ነጻ ምርጫ ባልዋለበት መስከረም 30 – ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ

/

የኢትዮጲያ ሕገ መንግስት አንቀጽ 54

ቁጥር 1 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ፤ ሁሉ አቀፍነጻቀጥተኛ ትክክለኛ በሆነና ድምፅ በሚስጥር በሚሰጥበት ሥርዓት በየአምስት ዓመቱ በሕዝብ ይመረጣሉ።

የኢትዮጲያ ሕገ መንግስት አንቀጽ 58

ቁጥር 2 የምክር በቱ የሥራ ጊዜ ከመስከረም ወር የመጨረሻ ሳምንት ሰኞ አስከ ሰኔ ሠላሳ ነው፤

ቁጥር 3 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚመረጠው ለአምስት ዓመታት ነው፣የሥራ ዘመኑ ካማብቃቱ ከአንድ ወር በፊት አዲስ ምርጫ ተካሂዶ ይጠናቀቃል።

በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ 1995 በተካሄደው የሕዝብ ተወካዮች ምርጫ ነጻ፤ ቀጥተኛና ትክክለኛ በሚል የራሱ የህወሃት ማኒፌስቶ በሆነው ሕገ መንግስት በግልጽ የተደነገጉ ድንጋጌዎች በህወሃት/ኢህአዴግ አምባገነናዊ አገዛዝ በግልጽ በተጣሱበት ኢ- ሕገ መንግስታዊ ምርጫ፣ አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝን ጠቅላይ ሚንስትሩ አድርጎ የሾመው ፓርላማ፣ መቶ በመቶ ኢህአዴግ እና አጋር ድርጅች ተወካዮችን ይዞ ተሰየመ።ሕገ መንግስቱ ስልጣን የሚያዘው ነፃና ገለልተኛ በሆነ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ብቻ መሆኑን ስለሚደነግግ፣በ1995 የተሰየመው ፓርላማና በዛ ፓርላማ የሚመረጥ ጠቅላይ ሚንስትር ሁሌም ኢ-ሕገ መንግስታዊ ናቸው። ይህ ተመሳሳይ የሕገ መንግስት ጥሰት ፣በየክልሎች ባሉ ምክር ቤቶችም ተፈፅሟል።

እውነተኛ ዲሞክራሲ ባለበት ስርዓት ፣ሕገ መንግስትን ጭምር ድምፁን በመስጠት ብቻ፣ መቀየር ወይም ማሻሻል የሚችለው፣ ማለትም ከሕገ መንግስት በላይ የሆነው ህዝብ ፣ከላይ የተዘረዘረውን የህወሃት/ኢህአዴግ ህገ ወጥ አካሄድ በመቃወም፣ ከፍተኛ የህዝብ አመፅ አካሄደ። ከፍተኛ መስዋዕትም ከፈለ።በዛም የአቶ ሃይለማርያም አስተዳደር ፣ብሎም ጠቅላላው የህወሃት የመጨቆኛ መሳሪያዎቹ መፈናፈኛ ስላጡ ፣እውነተኛውን የፖለቲካ ስልጣን ለቀው ወደ መቀሌ ለማፈግፈግ ተገደዱ።

የእውነተኛው የፖለቲካ ስልጣን ባለቤት በነበረው ሕወሃት ስር፣ ኢህአዴግ በሚል ተሰባስበው የነበሩትም የለውጥ ሃይሎች፣ እንደማንኛውም የኢትዮጲያ ህዝብ የግፉ ሰለባ ስለነበሩ ፣የህዝብን የመነሳሳት ስሜት ተመክተው እንቅስቃሴውን ተቀላቅለው ስለነበር፣ህወሃት ከህዝብ በደረሰበት ጫና ላይ ፣ተጨማሪ የውስጥ አስገዳጅ ጉልበት በመሆን፣ ኢህአዴግ ለመጀመርያ ጊዜ ከህወሃት ፍቃድ ውጪ የሆነና በራሱ የቆመ ጠቅላይ ሚንስትር መምረጥ ቻለ። ኢህአዴግ ከህውሃት ጭቆና ነጻ ወጣ።

