የረመዳን ፆም

(በዘ-ሐበሻ ጋዜጣ ቁጥር 53 ላይ ታትሞ የወጣ፤ ሚኒሶታ)

በዓለማችን ላይ በርካታ ቁጥር ያላቸው እምነቶችና ኃይማኖቶች የመገኘታቸው ነገር እሙን ቢሆንም ካላቸው የረዥም ዓመታት ታሪክ፣ ወግ፣ ስርዓትና ባህል አኳያ ኢስላም (እስልምና)፣ ክርስትናና የአይሁድ እምነቶች በግንባር ቀደምነት ይጠቀሳሉ፡፡ እነዚህ እምነቶች፡-

በተለምዶ ሰማያዊ ሃይማኖቶች ወይም ዋና መሰረተ ምንጫቸው ከሰማይ መለኮታዊ ኃይል ነው የሚባሉ እምነቶች ናቸው፡፡ በእርግጥም ይህን ዘልማዳዊ አነጋገር ከእውነታው ጋር ሲነፃፀር በእውነትም ሰማያዊ እምነቶች (ሃይማኖቶች) እንደሆኑ በቀላሉ ለማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ሃይማኖቶቹ ለፈጣሪያቸው አልያም ለአምላካቸው ቅንነታቸውንና ታዛዥነታቸውን የሚገልፁበት የተለያዩ አምልኮታዊ ተግባራት ያላቸው ከመሆኑ ባሻገር እነዚህ አምልኮታዊ ተግባራት በምን መልኩ እንደሚፈፀሙ የሚያመላክት የየራሳቸው የሆነ ሰማያዊ መመሪያዎች አላቸው፡፡ ይህ ሰማያዊ መመሪያቸው በሚያመለክተው መሰረትም የአምልኮ ተግባራቸውን ይፈጽማሉ፡፡

ለዛሬ እንደ ርዕስ የያዝነው በአሁኑ ወቅት በመላው ዓለም የሚገኙ ሙስሊሞች እየፈፀሟቸው ከሚገኙት የአምልኮ ተግባራት መካከል አንዱ ስለ ሆነው የረመዳን ፆም አንዳንድ ነገሮችን ለማንሳት ነው፡፡

 

የፆም ትርጓሜ በኢስላም ሃይማኖት

በኢስላማዊው የስነ ቃላት ትርጓሜ መሰረት ፆም ማለት ጎህ ከቀደደበት ጊዜ አንስቶ ፀሐይ እስከምትጠልቅበት ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ከምግብ፣ ከመጠጥ፣ ከወሲባዊ ፍላጎት እና ከሌሎች መሰል ድርጊቶች በልበ ውሳኔ ተነሳሽነት ከአላህ ዘንድ ምንዳ አገኛለሁ በሚል እምነት መታቀብ (መከልከል) ማለት ነው፡፡

በእስልምና ሃይማኖት የተለያዩ የፆም አይነቶች ያሉ ሲሆን እነዚህ የተለያዩ የፆም አይነቶች የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሀ. ግዴታ የሆኑ ፆሞች

ለ. ግዴታ ያልሆኑና በፍላጎት የሚፆሙ ፆሞች

– ክልክል የሆኑ ጾሞች

ፆም የሚሰጣቸውም ጠቀሜታዎች እንደሚከተለው በአጭሩ ማስቀመጥ ይቻላል፡፡

ሀ. በመንፈሳዊ ጠቀሜታዎች

1. በልቦና ውስጥ የአላህ ፍራቻ እንዲሰርፅ ከማድረጉ ሌላ ህሊና ወደር የማይገኝለትን የውስጣዊ ደስታ እንዲቀዳጅ ያደርጋል፡፡

2. ትዕግስትን ሲያላብስ፣ ፍላጎትን ያጠነክራል፡፡

3. ማንኛውም ሰው በማናቸውም ክስተቶችና ሁኔታዎች ውስጥ ራሱን እንዲቆጣጠር በማድረጉ ሂደት ፆም ከፍተኛውን ሚና ይጫወታል፡፡

4. ፆም የሰው ልጅ ህይወት ስርዓት ባለው መልኩ እንዲጓዝ ያደርጋል፡፡

5. ፆም አዕምሮ ለትንሽ ጊዜያትም ቢሆን ስለ መልካም ነገሮች እንዲያስታውስ ብሎም የሰው ልጆች አላህን አስበው እንዲፈሩና ቅን ታዛዥ እንዲሆኑ መንፈሳዊ ስልጠናን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ይሰጣል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: HPV ክትባት አብዛኛውን የአባለዘር እከክ (Genital Warts) እና አብዛኛውን የማኅጸን ነቀርሳ (Cervical Cancer) ለመከላከል ያስችላል

