ሊቨርፑል ስኳዱን ለማጠናከር አማራጮችን እየተመለከተ ነው

ሊቨርፑል በኬኒ ዳልግሊሽ እጅ ውስጥ ከገባ በኋላ ውጤታማ መሆን ችሏል፡፡ ለከርሞም ቡድኑን የበለጠ አጠናክሮ ሊጉም ሆነ በአውሮፓ ውድድር ላይ ተፎካካሪ ለመሆን ከአሁኑ እቅድ እየነደፈ ይገኛል፡፡ ቀጣዩ ዝግጅትም የአንፊልዱ ክለብ በቀጣይ ሊያስፈርማቸው በእቅድ ደረጃ የያዛቸውን ተጨዋቾች ያስቃኘናል፡፡
በፕሪሚየር ሊጉ የውድድር ዘመኑ ሊጠናቀቅ መቃረቡን ተከትሎ ከአሁኑ የዝውውር ጉዳዮች መነሳት ጀምረዋል፡፡ የተለያዩ የዓለማችን ከዋክብትም ከተለያዩ ታላላቅ ክለቦች ጋር ስማቸው ተያይዞ እየተነሳ ይገኛል፡፡ በእርግጥም አሰልጣኞችም ሆኑ ሌሎች ስታፎች ታላላቅ የሚባሉ ተጨዋቾችን በእጃቸው ለማስገባት ስራቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል፡፡ ነገር ግን በዚህ ወቅት ላይ ኦፊሴላዊ በሆነ መንገድ እውቅና የሚሰጣቸው እና ይፋ የሚሆኑ ዝውውሮች እጅግ ጥቂት ናቸው፡፡ ይህ ሁኔታ ግን ጭምጭምታዎች እንዳይሰሙ እንዲሁም እውነተኛም ይሁኑ መሰረት የለሽ የዝውውር ዜናዎች እንዳይወጡ ሊያግድ አይችልም፡፡ ቀደም ሲል እንደተለመደው ሊቨርፑልም ስሙ ከተለያዩ የዓለማችን ከዋክብት ጋር ከሚያያዙ ክለቦች አንዱ ነው፡፡ እንዲያውም ከአሁኑ ወደ አንፊልድ ይጓዛሉ ተብለው የተገመቱ በርካታ ተጨዋቾች ስም እየተነሳ ይገኛል፡፡ ከዚህ ጋር በተገናኘም ተጨዋቾቹ ክለቡን ለመቀላቀል ስላላቸው እድል እና ለክለቡ ስለሚኖራቸው ጠቀሜታ ብዙ እየተባለ ይገኛል፡፡ በእርግጥ በዚህ ወቅት ስለ ዝውውሮቹ ስኬት በእርግጠኝነት ማውራት ከባድ ነው፡፡ ቢሆንም ሊቨርፑል በየቦታው ሊያስፈርማቸው ይችላል የተባሉ ሁለት ሁለት ተጨዋቾች እንዲህ ቀርበዋል፡፡ (በዚህ ስሌት የመስመር አማካይ እና የመስመር ተከላካይ እንደ አንድ ቦታ ተወስዷል)
ጋሪ ካሂል
(የመሀል ተከላካይ)
ሊቨርፑል ከቦልተኑ ተከላካይ ጋር ተያያዞ መነሳት የጀመረው አሁን አይደለም፡፡ የ25 ዓመቱ ጋሪ ካሂል ከፍተኛ የፕሪሚየር ሊግ ልምድ ያለው ሲሆን በጥሩ ዋጋም ሊገኝ ይችላል ተብሎ ይታመናል፡፡ ቦልተንም የአውሮፓ እግርኳስ ተሳትፎን ሊሰጠው ስለማይችል እርሱን ለማቆየት ይቸገራል፡፡ ጠንካራው የመሀል ተከላካይ የአየር ላይ ኳስ ብቃቱ ድንቅ ነው፡፡ ኳስ በእግሩ ስር ስትገባም ምቾት ይሰማዋል፡፡ እንዲያውም በርካቶች በዚህ ረገድ ከሳሚ ኒፒያ እና ዳንኤል አገር ጋር ያነፃፅሩታል፡፡ ምንም እንኳን ካሂል የአገርን ያህል ኳስን የመቆጣጠር የተመጠነ ኳስ የመስጠት እና አክርሮ የመምታት ብቃት ባይኖረውም የተረጋጋ መሆኑና በጉዳት የመጠቃት አጋጣሚ ስለሌለው ለሊቨርፑል ጠቃሚ እንደሚሆን አያጠራጥርም፡፡ የመዘዋወር ዕድሉ 8/10
