የመሬት እድሜ ስንት ነው? እንዴትስ ለማወቅ ይቻላል? ስነ መለኮትና የተፈጥሮ ሳይንስ አመለካከት

ክፍል 3 ካለፈው የቀጠለ

አኒሳ አብዱላሂ

10.07.2022

ስለ ሰው ፍጡር ምንነት ውይይት በሚደረግበት ወቅት ከራሱ አልፎ ከመሬት መፈጠርና እድሜ ጋር ተያይዞ በጥልቀት ለማወቅ በተፈጥሮ የሳይንስ ሊቃውንቶች ዘንድ እንደ እሳት የሚንጎበጎብ የውስጥ ፍላጎታቸው እንደሆነ የሚነገር ነበር። ይህንን ሁናቴ በአግባቡ ለመተንተን የሚያስችሉ ደግሞ ሁለት መንገዶች ሲኖሩ አንደኛው በፍልስፍናና እምነት ላይ የሚመሰረት ገለፃን አምኖ መቀበልን ብቻ የሚጠይቅ ሲሆን ከዚህ በተቃራኒ የሚገኘው ደግሞ በተፈጥሮ ሳይንስ ከዬት መጣሁ? ለምንስ? እንዴትስ? ወዴትስ? በተሰኙ ጥያቄዎች ላይ ተንተርሶ በሚደረግ የምርምር ውጤት ላይ በሚገኝ ትንታኔ ላይ በመደገፍ መልስ ለማግኘት የሚጥር ሆኖም  ግን ሁሌም ለእርምት ዝግጁ የሆነ የአቀራረብ ዘዴ ነው። ስለ ሰው ፍጡር ምንነት ያለንን አስተያየትና ግንዛቤ በሌላ ጊዘ የምንዳስሰው ስለሚሆን በዚህ እትም የመሬትን እድሜና ከዚህ ጋር ተያይዞ ያለውን የእድሜ መተመኛ ዘዴዎች በሚመለከት አጠር ባለ መልኩ እንደሚከተለው እናቀርባለን።

ስለ መሬታችን አፈጣጠርን እስካሁኑ ወቅት ድረስ ሊኖራዝ ስለሚችለው እድሜዋ በሚመለከት ይፋ የሆኑ የታሪክ ትንታኔዎችን ስንዳስስ የሚከተለውን እናገኛለን። ለምሳሌ

በአይሁድ እምነት ላይ ተመስርቶ የተቀመረው የአመት ቆጠራ እንደሚገልፀው የመሬት እድሜዋ 5778 አመት ብሎ ሲያስቀምጥ፣

መፅሀፍ ቅዱስ ደግሞ በበኩሉ 6021 አመቷ ነው ሲል.

ሽፈራው ሉሉና እንግዳሸት ቡናሬ ደግሞ መፅሀፍ ቅዱስን ማጣቀሻ አድርገው 6756 ዓመት ነው ተብሎ የተሰላውን ስሌት እንመለከታለን። የአለምና በውስጧ የሚገኙ ፍጥረታትን አስመልክቶ በእስልምናም ሆነ በአይሁድ እምነት ከሚሰጡት እሳቤዎች ጋር ከሞላ ጎደል ተመሳሳይ ሲሆኑ ሁሉም በቅዱስ መፅሃፎቻቸው ውስጥ ግልፅ የሆነ የእድሜ ልክ አልተገለፀም። ሆኖም የሳይንስንና የኃይማኖት መረጃዎችን በአንድ መስመር ለማገናኘት የታላቁ ፍንዳታ ፅንሰ መሰረቱ ፈጣሪ ነው የሚል እሳቤ አልፎ አልፎ መነሳቱ አልቀረም ምንም እንኳ በሁለቱም ጎራዎች ሰፊ ድጋፍ ለማግኘት ባይችልም።

የተፈጥሮ ሳይንስ ጠበብቶች የአለምንና የሕያዊያንን፣ የእፀዋትን አፈጣጠርና እድሜን አስመልክቶ የራሳቸው ቀመርና ምን? የት? እንዴት?! ተብለው በሰው ፍጡር ስለሚጠየቁት ጥያቄዎች የራሳቸው መልሶችና የአተናተን ዘዴዎች አሏቸው። ለዚህም የሚገለገሉባቸው ዘዴዎች የሰው ልጅ  ሲፈጠር የተጎናፀፋቸውና ስሜቶቹን የሚገልፅባቸው “ማየት፣ መስማት፣ ማሽተት፣ መዳሰስ፣ ማጣጣም፣” የመሳሰሉትን የስሜት መግለጫዎች ብቻ ሳይሆኑ በየጊዜው በሂደት የሚገኙ ዘመናዊ የሂሳብ ማሳለጫዎች(ኮምፕዩተር) ዘመናዊ የቴክኒክ መሳሪያዎችን ጭምር ለአገልግሎቱ ያውላል።

የኃይማኖት እምነቶች ስለ አለምና ስለ ሰው ፍጡር ያላቸውን ግንዛቤ የሚያስረዱበት ዘዴ ከሳይንሱ ጠበብታት የተለየ ሲሆን ዋና ትኩረታቸው ሥዕላዊ ገፅታዎችንና ትንታኔዎች ላይ የተመረኮዘ ሲሆን በተለይም ደግሞ የዚህ ሁሉ ፍጥረታት ምንጭ ማን ነው? ከሚለው ላይ እንደሆነ የሚሰጧቸው የእምነት ሰበካዎችና ትንታኔዎቻቸው የሚያመላክቱት ናቸው።

