May 31, 2022
24 mins read

እውነት ለጊዜው ትመነምን እንደሆን እንጂ ውሎ አድሮ፣ የኋላኋላ ጨለማውን ገፋ ፍንትው ብላና ገና ትወጣለች !!! – ተዘራ አሰጉ ከምድረ እንግሊዝ

የሎንዶን የነ ኢትዮጵያን እናድን /Defened Ethiopia/ ዲስኩርና እፀፅ።

መግቢያ 

እንደሚታወቀው በአለም የተክፈቱ የኢትዮጵያ ኢምባሲዎች ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በኢትዮጵያ በሚከናወኑ ታላላቅ ፕሮጀክቶች የገንዘብ ድጋፍና የዕውቀት ሽግግር  እንዲያደርጉ ያበረታታል።

ይህ ሰናይ ተግባር እሰየው ቢያሰኝም በተለይ ገንዘብ የማሰባሰቡ ሂደት ተጠያቂነት የማይታይበትና ሃላፊነት የጎደለው በመሆኑ  በኢትዮጵያዊው፣በትውልደ ኢትዮጵያዊውና ኢምባሲዎች መካከል ክፍተትና መወነጃጀል የየዕለት ተዕለ ክስተት ከሆነ ውሎ አድሯል።  ለመወነጃጀሉና ለመነታረኩ ዋናው ምክንያት የየኢምባሲዎች  ሹማምንቶች ጣልቃ ገብነት ፣ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያንን ወክለው የሚቋቋሙት የኮሚቴ አባላት የየስርዓቱ አገልጋዮች መሆን ፣ ብሔር ተኮርን መሰረት አድርገው የተመለመሉ፣ ከእሽታና ከአገልጋይነት  በስተቀር የሕዝብን ምሬትና ጥያቄዎች እንዲፈቱ ለማድረግ የመሟገትና ደፈር ብለው ለሚመለከተው አካል የማቅረብ ብቃትና ልበ ሙሉነት የማይታይባቸው በመሆኑ ነው።

ከዚህ ባሻገር የሚኖሩበትን ሃገር ሕግጋትና የስራ አሰራር ሂደቶች በቅጡ ስለማያውቁ ስህተት ውስጥ ከመግባት ባሻገር፣ በኢምባሲ አካባቢ ያሉትን ዲፕሎማቶች ወደ ስህተት እንዲዘፈቁና ላልታሰበ የገንዘብ ብክነትና ዝርፊያ ምክንያት ይሆናሉ። እንዳንድ ብልጣብልጦች የዲያስፖራ ተወካዮች ደግሞ የዝርፊያው አካል እንዲሆኑ ምክንያት ይሆናሉ።

ይህ ካልን ዘንዳ በለንደን ዮናይትድ ኪንግደም /እንግሊዝ/  የዲያስፓራው አባላት “ የተሰባሰበው ገንዘብ የት ደረሰ እና መዳረሻው ሪፓርት ይደረግልን” ብለው ለጠየቁት ጥያቄ የሰጡት ሰሞነኛ ምላሽና እፀፁን እንደምሳሌ ወስደን እንተነትላለን ፣ ለወደፊት ስህተቶች እንዳይደገሙ አስተምሮ ይሆን ዘንድ ያለንን ልምድና የህግ ተግባቦት ተከትለን መላ ሂደቱን እንገመግማለን።

 

አስተዳደራዊ እፀፆች

መቸም እምየ ኢትዮጵያ እያጋጠማት ያለው ፈተና የትየለሌ ነው። እንደሚባላው እስራኤላውያን የሚወዳቸውን አምላክ አልታዘዝ በማለታቸው ለግብፅ ባርነት ከመዳረጋቸው ባሻገር በቁጣው ያደረሰባቸውን ፈተና ልብ ይሏል። እንዳንዴ ይህ ፅንሰ ሃሳባዊ ግጥምጥሞሽ ” በኛይቱ ሃገረ ኢትዮጵያ የአምላክ የቃል ኪዳን ሃገር ኢ – ሰባዊነት በጎደለው ክዋኔና ከሞራል ያፈነገጠ  ድርጊታችን ምክንያት ተመሳሳይ የአምላክ የቁጣ ፍርድ እየተፈፀመ ነው ወይ ? “ ብየ እንዳስብ ይዳዳኛል።

ኢትዮጵያ ሃገራችን ደግሞ ዙሪያ ገባዋ የተዋበ ፣ መልክአ ምድሯ ለምለም፣ እንደጥርኝ ሽቶ የሚያውደው ጥዑም ነፋሻ አየሯ ፣ የተፈጥሮ ሃብቷና ከዛም የህዝቦቿ ተክለቁመናና በራስ የመተማመን ቀመር የትየለሌና ተወዳዳሪ የለውም።

