August 19, 2022
7 mins read

የግጭት ወሰን ለማስመር የሚሮጠው የአዲስ አበባ አስተዳደር በህዝባችን ትግል ሊገታ ይገባል – ባልደራስ 

balderas abssnia

balderas abssniaመግለጫ

የአዲስ አበባ ከተማ ከኦሮምያ ክልል ጋር የአስተዳደር ወሰን እንዲኖራት ለማድረግ መስመር በማስመር ላይ ነን የሚል ዜና ከወይዘሮ አዳነች አበቤ ቢሮ ተሰምቷል። እኚህ ከንቲባ የኦሮምያን  ህገ መንግስት ተግባራዊ  ለማድረግ አንደሚሰሩ በቅርቡ በምክር ቤቱ ስብሰባ ላይ ያሳወቁ መሆናቸው አይዘነጋም። ከንቲባዋ ይህንን ባሳወቁ በጥቂትጊዚያት ዛሬ ደግሞ በአዲስ ኣበባና በኦሮምያ መካከል  የአስተዳደር ወሰን  ለማስመር ሲጣደፉ እየታዩ ነው።  መቼስ ይህ ጥድፊያ አሻጥር እንዳለው ለማንም ግልጽ ነው። ከሁሉ በላይ ግን የሃገራችን ህዝብ የህወሃት ኢሕአዴግን መንግስት በቃኝ ብሎ አምርሮ ታግሎ  የጣለው በሃገራችን ውስጥ መዋቅራዊ ለውጦች እንዲመጡ፣ በፌደራል ስርዓቱ ላይ ምክክር አድረገን አጠቃላይ የሃገራችንን የፖለቲካ አሃዶች ለመከለስ፣ ብሎም በዚህ በሚሻሻል የመዋቅር ለውጥና የህገ መንግስት ማሻሻያ ስር የአዲስ አበባም የመልካም አስተዳደር ጉዳይ፣ የአስተዳደር ወሰን ጉዳይ፣ የከተማዋ የፖለቲካ አሃድነት ጥያቄ ጉዳይ እንዲፈታ ነበር። ባለፉት  አመታት  መንግስት  በአንድ  በኩል የአስተዳደር፣  ወሰንና ማንነት ኮሚሽን አቋቁሜ የሃገሪቱን ተያያዝዥ ጉዳዮች እፈታለሁ ብሎ ሶስት ኣመት ሙሉ ኮሚሽኑ ለአ ስተዳደር፣ ማንነትና ወሰን ጉዳዮች አንዲት ጠብታ  መፍትሔ ሳያቀርብ የህዝብን ገንዘብ አክስሮ እንዲከስም ተደርጓል። መንግስት በአጠቃላይ ላሉ የኣስተዳደርና ወሰን ጉዳዮች እልባት መስጠት ተስኖት እስካሁን አለ። ከፍ ሲል እንደገለጽነው ብዙ ሳንካና ግጭት ያለበትን ህገ መንግስት አሻሽሎ ለአዲስ አበባ ከተማ በሚገባ የተጠና ማስተር ፕላን ሰርቶ በዚያ መሰረት ወሰን ለመመስረት መነሳት የከተማዋን  እድገት ያሳልጣል።  ነገር ግን በተለይ በዚህ ወቅት ማንነትና  መሬት በተጣበቁበት  ሃገር ውስጥ የወሰን ጉዳይን አንስቶ በጥድፊያ ለመከለል መሞከር ግጭትን መጥመቅ ነው። የአዲስ አበባ አስተዳደር በዚህ ወቅት የህዝቡን ስራ ማጣትና የኑሮ ሁኔታ ለመፍታት እንደ መታገል ወቅታዊነት በሌለው የግጭት ስራ ላይ ተጠምዶ ይገኛል።

