ሃላፊነትን በአግባቡና በጊዜው አለመወጣት ያስከተለውና እያስከተለ ያለው አደገኛ  ውጤት

ጠገናው ጎሹ

February 25, 2024

ሃላፊነት (responsibilty) አንድን ጉዳይ በተቀመጠለት መሠረታዊ ተልእኮ፣ ዓላማና ግብ መሠረት ተፈፃሚ ለማድረግና ለማስደረግ ይቻል ዘንድ በየደረጃው እንደ ሚገኝ አመራር ፣ እንደ ማህበረሰብ እና እንደ ግለሰብ የምንሸከመውን ግዴታና ተግባር የሚገልፅ ቃል (ፅንሰ ሃሳብ) ነው። ሃላፊነትን በአግባቡና በወቅቱ የመወጣት ጉዳይ ደግሞ በፅዕኑ መርህ ላይ ፀንቶ የመቆምን ፣ የአስተማማኝነት ሰብዕናን ፣ የታማኝነት ልዕልናን  እና በራስ የመተማመን ማንነትንና ምንነትን ይጠይቃል ።

ሃላፊነትና ከእርሱ ጋር የተያያዙ ፅንሰ ሃሳቦች ለምንነትና እንዴትነት በምድራዊውም ሆነ በሃይማኖታዊ ዓለም በጉልህና በአፅንኦት የሚታወቁና የሚጠቀሱ መሆናቸውን ለማሳየት የመፅሐፍት ምዕራፍና   ቁጥር መጠቃቀስ የሚያስፈልገኝ አይመስለኝም።

እንደ እውነቱ ከሆነ ሁለቱንም ማለትም ዓለማዊውን እና ሃይማኖታዊውን እምነት በጥብቅ ከሚያገናኟቸው (ከሚያቆራኟቸው) እጅግ ግዙፍና ጥልቅ ጉዳዮች መካከል የሰው ልጆችን መሠረታዊ ሰብአዊ መብቶች ፣ የነፃነትና የፍትህ እሴቶች፣ የሃይማኖታዊ እምነት ነፃነቶች፣ በገዛ ምድራችው (አገራቸው) በሰላም ሠርተው የመኖር ማንነቶች፣ መልካም የታሪክ አሻራን ለትውልድ የማስተላለፍ ወርቃማ ተልእኮዎች እውን ለማድረግ የሚደረጉ የጋራ ጥረቶችን በማሳያነት መጥቀስ ይቻላል።

እኛ ግን ከዚህ  አይነት ጤናማና ትውልድ ቀራፂ ከሆነ ሚዛናዊ አስተሳሰብና አካሄድ ተንሸራተን ከወደቅን ዘመናትን አስቆጠርን። ይህ የዘመናት አስከፊና አሳፋሪ እንዴትነታችንና ከየት ወደ የትነታችን ያስከፈለንና እያስከፈለን ያለው ግዙፍና መሪር ዋጋ አሁንም ከምር የቆጨን/የፀፀተንና ከምር በቃን ያሰኘን አይመስልም።

በእውነት ስለ እውነት ከተነጋገርን ከተለመደ (ሊያጋጥም ከሚችል ፈተናነት ችግርነት) አልፎ በስፉትም ሆነ በአስከፊነት ማነፃፀሪያ ሊገኝለት በማይቻል ሁኔታ ውስጥ ራሳችንን ያገኘነው በሁለቱ ተቋማት (ሃይማኖታዊና ፖለቲካዊ) የአመራር  ሥልጣነ  መንበር ላይ በሚሰየሙና በየደረጃው በሚዘጋጁ ሥልጣነ መንበሮች ላይ በሚቀመጡ ወገኖች በእጅጉ  የተደበላለቀና ያልተቀደሰ  ጋብቻ (ግንኙነትምክንያት ስለመሆኑ የሚጠራጠር የቅንና የእውነተኛ ህሊና ባለቤት የአገሬ ሰው የሚኖር አይመስለኝም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ከፕ/ር ማሞ ሙጬ ጋር የተደረገ ቃለ ምልልስ