6. ፆም አንደበትንና መላ አካላትን እንዲሁም ስጋዊ ስሜትን በማድከም ሰዎች ለሰይጣን (ዲያቢሎስ) ታዛዥ እንዳይሆኑ ስለሚከለክል ሰዎች መልካምና ቀጥታውን የኢስላም መንገድ እንዲከተሉና ከትንሣኤ በኋላ ባለው ዘልዓለማዊ ህይወት ተደሳች እንዲሆኑ ያደርጋል፡፡

ለ. ማህበራዊ ጠቀሜታዎች

1. ፆም ሙስሊሞች በአንድነት አንድ ወጥ ለሆነ ስርዓት ተገዢ እንዲሆኑ ያደርጋል፡፡

2. በሰዎች መካከል ፍትህና እኩልነት እንዲሰፍን ይረዳል፡፡

3. ማንኛውም ሙስሊም በመልካም ስነ ምግባር የታነፀና ለሌሎች ሰዎች አርአያነት ያለው ሰው እንዲሆን በማድረጉ በኩል ፆም ከፍተኛውን ሚና ይጫወታል፡፡

4. ፆም ማንኛውንም ባለሀብት አላህ የገለሰውንና የቸረውን ሀብቶች በይበልጥ የሚያስታውስበት ልዩ አጋጣሚ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር የተቸገሩ ወገኖቹን በማስታወስና ህመማቸውን በጋራ በመቅመስ ከጎናቸው እንዲቆም ይረዳል፡፡

ሐ. በጤና መስክ የሚሰጠው ጠቀሜታ

1. ፆም የስኳር ህመምን በመከላከሉ ረገድ የሚሰጠው ጠቀሜታ፡-

ሰውነታችን በተመጣጣኝ ሁኔታ ከሚፈልጋቸው ንጥረ ነገሮች መካከል ስኳር አንዱ ነው፡፡ ሰውነታችን የሚፈልገውን ይህን ስኳር በሚፈለገው መጠን ተዘጋጅቶ በተመጣጠነ ሁኔታ የሚቀርበው በጉበት አማካኝነት ነው፡፡

የስኳር ክምችት መጠኑ ከሚፈለገው በላይ ከሆነ በጤንነት ላይ ችግር ይፈጥራል፡፡ ስለዚህ የጤና ችግር እንዳይፈጠር በፆም ምክንያት የተከማቸው ስኳር በደም ውስጥ በመቀላቀል ወደተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ስለ ሚሰራጭ፣ ፆም የስኳር ክምችት በጤናነት ላይ ከሚያደርሰው የጤና መታወክ ይታደጋል፡፡

2. የልብን ጤንነት በመጠበቁ ረገድ፡-

የጤነኛ ሰው ልብ ምት ከ70-80 በደቂቃ ያመለክታሉ፡፡ ነገር ግን ዕድሜ እየጨመረና እየገፋ በሄደ ቁጥር የልብ ምት ድክመትን እንደሚያመለክትና በአብዛኛው ዕድሜአቸው ከሃምሳ በላይ የሆኑ ሰዎች በልብ ድካም በሽታ እንደሚጠቁ የህክምና መረጃዎች አረጋግጠዋል፡፡ ሆኖም ግን በፆም ጊዜ ወደተለያዩ የሰውነታችን ክፍሎች የሚሰራጨው የደም መጠን ከሚፈለገው መጠን በላይ ስለሚያንስ የልብን ስራ ያቃልላል፡፡ ስለዚህ የልብ ምት መጠን 60 በደቂቃ ይደርሳል፡፡ ይህ ደግሞ ልብ የተወሰነ የስራ ጫናንና መጨናነቅን አስወግዶ ለጥቂት ጊዜ እረፍት እንዲያገኝ ይረዳል፡፡

 

