ድህነቷን እናፍቀዋለሁ፤ ሊያሳስበኝ ግን ልቦናዬ ጊዜ የለውም፡፡ ህይወት ረከሰ፤ ሞት ነገሰ! (ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ)

ኢትዮጵያ ድሀ የነበረች ጊዜ – ያኔ ያለው ለሌለው ያካፍል ነበር፤ የሌለው ጎዳና ወጥቶ፣ ደብር ተጠግቶ ለምኖ በልቶ ያድር ነበር፡፡ የድሀ ልጅ በባዶ እግሩ ትምህርት ቤት እየተመላለሰ ፊደል ይቆጥር ነበር፡፡ በኩራዝ ጭለማ ይረታ ነበር፡፡ . . . . ያኔ ነብስ ካወቅን ጀምሮ የሀገራችን ከድህነት መውጣት ያሳስበን ነበር፡፡ ወጣት ሆነን ሀገራችንን ከድህነት ለማውጣት እድገት በህብረት ዘመትን፣ መሰረተትምህርት ዘመትን፤ ሰላም እንድትሆን በብሄራዊ ውትድርና አገልግሎት ዘመትን፡፡
በወጣትነቴ ጠመንጃ ይዤ ዘብ የቆምኩላት ሀገር ዛሬ በጎልማሳነቴም ሰላም አለማግኘቷ ልቤ ድረስ ይጠዘጥዘኛል፡፡ ድህነቷንም እናፍቀዋለሁ፤ ድሀ ለምኖ የሚበላበትን፣ አባወራ ጥጥ ለቀማ ቆላ የሚወርድበትን፣ ‹‹ግፋ ቢል አዶላ!›› ብሎ ወርቅ ቁፋሮ በቀን ሰራተኝነት የሚሰደድበትን፣ . . . . ድህነቷን እናፍቀዋለሁ፤ ሊያሳስበኝ ግን ልቦናዬ ጊዜ የለውም፡፡
ህይወት ረከሰ፤ ሞት ነገሰ፡፡ ከእንቅልፌ የሚቀሰቅሰኝ የወፎች ዜማ ሳይሆን የሞት ዜና ነው፡፡ በድህነት ያለፉት እናትና አባቴ ሰው ተሰቅሎ ሲሞት አይተው ለሳምንታት እንቅልፍ አይተኙም ነበር፡፡ የእኔ ዘመን አገዳደል ያኔ አልነበሩም፤ የሀገሬ ልጆች ከዚያ ወዲህ ተጠበው የደረሱባቸው የጭካኔ ፍሬዎች ናቸው፡፡ ከእንቅልፌ ስነቃ ስለምሰማው ሞት ሳስብ ውዬ ስለእሱው ሳስብ ያሸልበኛል፡፡
በየት በኩል ስለሌላ ነገር ማሰብ ይቻላል! የሀገሬ መልክ ሆኖ የሚያሳስበኝ ሞት እንጂ ድህነት አይደለም፡፡ ስለሞት ባሰብኩ ቁጥርም በልጅነቴ የኖርኩት ሰላማዊ ድህነቷ ይናፍቀኛል፡፡ ሞት በሚዘመርባት ሀገሬ ውስጥ እየኖሩ፣ ከድህነት ሊፈውሷት የሚጥሩ ዜጎቿን ልረዳቸው አቅቶኛል፡፡ እኔ ግን እላለሁ! ኢትዮጵያ ከድህነቷ የምትወጣው ማለቂያ በሌለው የዜጎች ሞት ከሆነ፣ ለዘለአለም ድሀ ሆና ትኑርልን፤ እንኑርባት፡፡
ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢህአዴግ በምርጫ ዋዜማ የጀመረው እስር የ2007ን ምርጫ ጠቅልሎ ለመውሰድ ያደረገው መጀመሪያው ርምጃ ነው!!! (አንድነት ፓርቲ )