አዎ! መቸም የገዛ ራሳችንን ግዙፍና መሪር ሃቅ የመጋፈጡና ትክክለኛውን ፍኖተ አስተሳሰብና የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሥረታ ፈልገን ከማግኘትና የጋራ ተጋድሎ ከማድረግ ይልቅ ልክ ለሌለው ውድቀታችን የሰበብ ድሪቶ መደረት ተጠናውቶን ነው እንጅ በቤተ ክህነቱ ጽ/ ቤት እና የሴራና የመከራ ዶፍ በሚመረትበት ቤተ መንግሥት መካከል ለተፈጠረው  ያልተቀደሰና አደገኛ ለሆነ ግንኙነት ሃላፊነቱንና ተጠያቂነቱን የሚወስዱት በሃይማኖታዊ ሥልጣነ መንበር ላይ ተሰይመው  በንፁሃን ዜጎች ላይ የመከራና የውርደት ዶፍ ካወረዱትና ከሚያወርዱት ሴረኛና  ጨካኝ ገዥ ቡድኖች ጋር እየተሻሹ ራሳቸውን እንደ ትጉህ እረኞች የሚቆጥሩ የሃይማኖት መሪዎች ነን ባዮች ናቸው።

አዎ! ከምር የሆነ የጋራ ተጋድሎ በማድረግ ለዘመናት የዘለቀውንና በተለይ ደግሞ ከስድስት ዓመታት ወዲህ  አገርን ወደ ለየለት አለመኖር እያመራት ያለውን የፖለቲካ  ካንሰር በማስወገድ ሃይማኖትን ጨምሮ ሁሉም አይነት ነፃነቶችና መብቶች የሚረጋገጡበትን  ሥርዓት እውን ማድረግ ካለብን በዚህ ደረጃ ነው መነጋገር ያለብን።

“የምንነግርህን እንጅ የምናደርገውን ለእግዚአብሔር ተወለት፣ የምትሳለመው መስቀሉን ስለሆነ የሚያሳልምህን ካህን ወይም ባለ ሌላ ማእረግ ባህሪና ድርጊት ለፈጣሪ ተወው፣ ካህን በምድር ያሰርከው በሰማይ የታሰረ ይሁን ተብሏልና …. ፣ ወዘተ” በሚል ደምሳሳና ራስን አይነኬ  የማድረግ ጉዳይ አማኝን (ተከታይን) ያለ አግባብ ያደነቁራል እንጅ ፈፅሞ የፅድቅ መንገድ አይሆንም።

ካህንም ይሁን ከፍተኛ  የሃይማኖት መሪና ሰባኪ ሰው እንደመሆኑ መጠን ሳያውቅም ሆነ አውቆት ሊሳሳት እንደሚችል አያጠያይቅምና እንዲህ አይነቱን ከሰዋዊ ባህሪ የሚመነጭ ድክመትንና ውድቀትን ሲሆን በራስ ህሊና አስተዋይነትና ዳኝነት ካልሆነም በቅርብ ሰውም ይሁን በሁኔታዎች መካሪነት ማረም(ማስተካከል) ይቻላልና ችግሩን እያወቁም ለተወሰነ ጊዜ መታገሥ አስፈላጊ ይሆናል ።

እንደ እኛ አይነቱን ለዘመናት የዘለቀን ፣ በእጅጉ አስቀያሚ የሆነን እና እየሆነ የቀጠለን ቀውስና ውድቀት ግን በቀላሉ ወይም በማለባበስ  ለማስተካከል አይቻልም።

ለመሆኑ ከገዳይነት፣ ከአስገዳይነት እና ከአገዳዳይነት ፖለቲካ ሥርዓት ዘዋሪዎች (አራጊና ፈጣሪዎች) ጋር የሚተሻሽ ወይም የሚሞዳሞድ የሃይማኖትመሪ ወይም ካህን ተሸክሞት የሚዞረውን መስቀል መሳለም  በመስቀሉ መቀለድ ወይም መነገድ አይሆንም እንዴ?