ህወሃት ከስልጣን ኮርቻ የወረደበት ሂደት ውጫዊ ነው ወይስ ውስጣዊ ለሚለው ፣ከኢህአዴግ ውጪ ያለው ህዝብ እና ተቃዋሚው ሃይል በተለያየ መልኩ ግብ ግብ ባያደርጉ ኖሮ ፣ውስጣዊው የለውጥ ሃይል መጨረሻው መስሎ ማደር፣ስደትና ተከርቸም ይሆኑ ነበር።የተማሪውን ንቅናቄ ተከትሎ ለመንግስት ቅርበት የነበረው ደርግ ስልጣን ላይ አንደወጣው፣የሕዝብ አመጽን ተከትሎ መንግስት ውስጥ የነበሩት ኢህአዴጎች የለውጥ ሃይል የሚል ስም ይዘው ስልጣኑን ተረከቡ።ሃቁ ይህ ነው።

የተማሪውን እረብሻ ተከትሎ ፣ከንጉሱ ስልጣን የተረከቡት ደርጎችም ይሁኑ፣ ህወሃትን የተኩት የለውጥ ሃይል ኢህአዴጎች የማህበረሰቡ ክፋይ በመሆናቸው፣ ፍጹም ተመልካች ነበሩ ማለት ሳይሆን፣እነዚህ የውስጥ ሃይሎች ለሚፈልጉት ለውጥ ያበረከቱት ነገር ቢኖርም ፣ብቻቸውን ለውጥ ማምጣት የሚችሉ አልነበሩም። በአንጻሩ ውጫዊው ሃይል፣ በሁለቱም ጊዜ ብቻውን ለውጥ ላማምጣት ሙሉ አቅምና ዕድል ነበረው። የተማሪው ንቅናቄ ንጉሳዊውን ስርዓት አሽቀንጥሮ መጣል ይችል ነበር።አሁን ከሁለት ዓመታት በፊት የተካሄደውም የሕዝብ አመጽ ፣ ህወሃት ኢህአዴግን ለመቀሌም ሳያደርስ ጠራርጎ ለመብላት ሙሉ አቅም እና ዕድል ነበረው። የለውጡ ባለቤት ባመዛኙ የውጪው ሃይል ነው#ይህም አሌ የማይባል ሀቅ ነው።

ህወሃትን ገፍቶ ወደ መቀሌ ያባረረውን ውጫዊ ሃይል፣ ካለው ህገ መንግስት አንፃር ስንመለከተው በሶስት ተከፍሎ የሚታይ ነው።አንደኛ ሕገ መንግስቱ ሙሉ በሙሉ በስራ ላይ ይዋል የሚል። ሁለተኛ በወያኔ ቦታ ተተክቶ ለመዝረፍ የቋመጠ። ሶስተኛ የኢትዮጲያ መሰረታዊ ችግር የወያኔ ማኒፈስቶ የሆነው ሕገ መንግስት ስለሆነ፣ ቢያንስ ይሻሻል ወይም ሙሉ በሙሉ ተቀዶ አዲስ ሕገ መንግስት ይቀረጽና ስራ ላይ ይዋል የምንል።ሕገ መንግስቱ ይከበር ወይም ከወያኔ ተራ ይድረሰን የሚሉት ፣ላለው ከፋፋይ ሕገ መንግስት ቅርብ የሆኑና ከሕገ መንግስቱ ምንም ችግር የሌላቸው እንደሆኑ እንመለከታለን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  "መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ" መጽሐፍ ላይ የተደረገው ውይይት

ሃሳቡን ላለማወሳሰብ፣ በሁለትና በሶስተኛ ተራ የተቀመጡትን ለሕገ መንግስቱ ቅርብ የሆኑ የአመፅና የተቃውሞ ሃይሎች ፍላጎት ብቻ ይዘን ብንነሳና ፣ህገ መንግስቱ የተጣሰው የት ነው ብንል፣ በርካታ ጉዳዮችን ማንሳት እንደምንችል ቢታወቅም፣ ምርጫን ስንወስድ፣ ሕገ መንግስት የተጣሰው በ1995 ነው። መጪው መስከረም 30 አይደለም።ጥሰቱ ሕዝብ ዶር አብይን መርጦ፣ ግን ድምፅ ተጭበርብሮ አቶ ሃይለማርያም ስለተመረጡ አልነበረም።ጉዳዩ ያ ቢሆን ኖሮ ፣ዶር አብይ ጠቅላይ ሚንስትር ሆነው በመመረጣቸው የህገ መንግስት ጥሰቱ ይታረም ነበር።ከዛም ክርክሩ የዶር አብይ የስልጣን ዘመን አቶ ሃይለማርያም ከተሾሙበት አንስቶ አምስት ዓመት ተቆጥሮ የነ ልደቱ ጁሃር መስከረም 30 ያብቃ ወይስ ጠቅላይ ሚንስትር ከሆኑበት ቀን ጀምሮ ማለትም ከሁለት ከምናምን ዓመት በኋላ የሚመጣው መስከረም 30 ይሁን በሚል ይሆን ነበር።