የኢትዮጵያ ፈርጣማ ክንድ ያረፈባቸው ሰላቶዎች ፣ ነጫጭባ የነጭ ሳጥናኤሎችና በምዕራባውያን ጉርሻ የናፈዙ ግርፍ የእንግዲህ ልጆች እምየ አገረ ኢትዮጵያን አሳልፎ ለመስጠት፣ ለማውረድና ለመዝረፍ ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም። ግን ይህ ሁሉ ደባና ሽረባ አልቦ ሁኖ ቀርቷል። ኢትዮጵያ ሃገራችን በሰው ሰራሽ ችግሮች የተነሳ ብትድኅይም፣ ባንዳዎች ጋር ተባብረው ቢያራቁቷትም አምላክ ይክበር ይመስገን

፣ አለች እንደተከበረች።

የኢትዮጵያ ህዝብ ኑሮው ተንበሸበሸ፣ ከፋው ፣ ተጎሳቆለ ፣ ጠላትን ድል ነሳ “በራስ ስሉጡነት ፣ እንደ ኤሮዶቶስ ጉልበቴ በርትቶ ፣ እንደታላቁ አሌክሳንደር የማይነካ ግዙፍ ኃይል ወ.ዘ.ተ. ኑሮኝ የዚህ ሁሉ የድል ባለቤት ሆንኩ ፣ ጠላቶቸንም ድል ነሳሁ” ብሎ አስቦ ፣ ተኩራርቶና በአንደበቱ ተናግሮት አያውቅም።

ይልቁንስ ጎተራው ሲሞላ “ለአንተ ምን ይሳነሃል” ብሎ ተንበርካኮ አመስግኖ። እስከ አፍንጫቸው ታጥቀው የመጡትን ድል ሲነሳ “ብርታቴና ጉልበቴ ሁነህ ፣ ከፊት ቀድመህ ጎልያድን በአንዲት ወንጭፍ ያሳፈርክ አምላክ የሃገሬን ጠላቴች ድል ስለነሳህ ምስጋና ይድረስህ ፣ ብርታቴና የድል መንሳቴ ምክንያት የሆንከው ፣ አንተው አምላኬ ነህ” ብሎ ከማመስገን ውጭ፣ በሆነውና ባገኘው ስኬትና ድል የማይታበይ ሕዝብ ኢትዮጵያዊ ነው።

ይሄን ሁሉ ያልኩት በምዕራቡ አለም ታጉረው የፈረንጅ ፍርፋሪ እየጠራረጉ በወሬ ፣ በዲስኩርና መፈክር በማነብነብ ኢትዮጵያየን የሚገሸልጧትን ያውም ኢትዮጵያዊ ዜግነታቸውን በጎረቤት ሃገር ማንንነት ለውጠው “ ሱዳናዊ፣ ሰማሌ፣ ግብፅና ከዛም አልፎ “የኤርትራዊነት ተነጥሏዊ ሃገረ ዜግነት  የኢትዮጵያዊነት ስነ-ልቡና ባይሆንም ዘመኑ ባመጣው የህውሃት ሴራ ኤርትራዊ ማንነት ተቋድሰው ፣ ኢትዮጵያዊነትን ገሸሽ አድርገው ከርመው፣ በየኢምባሲው ከኛ በላይ ኢትዮጵያዊ ብለው የሚያወናብዱ፣ ባለፈው ስርዐት  የኢትዮጵያዊ ማንነታቸውን የሸጡ ፣  ከዛም አልፈው  የኦሮሞነትን ተገንጥሎ ሃገራዊነት ባለፈው ስርዐት  ሲያቀነኑ የነበሩ ፣ ዛሬ “ከኛ በላይ ኢትዮጵያዊ ላሳር” ብለው ሲደሰኩሩና  “እንምራችሁ ፣ ኢትዮጵያን እንከላከል ፣ የአማርኛው ትርጉም ሳይገባቸው በእንግሊዝኛ” Defened Ethiopia “ ብለው ለአጫቸውና እያዝረከረኩ ባልሰላው ልሳናቸው ሊቀኙልን ሲሞክሩ ላየና ለሰማ “ሰው ሲታጣ ይመለመላል ጎባጣ” ከማለት ውጭ ምን እንላለን። ይህን ሁሉ እንደ መግቢያ ዲይስኩር የደሰኮርኩት ሲብሰኝና ነገሩ ሁሉ “እጅ እጅ” ሲለኝ ያዥጎደጎድከት ነው።

ወደ ዋናው ነጥቤ ለመግባት ይረዳ ዘንድና ኢትጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊው በውጭ ሃገር በተለይ በምዕራባዊው ምድር ኑሮውን ያደረገው ማህበረሰብ ያለውን እውነታና ልኩን አውቆ በእውቀትና በንቃት ታጅሎ ሃገሩን እንዲደግፍ ለማሳወቅ ነው።