የሰው ፍጡር መቼና እንዴትስ ስለ ራሱና ስለሚኖርባት አለም ማሰብ እንደጀመረ በትክክል ለማወቅ ባይቻልም በቀድሞ የሥልጣኔ ዘመን በፊት የሚኖሩ ፍጥረታት የጊዜ ግንዛቤዎቻቸው የሚመነጩት የብርሃንና ጨለማ (በቀንና ማታ) መደጋገም፣ የጨረቃ ምስል መለዋወጥ፣ የኮከቦች ቦታቸው መቀያየር፣ እንዲሁም በጊዜ ሂደት የሚደጋገሙ ክስተቶችን በመከታተል ላይ የተመሰረቱ እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት የሚገልፁት ናቸው። ይህ ሁናቴ በበርካታ የኃይማኖት እምነት ቀኖና በይፋ መሰበክ ከተጀመረ በኋላ ግን ፍጥረታት መቼ? እንዴትስ? መጨረሻችንስ ምንድን ነው? የሚሉትን ጥያቄዎች ከሚሰጠው የእምነት ሰበካ ጋር እያመሳከረ መልሶችን ለማግኘት ማሰላሰልና የራሱን ግንዛቤዎች በአደባባይ መገልፅ የጀመረው። ይህ ማለት ግን ሂደቱ እንከን የለሽ ነበር ማለት አይደለም። ስለነጋሊሌዮና መሰል ጓደኞቹ ታሪካቸውን ለማወቅ የጣረ ማናቸውም ሊቃውንት በቸልታ የሚያልፈው ሁናቴ እንዳልሆነ ማገናዘብ የቻለ ሁሉ የሚያውቀው ነው። ለማንኛውም ይህንን  በመረዳት ይመስላል ለምሳሌ በአይሁድ የዘመን አቆጣጠር አለም የተፈጠረቺው በ 6 ኦክቶበር 3761 ዓ.ም ከምሽቱ 23 ሰአት ከ 11 ደቂቃ ከ 20 ሴኮንድ እንደሆነ በምላሽነት ለመስጠት ጥረት ተደርጎ የነበረው።

ይህ ብቻ አይደለም። ከዚሁ ጋር በተያያዘም በአየርላንድ ኗሪ የነበረው ሊቀ ጳጳስ ጀምስ አሸር (James Usher) ና ጆን ላይት ፉት John Light Foot) በመተባበር ባዘጋጁትና በ 1650 ዓ.ም. ይፋ ባደረጉት የዘመን መቁጠሪያ  አለም የተፈጠረቺው ከክርስቶስ ልደት በፊት በ23 ኦክቶበር 4004 ዓ.ም እንደነበር ተገልጿል። ለዚህም በመረጃነት የተጠቀሙት እነሱ በሕይወት እስካሉ ድረስ የቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳትና የነገስታቱ የሥራ ዘመናቸውን ደማምረው ባገኙት ውጤት እንደነበር በተደረጉት ታሪካዊ ጥናቶች የሚያመላክቱት ናቸው። በ 10 ኖቬምበር 4004 ዓ.ም ሰኞ ለት ከክርስቶስ ልደት በፊት አዳምና ሄዋን ከገነት እንደተባረሩም በ 1650 ዓ.ም. በሊቀጳጳሱ መነገሩ የሚደበቅ ሚስጢር አልነበረም።

ይህንን ቀመር በታሪክ እውነትነት የተቀበሉ አሁንም ድረስ በዚሁ የፀኑ የመሬት እድሜ ግፋ ቢል በ 10 ሺዎችና ከዛም በታች የሚገምቱ፣ ራሳቸው መጠራት እንደሚፈልጉት ባይቢሊካል ክሬአሲዮኒስት (biblical creationist) በምንም አይነት ከዚህ ግመት የማይዛነፉ የመፅሃፍ ቅዱስ ቃልን እንዳለ በውነትነት አሁንም ድረስ በስብከታቸውና ትንታኔዎቻቸው የሚገልፁት ይገኛሉ። በመሬት ሆድቃ ውስጥ የሚገኘውን የእሳተ ጎመራ ሙቀት በመነሻነት በመውሰድ መሬት በዚያን ወቅት ዳረቻዋና የአየር ሽፋኗ ያላትን የሙቀት ልክ ለመያዝ ምን ያህል ጊዜ ይፈጅባታል የሚለውን የእድሜ ተመን በማሰላሰል የፊዚክስ ጠበብት የነበረው ዊሊያም ቶምሰን (William Thomson) በኋላ ሎርድ ኬልቪን (Lord Kelvin) በምርምር ያገኘውን የ 30 ሚሊዮን እድሜ አቅርቦ እንደነበርም የታሪክ ድርሳናት የሚገልፁት ናቸው።

በተመሳሳይ ሁኔታ ሽፈራው ሉሉና እንግዳሸት ቡናሬም በበኩላቸው ጊዜን በሚመለከት ስለ ምንነቱም ሆነ ውስጣዊ ይዘቱን አስመልክቶ አረዳዳቸው ምን እንደሆነ ሳይገልፁ እንዲያው በደፈናው አለም ከተፈጠረቺበት ጊዜ ጀምሮ የነበረው “ከጥፋት ውሃ በፊትና በኋላ” (2256 ሲደመር 2000 = 6756) ነው ሲሉ በፅሁፋቸው ዘግበዋል። በዚህ ብቻ አላቆሙም። “በኢትዮጵያዊያን የዘመን አቆጣጠር ቀመር ከአዳም እስከ ክርስቶስ ልደት 5,500 አመት ነው። ከአዳም እስከ ጥፋት ውሃ (ማየ አይህ) 2,256 አመት ነው። ከጥፋት ውሃ (ማየ አይህ) እስከ ክርስቶስ ልደት 3,244 አመት ይሆናል። ስለዚህ ከጥፋት ውሃ (ማየ አይህ) እስከ አሁኑ ዘመን ድረስ 5,254 አካባቢ ነው። ስለሆነም የአለም ዕድሜ በቢሊዮን አመታት የሚቆጠር ሳይሆን በጣም አጭር መሆኑን እንረዳለን።” ሲሉ እርግጠኝነታቸውን በማስረገጥ በትንተናቸው ገልፀዋል።

ቀደም ብለው “እግዚአብሄር ሰማይንና ምድርን ሲፈጥር ዘመንን መቁጠር እንድንችል የጊዜን መቁጠሪያ አብሮ ፈጥሮልናል።” ካሉ በኋላ ይህንን ከሰው ፍጥረት የእድገት ታሪክ ጋር እጅግ በጣሙኑ የተቃረነ ፍረጃ አስቀመጠው የፈረደባቸውን “የዝግመተ ለውጥ አማኞች መነሻቸው እግዚአብሔርን መካድ ስለሆነ፣ ፈጣሪ ከሌለ ደግሞ በቢሊዮኖች አመታት የዝግመተ ለውጥ፣ ፍጥረታት ያለ ፈጣሪ፣ ልጅ ያለ ወላጅ፣ እንቁላል ያለ ዶሮ ይመጣል (ለመሆኑ ዶሮ ነው ወይንስ እንቁላል መጀመሪያ የተፈጠረው? በኔ የተጨመረ) በማለት ሰውን ማጃጃል ነው።” በማለት የጭቃ ጅራፋቸውን በማስጮህ ጥላሸት ይቀቧቸዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  እሬቻ ከገዳ የወረራ ሥርዓት ጋር ምን ያገናኘዋል? እሬቻስ የማን በዓል/ባሕል ነው? (አቻምየለህ ታምሩ)