በእኛ እምነት ይህ የአዲስ አበባ ወሰን ጉዳይ መጀመሪያ በሃገር ደረጃ የፌደራል ስርዓትና የህገ መንግስት ማሻሻያ ተደርጎ ሊከወን የሚገባው ጉዳይ ነው። ሃገሪቱ በገለልተኝነት የሁለት ክልሎችን አስተዳደራዊ   ወሰን የሚከውን የባለሙያ ተቋም እንኳን የሌላት ሃገር ናት።  ስለሆነም ሃገራችን አሁን ያለችበትን ያለመረጋጋት ከግንዛቤ በማስገባትና የሚጠበቀውን የህገ መንግስት  መሻሻል ስራ ከግንዛቤ በማስገባት የአዲስ አበባን ወሰን ከማስመር መታቀብ ያስፈልጋል። በተለይም ደግሞ የአዲስ ኣበባ ህዝብ ቆጥቦ የሰራቸውን የኮንደምንየም የመኖሪያ ቤቶች ወዲያና ወዲህ ማድረግ መሬትና ማንነት በተጣበቀበት  መርህ ስር ብዙ እምቅ ግጭቶች አሉበት። ስለሆነም የአዲስ አበባ አስተዳደር ከልማት ይልቅ በየጊዜው ግጭት ባላቸው ጉዳዮች ውስጥ አየተዘፈቀ የከተማችንን ህዝብ ሰላም መንሳት  የለበትም። ከዚህ ስራው ታቅቦ የሃገራችን የፖለቲካ አሃዶች እንደገና በጥናት እንዲከለሱ የአዲስ አበባ አስተዳደር ጉዳይም በዚህ ማእቀፍ ስር እንዲሆን ቅቡልነት ባለው የምክክር  ሂደት ሊፈታ ይገባል። ስለሆነም  ይህ ህገ ወጥና ህዝብ ያልመከረበት ድርጊት ተቀባይነት እንደሌለው እየገለጽን  መላው የአዲስ አበባ ህዝብ መብትህን ለማስከበርና ከተማህን  ለመጠበቅ ቆርጠህ አንድትነሳ ጥሪያችንን  አናቀርባለን።  ዘወትር ከግጭት ጠማቂነት የማይታቀበው የወይዘሮ አዳነች አስተዳደር በህዝባችን ንቁ ትግል ሊገታ ይገባል።