በ1995 የተሰየመው ፓርላማ የምርጫ ሂደትና ውጤት ፣ሕገ መንግስታዊ ስላልነበር ፣በህገ መንግስቱ መስፈርት ከሄድን፣ የኦቶ ሃይለማርያምም ይሁን የዶር አብይ ስልጣን በምንም መልኩ ህጋዊ ሊሆን አይችልም። ዶር አብይ በአቶ ሃይለማርያም ድምፅ ተጭበርብሮባቸው በምርጫው የተሸነፉ ስላልነበሩ ፣የዶር አብይ ወደ ስልጣን መምጣት፣የተጭበረበረውን ምርጫ ህጋዊ አያደርገውም።እንዴት ወደ ሕጋዊነት እንመለስ ሲባል ፣ለምሳሌ በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 15  ማንኛውም ሰው በሕይወት የመኖር መብት አለው ።ማንኛውም ሰው በሕግ  በተደነገገ ከባድ ወንጀል ቅጣት ካልሆነ በስተቀር ሕይወቱን አያጣም ይላል።ይህ በህወሃት ኢህአዴግ አልተከበረም። ይህን ለማክበር የአምስት ዓመት የምርጫ ቀጠሮ መያዝ አያስፈልገውም።ከዛሬ ጀሞር ሊታረም ይችላል። ከሕግ ውጪ አትግደል ።አለቀ።

በአንቀጽ 54 ላይ የተፈጸመውን የሕገ መንግስት ጥሰት ለማረም ግን ፣ያለው አመራጭ አንድ እና አንድ ብቻ ነው። ይህም ሁሉ አቀፍ ፤ ነጻ፤ ቀጥተኛ ትክክለኛ በሆነና ድምፅ በሚስጥር በሚሰጥበት ሥርዓት ምርጫ ማድረግ።እስካዛ ድረስ ሕገ መንግስቱ እንደተጠሰ ነው።በሕገ መንግስቱ መሰረት ከሄድን የዶር አብይ ስልጣን ሕገ ወጥ የሚሆነው መስከረም 30 ሳይሆን ዛሬ ነው።የአቶ ሃይለማርያም ስልጣን ሕገ ወጥ ስለሆነ ማንም ቢተካቸው ያንን ስልጣን፣ከሕገ መንግስት አንጻር ህጋዊ ሊያደርገው አይችልም።ስለዚህ በሕዝብ ያልተመረጠ መንግስት የሚመጣው መስከረም 30 ሳይሆን ዛሬ ነው።በዛሬና ባዛሬ ዓመት ፣በነሃሴ 30 እና በመስከረም 30 መሃከል ምንም ልዩነት የለም።በሕገ መንግስቱ መሰረት ዛሬም፣የዛሬ ዓመትም ሆነ የዛሬ ሁለት ዓመት በኢትዮጲያ በሕገ መንግስቱ መሰረት በህዝብ የተመረጠ ፓርላማና ጠቅላይ ሚንስትር የለም።