የረመዳን ፆም

የረመዳን ወር ፆም ከዚህ በላይ እንደተመለከትነው ግዴታዊ ፆም ከሚባሉት የፆም አይነቶች አንዱ ነው፡፡ የረመዳን ወር ፆም በሙስሊሞች ላይ ግዴታዊ የአምልኮት ተግባር ሆኖ የተደነገገው ነብዩ መሐመድ ከመካ ወደ መዲና በተሰደዱ በሁለተኛው ዓመት ነው፡፡ የረመዳን ወር ፆም ግዴታ የተደረገው በሚከተሉት የቁርአን አንቀጽ ሲሆን ነብዩ በህይወት ዘመናቸው ዘጠኝ የረመዳን ፆሞችን ብቻ እንደ ፆሙ ታሪካቸው ያስረዳል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በየቀኑ ገላን መታጠብ የሚያስገኘው የጤና ጥቅም

‹‹እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ፆም ለነዚህ ከናንተ በፊት በነበሩት (ህዝቦች) ላይ እንደተፃፈ በናንተም ላይ ተፃፈ ልትጠነቀቁ ይከጀላልና›› (አአል በቀራህ፡ 183)

‹‹(እንድትፆሙ የተፃፈባችሁ ያ በርሱ ውስጥ ለሰዎች መሪ ከቅን መንገድና (እውነትን ከውሸት) ከሚለዩም ገላጮች (አንቀፆች) ሲሆን ቁርአን የተወረደበት የረመዳን ወር ነው)›› (አል-በቀራህ 185)

የረመዳን ወር የጨረቃን የዘመን አቆጣጠር ቀመር ተከትሎ እንዲፆም የተደረገበት ዋና ምክንያት የሚከተለው ነው፡፡

ጨረቃ በመሬት ዙሪያ ዙር ለመፈፀም የሚወስድባት ጊዜ 29 ቀናት ከ12 ሰዓት ከ44 ደቂቃ 03 ሰከንድ ሲሆን በዚህ የጨረቃ አቆጣጠር አንድ ዓመት ማለት 354 ቀኖች ከ8 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ36 ሰከንድ ነው፡፡ አላህ የሰው ልጅ ይህን ተመልክቶ በቀላሉ ሊጠቀምበት የሚችለውን የዘመን አቆጣጠር በኢስላም ውስጥ ላሉና የተወሰኑ ወራትን ጠብቀው ለሚፈፀሙ አምልኮታዊ ተግባራት የዘመን መለኪያ አድርጎ አስቀምጧል፡፡ ይህንንም ጠቀሜታ አላህ ለሰው ልጆች ሲያብራራ በቁርአን ላይ እንዲህ ብሏል፡፡

‹‹(ሙሐመድ ሆይ!) ስለ ለጋ ጨረቃዎች ይጠይቁሃል ሰዎች

(ለዚህችም ሆነ ለቀጣዩ ዓለም ክንውኖቻቸው) ጊዜያቶችን የሐጅንም ወቅት (የሚያውቁባቸው) ምልክቶች ናቸው በል›› (አል-በቀራ 189)

ጨረቃዊው የዘመን አቆጣጠር ቀመር እንደ ፀሐያዊው የዘመን አቆጣጠር ቀመር በዓመት ውስጥ ባሉ የተለያዩ ወቅቶች (seasons) የተከፋፈለ አይደለም፡፡ በዚህም የተነሳ ለምሳሌ ያህል ለሰላሳ ዓመታት የረመዳንን ወር ፆም የፆመ ግለሰብ በአንድ ዓመት ውስጥ ባሉት የተለያዩ ወቅቶች ማለትም በበጋ፣ በክረምት፣ በፀደይና በበልግ ውስጥ የአየር ሁኔታዎቹ የሚፈጥሩበትን ተፅዕኖዎች ተቋቁሞ ግዴታ የሆነበትን ይህን የአምልኮ ተግባርን እንዲፈፅም ያደርገዋል፡፡ ይህም የግለሰቡ ሰውነት የአየር ለውጥ የሚያስከትለውን የጤና ችግር እንዲቋቋምና እንዲላመድ ያደርገዋል፡፡ ከዚህም ሌላ ማንኛውም ሙስሊም አመቺና አስቸጋሪ በሆኑ ወቅቶች ሁሉ ለጌታው ቅን ታዛዥ እንዲሆን በማድረግ ሂደት የጨረቃ የዘመን አቆጣጠር ቀመር ጉልህ አስተዋፅኦ አለው፡፡ ፆም በፀሐያዊው የዘመን አቆጣጠር ቀመር የሚፈፀም ቢሆን ኖሮ ማንኛውም ሙስሊም ምን ጊዜም በተወሰነ የአየር ሁኔታ ውስጥ የተጣለበትን አምልኮታዊ ተግባር እንዲፈፅም በተገደደ ነበር፡፡ ይህ ደግሞ በእርሱ ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ችግር በቀላሉ ለመገመት አያስቸግርም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: ስለ ወንዶችም ሆነ ሴቶች ስንፈተ ወሲብ ከባለሙያ ጋር የተደረገ ቃለምልልስ

