናለሁ ለማለት እወዳለሁ።
በመቀጠል አላስፈላጊ እሰጥ አገባ ለመጋበዝ ሳይሆን ይበልጥ ግልፅ ለመሆን የሚከተለውን ለማለት ወደድኩ። ይህንን ለማድረግ የወደድኩት በእንዲህ አይነት እጅግ ግዙፍ እና
ጥልቅ አገራዊ ጉዳይ ላይ ስንነጋገር የግለሰብን ወይም የግለሰቦችን አስተሳሰብ፣ አመለካከትና የተግባር አካሄድ እንደ ማሳያ የምንጠቅሰው  እነርሱን ብቻ የሚመለከት ስለሆነ አይደለም ።  ይልቁንም የየራሳችንን ዘመን ጠገብ የውድቀት ፖለቲካ አስተሳሰብና አካሄድ ከምር ተረድተንና ተቀብለን ተገቢውን እርምት ማድረግ እንዳለብን ይበልጥ ግልፅ ለማድረግ መሆኑ ግልፅ ይሁንልኝ።
1) የዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን እውን መሆን ከምር የምንፈልግ ከሆነ እንዲህ አይነቱን የሃሳብ ልውውጥ የግድ መለማመድ ይኖርብናል ። ይህንን ስናደርግ ግን በሚሰነዘሩ አስተያየቶቻችን ውስጥ ከተጠቀሱ የትኩረት ነጥቦች እየወጣንና በስሜታዊነት የየራሳችንን ትርጉም እየሰጠን ባይሆን ይመረጣል። በአንድ ጉዳይ ወይም ሙያ የህዝብ እውቅና ማግኘት ማለት ሁሉን ወይም አብዛኛውን ነገር ማወቅ እንደሆነ አድርገን ካሰብን እና በእንደ እሸቱ አይነት ግለሰቦች ላይ ሂሳዊ አስተያየት ሲሰነዘር ፈጣሪ የተደፈረ ያህል የምንደነግጥ እና የሚከፋን ከሆነ ዴሞክራሲንና ዴሞክራሲያዊ ማህበረሰብን መናፈቃችን ከንቱ ነው የሚሆነው።

2) እኔ በበኩሌ የምሰነዝረው ሂሳዊ አስተያት በመሬት ላይ ከሆነውና እየሆነ ካለው መሪር እውነታ እና ይህንኑ የገዛ ራሳችንን እውነታ እንደ ግለሰብ ወይም እንደ ቡድን ወይም እንደ ማህበረሰብ (እንደ ህዝብ) ያስተናገድንበትና እያስተናገድን ያለንበት ሁኔታ ምን ያህል ትክክለኛና ውጤታማ ነው? ከሚል መሠረታዊ ጥያቄ የሚነሳ እንጅ በግለሰቦች የግል ህይወት ፣ አኗኗር ፣እምነት፣ አመለካከት፣ ወዘተ ላይ የሚያነጣጥር ፈፅሞ አይደለም። በሌላ አባባል የጋራ (አገራዊ) ጉዳዮቻችንን በተመለከተ እንደ ግለሰብ ወይም እንደ ቡድን ወይም እንደ ማህበረሰብ ስነጋገር እንደ እሸቱ አይነት ግለሰቦችም በተሰማሩበት የሥራ መስክ ሊያዋጡት የሚችሉት በጎ ነገር እንደተጠበቀ ሆኖ እኩያን ገዥዎች ያሸከሙንን የመከራ ቀንበር ለማስወገድ ከምናደርገው ብርቱ ተጋድሎ አንፃር የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረታችንን በሚፈልጉ ጉዳዮቻችን ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አያሳድሩም ከማለት አልፎ ሊተቹ አይገባቸውም የሚለው አስተሳሰብ ግን በእጅጉ የተሳሳተ ነው።  ይህ ደግሞ ለዘመናት የመጣንበትና ደጋግመን የወደቅንበት ክፉ አዙሪት ነውና ጨርሶ ለማስወገድ ባንችልም ከምር በሆነና ገንቢነት ባለው ፀፀትና የእርምት እርምጃ ልናስተካክለው ይገባል።

3) አዎ! እሸቱ ግለሰብ ነው። አዎ! እሸቱ ሰውን እረዱ አላለም። አዎ! እሸቱ እንደ ግለሰብ መልካም ሊያሰኝ የሚችል ባህሪና አድራጎት እንዳለው ለመቀበል አይቸግርም። አዎ! እሸቱ ቤተ እምነቶችን ስለ መግዛት ወይም ስለ መገንባት የሚያደርገው ዘመቻ በመሠረት ሃሳብ ደረጃ ለመቀበል አይገድም።

ለዘመናት የዘለቀውና ከአምስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ እንኳንስ ይሆናል ብሎ ለመገመት ለማሰብ በሚከብድ አኳኋን እየሆነ ያለው አገራዊና ሁለንተናዊ መከራና ሰቆቃ ከሚጠይቀው የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት አንፃር ሲታይ ግን እንደ እሸቱ አይነት ወገኖች ሚዛናዊነት እንደሚጎላቸው ለመረዳት የተለየ ጥናት ሳይሆን ከምር የሆነ ግንዛቤና ሚዛናዊ የሆነ ህሊና በቂ ነው።