የሚያሳዝነው ይህንን የመሰለ ውንጀላቸውን ያቀረቡት በ አፕሪል 23 ቀን 2019 ዓ.ም. ይፋ ባደረጉት መፅሄታቸው ሲሆን ቢያንስ ቀደም ብለው ላለፉት 15 አመታት የተደረጉ የተፈጥሮ ሳይንስ የምርምር ውጤቶችን ጊዜ ወስደው ለማጥናትና ለመረዳት ምንም አይነት ጥረት ባለማድረግ ነው እንግዲህ ወደዚህ የተሳሳተ ድምዳሜ ለመንደርደር የበቁት። ብታልም ጥሬዋን ሆነና ነገሩ በብዙ ሁናቴ የሚታሙ፣ ለምንም ነገር ወደኋላ የማይመለሱ፣ በተቻላቸው መጠን የተሳሳተ የሳይንስ ምርምር ውጤት በማሰራጨት ብዥታና ጥላሸት በመቀባት ግላዊ አጀንዳቸውን ተግባራዊ ለማድረግ የሚንፈራገጡ ሊቃውንት ተብዬ ተመራማሪውችን በዋቢነት በመጥቀስ የመሬት እድሜን ከቢሊያርድ ወደ አሥር ሺዎች አመታት ለማሳነስ የተንቀሳቀሱት።

ለዚህም ነው ከመጀመሪያውኑ “የአለም እድሜ በቢሊዮን ሳይሆን በጣም አጭር መሆኑን” ማስፀረስ አላማን አንግበው የተነሱ በመሆናቸው የነሽፈራው ሉሉና እንግዳሸት ቡናሬም በፅሁፋቸው እንዳረጋገጡት በሥም ባይጠቅሷቸውም ከኃይማኖት ጉያ ተሸጉጠው የአስተማሪዎቻቸውን የክሬኤሽንስቶችን አጀንዳ በኢትዮጵያ ተግባራዊ ለማድረግ የተሰለፉ ሆነው የተፈጠሙት። የስድብ ጋጋታና ጥላሸት መቀባት የማን አጀንዳ እንደሆነ እነሽፈራው በዋቢነት የሚጠቅሷቸውንና፣ በነሱ ላይ ቀርበው የነበሩ ትችቶችን ማገላበጡ ብቻ በቂ ነበር፣ አሁንም ነው። በተለይም ለሀገሩና ለወገኑ ቀና አስተሳሰብ ያለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ በተለያዩ ቋንቋዎች በአሜሪካና በአውሮፓ፣ በአፍሪካ ሰለ ዝግመተ ለውጥ፣ ስለ ታላቁ ፍንዳታ የተፃፉትን ከበርካታዎቹ ጥቂቶቹን ብቻ ቢመለከቱ የየራሳቸውን ግንዛቤ ሊያዳብሩ ከመቻላቸው በላይ ስለ አለምና ስለሚኖሩባት መሪት የተሳሳተ ምልከታቸውን የሚያሰወግድላቸው ለመሆኑ በርግጠኝነት ለመናገር የሚቻል ነው የሚል ምክር ቢጤ መለገሱ መዳፈር አይመስለንም።

የተፈጥሮ ሳይንስ ሊቃውንቶች የመሬትን እድሜ በሚመለከት የሚሰጡት አስተያየት ከኃይማኖቶቹ እምነት የተለየና ግምቶቻቸውና የእድሜ ተመኖቻቸው እጅግ በጣም የተራራቁ ቢሆኑም ሁለቱን ክፍሎች ለማቀራረብ የሚደረጉ ጥረቶች እንዳሉ ይታወቃል። ሊቃውንቶቹ የሚመኩበት ሁናቴ በምርምር በሚያገኙት ውጤቶችና አዳዲስ እውቀቶች ላይ ሲሆን የሚያቀርቡት መረጃዎቻቸው ትክክለኛነት የሚላበሱት ግን ይህንን የሚያፋልስባቸው አዳዲስ መረጃዎች በሌሎች ሊቃውንቶች ለእይታና ለእርምት ቀርበው በርግጥም በአብዛኛው በሚታመኑባቸው የምርምር ዘዴዎችን በመጠቀም በተደጋጋሚ ተመሳሳይ ውጤቶች መሆናቸው ሲረጋገጥ ብቻ እንደሆነ በባለሙያውቹ ተበክሮም የሚገለፅ ነው። የሆኖ ሆኖ በተፈጥሮ ሳይንስ ምርምር የተገኙ ውጤቶች ከእምነት ተቋማት ከሚገለፁት እጅጉኑ የተለዩ ቢሆንም በሊቃውንቶቹ ቀርበው የነበሩትም (ከ 75 000 እስከ 3 ሚሊያርድ አመት የሚደርሱ) ልዩነቶች ስለነበራቸው ከፍተኛ እረፍት የነሳቸው ክስተት እንደነበረ የተደበቀ ሚስጢር አልነበረም።

ተቃዋሞዎቻቸውም ይህንን ድክመታቸውን ለመሰሪ ተንኮሎቻቸው  ለመጠቀም በርካታ ጥረቶች ማድረጋቸው አልቀረም። እምብዛም አመርቂ ውጤት አላስገኘላቸውም እንጂ። ሽፈራው ሉሉና እንግዳሸት ቡናሬም “በተለያዩ ጊዜ የተደረጉ ጥናቶች የሚያመላክቱት እድሜን ለመለካት የምንጠቀምበት የራዲዮ አይሶቶፕስ የልውጠት ሂደት(decay rate) ትክክል አለመሆንና የመሬት እድሜ በዝግመተ ለውጥ ሰባኪዎቸ እንደሚታመነው በቢሊዮኖች የሚቆጠር ሳይሆን አጭር እንደሆነ ነው”  በማለት የገለፁት ከዚሁ ተርታ የሚመደቡ ናቸው። የሚገርመው ግን እነዚህን ምስክሮቻቸውን ከተለያዩ መጣጥፎች ውስጥ አንዱን እንኳን ለመጥቀስ ድፍረት ማጣታቸው ነው።

ለዚህም ነው በ 19ኛው መቶኛ አመት በፊዚክስ የትምህርት መስክ የተሰማሩ ሊቃውንቶች ትኩረታቸውን በመሬት ላይ ብቻ ማድረጉን አርግበው በፀሃይ ሥርአት (ፀሃይና በዙሪያዋ ከሚሽከረከሩት ፕላኔቶች) ጋር በአንድነት በማየት ይህ ሁናቴ ቀድሞዉንስ እንዴት ሊፈጠሩ ቻሉ? ፀሃይስ የምታሰራጫቸውን የሙቀት ኃይሏንም ሆነ ጨረሯን እንዴት ልታፈልቅ ቻለች? የሚሉትን ጥያቄዎች መሰረታዊ በማድረግ ምርምራቸውን ተያያዙት። በዚህም የመጀመሪያ የምርምር ውጤት ሆኖ ይፋ የተደረጉት፣-

ሀ.) ፀሃይና በሷ ዙሪያ የሚሽከረከሩት ፕላኔቶች በተመሳሳይ ወቅት ከጋዝና የአቧራ ጢሶች የተፈጠሩ መሆናቸው፣

ለ). የፀሃይ እድሜ 22 ሚሊዮን አመት ሊኖራት እንደሚችል

ሐ) ይህ የእድሜ ተመን ለሌሎቹ በተለይም ለመሬት በመመሪያነት መገልገያ ሊሆን እንደሚችል በሎርድ ኬልቪንና በጀርመናዊው የፊዚክስ ሊቃውንት ኸርማን የቀረበ ነበር። ነገር ግን የነዚህ የሁለቱ ሊቃውንቶች እሳቤ የዝግመተ ለውጥ ጽንሰ ሃሳብ ዋና አመንጭ የነበረውን ቻርለስ ዳርውን በዝሪያዎች አፈጣጠር መፅሃፉ የቀረበውን የ300 ሚሊዮን የመሬት እድሜ በእጅጉ የሚቃረን ነበር።  ክፉኛ ተቃውሞም አቅርበውበት እንደነበረ ከታሪክ ድርሳናት መመልከት የሚቻል ነው። ሁናቴው በዚህ ቀጥሎ እያለና የሚቀርቡትም የመሬት እድሜ በሚሊዮኖች አመት የሚቆጠር ቢሆንም የተወሰኑ የኬሚካል ንጥረ ነገሮች እርጋታ የሚጎድላቸው በመሆኑ ጨረር ከውስጣቸው በማፍለቅ ወደ ሌላ ጠንካራ እርጋታን ወደተላበሰ  ንጥረ ነገር መቀየራቸው ተመርምሮ እስከሚገኝ ድረስ ወሳኝ የሆነ የምርመራ ውጤት አልተገኘም ነበር።

የፊዚክስ ሊቃውንት የሆነው ኤርነስት ሩተርፎርድ (Ernest Rutherford) ና የኬሚስትሪ ሊቃውንት (Frederic Soddy) ሁለቱ በጋራ ከንጥረ ነገር የሚፈልቁ ጨረሮችን (radioactivity) አስመልክቶ ጥልቅ እውቀት ያገኙ በመሆናቸው ይህን የተፈጥሮ የጨረር መፍለቅን ግኝት ለእድሜ መተመኛ ዘዴነት ጠቃሚ ሊሆን እንደሚችል የተገነዘቡት የመጀመሪያ ሊቃውንቶች እነዚህ ሁለቱ ነበሩ። ለዚህም የረዳቸው በ 19ኛው መቶኛ አመት መጨረሻ አሜሪካዊው የኬሚስትሪ ሊቃውንት ቤርትራም ቦልትዉድ (Bertram Boltwood) በተፈጥሮ ድንጋይ ውስጥ ያገኛቸው ሁለት ንጥረ ነገሮች (ኡራኑየም U ና ሊድ PB) በ እጅጉ ተመሳሳይነት ያላቸው መሆናቸው ነበር። ይህ ሊቃውንት ግን በወቅቱ ሊድ ከ ኡራኒየም የልውጠት ሂደቱ የመጨረሻው ንጥረ ነገር መሆኑን አልተገነዘበም ነበር። የመጨረሻውን ወሳኝ እርምጃ በምርምር ውጤታቸው ያስገኙት የጂኦሎጂ ሊቃውንቱ አርተር ሆልመስና አሜሪካዊው የፊዚክስ ሊቃውንት አልፍሬድ ኒዪር ነበሩ። በተለይ ኒዪር (Massspectrometer) ለማስፔክትሮሜትር መዳበርና መጎልበት ከፍተኛ አስተዋፆ ያበረከተ ነበር። ሁለቱ በጋራ ደግሞ ዚርኮን ((Zirkon) ንጥረ ነገርን በእሳተ ጎመራ ፍንዳታ በኋላ በሙቀት የመቀዝቀዝ ሂደት በሚፈጠር የተፈጥሮ ድንጋይን እርግጠኛ ተብሎ የሚገመት  እድሜውን ለማግኘት ንጥረ ነገሩ ወሳኝ ሚና እንዳለው ያረጋገጡ ነበሩ።

በዚህና መሰል የምርምር ውጤቶች ላይ የተመሰረተ የእድሜ መለኪያ ፅንሰ ሃሳብና የመሳሪያ ቴክኒክ በሚያስደንቅና በሚያስገርም ፍጥነት እየዳበረና እየጎለበተ ዛሬ ያለንበት ደረጃ ደርሰናል። ታዲያ በአሁኑ ወቅት በተግባር ላይ እየዋለ ያለው አድሜን መተመኛ የመሳሪያ ቴክኒኩና ውስጣዊ ይዘቱ ምን ይመስላል? የሚለውን ጥያቄ ማቅረቡ አግባብነት ያለው ይሆናልና እስቲ አብረን እንዳሥሰው።

ፅንሰ ሃሳቡና የቴክኒክ መሳሪያዎቹ የሚመሰረቱት የተወሰኑ ንጥረ ነገሮች በጊዜ ሂደት ቀስ በቀስ ወደ ሌላ ንጥረ ነገር የመለወጥ ጠባይ ያላቸው መሆናቸውን በመገንዘብ ነው። በአሁኑ ወቅት ከ 40 የሚበልጡ የቴክኒክ መንገዶች እንዳሉ ሲታወቅ እያንዳንዳቸው ደግሞ በበኩላቸው የየራሳቸው ልዩ የመተመኛ ቀመርና ቴክኒክ ያላቸው ናቸው። የተወሰኑቱ ከታች በተገለፀው የሰንጠረዥ ምስል ውስጥ ተካትተው የሚገኙት በአይነተኛ ምሳሌነት የሚጠቀሱ ናቸው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለአማራ ህዝብ ታሪካዊ ጉዞ ጥናታዊ ፅሁፍ መነሻና መንደርደሪያ የሚሆን ግንዛቤ፣

ሰንጠረዥ 1 ከድረገፅ የተገኘ

ራዲዮ አይሶቶፕ(እናት አይሶቶፕ)በሂደት የሚፀነሰው ምርትግማሸ እሴታዉ ጊዜ በአመት
Samarium-147Neodym-143106 ሚሊያርድ
Rubidium-87Strontium-8748.8 ሚሊያርድ
Rhenium-187Osmium-18742 ሚሊያርድ
Lutetium-176Hafnium-17638 ሚሊያርድ
Thorium-232Blei-20814 ሚሊያርድ
Uran-238Blei-2064.5 ሚሊያርድ
Kalium-40Argon-401.26 ሚሊያርድ
Uran-235Blei-2070,7 ሚሊያርድ
Beryllium-10Bor-101,52 ሚሊዮን
Chlor-36Argon-36300.300
Kohlenstoff-14Stickstoff-145.715
Uran-234Thorium-230248.000
Thorium-230Radium-22675.400

 

በአሁኑ ወቅት በተግባር ላይ እየዋሉ የሚገኙት መሳሪያዎች በጣም ያልተራራቁ ውጤቶችን እያስመዘገቡ ያሉ በመሆናቸው  ለስህተት የመጋለጣቸው አደጋ አነስተኛ ነው። ከተገኘም የስህተቱ ምንጭና ምክንያቱ አግባብነት ባለው ፍጥነት ለማረም ከፍተኛ ጥረት እየተደረጉ መሆናቸው ከግምት ሲገባ፣ የእድሜ መተመኛ ቴክኒኮቹ በአዳዲስ ግኝቶች እየተተኩ፣ የተሻለ ውጤትም እያስመዘገቡ መሆናቸው፣ በየጊዜው የሚወጡ ጥናታዊ ምርምሮች የሚያመላክቱት ናቸው። በዚህም የተነሳ እጅግ በርካታ የሆኑ የተፈጥሮ ሳይንስ ሊቃውንቶች የመሬት እድሜ በዝግመተ ለውጥ ተቃዋሚዎች እንደሚገምቱትና እንደሚመኙት ወይንም ደግሞ ሽፈራው ሉሉና እንግዳሸት ቡናሬ እንደዘገቡት አጭር ሳይሆን በሚሊያራድ የሚቆጠር እንደሆነ በሚያቀርቡት መረጃዎቻቸው የሚስማሙበት ናቸው። ከሌሎች የእድሜ ተመን መለኪያዎች የተገኙትም ውጤቶች እንዲሁ ተመሳሳይ ያላቸው መሆናቸው ይህንኑ የሚያጠናክሩ ናቸው። የትኛውን የእድሜ መተመኛ ዘዴ መቼና እንዴት መጠቀም እንደሚቻል በመስኩ በርካታ ተመክሮን ያካበቱ ሊቃውንቶች በመመሪያነት ከታች የተጠቀሰውን  ቀመር(ፎርሙላ) መጠቀም መልካም ነው ሲሉ ምክራቸውን ይለግሳሉ።

0,01 t½  <    t   <  100 t1/2

መለኪያዎቹን እያዘበራረቁ ሳይሆን አመርቂ ውጤትን ሊያስገኙ በሚችሉበት መስክ ተግባር ላይ እንዲውሉ ካልተደረገ በርግጥም የተለያዩ ለብዥታ መንገድ ጠራጊ መሆናቸው ግልጽ ነው። በተለያዩ የአለም አካባቢዎች በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚገኙ የምርምር ተሳታፊዎችም ይህንን ሁናቴ በግልፅ የሚያውቁት በመሆናቸው ለስህተት እንዳይጋለጡ ከፍተኛ ጥንቃቄ እያደረጉ ይገኛሉ። ለዚህም ነው እንዲያው በጅምላ “ ጥናቶች የሚያመለክቱት ለራዲዮ አይሶቶፕስ የምንጠቀምበት የልውጠት ሂደት (decayrates) ትክክል እንዳልሆነና የምድር እድሜ አጭርና ከ 10.000 ሺዎች አንደማይበልጥ ነው” ብሎ መፈጠም ውሃ የማይቋጥር መከራከሪያ የሚሆነው።

በበርካታ የክርስትና እምነት ተከታዮች በተለይም በክፉኛ ወግ አጥባቂዎች ዘንድ ከላይ የተገለፁት የእድሜ መተመኛ ፅንሰ ሃሳብና የቴክኒክ መሳሪያዎች ተቀባይነት እንዳያገኙ መጠነ ሰፊ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ እየተደረገባቸው ይገኛል። ይህ ጥረታቸው ፍሬ አላስገኘም ማለት አይቻልም። ሽፈራው ሉሉና እንግዳሸት ቡናሬ እንዲሁም መሰሎቻቸው የዚሁ ጥረት ሰለባ ናቸው ተብሎ ቢነገር ከውነቱ የራቀ ሊሆን አይችልም። የሚያሳዝነው ግን ፅንሰ ሃሳቡም ሆነ የእድሜ ተመን ማግኛ መሳሪያዎቹና ያስገኙት ውጤቶችም ሃሳበ ፅኑነትና ተአሚነት ያላቸው መሆናቸውን ለመገንዘብ አሻፈረን ማለታቸው ብቻ ሳይሆን በርካታዎች ግልፅ ያልሆነላቸው በዚህ የምርምር መስክ ተሳታፊ በመሆን የራሳቸውን አስተዋስጽዖ የሚያበረክቱ የክርስትና አምነት ተከታዮች መኖራቸውን ለማመን መቸገራቸው ነው። የችግሮቻቸው ምንጮች ደግሞ የሚታወቁ እንጂ ልዩ ሚስጢር ኖሯቸው አይደለም። ታዲያ እነዚህ ሁሉ “ጤናማ የሆነ አስተሳሰብና ጥሩ ግብረገብነትና ስነምግባር” የሌላቸው ተብለው ሊወቀሱና ሊወገዙ ይገባል? በበኩላችን አይመስለንም።