በኢስላም ኃይማኖት ሙስሊም ሆነ ወይም መፆሙ ግዴታ ያልሆነባቸው ሰዎችም አሉ፡፡ እነዚህም ሰዎች እንዳይፆሙ የተደረገበት ምክንያት ካሉባቸው ችግሮች አንፃር እንጂ በሌላ አይደለም፡፡ እነርሱም፡-

1. በሽኞች (ህሙማን)

2. የአዕምሮ ህመምተኞች

3. ለረዥም ጉዞ የሚያደርግ መንገደኛ

4. በወር አበባ ደም ላይ ያለች ሴት

5. በወሊድ ደም ላይ ያለች ሴት

6. ለአቅመ አዳም ወይም ለአቅመ ሄዋን ያልደረሱ ህፃናት፡፡

በኢስላም ሴቶች በወር አበባ ወይም በወሊድ ደም ላይ ሳሉ እንዳይፆሙ ያደረገበት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉ፡፡ እነርሱም፡-

1. አንዲት ሴት በወር አበባ ወይም በወሊድ ደም ውስጥ ካለች ከሰውነቷ የሚፈሰው ደም አብዛኛውን ጊዜ ራሷን የመቋቋም ችሎታዋን እንድታጣ ስለሚያደርጋትና የመቋቋም ችሎታዋን ለመመለስ ተጨማሪ ምግቦችንና መጠጦችን መውሰድ ይኖርባታል፡፡ ያለዚያ ህይወቷ ለአደጋ እንደሚጋለጥ ጥርጥር የለውም፡፡ ስለዚህ ህይወቷን ከከፋ አደጋ ለመታደግ ኢስላም በዚህ ጊዜ ሴቶች እንዲፆሙ አያስገድዳቸውም፡፡ እንደውም መፆማቸውን ውግዝ (ፍፁማዊ ክልክል) ‹‹ሐራም›› አድርጎባቸዋል፡፡

2. አንዲት ሴት በወር አበባ ወይም በወሊድ ደም ላይ ካለች ባህሪዋ እንደሚለዋወጥ የስነ ልቦና እና በመስኩ ላይ ጥናት የሚያደርጉ ባለሙያዎች በጥናቶቻቸው አረጋግጠዋል፡፡ ስለዚህ ሴቶች በዚህ አይነት ሁኔታ ላይ እያሉ የባህሪ መለዋወጥ የሚያጋጥማቸው ከሆነ በቅንነት ለፈጣሪያቸው አላህ ቅን ታዛዥ ግዴታ የሆነባቸውን የረመዳን ፆምና ሌሎች የአምልኮ ተግባራትን ስርዓታቸውን ጠብቀው መፈፀም አይችሉም፡፡ ስለዚህ በሙሉ አንደበት፣ በሰከነ አዕምሮና መንፈስ የአምልኮ ተግባራትን ይፈፅሙ ዘንድ የኢስላም ሃይማኖት እንዲጾሙ አላስገደዳቸውም፡፡

እንግዲህ ከዚህ በላይ እንደተመለከትነው የኢስላማዊ ፆም ትርጓሜ፣ ስርዓትና ጠቀሜታዎች ይህን ይመስላሉ፡፡ በዚህ ፅሑፍ ላይ ያልተነሱትንና መነሳት የነበረባቸውን ነጥቦች አጋጣሚውን ጠብቀን በሌላ ጊዜ ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች እንኳን ለኢድ አልፈጥር ረመዳን በዓለም በሰላም አደረሳችሁ እላለሁ፡፡

ቸር እንሰንብት፡፡

 

1 Comment

Comments are closed.

Share