እናንተ ፈስኩ! – በላይነህ አባተ

/

ነፋስና ጊዜ በበልጉ ዘርቷችሁ፣
እንደ ባድማ አረም ያገፈገፋችሁ፣
ይሁና ዘር አጥፉ እየተሻማችሁ፣
ብርቱ ክንድ መንግሎ እንሰተሚነቅላችሁ፡፡

ዘራቸው ተቆጥሮ ድሆች ይጨፍጨፉ፣
ዘር አይጥፋ ያሉ ወህኒ ይታጎሩ፣
እናንተ ለድግስ ሂዱ ተሰብሰቡ፣
ሆድን አስፍታችሁ ዛቁ ብሉ ጠጡ፡፡

ሕፃናት እናቶች የእንባ ጎርፍ ያፍስሱ፣
እናንተ ዶልቱ ገልፍጡና ሳቁ፣
የብርቱካን ውሀ ጨምቃችሁ ሰርብቁ፣
ጠጅ በብርሌ ብርዙንም ጨልጡ፣
ደም እንደሆነ ግን ጭራሽ እንዳትረሱ፡፡

ምዕመናን ታቦት ውስጥ መስጊድ ይቃጠሉ፣
እናንተ ግን በሱፍ ከራባት ታነቁ፣
ቁማርን ተንኮልን እንዳምናው ዶልቱ፣
እንደ በፊቶች መቃብር እስክትገቡ፣
አፈርና ትቢያ አመድ እስክትሆኑ፡፡

እንደ ዘመሚቶች እንደ ቅንቡርሶቹ፣
የሰማእት ሥጋን አጥንትን ቆርጥሙ፣
እንደ እምቧይ አብጣችሁ እስከምትፈርጡ፡፡

የፀደቀ የለም ውስዶ የእግዜርን ነፍስ፣
ተነቅሎ ይሞታል ይሸታል እንደ እርኩስ፣
ልክ እንደ ይሁዳ እንደነ ጲላጦስ፡፡

ያ ጊዜ እስኪመጣ እናንተ ፈስኩ፣
እናቶቹ ታርደው ህፃናት ሲያለቅሱ፣
አዛውንት ተሰደው መንገድ ዳር ሲተኙ፣
ፍትህ የጠየቁ ወህኒ ወርደው ሲያድሩ፡፡

እናንተ ፈስኩ!

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)
ታህሳስ ሁለት ሺ አስራ አምስት ዓ.ም.

ተጨማሪ ያንብቡ:  ‹‹በትግራይ ግጭት የተካሄደው የምርመራ ሪፖርት ዓለም አቀፍ ተቀባይነት አግኝቷል›› – ዶክተር ዳንኤል በቀለ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share