ለዋሊያዎች አጭር መልእክት አለኝ – ይድረስ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን!

ከይነጋል በላቸው

በጉጉት ለምንጠብቀው የጥቅምት ወር የዓለም እግር ኳስ የማጣሪያ ጨዋታ እንኳን በሰላም ሊያደርሰን ነው፡፡ እኔ ታላቅ ወንድማችሁ ስለስፖርት አንዳችም ግዴለኝም – እዬዬም ሲደላ ነውና፡፡ ስሜቴ ሙሉ በሙሉ ሀገር ላይና የዓለም ፖለቲካ ላይ ነው ብል ብዙም አልተሳሳትኩም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን የሀገሬ ስፖርተኞች በተለይ በውጭ ሀገር ሩጫ ወይም የኳስ ግጥሚያ ካላቸው ስፖርቱ ውስጥ ፖለቲካው እየተዛነቀብኝ ቁጭ ቁጢጥ ነው እሚያደርገኝ፡፡ ስለሆነም ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ 180 ደቂቃ እስከቀራችሁ ያን ሰሞን ድረስ የነበረውን ሂደት በከፍተኛ ፍቅርና የሀገር ስሜት እከታተል ነበር፡፡ ምን አለፋችሁ ብዙ ብርጭቆ ድራፍቶችንና ‹ሲስተር ጤናየ›ን አስጨርሳችሁኛል – ግልጽነት አይከፋም፡፡

በነገራችን ላይ እናንተ ሀገራችሁን ለማስጠራት በሜዳዎች ስትማስኑ እኔ ደግሞ በወያኔ የተነጠቅነውን ነጻነታችንንና የሕዝቡን መበደል በሚመከለት በብዕር እየጫጫርኩ በድረገፆች አማካይነት ለአንባቢያን እልካለሁ – በስሜ ገብታችሁ በትዳስሱ ብዙዎችን ታገኟቸዋላችሁ፡፡ ይህን የማደርገው ታዲያ በነጻና በፍጹም ፍላጎትም ነው – ብዙውን ጊዜ ሌሊት እንቅልፍ የለኝም፤ ቀንም መደበኛ ሥራየን እየበደልኩ በዚሁ ‹ሥራ› እጠመዳለሁ፡፡ ካለችኝ አነስተኛ ገቢ ደብዳቤዎቼን ለመላክና የተጻፉ ጠቃሚ ሀገራዊ መጣጥፎችንና መረጃዎችን ለማንበብ እንዲሁም ዳውንሎድ ለማድረግ ለኢንተርኔት ካፌዎች ብዙ ገንዘብ እከፍላለሁ፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ገንዘብ የሚያስገኙ ሥራዎች እያስጠሉኝ መጥተው ያለችኝን ገንዘብ በሚያከስረኝ የሀገሬ ጉዳይ ላይ ተጠምጄ ብዙ … እያየሁ ነው፡፡ ብዙ ሌሊቶችን በቅጡ አልተኛም፡፡ በማየው የተበለሻሸ ሀገራዊ ነገር ሁሉ መጨነቅ መጠበቤን ደግሞ አታንሱት፡፡ ይህን የምላችሁ ‹ገድሌ›ን ልነግራችሁ ፈልጌ ሳይሆን ዛሬ በቋጠሮ ድረገፅ እንደተከታተልኩት ቦነስ አነሰን የሚል ጥያቄ ለመንግሥት ማቅረባችሁን በመረዳት የተሰማኝን ሀፍረት በመግለጽ በሀገራዊ ስሜት ብቻም እንደኔ ዓይነት ኑሮ የሚኖሩና ከኔም እጅግ በባሰ ወረድ ብዬ ልጠቁማችሁ የሞከርኩትን የመሰለ ሕይወት የሚመሩ፣ በተቻላቸው አቅም ሁሉ ለሀገራቸው የሚተጉ ዜጎች መኖራቸውን ልገልጽላችሁ ፈልጌ ነው – ከነሱ ተማሩና አስተያየቴን በጥሞና አድምጡ፡፡ አልደብቃችሁም – ባነበብኩት በጣም፣ እጅግ በጣም አፍሬያለሁ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ማን ይናገር የነበረ..... የታኅሣሡ ግርግር እና መዘዙ!

