አቡነ ሳሙኤል “እገሌን ካልመረጣችኹ፣ ካላስመረጣችኹ” የሚሉ አካላት እንዳሉ አመኑ

“በየብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ቤት፣ በእኔም ቤት ሳይቀር እየዞሩ እገሌን ካልመረጣችኹ፣ ካላስመረጣችኹ የሚሉ አካላት እንዳሉ ግልጽ ነው” አቡነ ሳሙኤል ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ

(ዘ-ሐበሻ) አቡነ ሳሙኤል በኢትዮጵያ ከሚታተመው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ “እኔ ለፓትርያርክነት ምረጡኝ ብዬ ቀስቅሼ አላውቅም፤ ሆኖም ግን እገሌን ካልመረጣችሁ፤ ካላስመረጣችሁ የሚሉ አካላት እኔም ቤት መጥተው ነበር” በማለት በተደጋጋሚ ዘ-ሐበሻን ጨምሮ በሌሎች ሚድያዎች የተዘገበውን ነገር አመኑ።

የ6ኛው ፓትርያርክነት መንበር ወደ አቡነ ማቲያስ እያመራ ነው እየተባለ ባለበት በዚህ ወቅት “መንግስት ተጠቅሞብኝ ጣለኝ” እያሉ የሚገኙት አቡነ ሳሙኤል በተለይ ውጭ ሃገር ከሚገኘው ሲኖዶስ ጋር የነበረው እርቀ ሰላም እንዳይሳካ ከፍተኛውን ጥረት በማድረግ ለመንግስት ውለታ ውለዋል ተብሎ ይነገርላቸዋል። ከአዲስ አድማስ ጋር ያደረጉት ቃለ ምልልስ ብዙዎችን ያነጋገረና ምናልባትም ተሸናፊነታቸውን በጉልህ ያሳየ ነው የሚሉ ታዛቢዎች አሉ።
በተለይም አቡነ ሳሙኤል “ፓትርያርክነት የአባትነት፣ የቡራኬ ሥልጣን ነው፤ ለእኔ አገልጋይነት ይሻለኛል፤ አገልጋይ መኾን ነው እንጂ፤ አገልጋይነት÷ ሃይማኖትን መጠበቅና ማስጠበቅ፣ ሕዝብንና እግዚአብሔርን በማእከል ኾኖ ማገናኘት እንጂ አዛዥ፣ ገዥ፣ አሳሪ፣ አሳሳሪ መኾን አይደለም፡፡ ለመኾኑ እንዴት ነው የፓትርያሪክነት ሥልጣን ይሰጠኝ ብዬ የምጠይቀው?” ማለታቸው ያስገረማቸው የዘ-ሐበሻ የቤተክህነት ምንጮች አቡነ ሳሙኤል በመንግስት ተከዳሁ እያሉ ከማውራታቸው ጋር ተያይዞ አባባሉ በተለያዩ መንገዶች እየተመነዘረ ነው ብለዋል።
አቡነ ሳሙኤል ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ በሰጡት ቃለ ምልልስ “ከምርጫው ጋር በተያያዘ÷ ሹመት እንደሚሰጣቸው፣ በሥራ እንደሚመደቡ፣ በሕንጻ ኪራይ፣ በውጭ ዕድል ቃል የተገባላቸው መራጮች አሉ ተብሏል…” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ “ለመሾምም፣ ሕንጻ ለማከራየትም፣ በሥራ ለመመደብም፣ ወደ ውጭ ለመላክም ሥርዐት አለው፡፡ ከተጠቀሱት የትኛውም ነገር ከሥርዐት ውጭ እንዳይፈጸም ተከፍቶ የነበረው መንገድ ተዘግቷል፡፡ በሌላ በኩል የፓትርያሪክ ምርጫ መንፈሳዊ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ መንገድ ፕትርክናውን ለማግኘት ማሰብና መሞከር ሕግም አይፈቅድም፡፡ ይህ የሥልጣን ስግብግብነት ነው፡፡ መራጮቹስ እነማን እንደኾኑ በስም ይታወቃሉ ወይ? ይህን አሉባልታ ያመነጩትና የሚያስተጋቡት የምርጫውን ሂደት ለማወናበድ፣ ሕጋዊውን አሠራር ወደ ቤተሰባዊነት፣ ዘረኝነትና አድሏዊነት ለመውሰድ ማመኻኛ የሚሹ ሕገ ወጥ ቡድኖች ናቸው፡፡” ብለዋል።
“ስድስተኛው ፓትርያሪክ ኾነው እንዲመረጡ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን፣ የቤተ ክህነት አመራሮችንና ታዋቂ ግለሰቦችን አግባብተዋል? ስለጉዳዩ ላይ ሊቃነ ጳጳሳቱ ትችት እንደሰጡ ተዘግቧል። መንግሥት ባለሥልጣናትን ማግባባትዎና ‹‹መንግሥት ፓትርያሪክ ኾኜ እንድመረጥ ይፈልጋል›› እያሉ ማስወራትዎ. . .” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄም “ምረጡኝ ብዬ አላልኹም፤ ምረጡኝ ብዬ አላውቅም፡፡ ይህን አድርገኻል የሚሉኝ ወገኖች እውነተኛ ከኾኑ መረጃውን ለምን አያቀርቡም? የቤቱን [የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን] ዕድገት፣ ልማትና መሻሻል ርምጃዎች ሲያኮላሹ የነበሩ ሰዎች ስሜት ነው፡፡ ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል፤ በየትኛውም አቅጣጫ የተለያዩ አካላት ብዙ ሊናገሩ ይችላሉ፤ ይህንንም የሚሉት የቤታችንን የዕድገትና ልማት ርምጃ ሲያኮላሹ የነበሩ ግለሰቦችና አሁን ደግሞ በምርጫው ዙሪያ የተደራጁ ቡድኖች ናቸው፡፡ ፓትርያርክነት የአባትነት፣ የቡራኬ ሥልጣን ነው፤ ለእኔ አገልጋይነት ይሻለኛል፤ አገልጋይ መኾን ነው እንጂ፤ አገልጋይነት÷ ሃይማኖትን መጠበቅና ማስጠበቅ፣ ሕዝብንና እግዚአብሔርን በማእከል ኾኖ ማገናኘት እንጂ አዛዥ፣ ገዥ፣ አሳሪ፣ አሳሳሪ መኾን አይደለም፡፡ ለመኾኑ እንዴት ነው የፓትርያሪክነት ሥልጣን ይሰጠኝ ብዬ የምጠይቀው? ሹመቱ የመንፈስ ቅዱስ ምርጫ ነው፤ ሥርዐቱ የሚፈጸመው በፍትሕ መንፈሳዊ፣ በሕገ ቤተ ክርስቲያን፣ በፓትርያርክ ምርጫ ሕገ ደንቡ መሠረት ነው፤ ሕጉን፣ ሥርዐቱን የሚፈጽመውና የሚያስፈጽመው ቅዱስ ሲኖዶሱና ሕዝቡ እንጂ መንግሥት አይደለም፤ በሕገ መንግሥቱ የመንግሥትና ሃይማኖት ግንኙነት ምን መኾን እንደሚገባው በግልጽ ተደንግጓል፡፡ ያግባባኹትም የጠየቅኹትም የመንግሥት አካል ይኹን ባለሥልጣን የለም፡፡” በማለት መልሰዋል።
በመጨረሻም አዲስ አድማስ ጋዜጣ “በምርጫው የሚሳተፉ ካህናትና ምእመናን ለሚኖራቸው ድርሻ እርስዎ ምን ይላሉ? በምርጫው ዙሪያ ይካሄዳል ስለሚባለው የቡድኖች እንቅስቃሴስ?” በሚል ላቀረበላቸው ጥያቄ “በየብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ቤት፣ በእኔም ቤት ሳይቀር እየዞሩ እገሌን ካልመረጣችኹ፣ ካላስመረጣችኹ የሚሉ አካላት እንዳሉ ግልጽ ነው፡፡ ሥልጣን ባለው አካል መንፈሳዊ ሥልጣንን ለመያዝ የሚደረገው ሽር ጉድ ሁሉ በፍትሕ መንፈሳዊ፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የተወገዘ ነው፤ ይህን የሚያደርጉ አካላት በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ ይጠየቃሉ፡፡ እንዲህ ኾኖ የሚሾመው አባትም ቢኾን ሢመቱ ሥጋዊ ሹመት ይኾንና በነፍስም በሥጋም ያጎድለዋል፤ ያለጊዜውም ሊያሥቀስፍ ይችላል” ሲሉ መልሰዋል።
በሌላ ዜና ዛሬ አዲስ አበባ ላይ ታትሞ የወጣውና ለመንግስት ቅርበት ያለው ኢትዮቻነል ጋዜጣ “የስድስተኛው ፓትሪያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ የመጨረሻ አምስት ዕጩዎችን ለማቅረብ ስምንት ጳጳሳትን መምረጡ ታወቀ” በሚለው ዜናው የ8 ሊቃነጳጳሳትን ስምና ፎቶ ግራፍ ዘርዝሯል።
የኢትዮቻነልን ዘገባ ለግንዛቤ ይረዳዎት ዘንድ ያንብቡት።

ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስትያን ስድስተኛውን ፓትሪያሪክ ለማስመረጥ የተቋቋመው አስመራጭ ኮሚቴ ከየካቲት 1 እስከ 8 / 2005 ዓ.ም ከምዕመናኑ የተለያዩ ጥቆማዎችን ሲቀበል የሰነበተ ሲሆን ከእምነቱ ተከታዮች የተገኘውን ጥቆማ መሰረት በማድረግ ኮሚቴው አምስት ጳጳሳትን በዕጩነት ለማቅረብ በዝግጅት ላይ ሲሆን የምርጫ መስፈርቱን ካሟሉ አስራ ዘጠኝ ዕጩ ጳጳሳት መካከል የተሻለ ተቀባይነት አላቸው የተባሉ ስምንት ጳጳሳት ለይቶ ማስቀመጡን በመንበረ ፓትሪያሪክ የሚገኙ ምንጮች ለዝግጅት ክፍላችን ገልፀዋል ፡፡ ከነዚህ ዕጩዎች መካከል አቡነ ማትያስ ፣ አቡነ ጎርጎርዮስ እና አቡነ ሳሙኤል ከትግራይ ፣ አቡነ ኤልሳዕ ከጎንደር ፣ አቡነ ማቲዎስ እና አቡነ ዮሴፍ ከሸዋ እንዲሁም አቡነ ህዝቅኤል እና አቡነ ማቲያስ ከወሎ እንደሆኑ ምንጮቻችን የላኩልን ዘገባ ያሳያል ፡፡

የዝግጅት ክፍላችን ይህንን መረጃ መሰረት በማድረግ እላይ ስማቸው በተዘረዘሩ ጳጳሳት ዙርያ የተለያዩ መረጃዎችን ለማሰባሰብ ጥረት ያደረገች ሲሆን ምዕመኑና ለቤተ ክርስትያን ቅርበት ካላቸው አንዳንድ ወገኖች ያገኘነው መረጃ በሚከተለው መልኩ ለማቅረብ እንሞክራለን ፡፡

አቡነ ማቲያስ በአሁኑ ሰአት በእየሩሳሌም በሚገኘው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በመሆን በመስራት ላይ የሚገኙ በቅዱስ ሲኖዶሱ ከሚገኙ ጳጳሳት መካከል ሲኒየር የሚባሉ አባት ናቸው ፡፡ ጳጳሱ አብዛኛውን የጵጵስና ዘመናቸው በተለያዩ አገራት በሚገኙ ሀገረስብከቶች ያሳለፉ እና ጥሩ አለምአቀፋዊ ልምድ እንዳላቸው እንዲሁም በሀይማኖት ትምህርታቸው የበሰሉና በአካዳሚያዊ ትምህርትም የመጀመርያ ዲግሪ እንዳላቸው እንዲሁም በስነምግባራቸው የተመሰገኑና በሲኖዶሱ ውስጥ ጥሩ ተቀባይነት ያላቸው መሆኑ ከምንጮቻችን ያገኘነው መረጃ ያሳያል ፡፡ ነገር ግን ከዜግነት ጋር በተያያዘ የሌላ ሀገር ዜግነት አላቸው የሚል ወሬ በተለያዩ ወገኖች በመነሳት ላይ ይገኛል ፡፡

