ህዝባዊ የብዙሃን አቀፍ ስነልቦና ልክ አንደ አንዲት ኩሩ ልዕልት ስነልቦና ነዉ:- በምርጫም ሆነ በጦርነት አሸናፊዉ ንጉስ ብቻ የሚማርከዉ – ሸንቁጥ አየለ

ለመኢአድ: ለባልደራስ: ለአብን: ለህብር : ለአዴሃን መወያያ መሰረት እንዲሆን የቀረበ ትንታኔ
———————-
ሶሻሊስቶች እና ኮሚኒስቶች የፖለቲካ ርዕዮተ አለማቸዉን ለመንደፍ ከሚቃትቱባቸዉ ቁልፍ መነሻዎች የግለሰቦች ስነልቦናን እና ህዝባዊዉን የብዙሃን ስነልቦና በመተንተን ነዉ:: የግለሰቦችን ስነልቦና ሲተነትኑም በመጨረሻ በሚፈጠረዉ የኮሚኒስት ስርዓት ዉስጥ እያንዳንዱ ከግለኝነት ስነልቦና በመላቀቀ ለብዙሃን እያንዳንዱ ስለሚኖር በብዙሃኑ መሃከል እኩልነት እንጂ ልዩነት አይፈጠርም::
የመጨረሻዉ የኮሚኒስት የማህበረሰብ እኩልነትን ለማንበር የሚቻለዉ አሁን በመላዉ አለም የተንሰራፋዉን ግለኝነት:ለልዩነት የሚስገበገብ እና እራስ ወዳድ የግለሰቦችን ስነልቦና በማረቅ መርህ ላይ የሚቆም ነዉ ሲሉ ያብራራሉ::እዚህ ላይ ሊበራል/ካፒታሊስት ፈላስፎች የሰዉን ልጂ ተፈጥሯዊ መሰረት የሳተ ህልም ነዉ ኮሚኒስቶች የሚያልሙት ሲሉ ይተቿቸዋል::
ኮሚንኒስቶች ግን የሊበራሊስቶችን ትችት ወደጎን በማድረግ ህዝባዊ የብዙሃን ስነልቦናል ትንታኔያቸዉን ያስከትላሉ::ሌኒን “the state and revolution” በሚለዉ መጽሃፉ ህዝባዊዉ የብዙሃን ሀይል የመደብ አንድነት ስለሚያስተሳስረዉ አቢዮቱን ለመምራት የሰራተኛዉን መደብ ከፊት በማድረግ በጋራ የሚሰለፈዉ ከቁሳዊ የመደብ ጥቅሞቹ ባሻገርም የህዝባዊ የጋራ ስነልቦና እሴት ስላለዉ ነዉ ሲል ያብራራል::ይሄንኑ የሌኒን ትንታኔ በርካታ ሶሻሊስቶች እየተቀባበሉ ብዙ ብለዉበታል::
የስነልቦና እና የሶሺዮሎጂ/አንትሮፖሎጂ ጠበብቶች ደግሞ ቡድናዊ የጋራ ስነልቦና የሚሉት አባባል አላቸዉ::የፖለቲካ ሳይንቲስቶች ይሄንኑ የቡድን ስነልቦና መሰረታዊ ጭብጥ በመንተራስ የምርጫ ፖለቲካ ቁልፍ የድል ማጠንጠኛዉ በቡድናዊ ስነልቦና ላይ የሚገነባዉ የህዝባዊ የብዙሃን የጋራ የትሥስር እና የአሸናፊነት ሀይልን የሚያንጸባርቅ ስነልቦናን በደጋፊዎችህ ዉስጥ ማስረጽ ስትችል ብቻ በእርግጠኝነት ታሸንፋለህ ይላሉ::
ወታደራዊ ጠበብት በአንድ አካባቢ በአንድ በታመነ ድርጅት የሚገኝ የጦርነት ድል በቀላሉ በመላዉ ማህበረሰብ ዉስጥ ተንሰራፍቶ ማህበረሰቡ እራሱ የጦር መሪ ሆኖ ጠላትን መደምሰስ የሚችልበት ቁልፍ ቅድመ ሁኔታ ብለዉ የሚያስቀምጡትም ይሄንኑ ከፕሮፖጋንዳ በዘለለ በጋራ እሴታዊ ትሥስር ላይ የቆመ ህዝባዊ የብዙሃን ስነልቦና መፍጠር ሲቻል ነዉ ይላሉ::
ቅንጂት በ1997 ዓም ይሄንኑ የህዝባዊ የብዙሃን ስነልቦናዊ ትሥስር ስትራቴጂ በደንብ ተጠቅሞበት ነበር:: ወደዚያናዉ ዝርዝር ዉስጥ ሳልገባ አሁን ስላለዉ አሰላለፍ ጉዳይ ትልቁን ክፍተት ለማመላከት ልሻገር::