ሮጀር ጆንሰን (የመሀል ተከላካይ)
ከ2009 በፊት ከካርዲፍ ደጋፊዎች ውጪ የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው፡፡ ሆኖም በ2008 ካርዲፍ ለኤፍኤካፕ ፍፃሜ ከደረሰ እና እርሱም ለሁለት ተከታታይ ዓመታት የክለቡ ኮከብ ተጨዋች ተብሎ ከተመረጠ በኋላ በ5 ሚሊዮን ፓውንድ በርሚንግሃምን ተቀላቅሏል፡፡ አምናም ከስኮት ዳን ጋር ጠንካራ ጥምረት በመፍጠር በርሚንግሀም በ12 ጨዋታዎች ባለመሸነፍ የራሱን ሪከርድ እንዲያሻሽል ቁልፍ ሚና ተወጥቷል፡፡ የ28 ዓመቱ ተከላካይ እጅግ ጠንካራ እና ሀይል ቀላቅሎ የሚጫወት በመሆኑ በተጨማሪም ርዝመቱ (1.92 ሜትር) የአየር ላይ ኳስ ብቃቱ ድንቅ እንዲሆን አድርጓል፡፡ በዚያ ላይ ሀገር በቀል ተጨዋች መሆኑ አዲስ በወጣው ደንብ ለሊቨርፑል ጠቃሚ ይሆናል፡፡ በእርግጥ ተጨዋቹ በሊጉ ያለው ልምድ አነስተኛ ነው፡፡ ዘንድሮም ነጥሮ መውጣት አልቻለም፡፡ የሊቨርፑሉ የእግርኳስ ስትራቴጂ እና ልማት ኃላፊ ዳሚዬን ኮሞሊ ግን በጥብቅ እየተከታተሉት ይገኛሉ፡፡
የመዘዋወር ዕድሉ 8/10
ሆዜ ኤንሪኬ (የመስመር ተከላካይ)
የዝውውር መስኮቱ ከመከፈቱ በፊት ስማቸው ከሊቨርፑል ጋር እየተነሳ ካሉ ተጫዋቾች ቅድሚያውን ይይዛል፡፡ ኒውካስል በ2007 ኤንሪኬን በ6 ሚሊዮን ፓውንድ ለማስፈረም በዝውውሩ ማንቸስተር ሲቲ እና ሊቨርፑልን መርታት ነበረበት፡፡ ምንም እንኳን ስፔናዊው በሳም አላርዳይስ ጊዜ ክለቡን ለመልመድ ቢቸገርም በጊዜ ሂደት ምርጥ አቋሙ ላይ ተገኝቷል፡፡ አምና የክለቡ የዓመቱ ኮከብ ተጨዋች ተብሎ የተመረጠ ሲሆን በፕሪሚየር ሊጉ የዓመቱ ምርጥ 11 ተጨዋቾች ዝርዝር ውስጥም ተካትቷል፡፡ ኤንሪኬ ገና 25ኛ ዓመቱ ላይ እንደመገኘቱ ከፊቱ በርካታ ብሩህ ዓመታት ይጠብቁታል፡፡ በዚያ ላይ በፕሪሚየር ሊጉ ያለው ልምድ እና የግል ክህሎቱ ኮሞሊ እና ኬኒ ዳንግሊሽ የሚፈልጉት አይነት ነው፡፡ ምክንያቱም ሁለቱ ሰዎች የሚያስፈርሟቸው ተጨዋቾች የቡድኑን የኳስ ቁጥጥር የሚያጠናክሩ እንዲሆኑ ይፈልጋሉ፡፡ ኤንሪኬ ደግሞ በአጭርም ሆነ በረጅም የተመጠኑ ኳሶች የተካነ ነው፡፡ የመዘዋወር ዕድል 8/10
ጋኤል ከሊሺ፤ (የመስመር ተከላካይ)