4)  የጥልቀቱና የስፋቱ ደረጃ አንድ አይነት ባይሆንም መላው የኢትዮጵያ ህዝብ  እጅግ አስከፊና አስፈሪ በሆነ አጠቃላይ ቀውስ ውስጥ እየጓጎጠ ባለበት በዚህ ወቅት እንኳንስ ባህር ማዶ አገር ቤትም ዓለምን የሚያስደምሙ አዳዲስ ቤተ እምነቶችን ወይም ገዳማትን ለመገንባት የሚያስችል የአያሌ ሚሊዮን ዶላር የማሰባሰብ  ዘመቻ ላይ  መጠመድ ፈፅሞ ሚዛናዊነት የለውም። ቀደም ባለው አስተያየቴ እንደገለፅኩት ይህንን ባርኮ ወይም ቀድሶ  የሚቀበል እውነተኛ አምላክ የለም። የአስተያየቴ ማዕከላዊ ነጥብም ይኸው ነው። እሸቱ ይህንን የማያወላዳ እውነታ አይረዳውም የሚል አረዳድ የለኝም። ይህን አብሮ እይኖረበት ያለውን መሪር እውነታ እያወቀ እንደ አክቲቪስትም፧እንደ ሰባኪም፣ እንደ ትንቢተኛም፣ እንደ የመንግሥተ ሰማያት ምስጢር አዋቂም፣ ወዘተ በመሆን “ለባህር ማዶ ገዳም ወይም ቤተ እምነት የቅድሚያ ቅድሚያ ሰጥታችሁ የገንዘብና (የዶላርና) ሌላም መዋጮ ካለገሳችሁ በረከቱ አመለጣችሁ” የሚል ዘመቻ ማካሄድ ፈፅሞ ትክክል አይደለም።

5) እያልኩ ያለሁት አገር በፖለቲካ ወለድ ወንጀል ምክንያት ከፍተኛ ሰቆቃና  ዋይታ ላይ ስለሆነ  ሁሉን ነገር ትተን አልቃሽና አስለቃሽ እንሁን ሳይሆን ፍፃሜ ባላበጀንለት የባለጌዎችና የጨካኞች አገዛዝ ምክንያት አብዛኛው ህዝብ ወደ ፍፁም የድህነት  ቁልቁለት ሲወድቅ  የሥራና የገቢ ማስገኛ የሆኑ  የቻሪቲ ድርጅቶችን እንደ አሸን እያፈላንና እነርሱኑ እንደ የምፅዋዕት ምንጭ እየጠበቅን የት እንደርሳለን? እንደ እሸቱ አይነት ለጋሾችስ የሚለግሱለት ግለሰብ ወይም ማህበረሰብ ተመፅዋች ካደረገው ብልሹና ወንጀለኛ የፖለቲካ ሥርዓት ሰብሮ ለመውጣት ይችል ዘንድ ምን ያህል የሞራል ግዴታቸውን ተወጥተዋል ወይም እየተወጡ ነው ወይም ለመወጣት ምን ያህል ዝግጁ ናቸውበሚሉ መሠረታዊ ጥያቄዎች ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው።

6) እንደ እሸቱ አይነት ወገኖች ድንቅ ልጆችንና ሌሎች የሰው ልብ ወይም ስሜት የሚያንጠለጥሉ ፕሮግራሞችን ለማፈላለግና ለማዘጋጀት  በእግር፣ በመኪና እና በአየር የሚዘዋወሩበት መሬት ወይም መንገድ እኮ አያሌ ሚሊዮኖች የደም እንባ የሚያነቡበትና በተለይ ደግሞ በቅጡ የማደግ እድል ቢያገኙ ከድንቅም ድንቅ ሊሆኑ የሚችሉና ድንቅ ሥራን በመሥራት አገራቸውን ድንቅ ለማድረግ ይቻላቸው የነበሩ ህፃናትና ታዳጊ ወጣቶች እጅግ አስጨናቂ ብቻ ሳይሆን የመፈጠርን ትርጉም በእጅጉ በሚፈታተን ሰቆቃ የተጥለቀለቀ ነው።