 

የኢትዮጵያን እናድን /Defend Ethiopia/ ስያሜና እፀፁ

“አላዋቂ ሳሚ ንፍጥ ይለቀልቃል “ እንዲሉ በአሁኑ ስዓት አገራችን ውስጥ እየተደረገ ያለው ግጭትና ትርምስ ወደድንም ጠላንም ፣ ታሪካዊ ጠላቶቻችን እርስ በርስ እድንባላ “ክብሪት አቀበሉ አላቀበሉ” ፣ የግጭቱ መንስሄ የአስተዳደር ክፍተት ፣ የሕግ የበላይነት መሰረት ተከትሎ አለመጓዝና ይህን ኩነት የሚመራው መንግስት አቅምና ብቃት ማነስ ሆኖ ሳለ ትርምሱ “ የአንድ ሃገር ወንድማማች ሕዝቦች ባለመግባባትና በግለኝነት ስሜታዊ ህሳቤ” እየተካሄደ ያለ መናረት “ ነው።

እንደ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ አመለካከት ሰሞነኛው የአገራችን ክስተት  ጦርነት ነው” ለማለት መስፈርቱን የማያሟላ ሲሆን፣ መሪዎቻችን በስልጣን ኮረቻ ለመሰንበት የፈበረኩት የቁማር ጭዋታ ኩነት እንደሆነ ልንገነዘብ ይገባል።

“በየአለም ክፍሉ ባሉ የኢትዮጵያ ኢምባሲ ተሰይመህ ያለህ የድል አጥቢያ አርበኛ ሆይ”፣  ሃገረ ኢትዮጵያ ከፍቷት ፊቷ ገርጥቶ ብታያት ፣ በእኛው ክፋትና መገፋት አገረ ኢትዮጵያ እያነባችና “የሎሄ ፣ የሎሄ” እያለች ቢሆንም አድናታለሁ /Ddefend Ethiopia/ ብለህ በእምየ ኢትዮጵያ የምታፌዝባት፣ ከማን ነውስ የምታድናት? /Defend/ የምታረጋት? እቅሙም ሆነ ፣ ቅርበት ቦታ /Access/  አለህ ወይ ?። የለህም አረጋግጨ እነግርሃለሁ!!!

እንደሚታወቀው ሃገረ ኢትዮጵያ ከጣሊያን፣ ግብፅ /ምስር/፣ ቱርክ/ ፣ ድርቡሽና ወ.ዘ.ተ. ጋር  ለጊዜው እየተዋጋች ባለመሆኑ /Defend Ethiopia/ የሚለውን ስያሜ ቀይራችሁ ” ኢትዮጵያን እንርዳ፣ ኢትዮጵያን እናልማ ፣ ኢትዮጵያ ትቅደም ፣ ሌብነት ይውደም” ብላችሁ የሚሰበሰበውን ሰብስባችሁ በዛው እራሳችሁን ብታበለፅጉ ይሻል ነበር ብለን እንመክራለን።  ነገር ግን ነገ ተጠያቂነት ይኖራልና ጠንቀቅ እድትሉም እንመክራለን።

በእምየ አገራችን ወደ ኋላ በ1977 የደረሰውን ድርቅ ስናስብ ፣ ልጅ በርሃብ ፣ በችግርና በጠኔ የተጎሳቆለ ወላጅ እናቱን ጡት ሊጠባ ሲውተረተር ላየ አንጀት ይበላል። ይህን ስል ምን አማራጭ አለው። የሚገርመው በውጭ ሃገር የተሻለ ኑሮ እየኖሩ “ የገቢያ ግርግር ለሌባ ይመቻል” እንዲሉ እቺን በግጭት የተጎሳቆለች ሃገረ እምየ ኢትዮጵያን ለመቦጥቦጥ የሚሄዱበት ዕርቀት ግርምትን ይፈጥርል፣ አንገት ይስደፋል፣ ያሳፍራል።

 

የፋይናንስ /የገንዘብ/ አያያዝ ዕፀፆች

የሎንደኑ የኢትዮጵያ ኢምባሲ የኢትዮጵያ እንመከት /Defend Ethiopia/ የዲያስፓራ የፋይናንስ ኮሚቴ አስተባባሪዎች በተለያዩ ጊዜያት የተደረጉ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ዝግጅቶችን የገንዘብ ወጭና ገቢ ፍሰት ሊያስረዱ ሞክረዋል።

ከዚህ ላይ ቅሬታ ያላቸው ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን እየጠየቁ ያሉት የገንዘቡ አሰባሰብና የወጩ ፍሰት የታላቅዋን ብሪታንያ ሕገ ደንብና የኢትዮጵያ መንግስት ለኢምባሲዎች ከሰጠው ስልጣንና ተግባር አንፃር ስህተቶች የታዮበትና ህገ ደንቦችን የጣሰ  ነው የሚል ነው።

፩) ኢምባሲው በንገዘብ ማሰባሰቡ ሂደት ውስጥ የቁሳቁስና የሎጅስቲክ ድጋፍ ከማድረግ ውጭ እጁን አረዝሞ መደርጎስ ነበረበት ወይ? ለሚለው ጥያቄ። በፍፁም መሆን አልነበረበትም ፣ ኢምባሲው በስልጣን ላይ ያለው መንግስት አፈ- ቀላጤ ፣ ቀኝ እጅ እንደመሆኑና ካለው መንግስት ጋር በመነጋገር ማህበረሰቡ ለተፈናቀሉት፣ ለተጎዱት  ወገኖች መርጃ ይሆን ዘንድ ያሰበሰበው ገንዘብ መንግስት በእጅ ጥምዘዛ ለአንገብጋቢ ሃገራዊ ጉዳዮች  ሊያውለው ይችላል የሚል ህሳቤ ስላለ፣ ኢምባሲዎች እንደዚህ በመሰሉ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ሂደቶች  እጃቸው እንዳይገባ ሃገራዊው የኢትዮጵያ ሕግ ሆነ  የተቀመጡባቸው ሃገራት ሕጎች በጭራሽ አይፈቅዱላቸውም።

፪) በተለይ ዳጎስ ያሉ ገንዘቦች ይሰባሰባሉ ተብሎ ከታሰበ የየሃገራቱን ህግጋት መሰረት በማድረግ በግብረ ሰናይ ( Charity) በመመዝገብ፣ የባንክ ሂሳቦች ተከፍተውና የሚመለከታቸው አካላት አውቀውት ሊከወን የግድ ይላል፣

፫) የተሰበሰበው ገንዘብ ገቢና ወጭ  በገንዘብ ፍሰት የውጭ ተቆጣጣሪዎች (External Auditors) ሊጣራና ለማህበረሰቡ የዚህ የማጣራት ሂደት የመጨረሻ ሪፓርት ለዲያስፖራው ማህበረሰብ በአግባቡ ይፋ ሊሆን የግድ ይላል፣

፬) ይህ የተሰበሰበ ገንዘብ ኢትዮጵያዊውንና ትውልደ ኢትዩጵያዊውን በሃቅና በአንፃራዊነት በዕውቀት በተካኑ በተወከሉ የማህበረሰቡ አባላት ቢመራና ገንዘቡ በአለም አቀፍ ደረጃ በተመዘገቡና በታወቁ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ቢተላለፍ ከገንዘቡ ዳጎስ ማለት የተነሳ መዳረሻውን ማወቅና ለተፈለገው ዓላማ መዋሉን ለመከታተል ይቻል ነበር እንላለን። ለዚህ ምሳሌ የግሎባል አልያንስ ለኢትዮጵያ /Global Alliance/ን ተሞክሮ ለመተግበር ይቻል ነበር፣

፭) የወጭን ፍሰት (Expenses) በተመለከተ የግብየት መግባቢያ ሰነድ (Proforma Invoices) ተሰብስቦ ቢከናወን ማልካም የነበር ሲሆን በሚዲያ ቀርቦ “ግለሰቦች በሚያቀርቡት ደረሰኝ መሰረት የወጭ ክፍያ (Reimburse) አከናውነናል” ብሎ ሪፓርት ማቅረብ ተናጋሪውን የሂሳብ ሹም ማኖ እንደነካ ያስቆጥረዋል።

፮) የተሰበሰቡ ገንዘቦች በኢምባሲው ካዝና (Safe box) በአደራነት ት ተቆልፈው ቁልፉ ለአምባሳደሩ ይሰጣል የሚለው አገላለፅ ኢምባሲውን በእንግሊዝ  መንግስት የሚያስጠይቅ ሲሆን እንደዚህ አይነት ክንውኖች በውስጠ ሚስጥርነት መያዝ የሚገባቸው ጉዳዮች  ሲሆኑ ማንኛውም የተሰበሰበ ገንዘብ በአማካይ ስዓት በ24 ሰዓት ውስጥ ጥሬ ገንዘቡ ገቢያ ውስጥ ይሽከረከር ዘንድ ባንክ ውስጥ ሊገባ ይገባዋል፣ ስለዚህ ይህ አካሄድ አለመከወኑ  ደግሞ ከሙያና እውቀት ማነስ የሚመጣና ወንጀል መሆኑን አለማወቅ አደገኛው ዕፀፅ ነው፣

፯) ኢትዮጵያዊውን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊውን ይወክላሉ ተብለው የተሰየሙት እንዳንዶቹ የአለፈው ስርዓት ብሄር ተኮር የልማት ማህበር ማለትም “የአማራ ልማት ማህበር ፣ የደቡብ ብሄር ብሄረሰብ ልማት ማህበር ተራ አባላት ፣ የግንቦት ሰባት ተቀዋሚዎች ስብስብ ፣ ከዚያ ባሻገር ትላንት ተገፋን ብለው የሚያምኑ የኦነግና የኦነግ ሸኔ ጋሻ ጃግሬዎችና የነዚህ ቡድኖች ጥቅም ተካፋዮች የሆኑ ተረኛ ሃገርን በመመሳጠር ለመዝረፍ ጥርሳቸውን ያሾሉ መሆናቸው የታወቀ ሲሄን ይህ ስንኩል ገቢር  ኢምባሲው ፍቃድ ሰጧቸው  ያለ ማህረሰቡ በጎ ፈቃድ ራሳቸውን የሾሙ ስብስቦች መሆናቸው ሊታወቅ ይገባል። ይህ አካሄድ ደግሞ ያቅለሸልሻል ፣ ሊታረም የግድ ይላል፣

፰) እነዚህ ማህበረሰቡ ሳይወክላቸው ራሳቸውን የሾሙ ግለሰቦች ገንዘብ የሚሰበስቡት ምን ብለው እራሳቸውን ሰይመው ነው ? የሚለው ጥያቄ እንዳለ ሆኖ የኢምባሲውንና የአምባሳደሩን ፕሮፋየል በሃገር ቤቱ መንግስት ከፍ ከፍ አድርጎ ለማሳየት ሲታታሩ ላየ ዘይገርም የሚያሰኝና የበታችነት ውርስ እንዳለባቸው ያሳያል። ቁራጭ መሬትና ፍርፋሪ ለመልቀም ብለው ሊወክሉት የሚገባውን  ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊ ሽጠው የኢምባሲው “ጋሻ -ጃግሬ” መሆናቸው የውርደት ውርደት ነው፣

፱) የግለሰቦች ስብስብ በመሆናቸውና እራሳቸውን በግብረ ሰናይ /Ccharity/ ስላላስመዘገቡ የገንዘቡን መዳረሻ እንጂ ለታሰበለት ዓላማ መዋሉን የመጠየቅ መብት የላቸውም ፣ ለ እንግሊዝ ቻሪቲ ኮሚሽን የሚያቀርቡት የእውቅና መዝገብ ስለሌላቸው እራሳቸውን ወደ ወንጀል እየዶሉ መሆኑን አልተገነዘቡትም እንላለን፣

፲) ከኮሚቴዎች ማካከል አንደኛው የተሰበሰበው ገንዘብ ለሚመለከተው አካል ቢሮ ወደ ኢትዮጵያ ተላልፏል (Remitted/ ሁኗል በማለት በኩራትና በማነለብኝነት ገልፀዋል ። ይህ የተላለፈ ገንዘብ (Remitted) የሆነው ፣ ባንክ ለባንክ ነው? ወይስ በሃዋላ ነው? የሚሉ ጥያቄዎችን ስለሚያስነሳ ግልፅ መሆን ያለበት ሲሆን በሃዋላ ተልኮ ከሆነ ሉቢራራ ይገባል፣ የተሰብስበው ገንዘብ በሃዋላ ተልኮ ከሆነ ደግሞ ወንጀልና የገንዘብ አላግባብ ልውውጥ /Money Laundry/ ጥያቄ የሚያስነሳ እንደሚሆን ግንዛቤ ውስጥ ማስገባት የግድ ይላል፣

፲፩) ሪፓርቱ ሲቀርብ ባለሙያዎች፣ ጋዜጠኞች ፣ ሽማግሌዎች ፣ የሃይማኖት አባቶች በአጠቃላይ ይመለከታቸዋል የሚባሉ አካላት ቢሳተፉበት ኑሮ ተአማኒ፣ ወደ ዕርቅ የሚያሻግርና መጠየቅ ያለባቸው ጥያቄዎች በአግባቡቡ ተነስተው አንፃራዊ ምላሽ ተሰጦበት መግባባት ላይ ይደረስ በነበር እንላለን።

 

ማጠቃለያ

በመጨረሻም እራሱን በራሱ የሾመውና ኢምባሲው በማወቅም ባለማወቅም እውቅና የሰጠው ኮሚቴ ማንነታቸውን ማለትም ኢትዮጵያዊ መሆናቸውን፣ በዚህ ሃገር የያዙትን የውጭ ሃገር ፓስፓርታቸውን ለህዝብ በማሳየት ግልፅ ሊያደርጉና ሊያሳውቁ ይገባል። ይህ አካሄድ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ቁመና ያለው የግብረ ሰናይ /Charity/ ለማቋቋም አንድ መስፈርት በመሆኑ ይህን እንዲፈፅሙ እንጠይቃለን።