1 Comment

  1. በአንድ የዓለማየሁ ገላጋይ የመድረክ ፕሮግራም ላይ ከአድማጭ የተነሳ ነገር ይህን የአንተን ሰቆቃ ሳነብ ትዝ አለኝ። ደራሲ አለማየሁ ገላጋይ መሻሻል የማያሳይ የሆነ ሃገር ነው እያለ ሲናገር ስለ ጋሪ ያነሳና ዝናብና ጸሃይ እንኳን እንዲከላከል አስቦ እንዴት ያን እንኳን ማድረግ ይከብዳል። መለወጥ አልቻልም እያለ ሲናገር ከታዳሚዎች አንዲት ቆንጂዪ ልጅ ትነሳና ” ችግሩ ምንድን ነው ባንለወጥ እሳ” ምን ችግር አለበት አለች። ሆዴን ነው ያሻረችው። መለወጥ አውሬ ለመሆን ከሆነ በአፍንጫዬ ይውጣ። ህጻናት በእሳት እየጋዪ፤ አዛውንቶች እየተደፈሩ፤ የሰው አንገት በቋንጭራ እየተቀላ ስንዴ ቢመረት፤ ፎቅ ቢደረደር ጥቅም የለውም።
    እኔም እንዳንተው የሚናፈቀኝ ያ የድሮው ዘመን ነው። ሰው በሰውነቱ የሚለካበት። አዎን የወያኔ፤ የሻቢያና የኦነግ ግርፎች የቀድሞ ሥርዓት ናፋቂ ይሉናል። እነርሱ ስርዓት አፍራሽ መሆናቸውን ማን በነገራቸው። ጠ/ሚ አብይ ነገሮችን አቅሎ ማየቱን ማቆም አለበት። ይህ ነገር ሲጠፋ፤ ሲቀጣጠል፤ መልሶ ሲፈጋ ቆይቶ በህዋላ የሚበላው ራሱንም ጭምር ነው። የኦሮሞ ጽንፈኞች አብደዋል። ለነገሩ የተቃመሱት በወያኔ አይደል። እብድ ለእብድ ተያይዞ ገደል። ይህ አሁን በየክልሉ የተውሶ ጠበንጃም ሆነ ታንክ ወይም ሌላ የጦር መሳሪያ ይዞ ህዝብን የሚያሸብረው የሙታን ጥርቅም ሁሉ የዓለም ጦር ሜዳ በሰው አልባ ውጊያ እየተከናወነ መሆኑ አልገባቸውም። David Hambling የተባለ ጸሃፊ የጻፈውን Swarm Troopers: How small drones will conquer the world መመልከት ብቻ በቂ ይሆናል። ግን በዘሩና በቋንቋው ለሰከረ መጽሃፍት ምን ሊያረጉለት። ከሁሉ በጣም የሚያሳዝነኝ ተምረናል ፊደል ቆጥረናል የሚሉ በጥቅል አብደው ሳይ ነው። በቅርቡ አቶ በቀለ ገርባ የሰጠውን ቃለ መጠይቅ ላዳመጠ እነዚህ ሰዎች የጭንቅላት በሽታ ያለባቸው እንጂ ጤነኞች እንዳይደሉ በቀላሉ መረዳት ይቻላል። ኦሮሞ ሞተ አማራ ሞተ ሰው ነው። የአንድ ደም ከሌላው የተለየ አይደለም። ግን በዘር ፓለቲካ ለበጨጩ ስመ ምሁራን የሚታያቸው ዘርና ቋንቋቸው ብቻ ነው። ህዝባችን በድህነቱ ያለውን ቆሎ ቆርጥሞ በሰላም እንዳይኖር የብሄር ነጻነት እያሉ ለዘመናት ሰቆቃ የሚያወርድ እነዚህ ቅጥረኛ ጠበንጃ አንጋቾች በልመና ሳይሆን በሃይል የገደለውን በመግደል ብቻ ነው ነገሩን መግታት የሚቻለው። ያው ታሪካችን ሲገድሉና ሲገዳደሉ ኖሩ አይደል የሚለው (ጦቢያ መጽሃፍን ይመልከቱ)።
    አሁን በወለጋና በሌሎች አካባቢዎች ኦነግ ሸኔ የሚፈጽመው ጭፍጨፋ በሰሜን የሞከሩት የከሸፈባቸው የውጭና የውስጥ ሃይሎች የሚቆሰቁስት ተግባር ነው። የአሜሪካው የስለላ ድርጅት በኢትዮጵያ ላይ ሥራ አልፈታም። በዚህም በዚያም ድንጋይ በመፈንቀል ላይ ናቸው። የሚያገኙትም የጊንጥ ክምችት ነው። እነርሱን ነው አይዞአችሁ እያሉ በተለያየ መልኩ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚሉኳቸው። ህዝባችን ሊነቃ ይገባል። ከንፈር እየመጠጡ ዝም ከማለት በተቀናጀ መልኩ ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት መንግስት ይህን የወለጋ ግድያ እንዲያቆም መጠየቅ ያስፈልጋል። በዝምታ ከእያንዳንድ በር ላይ መከራው እስኪደርስ መጠበቅ ለሞት እጅን ፈርሞ መስጠት ነው። የመንቂያው ሰአት አሁን ነው። በተረፈ ያ የቀደመው መተዛዘንና መተሳሰብ፤ ከየት ነህ ብሎ ሳይጠይቅ ቤት ለእንግዳ ብሎ ማስተናገድ ላይመለስ ተሸኝቷል። ዛሬ በኦሮሞ ክልል ተወልደው ኦሮሚኛ አልተናገራችሁም በመባል የሚገለሉ ብዙዎች ናቸው። አይ የዘር ፓለቲካ፤ አይ የክልል ፓለቲካ ማንን ጠቅሞ ማንን ጎዳ? አሁን ማን ይሙት የምታጠባ እናት አንገትን የቆረጠ ኦሮሞ ለኦሮሞ እናቶች ያዝናል። በጭራሽ። ሙት ፓለቲካ። በቃኝ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share