አቡነ ጎርጎሪዮስ በሀይማኖታዊ ዕውቀታቸው የበሰሉ እና በሲኖዶስም ሆነ በሀገረ ስብከታቸው ከፍተኛ ተቀባይነት ያላቸው የሀይማኖት አባት መሆናቸው እና የአስተዳደር አቅማቸውም ከፍተኛ የሚባል እንደሆነ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ ለጳጳሱ ቅርበት ያላቸው አስተያየት ሰጪ ለሪፖርተራችን ገልፀውለታል ፡፡

የዝግጅት ክፍላችን ሪፖርተሮች ከፓትሪያሪክ ምርጫው ጋር በተያያዘ በተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር መረጃ በሚያሰባስቡበት ወቅት አቡነ ሳሙኤል በአሁኑ ሰአት ፓትሪያሪክ ሆነው ለመመረጥ የሚያስችላቸውን የምረጡኝ ዘመቻ አጧጥፈው እያስኬዱ መሆናቸው መረጃዎችን አግኝተዋል ፡፡ አቡነ ሳሙኤል ከዚህ ቀደም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የነበሩ ሲሆን አሁን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስትያን የልማት ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ናቸው ፡፡

የሰ/ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሆኑት አቡነ ኤልሳዕ ከፓትሪያሪክ ምርጫው ጋር ተያይዞ የተሻለ ግምት ተሰጥቷቸው ይገኛል ፡፡ አሁን ካሉ ጳጳሳት በአገልግሎት ዘመን ሲንየር የሚባሉ ፣ በስነ ምግባራቸው የተመሰገኑና ጥሩ ተቀባይነት ያላቸው መሆኑን ያገኘነው መረጃ ያሳያል ፡፡

አቡነ ማቲዎስ አሁኑ ወቅት የወላይታና ዳውሮ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በመሆን እያገለገሉ የሚገኙ ፣ ጥሩ ሀይማኖታዊ ዕውቀት የተላበሱ ፣ በሲኖዶሱ እና በሀገረ ስብከታቸው ምዕመናን ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ፣ አካዳሚያዊ ትምህር ያላቸውና ከቀረቡት ዕጩዎች መካከል የተሻለ ብቃት እና ጥሩ መንፈሳዊ አባት መሆን የሚችሉ በመሆናቸው ከፍተኛ ግምት የተሰጣቸው ናቸው ፡፡ ከዕድሜ አንፃር ሲጣይ ግን ከቀረቡት ጳጳሳት መካከል ሲኒየር አለመሆናቸው ለማወቅ ተችሏል ፡፡

ሌላው የሸዋ ተወላጅ ዕጩ ጳጳስ አቡነ ዮሴፍ ሲሆኑ በሀይማኖት ዕውቀታቸው የተከበሩና በአካዳሚያዊትምህርትም የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው ጥሩ መንፈሳዊ አባት ቢሆኑም በህብረተሰቡ ዘንድ ብዙም ታዋቂነት የላቸውም የሚሉ አስተያየቶች ይሰጣሉ ፡፡

ከወሎ ተወላጅ ጳጳሳት መካከል አቡነ ህዝቅኤል እና አቡነ ማቲያስ በዕጩነት እንዲቀርቡ በአስመራጭ ኮሚቴው የተያዙ ጳጳሳት ናቸው ፡፡ አቡነ ህዝቅኤል በአሁኑ ወቅት የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ፀሀፊ ሆነው በማገልገል ላይ የሚገኙ እና በአመለካከታቸው የጎጠኝነት አስተሳሰብ የሚያጠቃቸው እንዲሁም ከሲኖዶሱ አባላትም ይሁን በስራቸው ከሚገኙ ሰራተኞች ጋር ተግባብተው መስራት የማይችሉ መሆናቸው ለጳጳሡ ቅርበት ካሉ ወገኖች ያገኘነው መረጃ ያሳያል ፡፡

አቡነ ማቲያስ የቶሮንቶ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በዚህ የዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱ ጳጳሳት ዝርዝር ውስጥ የሚገኙ ጥሩ ሀይማኖታዊ ዕውቀት ያላቸው አባት ቢሆኑም አብዛኛውን ጊዜያቸው በውጭ ሀገራት ያሳለፉና በአሁኑ ሰአትም ከአገር ውጭ የሚገኙ በመሆናቸው በሳቸው ዙርያ ሰፊ ማብራሪያ ማግኘት አልቻልንም ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጀነራል አበባው ታደሰ በወሎ ግንባር በሰሜን ወሎ ግምባር
Share