የዶር አብይ ቅቡልነት (legitimacy) የተመሰረተው በህገ መንግስት ወይም በምርጫ ሳይሆን በሌሎች ሁለት አበይት ምክንያቶች ነው።አንደኛ በነበረው የህዝብ አመፅ መሃል፣ የለውጥ ሃይሉ ይዞ በተነሳቸው ሃሳቦች ፣ይህ የለውጥ ህይል እንዲሁም መሪው ዶር አብይ አህመድ ከፍተኛ የህዝብ ድጋፍ በማግኘታቸው። ሁለተኛ ጠቅላይ ሚንስቱሩ ብሎም የለውጥ ሃይሉ ፣እንደማንኛውም በጉልበትም ቢሆን ስልጣን ላይ ያለ መንግስት፣ የሀገሪቱን የመከላከያ፣የፖሊስ ሰራዊት፣ ደህንነት እና ቢሮክራሲ የሚመሩ በመሆናቸው ።አሁን በስራ ላይ ያለውም ፓርላማ ስራውን የቀጠለው ሕገ መንግታዊ ፓርላማ ሆኖ ሳይሆን፣ በሀገራችን ብሂል ከቀዳዳ ይሻላል ጨምዳዳ ( necessary evil /ጠቃሚ እርኩስ) በሚል ነው።ይህ ካለን የፖለቲካ ምስቅልቅል ፣የኢኮኖሚ ኋላ ቀርነት እና የሀብት ውስንነት አንጻር ተገቢ ሊሆን ይችላል።

ዶር አብይም የሽግግር መንግስት የሚል ጥያቄ ሲቀርብላቸው ፣ህገ መንግስት አለ ፣እስከ መስከረም 30 በህግ የተመረጠ ፓርላማ አለ አላሉም።ያሉት እኔ አሸጋግራችኋለሁ ነበር።እኔ አሸጋርራችኋለሁ። አንተ አታሸጋግረንም ብሎ ተቃውሞ ማንሳት ያኔ ነበር። እስከ መስከረም 30 ተጠብቆ የሚቆይ ሕገ መንግስታዊነት የለም።አንተ አታሸጋግረንም ብሎ ለመቃወም ግን የህዝብ ድጋፍ ያስፈልጋል።በጊዜው ዶር አብይ ከፍተኛ የህዝብ ድጋፍ ስለነበራቸው ፣የትኛውም ግለሰብ ይሁን የፖለቲካ ድርጅት ከወረቀት ባለፈ ፣ህዝብ ልብ ውስጥ የሚገባ ሃሳብ አቅርቦ፣ ከዛ በፊት የነበረውን የህዝብ አመፅ በማስቀጠል፣ ሁሉን ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች ያሳተፈ የሽግግር መንግስት እስከማቋቋም ፣እነ ዶር አብይን ማስገደድ የሚችል ቁመና አልነበረውም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የወቅቱ የኢትዮጵያ ጠላቶች - በገ/ክርስቶስ ዓባይ

ጠቅላይ ሚንስትሩ አራሳቸው የተረዱት ባይመስልም ፣የዶር አብይ ቅቡልና (legitimacy)፣ በመላው አለም ግልብጥ ብሎ የወጣው፣ ከሕገ መንግስት በላይ የሆነው የሰፊው የኢትዮጲያ ህዝብ ድጋፍ እንጂ፣ የወያኔው ሕገ መንግስት አይደለም። ዶር አብይ ስልጣን ላይ የወጡት ፣ያንን ዘረኛ ስርዓት፣ያንን ኢ – ሕገ መንግስታዊ አካሄድ ለመገርሰስ በተደረገው ከፍተኛ መስዋእትነት ነበር።የዶር አብይ ቅቡልነትም የሚመነጨው ከዛ ሰፊ የህዝብ መስዋእትነት እና ሰፊ የሃዝብ ድጋፍ እንጂ ፣ባልነበረው ህገ መንግስታዊ ምርጫ አይደለም።