በርካቶች ባለፈው ጃንዋሪ ሊቨርፑል ጠንካራ የመስመር ተከላካይ ማስፈረም እንዳለበት ሲናገሩ ነበር፡፡ ሆኖም አስደናቂው ማርቲን ኬሊ እና ጠንካራው ጆን ፍላናጋን ከሚጠበቀው በላይ አቋም ካሳዩ በኋላ ለቦታው ሌላ ተጫዋቾች የሚያስፈልግ አይመስልም፡፡ በግራ መስመር ግን አሽሊኮል አርሰናልን ከለቀቀ በኋላ ባለፉት አምስት ዓመታት ክለቡን በቋሚ ተሰላፊነት ያገለገለው ጋኤል ክሊሺ ከሊቨርፑል ጋር ስሙ እየተነሳ ይገኛል፡፡ ፈረንሳዊው ተጨዋች ገና 25 ዓመቱ ቢሆንም ለመድፈኞቹ 200 የፕሪሚየር ሊግ እንዲሁም 50 የአውሮፓ መድረክ ተሳትፎዎችን አድርጓል፡፡ ፍላጎቱ እና ጊዜ አጠባበቁ መልካም የሚባል ሲሆን ከኳስ ጋር በተገናኘ ያለው ችሎታም ጥሩ ነው፡፡ ታዲያ አርሰናል ለምን ሊሸጠው ይፈልጋል? ተጨዋቹ ከክለቡ ጋር ያለው ኮንትራት ሊጠናቀቅ 12 ወራት ብቻ ቀርቶታል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘም አዲስ ኮንትራት የማይፈርም ከሆነ ክለቡ ከአንድ ዓመት በኋላ በነፃ ዝውውር ሊያጣው ካለመፈለግ ለሽያጭ ያቀርበዋል ተብሎ ይገመታል፡፡
የመዘዋወር ዕድል 3/10
ቻርሊ አደም ((አማካይ)
የ25 ዓመቱ ቻርሊ አደም የግላስጎው ሬንጀርስ አካዳሚ ውጤት ነው፡፡ ስለዚህም ሊቨርፑልን ቢቀላቀል እንኳን ክለቡ ለአውሮፓ በሚያስመዘግባቸው ሀገር በቀል ተጨዋቾች ውስጥ መካተት አይችልም፡፡ ተጫዋቹ በ2009 ብላክፑልን ከመቀላቀሉ በፊት ለሬንጀርስ ዋናው ቡድን በሊጉ 60 እንዲሁም በአውሮፓ ውድድሮች 20 ጨዋታዎችን አድርጓል፡፡ ከብላክፑል ጋር ባሳለፈው የመጀመሪያ የውድድር ዘመንም በአስደናቂ አቋም ክለቡን ለፕሪሚር ሊግ አብቅቶታል፡፡ ይህንን አቋሙን ቀጥሎበትም ዘንድሮ የበርካታ ታላላቅ ክለቦች አይን ማረፊያ ሆኗል፡፡ ብላክፑል አዳምን ካገኘ በኋላ በእርሱ ዙሪያ ቡድኑን በመገንባት በሚያቀብላቸው የመጨረሻ ኳሶች፣ ወደ ፍፁም ቅጣት ምት ክልል የሚያደርገው ሩጫ፣ በእይታው እና ጎል ማስቆጠር ብቃቱ (በየሶስት ጨዋታዎቹ ለብላክፑል አንድ ጎል አግብቷል) የሚደነቅ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ሊቨርፑል ውስጥ በእርሱ ቦታ የሚጫወቱት ተጨዋቾች (ራኡል ሜይረሌስ፣ ማክሊ ሮድሪጌዝ እና ስቲቨን ዤራርድ) በመኖራቸው ለክለቡ ቢፈርም እንኳን ከስኳድ ተጨዋችነት የሚያልፍ አይመስልም፡፡
የመዘዋወር ዕድል 7/10
ያም ምቪላ (ተከላካይ አማካይ)
ለፈረንሳዩ ሬን የሚጫወተው ምቪላ የበርካታ ክለቦችን ቀልብ መሳብ የቻለው ዘንድሮ ባሳየው አስደናቂ አቋም ምክንያት ነው፡፡ በእርግጥም ገና በ20 ዓመቱ ለሀገሩ ዋናው ቡድን ስምንት ጨዋታዎች ላይ መሰለፉ የብቃቱን ደረጃ የሚያሳይ ነው፡፡ በዚያ ላይ በአጨዋወቱ ለሊቨርፑል የተሰራ እንደሆነ ይነገርለታል፡፡ ሊቨርፑል ከዤራርድ ሁዬ ዘመን ጀምሮ ዳይትማር ሀማን፣ ስቴቨን ዤራርድ፣ ሞሞ ሲሶኮ እና ሀቪዬር ማሼራኖን የመሳሰሉ የተከላካይ አማካዮች ተጠቅሟል፡፡ በእርግጥ ሉካስ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በዚሁ ቦታ ጥሩ አቋም ማሳየት ችሏል፡፡ ወጣቱ ጄይ ስፕሪንግም ቢሆን በቅርብ ጊዜያት ተስፋ እንዳለው ተስተውሏል፡፡ ነገር ግን ሁለቱም ተጨዋቾች ለቦታው የሚመጥን እና ተጽዕኖ መፍጠር የሚያስችል አካላዊ ጥንካሬም ሆነ ቁመና የላቸውም (ማሽራኖም ግዙፍ አይደለም፡፡ ሆኖም ከእነርሱ በተሻለ ፈጣን እና ሀይልን ቀላቅሎ የሚጫወት ነበር) ምቪላ ግን ረዥም (1.90 ሜትር) ጠንካራ እና ፈጣን ነው፡፡ ሊቨርፑል ሚሼራኖን ከሸጠ በኋላ ያጣውን የአማካይ ክፍል ተፅዕኖም በደንብ መሸፈን ይችላል፡፡
የመዘዋወር ዕድል 9/10
ጆይ ባርተን (የተከላካይ አማካይ)
ባርተን ባህሪዩን ማረቅ ከቻለ ለየትኛውም ቡድን መጥቀም የሚችል ነው፡፡ ሆኖም በልጅነቱ የኤቨርተን ደጋፊ ስለነበር ወደ ሊቨርፑል መዛወር ላይፈልግ ይችላል፡፡ የአንፊልዱ ክለብ አሁን ብቻ ሳይሆን በታዳጊነቱም ሊያስፈርመው ጥረት አድርጓል፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ተጫዋቹ በተደጋጋሚ የሚፈፅመው ጥፋት እና በእግርኳስ ህይወቱ ለእስር እስከ መዳረግ በመብቃቱ ፍላጎቱን ደብቆ ቆይቷል፡፡ ከዚያ በተጨማሪም በ2009 ዣቪ አሎንሶ ላይ በፈፀመው አደገኛ ታክል በቀይ ካርድ መሰናበቱ እና ወንድሙም በ2005 ሊቨርፑል ውስጥ ‹‹ከዘረኝነት ጋር በተገናኘ ግድያ ፈፅሟል›› በሚል የዕድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት እየማቀቀ መሆኑ በመርሲሳይድ መልካም አቀባበል እንዳይደረግለት ይከለክለዋል፡፡ በእርግጥ ተጨዋቹ ክለቡን ቢቀላቀል ቡድኑ ላይ ጥንካሬን ይጨምራል፡፡ በዚያው መጠን ግን የቡድኑን ሰላም ሊያደፈርስ ይችላል፡፡
የመዘዋወር ዕድል 3/10
አሽሊ ያንግ (የመስመር አማካይ)
በሊቨርፑል ራዳር ውስጥ ከገባ ሰነባብቷል፡፡ በተለይ ለእንግሊዛዊያን ተጨዋቾች ትኩረት እንደመስጠቱ እና ሊቨርፑልም የመስመር አማካዮችን አጥብቆ እንደመፈለጉ ስሙ ከያንግ እና ስቴዋርት ዳውኒንግ ጋር መያያዙ የሚገርም አይሆንም፡፡ ከሁለቱ ግን ያንግ በርቀት የተሻለ ተጨዋች ነው፡፡ ያንግ ገና በ25 ዓመቱ በፕሪሚየር ሊጉ ለዋትፎርድ እና አስቶን ቪላ ከ150 ጨዋታዎች በላይ ማድረጉ በዚህ ዝርዝር ውስጥ ከተጠቀሱት ከፍተኛ ልምድ ያላቸው ተጨዋቾች አንዱ ያደርገዋል፡፡ የመስመር አማካዩ ለመጀመሪያ ጊዜ በሊጉ በተሳተፈበት የውድድር ዘመን ለሶስት ጊዜያት የወሩ ምርጥ ተጨዋች በመባል ሪከርድ ጨብጧል፡፡ ለእንግሊዝም 14 ጨዋታዎች ላይ ተሰልፏል፡፡ ተጨዋቹ ሊቨርፑል የሚፈልገውን ኳስ የመቆጣጠር ክህሎት ከመያዙ በተጨማሪ ሁለገብ እና የማጥቃት አደጋ መፍጠር የሚችል ነው፡፡ በዚህ ላይ ዳልግሊሽ ለሚከተላቸው የ4-5-1 እና 4-4-2 ፎርሜሽኖች የተመቸ ነው፡፡
