እግዜር ይጠይቃል! ትውልድ ይታዘባል! ታሪክ ይዘግባል! – በላይነህ አባተ

/

በዘር በቋንቋቸው በባትሪ በመብራት እየተፈለጉ፣
እንደ በግ እንደ ከበት ሰዎች ሲታረዱ፣
እግዜር ይጠይቃል ማን እንደነበሩ ስለቱን የያዙ፣
ትውልድ ያፋጥጣል እነማን አሳስረው ሕዝብ እንዳስጨረሱ፣
ታሪክ ይታዘባል ስንቶች ሆድ ለመምረግ አፍን እንደ ዘጉ፡፡

ግብር ገባሪዎች በደም በሥጋቸው እየተመረጡ፣
ተቤት ተእምነት ሥፍራ ለአውሬ ለጪራቆች ፍሪዳ ሲቀርቡ፣
ግብሩን የሚበሉት ፓርላማ ምንስቴር ወንጀል ሲደብቁ፣
እግዚአብሔር ይቆጣል ለዘር ማጥፋት ወንጀል ፍትህ በመጥፋቱ፣
ትውልድ ይዘግባል ምንስቴር ፓርላማ ማን እንደነበሩ፣
ታሪክም ያትማል ስንቶች ለከርሳቸው ሕዝብ እንደገበሩ፡፡

ለደም ለአጥንታቸው እየተፈለጉ በጎች ሲታረዱ፣
እረኞች “አባቶች” ይቺን ዓለም ወደው ዛሬም ዝም ሲሉ፣
እግዜር ልብ ያደርጋል በጥምጣም ካባቸው እንደሚያታልሉ፣
ትውልድ ያፋጥጣል በግን አሳልፈፈው ለምን እንደሰጡ፣
ታሪክም ይወቅሳል አቡነ ጴጥሮስን ስላልተከተሉ፡፡

ሕፃን ሴቶች ታርደው ደማቸው ከል ሲቀር፣
አምላክ ይጠይቃል ተችሎት ማን ነበር፣
ትውልድም ያስባል ሄሮድስ ቆሞ ሄዷል፣
ታሪክ ይዘግባል ሕግ ባለሙያው ጲላጦስን ሆኗል፡፡

በቋንቋ ቆንጨራ ትውልድ ሲመነጠር፣
እስተንፋስ ያለው ሰው ዝም ማለት ሲቀጥል፣
በሰው ልጅ ከንቱነት እግዜር ይቆዝማል፣
በዘመኑ ምሁር ትውልድ እፍር ይላል፣
ብዙው በአድፋጪነት ዝም ጪጭ እንዳለ ታሪክ ይዘግባል፡፡

እድሜ እንደ ጨርቅ ያልቃል ነፍስም ሽልብ ይላል፣
ታሪክና ትውልድ በእግዚአብሔር ቸርነት ዘላለም ይኖራል፣
እነማን ምን ሰርተው መቃብር እንደ ገቡ መሬት ላይ ይጥፋል፣
ጭራቁን ባንዳውን ሎሌውን አድፋጩን መዝግቦ ይይዛል፣
ጀግና ሰማእትን እንደ አቡነ ጴጥሮስ ሲያወድስ ይኖራል፡፡

እግዜር ይጠይቃል!

ትውልድ ያፋጥጣል!

ታሪክ ይዘግባል!

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)
ሰኔ ሁለት ሺ አስራ አራት ዓ.ም.


ሰባት ሰዓት ወስዶባቸዋል። በቪዲዮ እየቀረጹ የህጻናትን አንገት ቀንጥሰዋል። እየጨፈሩ የአዛውንቶችን ሰውነት በሜንጫ ተልትለው ገድለዋል። እየፎከሩና እየሸለሉ የእናቶችን ደረት በጥይት ደብድበው ጨፍጭፈዋል። አራት መቶ ነፍሶችን ለሞት ለመማገድ የከለከላቸው አልነበረም። ለእነዚያ ምስኪን ወገኖች ማንም ሳይደርስላቸው ይህቺን ምድር በግፍ ተሰናበቷት። ያማል…ያማል!
አሁንም የድረሱልን ጩኸት ከዚያ የስቃይ፣ አኬልዳማ ምድር ይሰማል። ስልኬ እረፍት አጥቷል። በውስጥ መስመር በሚደርሰኝ የጽሁፍና የፎቶግራፍ መልዕክቶች ፍጹም ተረብሼአለሁ። የእንባ ከረጢቴ ደርቋል። ውስጤ ድምጽ አልባ ሆኖ ይነፈርቃል። ዛሬም ከወለጋ ምድር ነፍሶች የሚታደጋቸው አላገኙም። ተጨማሪ ዕልቂት እንዳይኖር ምን እናድርግ? ቁጥሮች እየጨመሩ ነው። ምናልባትም በሚቀጥሉት ቀናት የተገደሉት ቁጥር በእጥፍ ሊጨምር ይችላል። የሰይጣን ጆሮ ይስማው። መንግስት አረ በህግ አምላክ?! ችግኙን ሌላ ጊዜ እንተክላለን።
እውነት ለመናገር ቀና ማለት አቅቶኛል። እነዚህ ነፍሶች የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት በመረጡት ምክር ቤት ተነፍጓቸው እንደመስማት ቅስም ሰባሪ ሀዘን የለም። አራት መቶ ነፍሶችን በግማሽ ቀን ውስጥ ያጣች ሀገር ድንኳን ጥላ፣ ሰንደቋን ዝቅ አድርጋ ሀዘን እንደመቀመጥ በቸበርቻቻና የፓርቲ ድግስ ስትምነሸነሽ እንደማየት ልብ የሚያቆስል በደል የለም። ምነው ፈጣሪስ ጨከነ? እንዴት መንግስት ከህዝብ ጋር እልህ ይገጥማል? ብሽሽቅ በሰው እልቂት?! አቤቱ! ወይ ፍረድ ወይ ውረድ!? ግድየለም፣ አሁንም ሞት አድፍጦ የሚጠብቃቸው ወገኖቻችን የድረሱልን ድምጽ ይሰማልና ተጨማሪ ዕልቂት እንዳይከሰት እልሃችንን እንዋጠው።
እያመመው መጣ…..

Mesay Mekonnen

ተጨማሪ ያንብቡ:   “ሁለቱም ባዶዎች ነበሩ!”---ፊልጶስ 

1 Comment

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share