በዚህ ሁኔታ ውስጥ ፈልገውና አፈላልገው አዳራሽ ውስጥ በመጋበዝ ከአቅማቸው በላይ በሆነ እልልታና ጭብጨባ በኢትዮጵያ ውስጥ ሳይሆን በሌላ ዓለም ውስጥ ያሉ እስኪመስላቸው የሚያሳዩንን ያህል ተራምደዋቸው የሚመጡትን ምስኪን ህፃናት ቢያንስ ለሚዛናዊ ንፅፅር ይረዳ ዘንድ ለምን አይነግሩንም ወይም አሳዩንም? መልሱ አሳዛኝ ቢሆንም ግልፅ ነው። ከገዛ ራሱ መሪር እውነት እየሸሸ በየሳሻል ሚዲያው በመታደም ራሱን ማታለል የለመደበት ትውልድ የመከረኛ ወገኖቹን ሰቆቃ የሚነግረውን ወይም የሚያሳየውን የሚዲያ መስኮት  ለማየትም ሆነ ላይክ፣ ሸር እና ሰብስክራይብ ለማድረግ የሚያስችል ወኔውን የተሰለበ በመሆኑ ነው። አዎ! እየማቀቅን ካለንበት አገራዊና ሁለንተናዊ የውድቀት (የቀውስ) አዙሪት ሰብረን መውጣት ካለብን በዚህ ልክ ነው መነጋገር ያለብን። አዎ! አካፋን አካፋ ለማለት እየተሽኮረመምን ዘመን ጠገብ የመከራና የውርደት ቀንበር ሰለባዎች በመሆን ሳንኖር ኖርን እያልን የመቀጠሉ አስከፊና አስፈሪ አባዜ ይበቃናል!

7) አዎ! አስተያየት ሰጭው እንዳሉት ምንም እንኳ የነፃነትና የፍትህ ጥያቄን ከምር የሚያዳምጥ ህሊና እና የሚያስተናግድ ፈቃደኝነት ፈፅሞ የሌላቸው ቢሆንም በማፈን፣ በማዋከብ፣ በማሳደድ፣ በቁም በማሰቃየት፣ ፍትህን በመንፈግ፣ በየማጎሪያ ሥፍራው በማጎር፣ በመግደልና በማገዳደል የሥልጣን እድሜያቸውን ለሚያራዝሙ እኩያን ገዥዎች ጥያቄን ማቅረብ ትክክል ነው። ይህ ግን ፖለቲካ ወለድ የመከራና የውርደት ዶፍ  እየወረደበት ያለውንና ከምንም በላይና ከምንም በፊት ትኩረትና ሁለንተናዊ ርብርብ  የግድ የሚለውን ጉዳይ ወደ ጎን ትቶ ወይም ለስም መጠሪያ የምትሆን ፍርፋሪ እየወረወሩ ዘመናዊ የባህር ማዶ ገዳምና ቤተ እምነት  ለማሠራት  የዶላር ማሰበሰብ ዘመቻ ላይ የመጠመድን ወለፈንዴነት ትክክል አያደርገውም።

ከገዛ ራሳችን አስከፊና አሳፋሪ የሆነ ተደጋግሞ የመውደቅ አዙሪት ሰብረን ለመውጣት ከሚያስችሉን ዘዴዎች አንዱ በአንድ የጋራ ጉዳይ ላይ የምናደርገውን የሃሳብ ልውውጥ/ሂሳዊ ፍጭት ወደ የመማማር ግብአትነት መለወጥ ነው። ይህንን አድርገን በመገኘት ወደ ተሻለ የነፃነትና የፍትህ ፍለጋ ተጋድሎ ለመሸጋገር ስንችል ብቻ ነው ለዘመናት የዘለቀውንና ከአምስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ በተረኛ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቁማርተኞች ተባብሶ የቀጠለውን ሥርዓት በማስወገድ  እውነተኛ ፌደራላዊትና ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እውን ማድረግ የምንችለው።

እናም ልብ ያለው ልብ ይበል!

 

 

2 Comments

  1. ጽሁፍህን አይቸዋለሁ እንካ ስላንትያም መፍጠር አልፈለግሁም ማንነትህን ወደ ኋላ ላይ ስመለከት ኢትዮጵያዊ በሆኑ ጉዳዮች ከፊት ተሰላፊ እንደሆንክ አስታወስኩ፡፡ እንግዲህ እባብ ያየ በልጥ በራየ እንዲሉ በረቀቀ መንገድ ሁለቱ ትግሬዎች በዚህ መልኩ እየገቡ የአንድነቱን ሃይል ስለሚበትኑ በዛ በኩል ስላየሁት ነው፡፡ ለማንኛውም ትችቴን ለማጽናት ወይም ዳግም በለቀቅኸው ጽሁፍ አጸፋ አላስፈለገኝም፡፡ ለማንኛውም ትልቁን ጉዳይ አንርሳው የጠላት ሃይል መጠነ ሰፊ የትግል መስክ ዘርግቶ ወዳጅ መስሎ ጠላት ጠላት መስሎ ወዳጅ ሁኖ እያዋከበን በመሆኑ ጥንቃቄ አይከፋም፡፡ ለማንኛውም የኢትዮጵያ ጉዳይ የሚገድህ ወገን በመሆንህ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡

  2. I sincerely appreciate your real sense of civility which is terribly missing in most our conversations or arguments!
    As nobody has a monopoly of knowledge and wisdom , the way we all engage in the process of dealing with the very tragic challenges in our country absolutely matters a lot !
    Thank you once again !

Leave a Reply

Your email address will not be published.

186488
Previous Story

“ጉዟችን ወደ መዲናችን ነው” | ኮ/ል ጌታቸው ከግንባር ያስተላለፈው መልዕክት | “እነሱ የታጠቁትን ሁሉ ታጥቀናል”

ብልፅግና ፈረሶች 1 1
Next Story

ይድረስ ለብልፅግና ፈረሶች!

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop