እንጉርጉሮ – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

 

amhara

ምን አለ እረኛ ብሎ መጠየቅ
ነው በጥንቱ ዘመን ህዝብህን ማወቅ ፡፡
ዛሬም ወርደህ ስማ አዲሱ መንግስት
እንዳይጎረናብህ የጉለቻው ድስት
እንዲኽም ይላል ህዝቡ ፣
ለመፍትሄው በጋራ አስቡ ፡፡
በቤቴ መች ጠፋ ሦሥትና ና አራት ዲግሪ
በቋንቋ ምክንያት ሆንኩ እንጂ ጦም አዳሪ ፡፡
የተማረ ይግደለኝ ይባል ነበር ዱሮ
ተገዳይ ሆነለት ገዳዩ ዘንድሮ ፡፡
” ነፃ ገብያ ነው ፤ መንግስት አይነግድም ፡፡ ” ይለናል ነጋዴ
አረፌ ልተኛ አልጫ እየበላሁ እየጨኸ ሆዴ ፡፡
ምን አለ ቢነግድ ሱቅ ከፍቶ መንግስት
ለምኖ ከሚሰጥ ፣ ዘወትር ምፅዋት ፡፡
ምን ነበር ሱቅ ቢከፍት ፤ በየከተማው
ህዝብ ከሚማረር ፣ በዝቶ ደላላው ፡፡
እያለ…እያለ
እንካ ሰላምተያውን ያስከተለ
እካ ሰላንቲያ !
በምንትያ !
እዚችው ፣ በእዚችው !
ምንአለ እዚቸው በዚችው !?
የመንግስትን ሥልጣን ደላላ ሻረቸው !
እየበዘበዘች ኪሶ ጨመረቸው !
ታክስ ምናምኒት ደንቡሎ አልሰጠቸው ! !
መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ
መስከረም 1/2014 ዓ/ም

ሰው የሚኖረው ተስፋን ሰንቆ ነው ፡፡ ለማንኛውም ፤ ” አናደጅ ጠፍቶ ነዳጅ ሊገኝ ነው ፡፡ ነገ ፡፡

ነገ በዙረቱ ይዞራል
ሰው ሥለ ነገ ፣በተስፋ ያስባል ፣
ዛሬ እንዲህ አድርጌ፣
ነገ እነዲህ ሆኜ ይላል ፡፡
” ዛሬ፣
የወጪዬን ቀዳዳ ዘግቼ
የገቢ በሬን፣ በሰፊው ከፍቼ
በቁጠባ እየኖርኩ፣ አበቃቅቼ…
ለጊዜው ተጎሳቁዬ ፣
የድሃ ድሃ መስዬ ፣
እየኖርኩ ጥሬ ግሬ
ሣንቲሜን ቋጥሬ
ነገ ስኖር ይታየኛል፣ተንደላቅቄ ፡፡
ህዝብ አዳምን አስደንቄ ! …….”
እያለ …
ሰው ሥለነገ በተስፋ ያስባል፣
ነገ እንዲህ አደርጌ ፤እነዲህ ሆኜ ይላል ፡፡
” ዛሬ የተባረከ ትዳር ፣ መስርቼ፣
ነገ የሚያስቀና ዘር አፍርቼ ፣
ተከብሬ በልጆቼ …
በወግ ማዕረግ ድሬ፣
አንቱ ተብዬ በሰፈሬ
በተድላ እኖራለሁ ተንቀባርሬ…”
ሰው እንዲኽ ሆኜ ይላል ፤
ሥለነገ በተስፋ ያስባል ፤
ነገ እንዲህ አደርጌ ፤እነዲህ ሆኜ ይላል ፡፡
” ዛሬ በአቋራጭ ንግድ ተሰማርቼ ፤
ከደላሎች ጋር ተስማምቼ ፤
እንከፍ ፣ ገሪባውን አጥምጄ ፤
ተቆጥሮ የማያልቅ ገብቶ በእጄ !
በብር ብርድልብስ ተከናንቤ፣
በጠብ እርገፍ ባይ አገልጋይ ተከብቤ ፤
ሙቅ አኝኬ ! ……ገንፎ አላምጬ ፤
ምድርን ለቅቄ ! ከሰው ሁላ በልጬ !
ሰው ዛሬ እንዲህ ና እንዲያ ሀኜ ይላል ፡፡
ሥለ ነገ ኑሮ ስኬት ያልማል ፡፡
በተስፋ ይታየኛል ይላል…
” ይታየኛል ፣ ነገ ለእኔ ብሩህ ሆኖ፣
በሐብቴ ብዛት ሥሜ ገኖ ፣
የሀብት ፀዳል ተከናንቤ ፣
ሰማይን ስረግጣት ጠግቤ ፣
ዓለሜን ስቀጭ
አዳሜን ሳስቆጭ ፤
ዘር ማንዘሬን ሳኮራ
ሣደርገው ቀብራራ ፡፡
………………………
እንዲህ ነው ፤
የሰው እና የነገ ፣ የህይወት ሂደቱ ፣
ራሳችሁን ጨምራቸሁ ፣
የሰውን ምኞት ስትመለከቱ ፡፡
ይኸው ነው ፡፡ …
እውቀት ያለው በእውቀቱ ፤
ገንዘብ ያለው በጥሪቱ ፤
ጉልበት ያለው በጉልበቱ ፤
ሥለ ነገ በተስፋ ያወራል ፡፡
ሥለ መጪ ቀሪው ያውጠነጥናል ፡፡
ሰው በዝንጋታ ኗሪ ነው ፤ የነገ ምርኮኛ
ነገን ዓላሚ ነው ፤ የተስፋም ቁራኛ ፡፡
ለዚህም አይደል !? ሰው ነገን የሚጠብቅ በተስፋ !
ሳያውቀው ነገ ፤ ያስደስት ወይ ያስከፋ !
ዳሩ ግና !
ነገ ሁልጊ ዜም ነገ ነውና !
ዛሬ ሲያከትም ፣ነገ ይመጣል እንደገና፣
ነገ ተመልሶ ፣ በዙረቱ ይዞራል ፣
መች ተመልሶ ከመምጣት ይቀራል ፡፡
ዕለት በዕለትም ፣ነገ በነገ ያታደሳል፣
ነገ ፣ ሁልጊዜም ነገን ይፈጥራል፣
ነገ ፣ ለሰው ሌላ ተስፋን ያረግዛል
ነገ ፣ ለሰው ፣ሌላ ነገን ይወልዳል ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  እጀታ! - በላይነህ አባተ

መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ
( 1982 ዓ/ም በደሌ ኢሉባቦር የተጻፈ ) 2014 ዓ/ም የታደተ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share