ከዚያም የዲያስፓራ ማህበረሰቦች ተሰብስበው የሚመጥናቸውን፣   በችሎታ የተካኑና በሕዝብ ተቀባይነት ያላቸውን የኮሚቴ አባላት እንደገና እንዲመርጡ እንመክራለን።

 

ተዘራ አሰጉ ከምድረ እንግሊዝ።

 

 

6 Comments

  1. እንዴ ምን ያህል ገንዘብ ቢሰበሰብ ነው የቻሪቲን፤ የፋይናንስን፤ የሞራልን ህግጋት አጣቅሰህ የተጠላለፈ ነገር የጻፍክልን? አምባሳደሩን በተመለከት የመንግስት ደጋፊ መሆኑ ሊገርምህ አይገባም ፖሊቲካል አፖይንቲ ነው። በተረፈ እንደሚገባኝ አውሮፓ ውስጥ ገንዘብ እንዲህ ተረፍረፍ አድርጎ እንዲባክን የሚሰጥ ዜጋ አለ ብዬ አላስብም። ባለው አናገብጋቢ ሁኔታ ለህዝብ ለመድረስ ላደረጉት ነገር ወደ ወንጀል የሚከታቸው ሃረግ እየተሳበ ማሸማቀቁም መልካም አልመሰለኝም። ባለፈው ከዛው ካንተው አገር እንዲሁ ከዚህ ያልተለየ መልእክት በቪዲዮ ተለቅቆ አይቻለሁ እንደዛ ግለሰብ አይነት በእውቀት የተጎዳ ዜጋ ሚዲያን ባይጠቀም መልካም ነው። በዛ ክሊፕ ላይ የታዘብነው ድርሻዬን አፍሼ እንዳልሄድ ዘጉብኝ የሚል ይመስላል። ባጠቃላይ ተስማሙ ስራ ከሌለም ኮርስ እየወስዳችሁ እራሳችሁን አሻሺሉ። ኤምባሲውም አቅሙ ካለው የዲፕሎማቲክ ስራ ይስራ በሰፈር ወሬ አትለጥጡት ዛሬ ግብጽንና ወያኔና የተገነጠሉ ኦነጎችን የመሰለ ነቀዞች ገጥመውናል ኤርትራዉያንም በሩ ተከፍቶልናል በማለት በህግም በህገወጥም ሃገሩን እያለቡት ነው። ኤምባሲውም እንዲህ ያለ አተካራ ውስጥ ሳይገባ ለኢትዮጵያ ጥቅም ከተለያዩ ኤምባሲዎች ጋር ግንኙነት በመፍጠር ስብሰባ በማዘጋጀት የኢትዮጵያን ገጽታ ለአለም ያሳውቅ። የትግሬ ወንበዴዎች የኢትዮጵያን ጦር በተኛበት አርደው ጩኽታችንን መቀማታቸውን ከነዲና ሙፍቲና ከኢትዮጵያ ወዳጆች በመገናኘት የዲፕሎማቲክ ስራ ይስራ። እናንተም እንዲህ ያለ የስሙኒ ጫወታና ዘገባ ተው አገር ችግር ላይ ነው። እርስ በእርስ ከመነታረክ አወል አሎ የሚያስተምርበት ትምህርት ቤት ሰልፍ አዘጋጅታችሁ ስብእናዉ ለአካዳሚክ ስታተስ ስለማያበቃው ወይ እንዲባረር ወይ ካለበት ዝቅ ብሎ በዘበኝነት እንዲሰራ ዩኒቨርስቲውን ጠይቁ።

    እንዴት ነው ጎበዝ ባለፈው በቤተክርስቲያን በሃሰት ፈጠራ ስትባሉ ከረማችሁ ዛሬ ደግሞ ኤምባሲው ይህን አደረግ ያንን አደረገ በሚል ንትርክ የሰውን ሃሳብ መበትን ጥሩ አይደለም። ዛሬ ቱባ ቱባ የሚያህሉ ከሽመልስ አብዲሳ ጦር የሚበልጡ ታላላቅ ዜጎች ታስረውብናል በነሱ ላይ እናተኩር በሰፈር ወሬ እንጠመድ።መስከርም አበራ ህጻን ልጅ ጥላ ታስራለች። አቶ ታዲዎስ ታንቱ በ80 አመታቸው ታስረዋል ሌሎቹም እንዲሁ። ያለው ስርአት ስብሃት ነጋን ፈትቶ አቶ ታዲዮስ ታንቱን የሚያሰር በአረመኔነቱ ወደር የሌለው ክፉ ስብስብ ነው። አብረሃም በላይን፤አብረሃ ደስታን፤ሙሉ ነጋን እና አሳዳጊ ትግሬዎቹን ለማስደሰት ኢትዮጵያንና አማራን ሊያስቀጥሉ ይችላሉ ብሎ የገመተውን እያጠፋ ወልቃይትን ለትግሬዎች ሊሰጥ ዝግጅቱን አጠናቋል። ዉል ባለው ነገር እናተኩር ይቅርታ ትንሽ ስሜታዊ ሆንኩ መሰል።

  2. ወንድማችን የፅሁፉን ውስጠ ወይራነት ከስሜት ውጭ ሁነህ አንብበው። ማንበብና ማየት አንድ አይደለም። ከዚህ ፅሁፍ ውስጥ በአማረ ስነ-ፅሁፋዊ ምቸት የኢትዮጵያ ፈተና፣ የመሪዎች ግድፈት፣ የብሄር ፅፈኝነት ክፋት በዲያስፖራ እንዴት መርዛማ እንደሆነ፣ ስለ-ሰባዊ መብት ገፈፋ ፣ በእጠቃላይ እኒህ ሰውየ የሚፅፉት ፅሁፍን በተደጋጋሚ አንቢቢያለው የኢትዮጵያን መከራ እያሰሱ እግረመንገዳቸውንመልካም ቁመናዋን እየጠቃቀሱ የሃገር ፍቅራችን እንዲጎለብት የሚያግዙ ታላቅ በስነ-ፅሁፍ የረቀቀ ችሎታ ያላቸው ናቸው።
    ርዕሱን አንብበን ስንጀምር ምን ይሉ ይሆን እንድንል ፣ እኔማ የማላውቀውን የአማርኛ ግዕዝ ለበስ ቃላት ባገኛቸው ትርጉሙን ልጠይቃቸው እፈልጋለሁ። እንዲያው ወይ ከዲማ ፣ ከሞጣ ቀራንዮ ወይ ከአደባባይ ጎንደር ቅኔ ቤት ተቀኝተው የወጡ ይመስለኛል። ስለዚህ እስክርቢቶ /ቤና/ ይዘህ መስመር በምስር ሊያስተላልፉት የፈለጉትን የፈለጉትን ጭብጥ ለማወቅ ታትር እልሃለው። አንተ የገባ ገለባውን ይመስለኛል እልሃሃለሁ። ውስጠ ሚስጥሩ ረጋ ብለህ ተረዳ። ለመተቸት አትቸኩል።

  3. ወንድማችን የፅሁፉን ውስጠ ወይራነት ከስሜት ውጭ ሁነህ አንብበው። ማንበብና ማየት አንድ አይደለም። ከዚህ ፅሁፍ ውስጥ በአማረ ስነ-ፅሁፋዊ መቸት የኢትዮጵያ ፈተና፣ የመሪዎች ግድፈት፣ የብሄር ፅፈኝነት ክፋት በዲያስፖራ እንዴት መርዛማ እንደሆነ፣ ስለ-ሰባዊ መብት ገፈፋ ፣ በእጠቃላይ እኒህ ሰውየ የሚፅፉት ፅሁፍን በተደጋጋሚ አንቢቢያለሁ የኢትዮጵያን መከራ እያሰሱ እግረ መንገዳቸውን መልካም ቁመናዋን እየጠቃቀሱ የሃገር ፍቅራችን እንዲጎለብት የሚያግዙ ታላቅ በስነ-ፅሁፍ የረቀቀ ችሎታ ያላቸው ናቸው።
    ርዕሱን አንብበን ስንጀምር ምን ይሉ ይሆን እንድንል ፣ እኔማ የማላውቀውን የአማርኛ ግዕዝ ለበስ ቃላት ባገኛቸው ትርጉሙን ልጠይቃቸው እፈልጋለሁ። እንዲያው ወይ ከዲማ ፣ ከሞጣ ቀራንዮ ወይ ከአደባባይ ጎንደር ቅኔ ቤት ተቀኝተው የወጡ ይመስለኛል። ስለዚህ እስክርቢቶ /ቤና/ ይዘህ መስመር በምስር እያሰመርክ ሊያስተላልፉት የፈለጉትን ጭብጥ ለማወቅ ታትር እልሃለው። አንተ የገባህ ገለባውን ይመስለኛል እልሃሃለሁ። ውስጠ ሚስጥሩ ረጋ ብለህ ተረዳ። ለመተቸት አትቸኩል።