ለማንኛውም ከተጠቀሱት የእድሜ መተመኛ ዘዴዎች ውስጥ ሁለቱን ብቻ አጠር ባለ መልኩ አብራርተን ይህንን ከፍል እንደመድማለን።

አንደኛው ለምሳሌ 2 ግራም ክብደት ያለው 238U ኡራን ግማሽ ክብደቱን ለመቀነስና ወደ 1 ግራም 206Pb ሊድ  ለመለወጥ የሚወስድበት የጊዜ ተመን 4.51 109 (4.5 ሚሊያርድ አመት) ነው። በዚህ እውነታ ላይ በመመስረት ለምሳሌ የመሬት ቅርፊትንም ሆነ በእሳተ ጎመራ ፍንዳታ በሙቀቱ የመቀዝቀዝ ሂደት የሚመሰረትን የአለት እድሜ ለመገመት የሚቻል መሆኑ ከግንዛቤ ገብቶ ከተግባር እየዋለ  አመርቂ ውጤትም እያስገኘ ነው።  በዚሁ መልክ የመሬትን እድሜ ከ Meteorite እንዲሁም ከጨረቃ ከተገኘው አለት ምርምራ ተደርጎ የተገኘው የእድሜ ተመን 4,54 ሚሊያርድ አመት እንደሆነ ተረጋግጧል።

በአሁኑ ወቅት ምርመራ ከሚደረግባቸው ናሙናዎች ውስጥ (sample) የሚገኘው 206Pb የሊድ  አይሶቶፕ ሥረ መሰረቱ 238U ኡራን እንደሆነ ማረጋገጥ ይቻላል። በመሬት ቅርፊት ውስጥ ምንም አይነት 206 Pb የሊድ አይሶቶፕ  ካልተገኘ ደግሞ ከታች በተቀመጠው

Nአሁን   =  Nመነሾ . e  d t

d =  decay rate

የልውጠት ሂደት ሕግን በመጠቀም የሚመረመውን የናሙና እድሜ ለማሰላሰል ይቻላል።

ይኸው ዘዴ በ Zirkon ንጥረ ነገር ላይ በመመስረት እንዲሁ የእድሜ ተመን ለማሰላሰል ይቻላል። ለምሳሌ በምዕራብ አውስታርሊያ ጃክ ሂል ላይ የተገኘን የዚርኮን ንጥረ ነገር ላይ ምርመራ ተደርጎ የተገኘው የእድሜ ተመን 4.404 ሚሊያርድ አመት እንደሆነው ነው። በመሆኑም የዚህ የምርምር ውጤት ከፍተኛ እድሜ ያለው ንጥረ ነገር በመሬት ላይ መገኘቱን ያስመሰከረ መሆን ችሏል። ልብ ማለት የሚገባው ምንም እንኳ ይህ የእድሜ መተመኛ ዘዴ ለተጠቀሰው የእድሜ ተመን በጣም ትክክለኛ የሆነ ውጤት ቢያስገኝም ውጤቱን የሚያዛቡ የተለያዩ ምክንያቶች ስለሚኖሩ የምርምሩ ሂደት ከፍተኛ ጥንቃቄ በተሞላበትና ከፍተኛ እውቀት ባካበቱ ባለሙያዎች ሊካሄድ የሚገባው የአተማመን ዘዴ ነው ተብሎ አፅኖዖት በተሞላበት ሁናቴ የሚነገር ነው።

በአለም አቀፍ ደረጃ በተለያዩ አካባቢዎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ልዩ የእድሜ መተመኛ ላቦራቶሪዎች ሲገኙ ሁሌም ተቀራራቢ የሆነ የምርምር ውጤት ነው እያቀረቡ የሚገኙት። የራዲዮ አይሶቶፕ የልውጠት ሂደት ላለፉት 40 እስከ 50 አመታት ጠቀሜታ ላይ አየዋለ ያለ ሲሆን አንድም ይህ ነው የሚባል ልዩነቶች አላሳዩም። የ 238U ኡራን አይሶቶፕ የልውጠት ሂደት ከታወቀ 90 አመት ይሆነዋል። እስካሁን ድረስ ምንም አይነት የተለወጠ ሁናቴ ታይቶ አይታወቅም። እድሜን ለመለካት በመጠቀሚያነት የሚያገለግለው የሂሳብ ስላጤ ደግሞ እጅግ በጣም ቀላልና ማንም የቁጥር እውቀት ያለው ሁሉ ሊገነዘበው ሊጠቀምበት የሚችል ነው።

ሌላው ደግሞ በሊቃውንቱ ኤፍ ሊቢ (W.F. Libby) በ 1947 ዓ.ም. ዳብሮትን አግኝቶ ተግባራዊ እየሆነ ያለው የእድሜ መተመኛ ዘዴ ከሆነውና በስፋትም ጠቀሜታ ላይ እየዋለ የሚገኘው (የካርቦን 14) 14C አይሶቶፕ ነው። ግማሽዬ የልውጠት ሂደቱ ጊዜው ደግሞ  t ½ = 5730 አመት ነው። ጠቀሜታውም ከ 50 000 እስከ 70 000 አመታት ባለው ጊዜ ውስጥ ነው። የሚያስፈልገው ከመሬት በላይ ያለውን የ 14C መጠን ማወቅ ብቻ ነው። ይህ መጠን በፀሃይ ጨረር ግለት መጨመርና እንዲሁም የመሬት የስበት ድባብ ዝግመታዊ ለውጥ ምክንያት ሊቀያየር ይችላል። ይህ እንዳለ ሆኖ እርግጠኛ የሆነ የ 14C መጠን በሌላ ዘዴ ማግኘት የሚቻል ሲሆን ይህንንም የኋላ ኋላ የእድሜን መተመኛ ዘዴን ለማመሳከሪያ (ጥሩ ስለት እንዲኖረው) ለካሊቢሬሽን በመገልገያነት የሚሰራ መሆኑ በተደጋጋሚ የተገለፀ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ስለኢምፔሪያሊዝም በአጠቃላይና፣ በተለይም ስለአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምያለኝን የራሴን አቋም ግልጽ ለማድረግ ያህል! - ፈቃዱ በቀለ(ዶ/ር)

ለማጠቃለል የተፈጥሮ ሳይንስን ለባለሙያዎቹ ትተው በጥልቀት ከማያውቁትና ከተሳሳተ ድምዳሜ ከሚያደርስ የእውቀት መስክ  ተቆጥበው  ከጭቅጭቅ ውስጥ ከማይከታቸው እምነታቸው ላይ ትኩረት ሰጥተው በኢትዮጵያዊ ጨዋነት በተሞላበት ለፈጣሪያቸው እየፀለዩ የቀረች ሕይወታቸውን ቢገፉ ይጠቅማቸዋል እንጂ አይጎዳቸውም። ከሁሉ በላይ ደግሞ የራሳቸው ያልሆነን ባእዳዊና አሳሳች እይታን የራሳቸው አድርገው እነሱ ተሳስተው ሌላውን ለማሳሳት ጥረት ማድረግ ፈጣሪም ቢሆን በበጎነት የሚመለከተው አይደለምና አደብ እንግዛ።

በቀጣዩ እስከምንገናኝ ድረስ መልካም ንባብ !!

ማስታወሻ

በቅርቡ በወለጋ በደረሰው ኢሰብአዊ የሆነ የዘር ማፅዳት ፍጅት አንዲት ከጭፍጨፋው የተረፈች ሴት ሕፃን ልጅ “ወላሂ ሁለተኛ አማራ አልሆንም” የሚል አረፈተ ነገር መናገሯና በግድያው መትርፏ ያናደዳቸው ጨፍጫፊዎች ልጅ ወልደው ለመሳም ያልታደሉና የልጅን ፍቅር የማያውቁ አረመኔዎች ምንም ሳይሰቀጥጣቸው እየሳቁ በጥይት እሮምታ የልጅነት ሕይወቷን ሲቀጩት የሰሙ እናት ድርጊቱን ሕዝብ እንዲያውቀውና ከታሪክ ማህደር እንዲዘገብ አስተዋፅዖ ላባረከቱት እናት ልባዊ ምስጋና ይድረሳቸው። ውለታቸውንም መሰል ጭፍጨፋዎች በማናቸውም የህብረተሰብ ክፍል ሆነ ግለሰብ ላይ እንዳይደርስ በትግሉ ድል አድራጊነት እንዲቋጭ ካለፈው በበለጠ ሀገር ወዳድና ለሕዝብ ቀናኢ ሁሉ የየበኩላቸውን የሚቻላቸውን ያህል አስተዋፅዖ ለማበርከት የውስጥ ግፊት እንዲሰጣቸው አበክሬ እማፀናለሁ።

 በውነቱ በዚች ሴት ሕፃን ላይ የወረደባት የጭካኔ በትር ማንንም የሰብአዊ ፍጡር በዘር ጥላቻ ሕሊናቸው ከታወሩት በስተቀር ያላሳዘነውና ያላበሳጨው ኢትዮጵያዊ ዜጋ ይኖራል ብሎ ማሰብ ይከብዳል። በርግጥም የዚህ አይነት መሰል ድርጊቶች ለረጅም እድሜ ቀመስነት የታደልንና አራት አገዛዞችን ያሳለፍን ኢትዮጵያዊያን በየቦታው ኢሰብአዊ የግፍ ድርጊቶች በሰላማዊ ዜጎቻችን ላይ ሲፈፀም በሀዘን የተኮማተርንባቸውና ያለቀስንባቸው ቀናቶች አሁንም ድረስ ከሕሊናችን ያልጠፉ ናቸው።

  1. በጃንሆይ አገዛዝ ዘመን በተደረጉ የግፍ ግድያና ጭፍጨፋ ሳቢያ አልቅሰናል፣ አዝነናል፣ ቀረርቶ አቅራርተናል፣ የትግል ቃል ኪዳን አድሰናል።
  2. በደርግ ጊዜም እንዲሁ ወገኖቻችን ሕፃን፣ ሽማግሌ አሮጊት ወላጅ እናቶችና አያቶች በመኖሪያ ቤታቸው ታጉረው በእሳት ተቃጥለው እንዲሞቱ ተደርጓል። በቀይ ሽብር ሕይወታቸውን ያጡ ለተለያዩ እንግልቶች የተዳረጉ የቁም ስቅልን የቀመሱ ቁጥራቸው በቀላሉ የሚገመት አልነበረም።
  3.  በወያኔ አገዛዝ ከ700 የሚበልጡ ዜጎቻችን በግፍ የተገደሉበት ብቻ ሳይሆን እናት በልጇ ሬሳ እንድትቀመጥ ተደርጋ ገዳዮች ሲሳለቁ አይተናል፣ ተመልክተናል፣ ከንፈር መጠናል፣ የሀዘን ልብስ ለብሰን ሬዳሳቀብረን አልቅሰናል፣ ሀዘናቸን ወሰን አጥቷል።
  4. በለከት የለሹ ፍፁም ዘረኛና ውሸታም ግፈኛ ግለሰብ በሚመራ አገዛዝ ሥር ደግሞ ትኩሱ ሬሳ ደረቁን አስረሳ ይመስላል ሕፃናትን እንደ ዶሮ የሚያርድና እርጉዝ ሴትን በሳንጃ ዘልዝሎ ለውልደት ያልበቃ ልጇን አውጥቶ ከሙት ደረት ማሳታቀፍ ብቻ ሳይሆን በገፍ የግድያ እርምጃ ተወስዷል። የሰጠነው ምላሽ ግን ድርጊቱን አቁሞ እንደ ሰው ፍጡር ለመኖር የሚያስችለንን ነፃነትን አልተላበስንም። ዛሬም ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ ሆኖብናል። የሀዘን እንባችን አልደረቀም። ልቦናችን እውነተኛ ደስታን አያንፀባርቅም። ከላይ የተጠቀሰቺው ህጻን ሕይወቷ እንዲቀጭ በተደረገበት  ቀን በሺዎች ታርደዋል። ሬሳቸውንና የጅምላ መቃብራቸውን አይተናል። ከ20 ቀን ህጻን እስከ መቶ ዓመት አዛውንት በማንነታቸው ብቻ አዕምሮ ሊደርስበት፣ ብዕር ሊከትበው፣  በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ተሰምቶና ታይቶ በማይታወቅ አረመኒያውነት  በገዛ አገራቸው፣ ሰብአዊነት ውስጣቸው በሌለ ግፈኞችና ጨካኞች ሕይወት ሲቀጥፉ ምንም የማይስቀጣጣቸው አውሬዎች በተወለዱበት፣ ባደጉበት ለወግ ማዕረግ በደረሱበት ሀገራቸው ተመርጠው ስጋቸው ተዘልዝሏል፣ ቆዳቸው ተገፏል። ነፍሰ ጡሮች ጽንሳቸው በጪቤ  ተተልትሏል።

