ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ የመጣውን የህገ ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውር ለማስቀረት የጦር መሳሪያ አያያዝና አጠቃቀም ህግ ሊወጣ መሆኑ ተሰማ፡፡ በፌደራል ጠቅላይ አቃቤ የህግ ጥናት ማርቀቅና ማስረፅ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ በላይሁን ይርጋ ለፖሊስና ርምጃው ጋዜጣ እንደተናገሩት እስካሁን ጦር መሳሪያን የተመለከተ ህግ አለመኖሩ ክፍተት ስለፈጠረ ይህን ህግ በዚህ አመት ለማውጣት እየተሰራ ነው፡፡ ህጉ ሲወጣ የጦር መሳሪያ ፈቃድ ማን ይሰጣል የሚለው ችግር ተቀርፎ በግልፅ እንደሚቀመጥም አስረድተዋል፡፡
ይህ የጦር መሳሪያ ህግ ፈቃድ ከመስጠት ባለፈ ሃላፊነት በሚሰጠው ተቋም አማካኝነት አቅም ያላቸው ድርጅቶች ጦር መሳሪያ እንዲያመርቱ፣ ከውጭ አምጥተው እንዲያከፋፍሉና እንዲሸጡ የሚያስችል እንደሆነም አመልክተዋል፡፡ የተለያዩ አገራት ልምድ በሚታይበት ጊዜ የጦር መሳሪያን አያያዝና አጠቃቀም የሚቆጣጠር አንድ መንግስታዊ ተቋም እንዳለ ያወሱት አቶ በላይሁን ይህንም ተሞክሮ በቀጣይነት በአገር ውስጥ ለመተግበር እየጠሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ‹‹በሀገራችን ማህበረሰቡ የጦር መሳሪያን እራሱን ለመጠበቅ፣ ጠላትን ለመከላከል እና ንብረቱን ለመጠበቅ ሲል ይዞ ይታያል:: ቢሆንም ግን አንዳንድ ህገ-ወጥ አካላት በማህበረሠቡ ያለን የጦር መሳሪያ ወደ ህገ-ወጥ ተግባር ለመቀየር የተለያዩ ምልክቶች ይስተዋላሉ:: ይህንንም ሁሉም አካል መከላከል ይኖርበታል›› ያሉት ሃላፊው አዲሱ ህግ መንግስት ትጥቅ ሊያስፈታ ፈልጎ ነው በሚል የሚወራው ሀሰት እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ ወደፊት የጦር መሳሪያ አያያዝን አሁን ማህበረሰቡ የታጠቀው መሳሪያ ምንድን ነው? የሚለውና ማህበረሰቡ ምን አይነት መሳሪያ መታጠቅ አለበት? የሚለው በግልፅ እንደሚዘረዘር ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም አዋጁ ከሚፈቅደው እስታንዳርድ በላይ የታጠቀ ማህበረብ እንዴት ነው መስተናገድ ያለበት? የሚለው በአዋጁ የሚገለፅ ይሆናል:: ይህን ሲያብራሩም ‹‹አውቶማቲክ ጠመንጃ በሀገራችን የሚታወቀው ተቀባብሎ ምላጭ ሲሳብ ሁለት እና ከዚያ በላይ ጥይት መተኮስ የሚችል ሲሆን በሌሎች ሀገራት ግን አውቶማቲክ ማለት ጠመንጃው ተቀባብሎ ምላጭ ሲሳብ በአንዴ ሁለትና ከዚያ በላይ በሆኑ አፈሙዞች ሁለትና ከዚያ በላይ ጥይቶችን መተኮስ ሲችል ነው:: ይህንንም በአዋጁ ትኩረት የተደረገው ጉዳይ ነው›› ሲሉ ተናግረዋል:: በሌላ በኩል ዋና ዳይሬክተሩ አቶ በላይሁን ይርጋ የፀጥታ ሀይሉን የጦር መሳሪያ አያያዝ በተመለከተ እንደገለፁት በሀገራችን ያሉ የክልል ፖሊሶች የሚይዙት የመሳሪያ አይነት የተለያየ መሆኑን ጠቅሰው አንዳንዶች እስከ ድሽቃ በመያዝ ለህብረተሰቡ ስጋት የሚሆኑ እንዳሉ አስረድተዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከባህርዳር 4 ሺህ 492 የሽጉጥና 370 የብሬን ጥይት ወደአዲስ አበባ ሊገባ ሲል ተያዘ። በትናንትናው ዕለት በህገ ወጥ መንገድ በመተማ በኩል ወደ መሃል ሀገር ሊገባ የነበረ 4 ሺህ 492 የሽጉጥና 370 የብሬን ጥይት በቁጥጥር ስር መዋሉን በጉምሩክ ኮሚሽን የባህርዳር ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት አስታውቋል፡፡ ግምታዊ ዋጋቸው 306 ሺ 640 ብር የሆኑት እነዚህ ጥይቶች የተያዙት በአካባቢው በነበሩ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ሲሆን በዝውውር ስራው ላይ የነበሩት ግለሰቦችም በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=KcPKUXGZAys&t=28s