በሚቀጥለዉ ምርጫ ሁለት ሀይላት ብቻ በምርጫዉ ላይ ይሳተፋሉ::እነዚህ ሀይሎችም ሁለት የሆኑበት ደጋፊዎቻቸዉን መሰረት አድርገን ስንከፍላቸዉ ነዉ::የመጀመሪያዉ ሀይል በአቢይ የሚመራዉ የብልጽግና ሀይል:በብልጽግና ዙሪያ የተሰለፉት እነ ኢዘማ እና በግል እንወዳደራለን የሚሉት የብልጽግና ደጋፊዎች( እነ ዳንኤል ክብረትን የመሳሰሉ) አሯሯጮች ናቸዉ::
ይሄዉ በአቢይ የሚመራዉ ሀይል አሁን ያለዉን ሀገመንግስት : የጎሳ አከላለል እና የኦህዴድን/ኦነግን የበላይነት የተቀበለ ኢትዮጵያን ከብሄር ብሄረሰቦች በታች ያሳነሰ የጋራ ህዝባዊ የብዙሃን ስነልቦናን የታጠቀ ደጋፊዎቹን በዚሁ እሴታዊ የስነ ልቦና ትሥስር በዙሪያዉ ያቆመ ሀይል ነዉ::የቤት ስራዉን በደንብ ሰርቷል::ለዚህ ሀይል ተዋህዶ ኦርቶዶክስ እና አማራ የዘር ፍጅት ቢደረግባቸዉም ምኑም ናቸዉ::
ዋና ቁልፍ ግብ ያደረገዉም ኢትዮጵያ እንዳትፈርስ የኦህዴድ/ኦነግ የበላይነትን ማስቀጠል እና ኢትዮጵያዊነትን ከብሄር ብሄረሰብ እሴት በታች ማዋል የሚል ነዉ::የዚህ ሀይል ግቡ ኦነግ/ኦህዴድ እንዳይከፋዉ እሹሩሩን እንደ ግብ የወሰደ ስነልቦና ላይ የቆመ ነዉ::
ሁለተኛዉ ተፎካካሪ ሀይል የሚቆምበት ህዝባዊ የብዙሃን ስነልቦና ደግሞ የብሄር ፖለቲካ በህግ መታገድ አለበት:የአማራ እና ኦርቶዶክስ ግድያ መቆም አለበት:ኢትዮጵያዊነት ከብሄር ማንነት በላይ ነዉ የሚል ነዉ:: በዚህ ሀይል ስር መኢአድ: ባልደራስ: አብን: ህብር : አዴሃን ሊጠቀሱ የሚችሉት ዋና ወካይ ሀይሎች ናቸዉ::
እነዚህ እዉነተኛ የኢትዮጵያ አንድነት ሀይል እና የአማራ ሀይላት በደንብ ካልተቀናጁ እና መናበብ ካልቻሉ በዋናነት የጋራ ህዝባዊ የብዙሃን የጋራ ስነልቦና ያለዉን ደጋፊያቸዉን ያዳክሙታል:: እስካሁን ባለዉ ሁኔታ የምርጫ ቅስቀሳቸዉ የተበተነ እና የጋራ የመቀስቀሻ አጀንዳን ቀርጸዉ ወደ ጋራ ህዝባዊ የብዙሃን መሰረታቸዉ መቅረብ አልቻሉም::
በተለይ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ብትን ሀይል መሆናቸዉን በደንብ ያሳያል:: አሁንም ፈጥነው መቀናጀት/መናበብ/መጣመር ካልቻሉ : የጋራ የምርጫ ምልክት ካልሰዬሙ: የጋራ የመቀስቀሻ የምርጫ አጀንዳዎችን መቅረጽ ካልቻሉ እንኳንስ ኢትዮጵያን መረከብ በራሳቸዉ ላይ ትልቅ አደጋን ደቅነዋል::
ይሄም አደጋ ምርጫዉን በተበታተነ ሁኔታ በማድረግ ህዝባዊ የብዙሃን የጋራ ስነልቦናዊ መሰረት ያለዉን ደጋፊውያቸዉን በመበታተን : ከዚያም በመጨረሻ ምርጫዉ መጭበርበር ሲገጥመዉ በተናጠል በመነጫነጭ ለአቢይ ሀይል ጭዳነት በተናጠል እራሳቸዉን የሚያቀርቡ ይሆናሉ::
የተበታተነ ትግል እና በተበታተነ መልክ ወደ ምርጫ ፖለቲካ መግባት ማለት ለተኩላ በጎቹን አስበልቶ ኋላ በየጓዳዉ ተወሻቂ መሆን ማለት ብቻ አይደለም የሚሆነዉ::ታዳኝ እንሰሳም መሆን ይከተላል እንጂ::
እነዚህ ሀይሎች የትግል መሰረታቸዉ የሆነዉ ህዝባዊ የብዙሃን ስነልቦና በጥልቅ እሴት ላይ የቆመዉ አማራ ላይ እየተከናወነ ያለዉ የዘር ፍጅት መቆም አለበት የሚል ነዉ:: እንዲሁም ኢትዮጵያዊነት ከብሄር ማንነት በላይ መሆን ስላለበት የጎሳ ፖለቲካ በህግ ታግዶ አሁን ያለዉ የጎሳ አከላለል መፍረስ አለበት ብሎ የሚያምን ስነልቦናዊ ጭብጥ ነዉ::
በአሁኑ ሰዓት በወለጋ:በመተከል:በኦሮሚያ : በጉራ ፋርዳ አማራ ህዝብ ላይ የዘር ፍጅት እየተደረገ:በአዲስ አበባ ኢትዮጵያዊነት ከጎሳ ማንነት በታች ተዋርዶ:ልዩ ልዩ የደቡብ ኢትዮጵያ ነገዶች ተገፍተዉ እየተጨፈጨፉና ወደዳር ተገፍተዉ ሳለ መኢአድ: ባልደራስ: አብን: ህብር : አዴሃን በጋራ በመቀመጥ ይሄንኑ አጀንዳ የምርጫ የጋራ መቀስቀሻቸዉ አድርገዉ በማስቀመጥ የጋራ የስነልቦና መሰረት ያለዉን ደጋፊያቸዉ በጋራ ለአንድ የጋራ ግብ እንዲንቀሳቀስ ማድረግ አልቻሉም:: የጋራ የምርጫ ምልክትም አላቀረቡለትም::
የፖለቲካ ብስለት በጎደለዉ ትንታኔ አንዳንዶች እንደሚመስላቸዉ እነሱ ጋ ብዙ ደጋፊ ያላቸዉ ስለሚመስላቸዉ በጋራ በጥምረት ሰፊ ሀይል ይዞ ለመምጣት ዳተኝነት ይታይባቸዋል::ሆኖም ከላይ ሶሻሊስቶቹም:ሊበራሊስቶቹም:የስነልቦና ጠበብቶችም: የማህበራዊ ሳይንስ ሊቃዉንትም: የምርጫ ፖለቲካ ተንታኞችም:የወታደራዊ የዉጊያ ጠበብ ተንታኞችም በጋራ እና በጥልቀት የሚስማሙበትን የህዝባዊ የብዙሃን የጋራ ስነልቦናዊ ትሥስር የመዘንጋት ስህተት ይስተዋላል::
ይሄም የስነልቦናዊ እሴት እና ጭብጥ ሊተነተን የሚገባዊ ከምልዓታዊ መስፈርት በመነሳት እንጂ በተናጠላዊ የማንነት ወጭት በመሰፈር ሊሆን አይገባዉም::ለምሳሌ አንድ የአማራ ድርጅት አማራ የሆነ ሁሉ በስነልቦናዉ እኔን ይመርጠኛል ብሎ ካሰበ የዘነጋዉ ነገር አለ::ከአማራነት ጋር የሚደረበዉን የኢትዮጵያዊነት ካባ ረስትቶታል::እንዲሁም አንድ የአንድነት ድርጅት ነኝ ብሎ የሚያስብ ሀይል አንድ ሰዉ ኢትዮጵያዊነትን ስለሚወድ እኔን ይመርጠኛል ብሎ ከተዘናጋ የዚያን ሰዉ ስነልቦና የተነተነዉ በጎዶሎዉ ነዉ::የአማራ ህዝብ እየታረደ ኢትዮጵያዊነት አለ ብሎ የሚቀበል እዉነተኛ ኢትዮጵያዊ አይኖርም::
ምክንያቱም ከላይ እንደተባለዉ የመኢአድ: የባልደራስ: የአብን: የህብር : የአዴሃን የድጋፍ መሰረታቸዉ የሆነ አንድ የጋራ ህዝባዊ የብዙሃን የጋራ እሴታዊ የስነልቦና ትስሥር ያለዉ ሀይል ሊተነተን የሚገባዊ ምልዓታዊ መሰረቱን ይዞ እንጂ በተናጠላዊ የስነልቦና ቅንጥብታቤአዊ ስሌቶች ሊሆን አይገባም::ብዙዎች የሚሳሳቱትበት መሰረታዊ ትንታኔ የብዙሃን ህዝባዊ ስነልቦና አንድን ሀይል የሚቃንነበትን መነጽር የሚያዩበት ስሌት ነዉ::
ህዝባዊዉ ስነልቦና የኔ የሚላቸዉን ፓርቲዎች እንደራሱ ይቆጥራል እንጂ መኢአድን ለብቻዉ:አብንን ለብቻዉ:አዴሃንን ለብቻዉ:ባልደራስን ለብቻዉ: ህብርን ለብቻዉ ነጥሎ አይመለከትም::በጋራ ከመዉደድም ብሎም የራሱ አድርጎ ከመቁጠርም በዘለለ ግን ለጋራ ድርጊት ሊያንቀሳቅሰዉ የሚችል የጋራ አላማ እና የጋራ ምልክት ይዘዉ እንዲቀርቡለት ይፈልጋል::
ይሄንንም የጋራ አላማ እና የጋራ የምርጫ ምልክት ካላገኘ ሶስት ነገሮች ይከተላሉ::አንደኛ ግራ ይጋባል::ሁለተኛ ስነልቦናዊ ዳተኝነት ይሰፍናል::ሶስተኛ የእኔ በሚላቸዉ ሀይሎች ላይ የህዝባዊ የብዙሃን የበቀል ስነልቦናዊ እርምጃ ይወስዳል::ስለሆነም እነሱ ከሚጠብቁት በተቃራኒ ይቆማል::
እናም መደምደሚያያዉ የተበታተነ ትግል እና በተበታተነ መልክ ወደ ምርጫ ፖለቲካ መግባት ማለት ለተኩላ በጎቹን አስበልቶ ኋላ በየጓዳዉ ተወሻቂ መሆን ማለት ብቻ አይደለም የሚሆነዉ::ታዳኝ እንሰሳም መሆን ይከተላል እንጂ::
ስለሆነም የጋራ መሰረት ያለዉን ህዝባዊ የብዙሃን ስነልቦናዊ እሴት ያለዉን ሀይል ለማንቀሳቀስ ለአሁኑ ምርጫ ብቻ ሳይሆን ለቀጣዩም የፖለቲካ ትግል በጋራ ለድርጊት ለማቆም የመኢአድ: የባልደራስ: የአብን: የህብር : አዴሃን ፈጣን የጋራ እርምጃ እጅግ ቁልፍ መሆኑን ሁሉ ቆሞ ማስተዋል ይጠበቅበታል::
ኢትዮጵያን እግዚአብሄር ይባርክ !
ተጨማሪ ያንብቡ:  አንድነት በአርባምንጭ ከተማ ያደረገው ሰላማዊ ሰልፍ ክፍል 1, 2, 3, 4 and 5

1 Comment

  1. የጋራ አቋም እንዳንይዝ እንቅፋት የሆነብን ነገር በገዢው ፓርቲ ማንአለብኝነት ያለጥፋታቸው በእስር ተወርውረው የሚገኙት አባላቶቻችን እና መሪዎቻችን የፍርድ ሂደት መጉዋተቱ ነው።ያለ ለውጥ “ልዋጭ ልዋጭ ልዋጭ!” እያልን መንቀሳቀሳችን ለእዚህ ጉድ አብቅቶናል።

    የገዢው ፓርቲ አብላጫውን የፓርላማ መቀመጫዎች ተቆጣጥሮ ሌሎቹ የአንድነት ፓርቲዎችን በቅርብ ርቀት ተገኝተው በአይነ-ቁራኛ እንዲታዩ የሚያስችል ለይስሙላ ያህል ጥቂት ምንም ፋይዳዎች የማይፈይዱበት ወንበሮች እንዲይዙ ለምርጫ አስፈፃሚ አካላት ትዕዛዝ መተላለፉ ታውቅዋል። ኢዜማ ለገዢው ፓርቲ ሲያጎበድድ የከረመውም የእዚህ ትዕዛዝ ሰለባ ነው። ስለዚህ በአሁኑ ወቅት የገዢውን ፓርቲን ከወሬ በዘለለ ምድር ላይ በተጨባጭ መልኩ በመገዳደር ላይ የሚገኙት በትጥቅ ትግል የሚገኙት ኃይሎች ብቻ መሆናቸው ታውቅዋል። በትጥቅ ትግል ወልቃይትን እና ራያን ተቆጣጥሮ የሚገኘው ኃይልም አንድ ተጠቃሽ ተገዳዳሪ ሆኖ መገኘቱ ታውቅዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share