ክስ ተመስርቶባቸው በእስር ላይ የሚገኙት የቀድሞ የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታና የገዢው ብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩት አቶ ታዬ ደንደዓ የዋስትና መብት ተጠብቆላቸው ከእስር እንዲለቀቁ ዛሬ ተወስኗል፡፡
ከዚህ በፊት በሦስት ክሶች ተከሰው በሁለቱ ነጻ የተባሉትና “ህገወጥ የጦር መሳሪያ ይዘው መገኘት” የሚለውን ክስ እንዲከላከሉት ፍርድ ቤት መበየኑን ተከትሎ በዋስትና ተለቀው ጉዳያቸውን ከውጪ ለመከታተል የጠየቁት አቶ ታዬ፤ በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እና ጠቅላይ ፍርድ ቤት የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ ሆኖ ነበር፡፡ ይሁንና እስካሁን ውሳኔን በመቃወም አቤት ያሉት ተከሳሽ አቶ ታዬ ዛሬ ባስቻለው የፌዴራሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ተወስኖላቸው የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅ ተብሏል፡፡
ዛሬ ጠዋት በፌዴራሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ቀርበው ጉዳዩን የተከታተሉት ባለቤታቸው ወ/ሮ ስንታየሁ ዓለማየሁ ለዶይቼ ቬለ እንደተናገሩት፤ ፍርድ ቤቱ ከዚህ በፊት በስር ፍርድ ቤቶች የተሰጠውን የዋስትና መከልከል ውሳኔ ሽሮ አቶ ታዬን በ20 ሺህ ብር ዋስ እንዲለቀቁ ወስኗል፡፡ “ሰበር ሰሚ ችሎቱ ዛሬ ጠዋት አራት ሰዓት ግድም በተሰየሙ ዳኞች አቶ ታዬ እስካሁን ያቀረቡትን ቅሬታም ጠቃቅሶ ጠባብ የህግ ትርጉም ተሰጥቶ የዋስትና መብት መከልከል ትክክል አይደለም ብሎ ነው የዋስትና መብት እንዲጠበቅ የወሰነው” ብለዋል፡፡

ወ/ሮ ስንታየሁ አክለውም አቶ ታዬ 20 ሺህ ብር አስይዘው አሊያም የሰው ዋስ ጠርተው ከእስር እንዲለቀቁ ሰበር ሰሚ ችሎቱ ዛሬ መወሰኑን አስረድተዋል፡፡ “ፍርድ ቤቱ ዛሬ ጠዋት ባዘዘው መሰረት አሁን ከሰዓቱን ለዋስትና የተባለውን 20 ሺህ ብር በመክፈል በውሳኔው መሰረት ሂደቶቹን በመከታተል ላይ ነን፡፡ አሁን ቃለምልልሱን በምሰጥበት ሰዓት እስካሁን የተፈጠረ ነገር ባይኖርም በፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መሰረት እየሄድን ነው ዛሬ በስራ ሰዓት የተቻለንን የህግ ሂደቶቹን እንሄድበታለን” ነው ያሉት፡፡ ዶቼ ቬለ ዜናውን እስካጠናቀረበት ዛሬ ከሰዓት ዘጠኝ ሰዓት ግድም አቶ ታዬ ከእስር አልተለቀቁም፡፡
የዛሬ አንድ ዓመት ግድም ከስልጣን የተነሱት አቶ ታዬ ደንደዓ ሁከት ማነሳሳት፣ ጸረ-ሰላም ኃይሎች መደገፍ እና ህገወት የጦር መሳሪያ ይዘው መገኘት በሚሉ ሶስት የክስ ጭብጦች ተከሰው የመጀመሪያዎቹ
ሁለት ክሶች ውድቅ ተደርጎላቸው ሶስተኛውን የክስ ጭብጥ በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት እየተከታተሉ ነው ሲል ከአዲስ አበባ የዘገበው ሥዩም ጌቱ ነው፡፡ አቶ ታዬ እንዲከላከሉት የተባለውን ህጋዊ ፈቃድ የሌለው የጦር መሳሪያ ጉዳዩን ያውቁልኛል ያሉትን አምስት ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት በተከላካይ ምስክርነት ጠርተው በመከላከልም ላይ ናቸው፡፡
ዘገባ ስዩም ጌቱ DW ከአዲስ አበባ