በህገ መንግስቱ መሰረት ከተሄደ መስከረም 30 የሚባለው ቀን ትርጉም የሚኖረው እናም ጥያቄ ሊነሳበት የሚችለው፣ ሕገ መንግስታዊ በሆነ መንገድ ፣ማለትም በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች መሃከል፣ በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 54 መሰረት ፣ነፃና ፍትሃዊ የምርጫ ውድድር ተደረጎ የተሰየመ ፓርላማ ቢኖርና ይህም ፓርላማ በአብላጫ ድምፅ የሾመው ጠቅላይ ሚንስትር ቢኖር ነበር። እንደዛ አይነት ፓርላማ ቢኖር፣ ዛሬ ሕጋዊ ነህ፣ መስከረም 30 በኋላ ህጋዊነትህ ያበቃል ማለት ይቻላል።ህወሃት ኢህአዴግ ይቅርታ የጠየቀው እኮ በጥፍር መንቀል ብቻ አይደለም።ግድያ፣ጥፍር መንቀል፣ማንጠልጠል፣እናትን ልጇን ገሎ የልጇ እሬሳ ላይ እንድትቀመጥ ማድረግ፣የዘር ማጥፋት ዝርፊያ ወዘተ ወንጀሎችን የፈለፈለው ግዙፉ ወንጀል እኮ፣ ጸረ ሕዝብ የሆኑትን የስልጣን ማማ ላይ ያወጣው ፣የ 1995 የምርጫ ማጭበርበር ነው።

 

ይህችን መሰረታዊ የሀገራችን የፖለቲካ ሀ ሁ የማይረዱ ብቻ ሳይሆን ቂል ፣ስግብግብ እና መርህ አልባ የፖለቲካ ልሂቃን ነን ባዮችን ማየት የእለት ተእለት ክስተት ሆኗል።ይባስ ብሎ የህግ ምሁራኑ ሳይቀር አይናቸውን ጨፍነው፣ በደመ ነብስ አንቀፅ 93 አንቀፅ ምናምን እያሉ ሲጃጃሉ በማየቴ እጅግ ተገርሜ አለሁ።በቦሃ ላይ ቆረቆር እንዲሉ ፣ፕሮፌሰር እንድርያስ ከመስከረም 30 በኋላ በሕዝብ ያልተመረጠ መንግስት ሊኖረን ነው እያሉ ፕሮፌሰራዊ ስላቅ ችሎታቸውን አሳዩን።ጋሽ ፕሮፌሰር አስቲ የትኛው ነበር በህዝብ የተመረጠ መንግስት ፣መለስ ወይስ ሃይለማርያም። ዶር አብይስ ይቅርታ የጠየቁት የምርጫ ማጭበርበሩንም አካተው ነበር። ይቅርታስ ለሕጋዊነት፣ለመግባባት በር ይከፍታል አንጂ፣ እንዴትሕገ ወጥነትን ሕጋዊ ሊያደርግ ይችላል።

 

የሀገሪቱን የህግ ምሁራን ሁሉ ሰብስቦ የሚያነጋግር ጉዳይ መኖር ካለበት ጉዳዩ መስከረም 30 ሊሆን አይችልም።መስከረም 30 ተራ የአዘቦት ቀን እንጂ ፣ህገ መንግስታዊ በሆነ መንገድ ፣ማለትም ነፃና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ስልጣን የያዘ ሃይል አምስት አመት ጠብቆ ህጋዊነቱ የሚያልቅበት ቀን ስላልሆነ።የወያኔው ሕገ መንግስት የተጣሰው ወይም የሚጣሰው መጪው መስከረም 30 ሳይሆን የዛሬ ሃያ ምናምን አመት ጀምሮ በተደረጉት ተደጋጋሚ ኢ ሕገ መንግስታዊ ምርጫዎች ነው።እነዚህም 1995፣2000፣2005፣2010፣2015 ናቸው።

 

እስካሁን ድረስ መንግስት በህዝብ የተመረጠ ነበር ፣ከመስከረም 30 በኋላ በህዝብ የተመረጠ መሪና ፓርላማ አይኖርም በሚል፣ የህግ ምሁራኑ ሳይቀሩ አይናቸውን ጨፍነው፣ በደመ ነብስ (mechanically) አንቀፅ 93 አንቀፅ ምንትሴ እያሉ ሲጃጃሉ መመልከትን ያህል አሳዛኛና ተስፋ አስቆራጭ ነገር የለም።ምሁራኑ ቢያንስ ምርጫን በተመለከተ፣ ህገ መንግስቱ እስካሁን ባሉት አስተዳደሮች ተረግጦ ያለ መሆኑንና፣ዛሬ ኢትዮጲያ ከህገ መንግስት በላይ የሆነው ህዝባዊ ድጋፍ የስልጣን ምንጫቸው በሆነው ዶር አብይ አሸጋጋሪነት፣ ወደ ህገ መንግስታዊነት ለመመለስ ሂደት ላይ መሆኗ የውይይቱ አልፋ መሆኑን ማስመር ነበረባቸው።