የድጋፍ በሰሜን አሜሪካ

2 Comments

  1. ነፎዝ ፓለቲካ አርቆ አያይም። የራሺያው መሪ “የታላቋ ሶቪዬት መፈራረስ የ 20ኛው ክፍለ ዘመን ትራጀዲ ነው” እንዳሉት ሁሉ ዛሬም በጎሳና በዘር እንዲሁም በቋንቋ የሰከረው የሃበሻው ፓለቲካ ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ በሚል ፈሊጥ ህዝባችን አረንቋ ውስጥ እየሞጀሩት ይገኛሉ። የሶቪዬት መፈራረስ ዓለምን ሁሉ እንዳስፈነጠዘው እኔን አያስፈነጥዘኝም። እነዚያ አብረው ይኖሩ የነበሩ ሃገሮች የራሳችን ሃገር እንሆናለን በማለት እልፍ መከራ ውስጥ እንደገቡና አሁን እዚያው የመከራ ደመና ውስጥ እንዳሉ መረዳት አይከብድም። ከእነዚህ ስመ ነጻ ሃገሮች ጎን ያሉ የበፊት ጎረቤቶቻቸውን አባረውና በድንበርና በሌላም ጉዳይ ተፋልመውና አፋልመው ዛሬም እንዘጥ እንዘጥ እንደሚሉ በዪክሬን የሚወርደውና የወረደው መከራ ዓይን ላለው አይቶ ከሌለው ደግሞ ዳብሶ መረዳት ይቻላል። በአዘርባጃንና በአርሜኒያ ግጭት የደረሰውን ግፍና መከራ የራሽያ ጦር ገብቶ እስኪገላግል ድረስ ያንተ ያለህ የሚያሰኝ ነበር። ግጭቱ አሁንም አልቆመም። ግን ከመካከላቸው የማይገፋ ሃይል ስለቆመ ለጊዜው በረድ ብሏል። ይህን ለምሳሌ ጠቃቀስኩ እንጂ ሶቪየት ህብረት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደ እንቧ ካብ ከተናደች ወዲህ አያሌ መከራዎች በምስራቅ አውሮፓ ተከስተዋል። ይህ የሚያሳየን ለውጥ የተባለው ትሻልን ሲሉ ትብስን መሆኑን ነው። የኢትዪጵያም እድል ፈንታ የተሰፈረው በዚሁ በአለም የፓለቲካ አሰላለፍና የንፋስ አቅጣጫ ለመሆኑ የቆመ ምስክር ነው።
    እድሜ ለዘረኛው ወያኔ ሃገሪቱን በልዪ ልዪ የመከራ ዶፍ ካደከማትና አጥንቷን ከጋጣት በህዋላ አሁን ደግሞ ትግራይን ሃገር አረጋለሁ በማለት እየዛተ ይገኛል። ነገርየው እብደት ቢሆንም ከሆነ እሰየው ነው። አይተናል የተገነጠሉ፤ ሃገር እንሁን ብለው ባንዲራ ያውለበለቡ እዚህ ግባ የሚባል ቆመንለታል ለሚሉት ያደረጉት ነገር እንደሌለ። ስለዚህም ነው የገንጣዪችና የከፋፋዪች ፓለቲካ ለራስ ጥቅም እንጂ ለህዝባቸው አይረባም የምንለው። አሁን ጊዜው ዘሞ ወያኔ ከሥልጣን ያለ ልቡ ተገፍቶ በሥፍራው የኦሮሞ ጠባብ ብሄርተኞች ጊዜው የእኛ ነው በማለት ወሰን ሲያካልሉ፤ ሰው ሲገድሉና ሲያባርሩ ማየትና መስማት ይዘገንናል። ግን ይህ የሚጠበቅ ጉዳይ ነው። ሃገሬ ምድሬ የቆምኩበት ደጃፍ ነው ብሎ ከሚያምኑ ገልቱ ፓለቲከኞች ምን ይጠበቃል። ያለፈን ታሪክ ትላንት እንደሆነ በመቁጠር ብቀላንና ጥላቻን የተላበሰ ልብ እንዴት ከራስ ያለፈ እይታስ ይኖረዋል? ግን አንድ ነገር እንወቅ። እንኳን ይህ ካርታ የለሽና ህዝብ አክ እንትፍ ያለው የክልል ፓለቲካ ቀርቶ የበርሊን ግድግዳም በጊዜው ተደርምሷል። ፓለቲካን ጊዜ ይሽረዋል። ዛሬ ለስማቸው ያቆሙትን ሃውልት ነገ አንድ ይንደዋል። ፓለቲከኞችና ፓለቲካ እንደ እስስት መልካቸውን በየጊዜው ይለዋውጣሉ። Svetlana Alexievich and Bela Shayevich “Secondhand Time: The last of the Soviets” በተሰኘው መጽሃፍ ላይ 70 ዓመት ሙሉ ስንት ህዝብ ያለቀበትን የሶሻሊዝም/ኮሚኒዝም መመሪያ ንደው በዚያው ስርዓት ያገለግሉ የነበሩ ተቋማትና ሰዎች እንደ አሮጌ ቁና ሜዳ ላይ የተጣሉበትን በመጽሃፋቸው ሲያትቱ ለመሰብሰብም ለመበተንም ጊዜ አለው የሚለው የጠቢቡ ሰለሞን ቃልን ወደ ልብ ያመጣል። በእኛ ሃገርም ወያኔ የኢትዮጵያን ሰራዊት በትኖ የራሱን ሲያነግስ የሆነው ተመሳሳይነት አለው። ባጭሩ በዚህ ምድር ላይ እኔን እዪኝ ማለት ጊዜአዊና ሃላፊ እንጂ ቋሚ እንዳይደለ አስረግጦ ልብ ላለው የምናየውና የምንሰማው ይናገራል። የአዲስ አበባ ከተማም ከኦሮሞ ክልል ጋር የአስተዳደር ወሰን እንዲኖረው የማድረጉ ብልሃትም ተንኮልና ሸፍጥ ያለበት እንጂ ለኗሪው ህዝብ ሰላምና ደስታን አያስገኝም። ውጤቱን ቆይተን እንይ። በቃኝ!

  2. ጎበዝ ትንሽ እንፈር አቶ ታዲዮስ ታንቱ ፤ተመስገን ደሳለኝ፤ስንታየሁ ቸኮል በእስር እየማቀቁ ነው ለራሳቸው ጉዳይ የገቡ አልመሰለኝም ኢትዮጵያዊ የት ነው?

Leave a Reply

Your email address will not be published.

5433cvc
Previous Story

የኢትዮጵያ ማክሮ ኢኮኖሚ ቀውስና የአይኤምኤፍና የዓለም ባንክ  ፕራይቬታይዜሽን ሴራ!! – (ክፍል 3)  

299755910 2193320627496067 6371529014738965991 n
Next Story

ሰው ለሰው እረኛ መሆን ካልቻለ ሠላምን አያገኛትም – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop