Health: ገንዘብህ ያገልግልህ እንጂ አታገልግለው

ከሊሊ ሞገስ

ድሃ ሀብታም፣ ነጭ ጥቁር፣ አጭር ረጅም፣ ሴት ወንድ፣ ህጻን አዋቂ ሁሉም በዚህች ምድር የህይወት ምህዋር ውስጥ የሚመርመሰመሱ ተዋንያን ሲሆኑ ህይወት ደግሞ በራሷ መድረክ ናት፡፡ እኒህ ሁሉ ፍጡራን በዚህች የህይወት መድረክ ላይ የተለያየ ህይወትን ይመራሉ፡፡ አንዳንዶች ህይወት በራሷ እየገፋቻቸው ለመውደቅ ሲፍገመገሙ ሌሎች ደግሞ ግፊያውን ተቋቁመውና ከግፊያው ተምረው ስኬታማ ይሆናሉ፡፡ አንድ ነገር እርግጠኛ ሁን፡፡ ዩኒቨርሲቲ ገብተህ ዲግሪና ፒኤችዲ መያዝህ በገንዘብ በኩል ያለህ ጡንቻ የበረታ እንዲሆን አያስችልህም፡፡ ምክንያቱም የገንዘብ ማግኛ ምስጢሩን ት/ቤት ውስጥ አልተማርከውም፡፡ ብዙ ቱጃሮችን እስኪ ተመልከት! ብዙዎች ሰርተፍኬት እንኳ የላቸውም፡፡ ይኸውልህ ምስጢሩ ያለው ከሀብታሙና ድሃው አባትህ ላይ ነው፡፡ ድሃው አባትህ የተማሩ ሲሆን አሁን ድረስ ግን ለገንዘብ ሲል ይለፋል ይደክማል፡፡ ሀብታም አባትህ ግን ባይማርም ስለገንዘብ ያለው እውቀት ላቅ ያለ ነው፡፡ ሮበርት ኪዬሳኪ ዛሬም የሀብታሙን አባቱን ባህርይ ይተርከዋል፡፡ እኔ እንዲህ አስማምቼ አቀናብሬዋለሁ፡፡

‹‹እናንተ ሁለቱ ህፃናት ስለገንዘብ ማግኛ ዘዴ እንዳስተምራችሁ ስትጠይቁኝ የመጀመሪያዎች ናችሁ፡፡ ከ150 ሠራተኞች በላይ ቢኖሩኝም አንዳቸውም ግን ስለገንዘብ ስላለኝ እውቀት ጠይቀውኝ አያውቁም፡፡ በመሆኑም ብዙዎች ወርቃማ ጊዜያቸውን ገንዘብ ለማግኘት ሲባክኑ ያሳልፉታል፡፡ የሚሰሩትን ነገር በምንም ተአምር አይረዱትም፡፡ በመሆኑም ማይክ አንተ ከእኔ ገንዘብ እንዴት እንደሚገኝ ልትማር እንደምትፈልግ ሲነግረኝ አንድ ከእውነተኛው ህይወት ጋር የተያያዘ ኮርስ ዲዛይን ለማድረግ ወሰንኩ፡፡ ፊቴ ሰማያዊ እስኪሆን ማውራት እችላለሁ፡፡ ነገር ግን የምትሰሙት ነገር አይኖርም ነበር፡፡ በመሆኑም ህይወት በራሷ ጊዜ እንድትገፋችሁ አደረኩ ያኔ ትሰሙኛላችሁ፡፡ ለዚያ ነው 10 ሣንቲም ብቻ የከፈልኳችሁ›› ‹‹ታዲያ ትከፍለን ከነበረው አስር ሣንቲም የተማርኩት ነገር ምንድነው? በቃ በርካሽ እያሰራህ የሠራተኞችህን ጉልበት መበዝበዝ ነው?›› ስል ጠየኩ፡፡ ሀብታሙ አባቴ ወንበሩን ወደኋላ ተደግፎ ከልቡ ከሳቀ በኋላ ንግግሩን ቀጠለ፡፡ ‹‹አመለካከትህን ብትቀይር የተሻለ ነው፡፡ እኔን መውቀስህንና የችግሩ ምክንያት መሆኔን ማሰብህን አቁም፡፡ የችግሩ ምንጭ እኔ እንደሆንኩ ካመንክ እኔን ልትቀይረኝ ይገባል፡፡ ነገር ግን ችግሩ ያልተ እንደሆነ ከተገነዘብክ ራስክን ትለውጣለህ፡፡ አንድ ነገር ተማርና ራስክን ሀብታም አድርግ፡፡ ብዙ ሰዎች ሌሎች ሰዎችን ራሳቸውን እንዲለውጡ ይፈልጋሉ፡፡ አንድ ነገር ልንገርህ፤ ከሌሎች ሰዎች ይልቅ አንተን ራስክን መለወጥ ይቀልሃል›› አለ ሀብታሙ አባቴ፡፡ ‹‹አልገባኝም›› ስል ጠየኩ፡፡ ‹‹ለአንተ ችግር እኔን አትውቀሰኝ›› ሲል መለሰ፡፡ ‹‹ነገር ግን 10 ሣንቲም ብቻ ከፍለኸኛል ስጠይቀው መለሰና ‹‹ታዲያ ምን ተማርክ?›› ሲል ሀብታሙ አባቴ እየሳቀ ጠየቀኝ፡፡

‹‹በቃ በርካሽ ታሰራለህ›› ሲል መለስኩለት፡፡ ሀብታ አባቴ ቀጠለና ‹‹አየህ አሁንም ችግሩ እኔ እንደሆንኩ ታስባለህ፡፡ ነገር ግን ችግሩ ያንተ ነው፡፡ በቃ ይህን አመለካከትክን ግፋበት፤ ነገር ግን የምትማረው ነገር አይኖርም፡፡ እኔ ችግሩ እንደሆንክ አሁንም አመለካከትክን ቀጥል! ግን ምን ምርጫ አለህ?›› ሲል ጠየቀኝ፡፡ ‹‹ማለት ጥሩ ክፍያ ካልከፈልከኝ ወይም ክብር ካልሰጠኸኝ ስራዬን እለቃለሁ›› አልኩት፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ደም ብዛት የያዘህ ጨው አብዝተህ በመመገብህ ነው ተባልኩ፤ እውነት ይሆን?

‹‹ጥሩ ድምዳሜ ነው፡፡ ይህንማ ብዙዎች ያደርጉታል፡፡ ስራቸውን ለቀው በመሄድ የተሻለ አጋጣሚ፣ ከፍተኛ ክፍያ በማግኘት ችግራቸውን የሚያቃልሉ ይመስላቸዋል፡፡ ነገር ግን አይሰራም፡፡ ‹‹ታዲያ ችግሩን ምን ይፈታዋል?›› ይችን በሰዓት አስር ሣንቲም እየወሰድኩ?›› ስል ጠየኩት፡፡ ፈገግ እያለ ‹‹ያን ሌሎችም ያደርጉታል፡፡ ያን ክፍያ እየተቀበሉ ቤተሰባቸውን ግን በገንዘብ እጥረት እንደሚሰቃዩ ያውቃሉ፡፡ ነገር ግን የሚያደርጉት ያ ብቻ ነበር፡፡ በቃ የገንዘብ መጨመርንና ያ ብር ችግሩን ይፈታዋል ብለው ያስባሉ፡፡ አንዳንዶች ይህን ሲቀበሉ ሌሎች ስራ በመቀየር ጠንክረው ይሰራሉ ግን አሁንም አነስተኛ ብር ይቀበላሉ፡፡

መሬት መሬቱን እያየሁ ሀብታሙ አባቴ ያለኝን ነገር መረዳት ጀመርኩ፡፡ ያለው ነገር የህይወት ፈተናዋ እንደሆነ እየተረዳሁት መጣሁ፡፡

ብሩህ በሆነው ቅዳሜ ጠዋት ከድሃው አባቴ ሙሉ በሙሉ ፍፁም የተለየ አመለካከት (Point of view) እየተማርኩ ነበር፡፡ ገና በ9 ዓመቴ ሁለቱም አባቴ እኔ እንድማር እንደሚፈለጉ እያወኩ አደኩ፡፡ ሁለቱም አባቴ እንድማር ያበረታቱኛል፡፡ ነገር ግን ተመሳሳይ የሆነ ነገር አያስተምሩኝም፡፡

ያ ድሃው አባቴ በቃ ልክ እርሱ የሰራውን እሰራ ሁሉ ዘንድ ይመክረኛል፡፡ ‹‹ልጄ ጠንክረህ እንድታጠና እፈልጋለሁ፤ ጥሩ ውጤት (grade) ማግኘት ይኖርብሃል በመሆኑም አስተማማኝ (Secure) የሆነ ስራ በአንድ ትልቅ ካምፓኒ ውስጥ ታገኛለህ፡፡ የተለያየ ጥቅማጥቅምም እንደምታገኝ እርግጠኛ ሁን ይለኛል፡፡ ሀብታሙ አባቴ ግን ከዚህ በተለየ ገንዘብ እንዴት እንደማገኝና እንዴትስ ለእኔ ሠራተኛ እንዲሆን ማድረግ እንደምችል እንድማር ይፈልጋል፡፡ ይህን ትምህርት ያገኘሁት ክላስ ውስጥ በተሰጠ ትምህርት አልነበረም፡፡

ሀብታሙ ሀባቴ አሁንም ትምህርቱን ቀጥሏል፡፡ ‹‹በሰዓት አስር ሣንቲም በመስራታችሁና በመናደዳችሁ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡ ባትናደዱና እንዲሁ ብትቀበሉት ኖሮ ላስተምራችሁ እንደማልችል በነገርኳችሁ ነበር፡፡ ልብ በሉ እውነተኛ ትምህርት ሃይልን ይፈልጋል፣ መከራን መቀበልና ከፍተኛ የሆነ ፍላጎትን ይጠይቃል፡፡ ንዴት የዚያ ክፍል ዋና ቀመር (formula) ነው፤ ስቃይ ፍቅርና ንዴት የተደባለቀበት ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ወደ ገንዘብ ሲመጣ ብዙ ሰዎች በጥንቃቄና በአስተማማኝ ሁኔታ ጨዋታውን ለመጫወት ይፈልጋሉ፡፡ ያለህ ጥንካሬ ደግሞ እኒህን ነገር ሊመራቸው አይችልም ፍርሃት እንጂ፡፡

ለዚያ ነው በዝቅተኛ ክፍያ ስራ ሊሰሩ የሚስማሙት? ስል ጠየቀኩ፡፡ አዎ አለ ሀብታ አባቴ፡፡ ብዙ ሰዎች የሰዎችን ጉልበት እንደበዘበዙ ይናገራሉ፡፡ ምክንያቱን ሲጠየቁ ደግሞ አነስተኛ ክፍያ እየፈከሏቸው እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን እንደ እኔ ከሆነ ጉልበታቸውን የሚበዘብዙት ራሳቸው ሠራተኞች ናቸው፡፡ ያ ደግሞ የእኔ ሳይሆን የእነርሱ ፍራቻ ነው፡፡

‹‹ነገር ግን ጥሩ ክፍያ ልትከፍላቸው እንደሚገባህ አይሰማህም?›› ስል ጠየኩት ‹‹በፍፁም አይሰማኝም፡፡ ይኸውልህ በተጨማሪም ብዙ ገንዘብ ችግርን ሊፈታ አይችልም፡፡ እስኪ የአንተን አባት ተመልከተው፡፡ ብዛት ያለው ገንዘብ እያገኘ ያለውን ቢል እንኳ መክፈል አልቻለም፡፡ ብዙ ሰዎች ብዙ ብር የሚሰጡት ትልቅ እዳ ውስጥ እንዲገቡ ነው፡፡ ‹‹ለዚያ ነው አስር ሣንቲም በሰዓት መከፈሉ›› አልኩና ጠየኩት፡፡ ሀብታሙ አባቴም ‹‹ይህም የምትምህርቱ አንድ አካል ነው›› አለኝ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የነጭ ሽንኩርት መድኃኒትነት

‹‹ትክክል ነው!›› አልኩና በድጋሚ ሳኩኝ፡፡ ሀብታሙ አባቴ ግን ንግግሩን ቀጠለ፡- ‹‹አየህ አባትህ ት/ቤት በመግባት በጣም አስፈላጊ ትምህርት ወስዷል፡፡ በመሆኑም የከፍተኛ ደመወዝ ተከፋይ ነው፡፡ ይህም ክፍያ የሰራበት ነው፡፡ አሁን ድረስ ግን የገንዘብ ችግር አለበት፣ ምክንያቱም ት/ቤት ውስጥ እንደነበር ስለገንዘብ ምንም የተማረው ነገር የለም፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ ለገንዘብ መስራት እንደሚገባ ያምናል፡፡ እኔም ቀጥዬ ‹‹አንተስ በዚህ ነገር አታምንም?›› ጠየኩት፡፡ ‹‹በፍፁም›› መለሰ ሀብታሙ አባቴ፡፡ ‹‹ለገንዘብ እንዴት መስራት እንዳለብህ ለመማር የምትፈልግ ከሆነ በቃ ሂድና ት/ቤት ቆይ›› ‹‹ታዲያ ብዙዎች ያን ለመማር አይፈልጉም ነበር?›› ስል አሁንም ጠየኩት፡፡ ‹‹አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ለገንዘብ እንዴት መስራት እንዳለብህ ለመማር በጣም ቀላል ነው፡፡ በተለይ ስለ ገንዘብ መወራት ሲጀመር ፍራቻ የአንተ መለያ ከሆነ፡፡ ‹‹አልገባኝም›› ስል ግራ ተጋብቼ ጠየኩት፡፡

‹‹ስለሱ ለአሁን ብዙ አትጨነቅ፡፡ አሁን ግን ብዙ ሰዎችን በስራቸው ላይ ተጣብቀው እንዲሰሩ የሚያደርጋቸው ፍራቻ መሆኑን እወቅ፡፡ የቤታቸውን ቢል ያለመክፈል ፍራቻ አለባቸው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ አይኖረኝ ይሆናል ብለው ይፈራሉ፡፡ ይህ ደግሞ ለአንድ ፕሮፌሽን ወይም ንግድ መማር ለገንዘብ በመስራት የሚገኝ ክፍያ ነው፡፡ ብዙዎች በራሳቸው ጊዜ ለገንዘብ ባርያ ይሆኑና ሲናደዱ በአለቃቸው ላይ መጮህ ይጀምራሉ፡፡

‹‹ገንዘብ እንዴት ማግኘት እንደሚቻል አንተ ጋር የሚሰጠው ትምህርት የተለየ ነው!›› ስል አስተያቴን ሰነዘርኩ፡፡ ‹‹በትክክል›› ሲል ሀብታሙ አባቴ መለሰልኝ፡፡

ሁለታችንም በዚያ የሚያምር የቅዳሜ የጠዋት ፀሐይ ላይ ፀጥ ብለን ተቀመጥን፡፡ ትንንሽ ጓደኞቼ የቤዝኾል ሊግ ጨዋታቸውን ጀምረዋል፡፡ እኔ ግን በተለያየ ምክንያት በሰዓት አስር ሣንቲም እየተከፈለኝ ለመስራት ወስኛለሁ፡፡ ለዚህም ምስጋናዬ ትልቅ ነው፡፡ አሁን ጓደኞቼ ት/ቤት የማያገኙትን ትምህርት ልማር እንደሆነ ይሰማኛል፡፡

‹‹ለመማር ዝግጁ?›› ሲል ሀብታሙ አባቴ ጠየቀ፡፡ እያስተማርኳችሁ ነበር፡፡ በዘጠን ዓመታችሁ ለገንዘብ ብሎ መስራት የሚፈጥረውን ስሜት አጣጥማችሁ አይታችኋል፡፡ ይህን ዘጠን ዓመትህን በአምሳ ዓመት አባዛውና እዚያ ቦታ ላይ ያሉ ሰዎች የሚሰማቸውን ስሜት አስብ፡፡

‹‹አልተረዳውህም›› አልኩና መለስኩ፡፡ ‹‹ቅድም እኔን ለማግኘት ቁጭ ብለህ ስትጠብቅ ምን ተሰማህ?›› አንደኛው ዕድገትንና ሁለተኛው ደግሞ ከፍተኛ ክፍያ ለማግኘት ስትፈልግ? ‹‹በጣም ንዴት››… አልኩና መለስኩለት፡፡ ሀብታሙ አባቴ ቀጠል አደረገና ‹‹አንተም እንደ ብዙዎች ለገንዘብ ስትል መስራትን ብትመርጥ ኖሮ ህይወትህ ያን ነበር የሚመስለው፡፡

‹‹እሺ ወ/ሮ ማርቲን በሶስት ሰዓት ውስጥ 30 ሣንቲም እጅህ ላይ ስታስቀምጥልህ ምን ተሰማህ?›› ሲል እንደገና ጠየቀኝ፡፡ ‹‹በቂ እንዳልሆነ ተሰማኝ፤ ምንም ነገር አልነበረም፡፡ በጣም ግራ ተጋብቼ ነበር›› ስል መለስኩለት፡፡ ‹‹በቃ ብዙዎች ሰራተኞች የሚሰማቸው ስሜት እንዲህ ነው፡፡ በተለይ የታክስና የሌሎች ነገሮች ተቆረጦ ከተነሳባቸው በኋላ፡፡ አንተ ግን ግፋ ቢል 100% አግኝተሃል›› ሲል መለሰልኝ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: የባህል መድሃኒት (ዶ/ር ቁምላቸው አባተ)

‹‹ማለት ሁሉም ሠራተኞች ደመወዛቸውን ሙሉ በሙሉ አያገኙም ማለት ነው?›› ስል ጠየኩ፡፡

‹‹ማን ያውቃል?›› መንግሥትም ቢሆን በመጀመሪያ የራሱን ድርሻ ያነሳል፡፡ ‹‹እንዴት አድርጎ ይሰራዋል?›› ሲል ደግሜ ጠየኩት፡፡ ‹‹በታክስ ነዋ! ስታገኝ! ስታጠፋ፣ ስትቆጥብ፣ ስትሞትም ቢሆን ታክስ ይቆረጥብሃል›› ‹‹ህዝቡ መንግሥት ይህን ሲያደርግ ለምን ዝም ይላል?›› በማለት ጠየኩ፡፡ ‹‹በሀብታሞች ይህ ነገር አይሰራባቸውም›› አለ ፈገግ እያለ፡፡ የሚገርምህ እኔ ከአንተ አባት የተሻለ ብር አገኛለሁ፡፡ ነገር ግን ከእኔ የበለጠ ታክስ የሚከፍለው እርሱ ነው፡፡ ‹‹ያ እንዴት ሊሆን ይችላል›› ስል ለእኔ ለአንድ ለዘጠኝ ዓመት ልጅ ሊገባኝ የማይችል ጥያቄ ጠየኩ፡፡ ‹‹ለምንድን ነው መንግሥት ይህን ሲሰራባቸው ዝም የሚባለው?››