 

ያ ሲሆን ውይይቱ ከደመ ነብሱ (mechanical) መስከረም 30 ንትርክ ወጥቶ፣ ስለ ትክክለኛና ስለ አንኳር የህገ መንግስት ጥያቄዎች ሊያተኩር ይችላል። ማን ህገ መንግስቱን ጣሰ፣ በጥሰቱስ ስንት እና የትኞቹ ህገ ወጥ ህጎች በህገ ወጥ ፓርላማዎች ፀደቁ ፣በነዚህስ ህገ ወጥ ህጎች ማን ተጠቀመ፣ ማንስ ተጎዳ ፣እንዴትስ ይታረሙ የሚሉት ጉዳዮች፣ ሀገር እና ህዝብን ወደ ልቀት ይወስዱ ነበር።የተመለከትነው ያን ሳይሆን ምሳሌያዊ ንፅፅር (logic) በዞረበት ያልዞሩ የሚመስሉ፣የወሎ ርሃብ ምንጩ የዲሞክራሲ እጦት ነው፣ዲሞክራሲ ባለበት ርሃብ አይከሰትም (ህንድ)፣ኮሮናን የፈጠረው ዲሞክራሲ አለመኖር ነው (እንደምታ)፣ዲሞክራሲ መኖር ኮሮናን በብቃት መከላከል ያስችላልና (ቻይና ና አሜሪካ) ህዝብም እየሞተ ምርጫ ይካሄድ የሚሉ ምሁራዊ ተብዬ የቁልቁለት ሃሳቦችን ነው።እዚህ ላይ ቢያንስ ዶር ታደሰ ሌንጮ እስካሁን የነበረው ምርጫ የይዘት ችግር እንደነበረው በማስገንዘቡ ሳላመሰግነው ማለፍ አልችልም። የካሊፎርንያው ፕሮፌሰር ዝም ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አድዋ እና "አንድ ወጥ" አከባበር -ሸንቁጤ - ከካናዳ

 

መስከረም 30 ምን ይጠበስ የምለው፣ እኔ በግሌ የአመፅ ቀጠሮ የያዙትን ፅንፈኞች የአመጽ እቅድ የማስቆም አቅም ኖሮኝ ሳይሆን ፣ዶር አብይ ህገ መንግስታዊ ስልጣን ያላቸው እስከ መስከረም 30 ነው የሚለው የቂል ሃሳብ ስለሆነ ነው።ዶር አብይ እኔ አሸጋግራችኋለሁ አሉ እንጂ እስከ መስከረም 30 በህገ መንግስታዊ መንገድ በህዝብ የተመረጠ መንግስት አለ፣ የምን የሽግግር መንግስት ነው የምታወሩት የሚል መልስ አልሰጡም።መሬት ላይ ያለውም እውነታ ያ አይደለም። እስከ መስከረም 30 ህገ መንግስታዊ የሆነ አሰተዳደር እንዳለ ቢታመን፣ አሻጋሪ ተሻጋሪ የሚባሉ ቃላትም አይደመጡም ነበር። ዶር አብይ ምርጫው መስከረም 30 የሚለውን መቀበላቸው ሊያስመሰግናቸው ይገባል።ነጻና ፍትሃዊ ምርጫ ከአራት ዓመት በኋላ ይካሄዳል የሚል ፍኖተ ካርታ ለማቅረብ የሚከለክላቸው ሕገ መንግስታዊ ሰነድ የለም።

 