ለመሆኑ በፈጣሪ አምሳል በተፈጠረ ፍጡር የሚነግዱትን ባለ ርካሽ ህሊና ወገኖች ክርስቶስ ከሞተበት የመስቀል ሃይል ጋር ምን ያገናኛቸዋል? እንዲህ አይነት የሃይማኖት ነጋዴዎች በፈጣሪ ስም ሲቀልዱበት ነውር ነው ለማለት ሞራሉ የሚከዳው ትውልድ ምን አይነት የነፃነትና የፍትህ ሥርዓት ነው የሚናፍቀው?

ለመሆኑ የክስተትን የትኩሳት መጠን እየተከተለ (እየለካ) እና የፖለቲከኞችን ስሜት እያዳመጠ  እንደ ሸፍጠኛ ገዥ ቡድኖች ከተግባር አንፃር ሲታይ ፈፅሞ ትርጉም የሌለውና በእጅጉ የሰለቸ መግለጫ ከማሳወቅ እና የአዞ እንባ ከማንባት ያላለፈና የማያልፍ  ቅዱስነት ወይም ቅድስና ምን አይነት ቅዱስነትና ቅድስና ነው?

ለመሆኑ የህዝብን የፖለቲካ ወለድ መከራና ውርደት ሰለባ መሆንና ግራ መጋባትን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ሰዎችን መልምሎና አደራጅቶ በየ አደባባዩና በየ አዳራሹ በሚያዥጎደጉደው ስብከተ ቃልና በሚያቀልጠው መውረግረግ (ዳንስ) የሰውን አእምሮ እያሸበረ በፈጣሪ ስም  የተኘኘውን ጥቅማጥቅም ሁሉ የሚዘርፍ ነብይ ነኝ ባይንና እውነተኛ ሃይማኖታዊ እምነትን ምን ያገናኛቸዋል?

ለመሆኑ በሴረኛና ሸፍጠኛ ገዥ ቡድኖች ተባባሪነትና አስተባባሪነት መፈንቅለ መጅሊስ አድርገው አመራሩን (ሥልጣኑን) በተቆጣጠሩት የእስልምና ሃይማኖት መሪዎች የበላይነት የሚፀለይ ፀሎትና የሚሰገድ ስግደት ለዘመናት ከመጣንበትና ይበልጥ ተዘፍቀን ከምንገኝበት ፖለቲካ ወለድ የመከራና የውርደት አረንቋ ለመውጣት እንዴት ነው የሚታደገ?

ለመሆኑ ሃይማኖትን ጨምሮ እጅግ መሠረታዊ የሆኑ የንፁሃን ዜጎች (ሰብአዊ ፍጡሮች)  ተሰምቶና ታይቶ በማይታወቅ አኳኋን የፖለቲካ ወለድ መከራና ውርደት ሰለባዎች ሲሆኑ እዚህ ግባ ከሚባል ሚና ያልተጫወተ (አስተዋፅኦ ያላደረገ) የሃይማኖቶች ምክር ቤት ከእውነተኛ ሃይማኖታዊ እምነት እሴት ጋር ምን ዝምድና አለው?