የመዘዋወር እድል 7/10
ኢከር ሙኒያይን (የመስመር አማካይ)
እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ስለዚህ ተጨዋች የተደመጠ ነገር አልነበረም፡፡ ዘንድሮ በላሊጋው እያሳየ ያለውን አስደናቂ አቋም ተከትሎ ከአውሮፓ ተስፈኛ ወጣቶች ጎራ የተመደበው ሙኒያይን በሊቨርፑል መልማዮች ክትትል ውስጥ የወደቀው ከወራት በፊት ነው፡፡ የአትሌቲኮ ቢልባኦው ኮከብ ለክለቡ በወጣት ዕድሜው በመጫወት ሪከርድ የያዘ ሲሆን ከሳምንት በፊት ደግሞ በአነስተኛ ዕድሜው ለክለቡ ጎል ያስቆጠረ ተጨዋች ሆኗል፡፡ በላሊጋውም እንዲሁ በአነስተኛ ዕድሜው ኳስ እና መረብን ያገናኘ ተጨዋች መሆን ችሏል፡፡ ገና 18 ዓመቱ ቢሆንም ቢልባኦን ወክሎ 56 የሊግ ጨዋታዎችን አድርጓል፡፡ በአውሮፓ ውድድሮችም ዘጠኝ ጨዋታዎች ላይ ተሰልፏል፡፡ የመስመር አማካይም ሆነ አጥቂ ሆኖ መጫወት የሚችለው እንዲሁም ሀገሩን ከ21 ዓመት በታች ቡድን የሚወክለው ሙኒያይን አጠር ያለ ቢሆንም ፍጥነቱ እና የግል ክህሎቱ አስደናቂ ነው፡፡ ሁለገቡ ወጣት ሊቨርፑልን የሚቀላቀል ከሆነ ለቡድኑ ጠቃሚ እንደሚሆን ችሎታው ይመሰክራል፡፡ µ
ሮሜሉ ሉካኩ
(አጥቂ)
ዳልግሊሽ በአጥቂ ክፍል ከሉዊስ ሱአሬዝ እና አንዲ ካሮል ውጪ ዴቪድ ንጎግን ብቻ እንደመያዙ ሌላ ተጨዋች ለማስፈረም አለመነሳሳቱ ያስገርማል፡፡ ምክንያቱም ንጎግ ግዝፈት እና ፍጥነት ይኑረው እንጂ ተከላካዮችን በሚፈልገው መጠን መረበሽ አይችልም፡፡ በዚያ ላይ ጠንካራ እና ከኳስ ጋር ያለው ንክኪ የሚያስመካ አይደለም፡፡ ስለዚህም ሊቨርፑል ሱአሬዝ እና ካሮልን በጉዳት ቢያጣ ችግር ውስጥ ላለመግባት ሌላ አጥቂ ለመመልከት ይገደዳል፡፡ ሉካስ ለአንዳርሌክት ዋናው ቡድን መጫወት የጀመረው 16 ዓመት ሊሞላው 11 ቀናት ሲቀሩት ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ወዲህ ለክለቡ 66 ጨዋታዎችን አድርጎ 31 ጎሎችን አግብቷል፡፡ ለቤልጅየምም ዘጠኝ ጊዜ ተሰልፎ ሁለት ኳሶችን ከመረብ አገናኝቷል፡፡ 192 ሜትር የሚረዝመው እና 97 ኪሎ ግራም የሚመዝነው ተጨዋች 18 ዓመት የሞላው ገና ከሳምንት በፊት መሆኑ ደግሞ የበለጠ አስገራሚ ነው፡፡ ፍጥነቱ እና ተፅዕኖ የመፍጠር አቅሙም ድንቅ ነው፡፡
የመዘዋወር ዕድሉ 5/10

ተጨማሪ ያንብቡ:  Ethiopia's Shumi Gerbada wins Stockholm Marathon
Share