እኔ አሸጋግራችኋለሁ። ግልፅ አማርኛ ነው። ሽግግር ሂደት ላይ ነን።የምንሸጋገረው ወደ ህገ መንግስታዊ ስርዓት ነው። በተቻለ መጠን አሁን ካለው ህገ መንግስት አንቀፆች አፍራሽ ያልሆኑትን እየተጠቀምን ፣በጥንቃቄ መጓዝ እንዳለብን ሃላፊነት በሚሰማቸው ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች እና በገዢው ፓርቲ መሃከል መናበብ ያለ ይመስላል። (አብዲ ኢሌ) የምረዳው ይህን ነው እንጂ ፣ህገ መንግስታዊ በሆነ መልኩ በነፃና ፍትሃዊ ምርጫ የተመረጠና ህገ መንግስታዊ ስልጣኑ መስከረም 30 የሚያበቃ ፓርላማም ይሁን ጠቅላይ ሚንስትር ኢትዮጲያ ውስጥ የለም። እዚህ ላይ ሕገ መንግቱን ሳያሻሽሉ ወደ ምርጫ መግባት፣ ለኢትዮጲያ ሃገራችን ትልቅ ችግር ይዞ ሊመጣ እንደሚችል እንደ አንድ ኢትዮጲያዊ አምናለሁ።

 

ቁልፉ ነገር የዶር አብይ የስልጣን ቅቡልና መሰረት (legitimacy) በመላው አለም በግልፅ ያየነው የህዝብ የድጋፍ ማእበል እንጂ፣, ኢህአዴግ መቶ በመቶ አሸናፊ የሆነበት፣ በፈረንጆቹ የ 1995 በኢትዮጲያ የተካሄደው የምርጫ ድራማ አይደለም።ያ ቢሆን አመጽም ባላስፈለገ።ይህን ከተረዳን መስከረም 30 ምንም ልዩ ቀን እንዳልሆነ እናውቃለን።ስለዚህ መስከረም 30 የሚባለው ጩኽት መቆም አለበት።የአብይ አስተዳደር ኮቪድ 19 መከላከሉ ላይ ይበርታ። የግብፅንም ጉዳይ ተረጋግቶ ይከታተል። ካለው ጊዜያዊ ችግር አንጻር የህዝብ ደህንነት ከፖለቲካ ስልጣን ሊቀድም ይጋባል።

 

ዶር አብይ አሸጋግራችኋለሁ በማለት ለህዝብ የገቡትን ቃል ይጠብቁ አይጠብቁ ለማየት ትእግስት ይኑረን። እንደተባለው የጤና ባለሞያዎችና የምርጫ ቦርድ ተነጋግረው ምርጫው ሊካሄድ ይችላል በሚሉበት ጊዜ ምርጫው ይካሄዳል። ከመጀመርያውም የለውጥ ሃይሉ፣ ምርጫ ቦርድ መስከረም 30 ን አገናዝቦ እንዲቀሳቀስ መስማማቱ የሚያስመግነው ነው።አሁን ደግሞ ኮቪድ 19 ትልቅ ችግር ይዞ መጥቷል። ትንሽ አንታገስ።መሰረታዊ ሀገረ ቅርፅ ላይ እንኳ ስምምነት በሌለበት ሁኔታ ፣የፖለቲካ ድርጅቶች የሽግግር መንግስት የሚለው የእቃ እቃ ጨዋታ ይቁም ።

 

የቀጣዩ ምርጫ ዋና ፋይዳ ከመስከረም 30 በኋላ አዲስ ፓርላማና ጠቅላይ ሚንስትር መትከልና አለመትከል አይደለም።ቀጣዩ ምርጫ በይዘት ልዩ የሆነ ፣ህዝብ ነፃና ፍትሃዊ መንገድ በዋነኛነት፣ በተዘዋዋሪ መንገድ ፣አሁን ያለው ሕገ መንግስት ይቀጥል አይቀጥል፣ይሻሻል አይሻሻል ፣በሚል የሚበይንበት መሆኑን እንረዳ።ይህ እጅግ ግዙፍ ቁም ነገር ስለሆነ ችኮላ ጥቅም አይኖረውም። ለዚህ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ትኩረታቸውን ከመስከረም ሰላሳው ትርጉመ ቢስ (random) ቀን ንትርክ አንስተው ፣ለወሳኙ ምርጫ ህዝብን ማንቃትና ማስተማር ላይ ቢያተኩሩ ኢትዮጲያ ተጠቃሚ ትሆናለች።ህዝቧን ትታደጋለች።

 

መስከረም 30 የሚል ቀነ ገደብ ያላስቀመጠው ሕዝብ ከህገ መንግስት በላይ ነው።

 

ሃላፊነት የሚሰማችሁ የአንድነት ሃይሎች ልብ በሉ።

 

መላኩ ከአትላንታ

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share