የሃይማኖት ተቋማት በሥልጣነ መንበር ላይ የሚፈራረቁ የሸፍጠኛ፣ ሴረኛና ጨካኝ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ሥርዓት ዘዋሪዎች (አራጊና ፈጣሪዎች) ሰለባ ከሆኑ እና ከባድ ፈተና ከገጠቸውው አያሌ ዓመታት ተቆጠረዋል። በአሁኑ ወቅት እየሆነ ያለው ግዙፍና መሪር እውነት ደግሞ ሰው ሆኖ መፈጠርን በእጅጉ ይፈታተናል። ለዚህ ደግሞ ቀዳሚ ተጠያቂዎች የእረኝነት ሥልጣን ተሰጥቶናል እያሉ በፖለቲካ ወለድ ወንጀል ከበሰበሰና ከከረፋ የፖለቲካ ሥርዓት ፖለቲከኞች (ዘዋሪዎች) ጋር እየተሻሹ ራሳቸውን ለዓለማዊ (ለሥጋዊ) ህይወት አሳልፈው የሰጡ የሃይማኖት መሪዎችና ቢጤወቻቸው ናቸው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  Hiber Radio: አንጋፋው የሜጫና ቱለማ አመራር ስንብትና ሕወሃት ሜጫና ቱለማን ለማዳከም የወሰዳቸው እርምጃዎች (ወቅታዊ ዘገባ)

ይህ ግን አማኝ (ተከታይ) ነኝ የሚለውን በተለይም ፊደል የቆጠረውንና ቆጣሪውን ከሃላፊነት ፈፅሞ ነፃ አያደርገውም። በባለጌ፣ በሴረኛ፣ በሸፍጠኛና ጨካኝ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ነጋዴዎች (ቁማርተኞች) የገዛ አገሩ ምድረ ሲኦል ስትሆን እያየ አጥፊዎችን ከምር ከመገሰፅ ይልቅ የሚያባብሉትን፣ የሚማፀኑትን፣ እና ከዚህም አልፎ በየአቅጣጫው የተወጠረ መንግሥት ፣ ወዘተ በሚል ራሳቸውን አዋርደው እረኛው እንደሆኑ የሚነግሩትን የዋህ አማኝ ያዋረዱ የሃይማኖት መሪዎችንና  ባልደረቦቻቸውን ለምንና እንዴት? ብሎ መጠየቅን እንደ ድፍረትና ሃጢአት የሚቆጥር አማኝ (ተከታይ) ከምር ራሱን መጠየቅ ይኖርበታል።

እናም  በእውነተኛና ከምር በሆነ የሃላፊነት አቋምና ቁመና ሃይማኖትን ጨምሮ ሁሉም መሠረታዊ መብቶች የሚረጋገጥበት ሥርዓትን እውን ለማድረግ ይቻል ዘንድ እልህ አስጨራሽ ተጋድሎ በማካሄድ ላይ ለሚገኙት ወገኖች ሁለገብ ድጋፍ በማድረግ ለድል ማብቃትና ዴሞክራሲያዊት አገርን እውን ማድረግ ብቸኛው መንገድ ነው።  ያለዚያ ግን የመከራውና የውርደቱ ዶፍ እንዳልነበርን ቢያደርገን ተጠያቂዎች እኛው ራሳችን እንጅ ከቶ ሌላ አካል አይሆንም ።

እናም ልብ ያለው ልብ ይበል!!!

 

1 Comment

  1. “ያለዚያ ግን የመከራውና የውርደቱ ዶፍ እንዳልነበርን ቢያደርገን ተጠያቂዎች እኛው ራሳችን እንጅ ከቶ ሌላ አካል አይሆንም ።”
    Aptly stated.
    We ignored the killings of the Orthodox clergy in Beshasha (then under the administrative oversight of Abiy Ahmed Ali) 20 years ago.
    We ignored the Burayu Massacre 6 years ago
    We ignored the massacres in Wellega, Benshangul Gumuz, Somali Region 5 years ago.
    We ignored the Shashemene, Arsi, Awasa, Ataye massacres 4 years ago.
    We ignored the Maikadra massacre 3 years ago
    We ignored massacres in Tigray 2 years ago.
    We ignored the Merawi massacre 1 month ago.
    Beshasha was a template for Ziquala which is a template for 5 kilo.
    Metekel was a template for Merawi which is a template for Addis Ababa.
    Unless we rise unified, the agents of destruction and their foreign sponsors are gearing the country towards the grandest genocide humanity has ever seen.

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share