እኛ ኢትዮጵያውን በዚህ አንታወቅም፡፡ ቀደም ሲል ናይጄሪያዎች የዚህ ዓይነት ጥያቄ ጠይቀው እንደነበር አስታውሳለሁ – ያኔም ራሴን ልክ እንደ አንድ ናይጄሪያዊ  በመቁጠር በነሱ አፍሬያለሁ – በባንዲራ እንዴት እንደዚህ ይጠየቃል ብዬ ተቆጥቻለሁ፤ በኛው ሲመጣ በሀገራችን አንድ የሆነ ዕንቁ ባህላዊ ዕሤት እንደጠፋብን ገመትኩ፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ደግሞ ከማንም የበለጥን ኩሩ ሕዝብ ነን፡፡ የዛሬውን ዘመነ ወያኔ አያድርገውና የሀገርን ባንዴራ በሚመለከት በሆድና በብልጭልጭ ነገር አንታማም፡፡ የፈረስ ሽንት እየጠጡና የጫማ ቆዳ እየበሉ የሀገራችንን ነጻነት አስጠብቀው ካለፉ ጀግኖች የተገኘን ትውልዶች በዚህ ጊዜ ምን መጣብንና ነው ‹እንዲህ ካላደረጋችሁልን የመጫወት ስሜታችን ይቀዘቅዛል› የምትሉት? በአሁኒቷ ቅጽበት እንደናንተ ያሉ ወጣች ለኢትዮጵያ ነጻነት ሲሉ በዱር በገደሉ ድንጋይ እየተንተራሱ አፈር እየላሱ ባሉበት ሁኔታ እናንተ በአንጻራዊ ሁኔታ በጥሩ ኑሮ ላይ የምትገኙ ወጣቶች እንዲህ ዓይነት በኢትዮጵያ ምድር ያልተለመደና ለባህላችን ባዕድ የሆነ ጥያቄ እንዴት ልትጠይቁ እንደቻላችሁ ገርሞኛል፤ እንደኢትዮጵያዊነቴም አሳስቦኛል – እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ አንዱአለም አራጌ፣ ውብሸት ታዬ፣ በቀለ ገርባ፣… ስለሚባሉ ምርጥ ዜጎች የምታውቁት ነገር ስለመኖሩ መጠራጠር ጀመርኩ – መጠራጠሬ ልክ እሆን? እርግጥ ነው – በዚህ በሰው በላ የወያኔ ሥርዓት ውስጥ ያደጋችሁ በመሆናችሁ፣ በዚህ ሀገሩን ሸጦ በበላ የወያኔ መንግሥት የሞተ የትምህርት ሥርዓት ውስጥ ያለፋችሁ በመሆናችሁ ለዚህ ዓይነቱ እንግዳና አስነዋሪ ስሜት ተዳርጋችሁ ሊሆን ይችላል፡፡ ግን ግን ሳይቃጠል በቅጠል ነውና ከኢትዮጵያዊ ጨዋነት ጋር ስለማይሄድ ከእንደዚህ ያለ ነገር ተቆጠቡ፡፡ አደራችሁን ተውት፤ ይቅርባችሁ፡፡

ይህን ጥያቄ ያነሳውን ጓደኛችሁንም ምከሩትና መልሱት፡፡ እንዲህ የምለው መንግሥትን ከወጪ ለመታደግ ብዬ እንዳልሆነ ከፍ ሲል በመግቢያዬ የገለጽኩላችሁ ነገር አለ – የእናቴን ገዳይ የምደግፍ ገልቱ ሰው አይደለሁመ፤ የተቃወመኳችሁ ይህ ነገር ለጆሮየም ስለቀፈፈኝ ነው፡፡ የለመዱት በዚያው በለመዱት ይደራደሩ፤ እኛ ግን ለባንዲራችን የምንሞት ጨዋ ሕዝብ ነን፤ ስለዚህ ምንም እንኳን ዋናዋ ባንዲራችን በገሃድ ለመውለብለብ ጥቂት ጊዜ ቢቀራትም ለጊዜው ያው ባለምናምንቴው ባንዲራቸው ይውለብለብበት – እኔን ስለማይወክለኝና ከእኔ ዕውቅናና ውዴታ ውጪ ስለተጣለብኝ ነው የማልወደው፡፡ ለማንኛውም ስለመንግሥት መክፈል መቻልና አለመቻል ሳይሆን ይህ ጥያቄያችሁ ሕዝብን ቅር ያሰኛል የሚል ከፍተኛ ፍራቻ አለኝ፡፡ ፍየል ከመድረሷ ቅጠል መበጠሷም ያስብልባችኋል፡፡ ድህነት ሰውን አይገድልም፡፡ ትህትና ይኑራችሁ፡፡ ከዚህ በላይ ብናገር ደስ አይለኝም፡፡ እስኪ እናንተንም ይቅናችሁ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በህገመንግስቱና በሽግግሩ ቻርተር ይሁን ቢባል እንኳ (ቢባል እንኳ ነው እያልኩ ያለሁት) ወልቃይቶችና ራያዎች የአማራ ህዝብ አካላት ከመሆን የሚያግዳቸው አንዳችም ነገር የለም!!!

ውድ ወገኖች እባካችሁን ይህች መልእክቴ ለነዚህ ምርጥ የሀገር አለኝታዎች እንዲደርስልኝ አድርጉልኝ፡፡

ጥቅምት 3 ቀን 2006 የድል ቀናችን እንዲሆን ዕድላችን የሠመረ ይሁን (በነገራችን ላይ – የናይጄሪያ ሞኝ ጳጳስ በመላዋ ናይጄሪያ የ9 ቀን ጸሎትና ሱባኤ እንዲያዝ ማወጃቸውን በዜና ዕወጃዎች ስሰማ በጣም ሳቅሁ፤ ገረመኝም፡፡ የኢትዮጵያው ፓትርያርክና ኢማም ለ18 ቀናት ቢያውጁስ? እግዚአብሄር በዚህ የሚገባ አይመስለኝም ወይም እንዲገባ አልጠብቅም፡፡ ሁላችን የእርሱ ፍጡራን በመሆናችን ከአንዳችን ለአንዳችን ያዳላል የሚል ግምትም ሆነ እምነት የለኝም፡፡ በርትቶ መጫወትና ባይሆን ሰይጣናዊ አንደርብና ደንቃራ እንዳይኖር አጥብቆ መጸለይ ብቻ ነው ትልቁ ጠቃሚ ነገር፡፡ በጸሎት ውድድሮችን ማሸነፍ ከባድ ይመስለኛል፡፡

 

3 Comments

  1. I agree with all these. And the praying? Is some how funny thing. Prayer is unconditionaly necessary . But in these case, it reminds me the Italian pope praying for and blessing the army!

  2. who are you you are. what are you talking about the Ethiopian team is the poorest in the world any national team will ask for bonce you think you are the only one who cares about Ethiopia you can not relate everything with badira and politices you know nothing
    long live for walyas do not her rubbish like this go go go walyas…./

Comments are closed.

Share