ታዲያ መልሳችን ምን ሆነ? በምንም ይሁን በምንም በአምሳሉ ተፈጠረ ተብሎ የሚነገርለት ወገናችን ይህ ሁሉ ስቃይ እንዲደርስበት ምን ጥፋት ቢኖረው ነው? ለሚለው ጥያቄ ማንም መልስ ሊኖረው አይችልም። ከላይ የቀረቡት የተለያዩ የግፍ ተግባራት በወገናችን ቀርቶ በሌላም እንዳይደርስ ፅኑ ፍላጎት ቢኖረንም ማክተሚያውን አስመልክቶ የተለያዩ መላ ምቶች መቅረባቸው የምናስታወስ እናስታውሳለን። ምን ያህል እርምጃ ወደፊት እንዳራመድን ግን አላውቅም። ከስህተት ባለመማር በክፉ የበደል አዙሪት ውስጥ እየተርመጠመጡ ከሀገር ወዳድና ቅን አሳቢ የሚሰጥ ምክርን ለመስማት አሻፈረን የሚል በበዛበት “ምከረው ምከረው እምቢ ካለ መከራ ይምከረው” ተብሎ የሚታለፍ አለመሆኑን መገንዘብ የመጀመሪያው እርምጃ ይመስለኛል። በበኩሌ በዚህ ጉዳይ ላይ ከልቤ ውስጥ የታመቀውን ንዴትና በሀዘን የተሞላ ጭንቀቴን አርግፌ አንባቢን ተደራቢ ሰቀቀን ውስጥ መክተት አልሻም። ማለት የምፈልገውን ምናልባት ጠንከር ባሉ ቃላቶች እገልፀው ካልሆነ በስተቀር ጠገናው ጎሹና አገሬ አዲስ የተባሉ በተደጋጋሚ በሚገባ ከትበውታልና ምስጋና ይድረሳቸው።

ታዲያ በዚችን ሕፃን ሴት ላይ የደረሰባትን የግፍ ግፍ በመነሻነት በመውሰድ በአንድም ሆነ በሌላ የተለዩኝን የትግል አጋሮቼን ሻማ አብርቼ ያለፉትን የትግል አመታት በደስታም ሆነ በሀዘን ያሳለፍነውን ጊዜያቶች በሕሊናዬ እያስታወስኩ ራሴን በራሴ በማፅናናት ላይ እያለሁ ፕሮፌሰር ኃይሌ ላሬቦ የተባለ ቂመኛ ግለሰብ በሰው ቁስል እንጨት ስደድበት እንዲሉ የዚያን ትውልድ አባላት በሽብርተኝነት ወንጅሎ በሕይወት መኖራቸው ክፉኛ የተናደደበት ቅርሻቱን ሳልወድ በግድ እየተናነቀኝም ቢሆን አነበብኩት። ይህ ግለሰብ ራሱን የገለልተኝነትን ካባ አላብሶ እንደ ሰው ፍጡር እንኳን የዛ ትውልድ አባላት ያላቸውን ሰብአዊ ክቡርነትን ነፍጓቸዋል። በሌሉበትና ባልዋሉብት የሃሰት ታሪክ ፈልፍሎ ጥላሸት ቀብቷቸዋል፤ ኢትዮጵያዊ ዜግነታቸውን ነጥቋቸዋል፣ ከኑግ የተገኘህ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ ሆነና የትግል አጋሮቻቸውንና ደጋፊዎቻቸውን ከገደሉ፣ ለአካለ ጉድለትና ለሞት ለዳረጉ መጠነ ሰፊ የሆነ የመብት ጥሰቶችን ካካሄዱባቸው ጠላቶቻቸው ጋር በማዳበል ዘልፏቸዋል፣ አብጥልጥሏቸዋል፣ በውሸት ታሪክ ከሷቸዋል፣ ተዝካራቸውንም እንዲያወጡ ምክር ቢጤም ለግሷቸዋል፤ ሌላም ሌላም።

እንግዲህ መታገስም ገደብ አለውና ሳይፈልጉት ፈልጎ እማሬ ጣቱን ቀስሮ የጫረውን በአሎሎ እሳት ጠቅልሎ ወርውሯልና እሱ ራሱ እየበገነ ለመውደቅ የተቃረበች ሕይወቱ ታሸልማለች እንጂ በምንም አይነት በሱና በመሰሎቹ  ዛቻ ትላንት ከትላንት ወዲያ አልጠፋንም፣ አሁንም አንጠፋም ወደፊትም የማንጠፋ መሆናችንን የሚገልጽ መልስ እስኪደርሰው ትዕግስቱን ይስጥህ እለዋለሁ።


http://amharic-zehabesha.com/archives/174163#:~:text=%E1%8B%A8%E1%8B%B3%E1%88%AD%E1%8B%8A%E1%8A%95%20%E1%8B%A8%E1%8B%9D%E1%8C%8D%E1%88%98%E1%89%B0%20%E1%88%88%E1%8B%8D%E1%8C%A5%20%E1%8D%85%E1%8A%95%E1%88%B0%20%E1%88%83%E1%88%B3%E1%89%A5%E1%8A%93%20%E1%8B%AB%E1%88%B5%E1%8A%A8%E1%89%B0%E1%88%88%E1%8B%8D%20%E1%8B%8D%E1%8C%A4%E1%89%B51%20%E2%80%9C%E1%8A%A5%E1%88%9D%E1%8A%90%E1%89%B5%20%E1%88%B2%E1%8C%80%E1%88%98%E1%88%AD%20%E1%88%B3%E1%8B%AD%E1%8A%95%E1%88%B5%20%E1%8B%AB%E1%8A%A8%E1%89%B5%E1%88%9D%E1%88%88%E1%89%B3%E1%88%8D%E1%8D%A3

http://amharic-zehabesha.com/archives/172438#:~:text=%E1%8C%A0%E1%89%8B%E1%88%AB%E1%8B%8D%20%E1%8C%89%E1%8B%B5%E1%8C%93%E1%8B%B5%20%E1%8B%A8%E1%88%9B%E1%8B%AD%E1%89%B3%E1%8B%A8%E1%8B%8D%E1%8D%A3%20%E1%8B%A8%E1%88%9B%E1%8B%AD%E1%8C%A8%E1%89%A0%E1%8C%A0%E1%8B%8D%E1%8D%A3%20%E1%8B%A8%E1%88%9B%E1%8B%AD%E1%8B%B3%E1%88%B0%E1%88%B0%E1%8B%8D.%20%E1%8C%8D%E1%88%8D%E1%8C%A5%E1%88%8D%E1%8C%A5%E1%8A%90%E1%89%B1%20%E1%8A%A0%E1%8B%AD%E1%89%80%E1%88%AC%20%E1%8A%90%E1%8B%8D!!%20%E2%80%93%20%E1%8A%A8%20%E1%8A%A0%E1%8A%92%E1%88%B3%20%E1%8A%A0%E1%89%A5%E1%8B%B1%E1%88%8B%E1%88%82

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share