  4. በጋሻው የድርሰቱ ባለቤት ትመስለኛለህ ይህን ለማዘጋጀት የባከነው ጊዜ የተሻለ ቁም ነገር ይሰራበታል ባይ ነኝ ይህንን ክፉ ስርአት ለመጣል የሚያግዝ ሁሉ አይናቅም። የጽሁፍህ አስኳል ገንዘብ ነው ተበልቶም ሊሆን ይችላል የምትለው ገንዘብ የተዋጣ ነው የትግሬ ፋሽስቶች የዘረፉትና የታገደባቸው ገንዘብ እና ንብረት እስከ ወለዱና ካሳው ሊከፈላቸው ነው ባንተ ትንሽ ብሮች ከተላቀስን በዚህኛው ላይ ያለን ምርጫ እራሳችንን መሰቀል ነው። ባጠቃላይ ትልቁን ስእል ብናይ ይሻላል ።በድር ገጽ የሚወጡት ጽሁፎች ለመረጃነት ስለሆኑ ማስታወሻ እየወሰድን ማንበብ የሚጠበቅብን አይመስለንም። በእርግጥ ሳይንሳዊና ታሪካዊ ከሆኑ ወደ ተነቦ ወደ ማህደራችን ይገባል። ለማንኛውም በክፋት አትየው ትችትንም መልመድ ጥሩ ነው ቃላት ለቃላት ተጋጩ እንጅ የሰው ህይወት አልጠፋ። ጽሁፉንም አልተቸሁም የባሰ አለብን ኃይልን በማይሆን ቦታ ተጠቅመን አናባክን ለማለት ያህል ነው።

  5. በጋሻው(ተዘራ) እዚሁ ድረ ገጽ ላይ አማራ ጠሉ ቢቢሲ ብሎ አንድ ወገን የዘገበልን አለ። አማራን እንዲያጠፉ አረንጓዴ መብራት የሚያበራ አባባል ነውና እናንተም ሆናችሁ ገንዘብ አባከኑ ያልካቸው ቢቢሲን በሰላማዊ ሰልፍ ብትቀውጡት ውጭ ጉዳይ ሚኒስተሩንና የጠቅላይ ሚኒስትሩን ቢሮ ፋታ ብትነሱት ስራ ሰራችሁ ይባላል። ትግሬዎች አርደው ታራጅ፣ቀምተው ተቀሚ፣ወግተው ተወጊ ሁነው አለምን ሲያሳምኑ እንዲህ ያለ ጽሁፍ በኛ በኩል ብዙም የሚያስገፋ አልመሰለኝም። በል እንግዲህ ያገር ጉዳይ ሁኖብን ነው

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Amharic Amharic Language Learning 737859
Previous Story

ቋንቋችንን ማጎልመስ ውጤቱ በሁሉም ዘርፍ የላቀ ነው – ባንትይሁን ትዕዛዙ

172892
Next Story

አርቲስት/ ዘማሪ/ ሙሉቀን መለሰ 

Latest from Blog

“መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የሚለው የዲያስፖራ ከንቱ አታካራ! – ክፍል ሁለት

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com) በአንዳንድ ስብሰባዎችና የሕዝብ መገናኛ መድረኮች የሚታየው የአንዳንድ ዲያስፖራዎች  “መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የበከተ ከንቱ አታካራ በልጅነታችን ወላጆቻችን ትምህርት እንዲሆነን ይተርኩልን የነበረውን ከጫጉላ ወጥተው ጎጆ ለመመስረት የታከቱ ሁለት ያልበሰሉ ባልና ሚስትን ታሪክ

መነሻችን አማራ መድረሻችን አማራ እና ወያኔያዊ መሠረቱ

የማይወጣ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል። የዛሬን አያድርገውና የትግሬ ልሂቆች “ትግራይ የጦቢያ መሠረት ናት ።  ጦቢያ ያለ ትግራይ፣ ትግራይ ያለ ጦቢያ ሊታሰቡ አይችሉም” በማለት ጦቢያዊ ከኛ ወዲያ ላሳር እያሉ አለቅጥ ይመጻደቁ፣ ይኩራሩ፣ ይታበዩ ነበር። ወያኔ

አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱባቸው ወንጀሎች ጥፋተኛ ተባሉ

ለአመታት በእረስር ላይ የሚገኙት  አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱባቸው የጥላቻ ንግግር ማሰራጨት እና የዕርስ በዕርስ ግጭት መቀስቀስ ወንጀሎች ጥፋተኛ መባላቸው ታውቋል፡፡ አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱበት ክሶች በዛሬ ቀጠሮ የጥፋተኝነት ፍርድ የሰጠው የፌደራል ከፍተኛ

ከ”ችርቻሮ” ድል አልፎ ለመሄድ የአንድነት አስፈላጊነት – ግርማ ካሳ

በአሁኑ ጊዜ ሁለት የፋኖ አሰላለፎች አሉ:: መኖር ያልነበረበት:: አንከር ሜዲያ ከሁለቱም አሰላለፎች፣ ሁለት ፋኖ መሪዎች ጋር ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ ሁለቱን አደመጥኩ፡፡ በሰማሁት ነገር ተደስቻለሁ:: ትልቅ ተስፋ እንድሰንቅም አድርጎኛል:: የአማራ ህዝባዊ ድርጅት የፖለቲካ
Go toTop