ዩናይትድ ኤንሪኬን ፈልጎታል

ማንቸስተር ዩናይትድ የኒውካስል ዩናይትድን የግራ መስመር ተከላካይ ሆዜ ኤንሪኬን ለማስፈረም ከሊቨርፑል ጋር ትግል ለማድረግ ቆርጧል፡፡ የሜርሲሳይዱ ክለብ ደጋፊዎች አሰልጣኝ ኬኒ ዳልግሊሽ ስፔናዊውን ተጨዋች እንደሚያስፈርመው እርግጠኛ ሆነዋል፡፡ ሆኖም ሰር አሌክስ ፈርጉሰንም ወደ አንፊልድ ያቀናል የሚለውን ዘገባ ያስተባበለውን ተጨዋች እየተከታተሉት ይገኛሉ፡፡ ባየር ሙኒክም 15 ሚሊዮን ፓውንድ የተገመተውን የ25 ዓመቱን ኤንሪኬ በቻምፒየንስ ሊግ የሚያሳትፈውን ዕድል እንደሚያቀርብለት ገልፆለታል፡፡ ኤሲ ሚላኖችም ኒውካስል በ2007 ከቪያሪያል ላይ በ6.3 ሚሊዮን ፓውንድ ያስፈረመው ተጨዋች አድናቂ ናቸው፡፡ ምንም እንኳን የ30 ዓመቱ ፓትሪስ ኤቭራ በኦልድ ትራፎርድ የሚቆየውን አዲስ ኮንትራት ቢፈርምም ፈርጉሰን በኤንሪኬ ላይ ያላቸው ፍላጎት አልቀነሰም፡፡ የኒውካስሉ አሰልጣኝ አለን ፓርዴው ግን ከክለቡ ጋር ተጨማሪ የአንድ ዓመት ኮንትራት የሚኖረው ተጨዋች በሴንት ጀምስ ፓርክ እንደሚቆይ ገልፀዋል፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ፒፕል ዘገባ ተጨዋቹን ከአሁኑ እንደሚያጡት በመፍራት ለፈረንሳይ ከ21 ዓመት በታች የሚጫወተውን የ22 ዓመቱን የቱሉዝ ተከላካይ ሼይክ ምዜንጉዋን በተተኪ እጩነት ይዘውታል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Ethiopia appoint Belgian Saintfiet as head coach
Share