ሀብታሙ አባቴ በዝምታ ተውጧል፡፡ እንደመሰለኝ ዝም ብዬ አፌ ያመጣውን ከመቀባጠር ይልቅ ዝም ብዬ እንድሰማው የፈለገ ይመስለኛል፡፡ መጨረሻ ላይ ዝም ማለትን መረጥኩ፡፡ የሰማሁትን ነገር ሁሉ አልወደድኩትም፡፡

ድሃው አባቴ በተከታታይ በሚከፍለው ከፍተኛ ታክስ እንደሚያማርር አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን አንድም የሰራው ነገር የለም፡፡ ህይወት በዙሪያዋ እየገፋቸው ነው ማለት ነው?

ሀብታሙ አባቴ ወንበሩ ላይ እንደ ተቀመጠ ትክ አድርጎ ከተመለከተኝ በኋላ ‹‹ለመማር ዝግጁ ነህ?›› ሲል በድጋሚ ጠየቀኝ፡፡ አውንታዬን አንገቴን በመነቅነቅ ገለፅሁለት፡፡

‹‹ቅድም እንደተናገርኩት ብዙ አይነት ትምህርት አለ፡፡ ለአንተ የሚያገለግል ገንዘብ እንዴት ማግኘት እንደምትችል የምትማረው የሙሉ ህይወት ትምህርት ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ኮሌጅ ውስጥ ይገቡና 4 ዓመት የሚሆን ተምረው ይጨርሳሉ፡፡ እኔ ግን እንዴት ስለ ገንዘብ የምማረው ትምህርት ህይወቴን ሙሉ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ምክንያቱም ብዙ ለማወቅ በጣርኩ ቁጥር ብዙ የማወቅ ፍለጎቴ እየጨመረ ይመጣልና፡፡ ብዙዎች ግን ይህን ትምህርት አያጤኑትም፡፡ ስራ ይሄዳሉ፤ ክፍያ ይከፍላሉ ቼክ ቡካቸውን ባላንስ ያደርጋሉ አለቀ በቃ፡፡ ሁሉም ሆኖ ደግሞ እንዴት የገንዘብ ችግር እንዳለባቸው ይገርማሉ፡፡ በመሆኑም ብዙ ብር ችግራቸውን እንደሚፈታው ያምናሉ፡፡ ጥቂቶች ግን ችግሩ የተፈጠረው ስለ ፋይናንስ ባላቸው ትምህርት ምክንያት እንደሆነ ይገነዘባሉ፡፡

ውድ አንባቢያን የፅሑፍ አቀራረብ ለየት ያለ ቢሆንም በውስጡ ያሉትን ነጥቦች ግን ነቅሳችሁ ለማውጣት እንደማይሳናችሁ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ይህ ሁኔታ በእናንተ ህይወት ቢከሰት ምን ትወስኑ ይሆን? ዲግሪና ማስተርስ መያዝ ገንዘብ ለመፍጠር መሰረት ናቸው ትላላችሁ? ያለ ክፍያ መስራቱን እንዴት አያችሁት? ለገንዘብ መስራት ሊባልና ገንዘብ ለእኛ እንዲሰራ መማር ሲባል ምን ማለት ይሆን? ህይወት እየገፋቻችሁ ነው እየገፋችኋት? ሰው ለምን ድሃ ይሆናል? አዕምሮህን በአግባሁ ተጠቅሜበታለሁ ብለህ ታስባለህ? የዛሬው ፅሑፌ እነዚህን ጥያቄዎች መልሶ ያለፈ ነው፡፡ በዚህ ግን አያበቃም ደጋግማችሁ አንብቡት፡፡ እስከ ሳምንት ሰላም ሁኑልኝ፡፡

 

Share