የሃይማኖት ጉዳይ ሊያስጨንቀን የሚገባው ለምድነው?

November 25, 2023

ጠገናው ጎሹ
ለዚህ አስተያየቴ ይህንን ርዕስ የመረጥኩት ስለ ሃይማኖት ምንነትና እንዴትነት ለማስተማር ወይም ለመስበክ አይደለም። ለማድረግ ብፈልግም ለዚህ የሚያበቃ እውቀቱና ችሎታውም ስለሌለኝ አላደርገውም።

ታዲያ ለምንድነው?  የሚል ጥያቄ ስለሚነሳና መነሳቱም ተገቢ ስለሆነ ይህንኑ ግልፅ ለማድረግ አስተያየቴን በጥያቄ መልክ በማቅረብ መልሱን ሃይማኖትን ጨምሮ መሠረታዊ ሰብአዊ መብት ፣ ነፃነት፣ ፍትህ (ዴሞክራሲ) ፣ ሰላም፣ ፍቅር ፣ የጋራ እድገት ፣ ወዘተ የሚረጋገጥበትና የሚከበርበት ሥርዓት እውን እንዲሆን ከምር ለሚሹ ወገኖች እተወዋለሁ።

ስለምንከተላቸው የሃይማኖት ተቋማት ነፃነትና ስኬታማነት ስንነጋገር ከምንኖርበት (ከምንገኝበት) የፖለቲካ ሥረዓት ለምንነት ፣ ለማንነት  ፣ እንዴትነት እና ከየት ወደ የትነት አንፃር መሆኑን መዘንጋት የለብንም።

 

እናም ልቀጥል፦

1)   ከማሰቢያ ረቂቅ አእምሮና ከማከናወኛ ብቁ አካል ጋር በክርስቶስ አምሳል የተፈጠረ ሰብአዊ ፍጡር ከፈጣሪው እርዳታ ጋር መሠረታዊ መብቱ ተጠብቆ፣ እርስ በርሱም ተከባብሮ፣ ተረደዳቶ ፣ ተፋቅሮ፣ ሰላምን ተንከባክቦ ፣ በጋራ በልፅጎ ፣ ወዘተ እንዲኖር እና እነዚሁ ወርቃማ እሴቶቹ ከሞት በኋላ ተስፋ ለሚያደርገው ህይወት ስንቅ እንዲሆኑት መርዳትና ማስቻል የሃይማኖት ዓላማና ግብ ካልሆነ ሌላ ምን?

 

2)   እነዚህን እጅግ መሠረታዊ እሴቶች ለምድራዊውና ተስፋ ለሚያደርገው የዚያኛው ዓለም ህይወት ስኬታማነት በአግባቡ ይጠቀምባቸው ዘንድ በነፃነት እና በራስ መተማመን አቋምና ቁመና እንዳይነቀሳቀስ (ጥረት እንዳያደርግ) የሚያሰናክሉ ወይም የሚከለክሉ እኩያን ገዥዎችና ግብረ በላዎቻቸው የሚፈፅሙትን እጅግ ክፉ ፖለቲካ ወለድ ወንጀል አቁመውና ንስሃ ገብተው የህዝብ መከራና ውርደት አብቅቶ ለሁሉም የሚበጅ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እውን ይሆን ዘንድ ሚያደርገውን ተጋድሎ እንዲያግዙ ከምር የሚቆጣና የሚመክር እና አስፈላጊም ከሆነ አስፈላጊውን መስዋእትነት ለመቀበል ፈቃደኛና ዝግጁ የሆነ  አመራር የማፍራትና የማሠማራት ሃላፊነትን መወጣት የሃይማኖት ተቋማት መሠረታዊ ተልእኮ ካልሆነ ሌላ ለምንና ለማን ?  

 

3)   እርግጥ ነው ይህንን እውን ለማድረግ መንገዱ አልጋ ባልጋ አይሆንም። ሃይማኖትን ጨምሮ መሠረታዊ መብቶች በተጠየቁ ቁጥር ሥልጣነ መንበራቸው ሥጋት ላይ የወደቀ እየመሰላቸው ነፃነትና ፍትህ በሚጠይቀው መከረኛ ህዝብ ላይ የጭካኔ ሰይፋቸውን የሚመዙ እኩያን ገዥዎችን አግባብነት ባለውና በማይታጠፍ መንፈሳዊ መሪነት መጋፈጥ የግድ መሆኑን ተረድቶና ተቀብሎ የእረኝነት ሃላፊነትንና ተልእኮን የመወጣት ጉዳይ የሃየማኖት መሪዎች ካልሆነ ሌላ የምንና የማን?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኮሚዩኒኬሽን ወይስ ፎልሲፊኬሽን? - ከመርሐጽድቅ መኮንን አባይነህ

 

4)   በእኩያን ገዥዎች ፖለቲካ ወለድ ወንጀል ምክንያት በግፍ ግድያ፣ ከገዛ አገር በመፈናቀል ፣ በጅምላ ግዞትና እስር ፣ በርሃብ ቸነፈር ፣ በእርዛት አለንጋ ፣ የወላድ መካን በመሆን ሁለንተናዊ ስቃይ ፣በወላጅ አልባነት መሪር ሰቆቃ ፣ እና በአጠቃላይ ለመግለፅ በሚያስቸግር የውድቀት አዙሪት  ውስጥ በመጓጎጥ ላይ ለሚገኝን መከረኛ ህዝብ ቀድሞ የመድረስ ሃላፊነት ካለባቸው ወገኖች መካከል የሃይማኖት መሪዎችና ሊቃውንት ዋነኞቹ  ካልሆኑ ሃይማኖት ለምንና ለነማን?

 

5)   በዚህ ረገድ ከዘመን ዘመን ከመሻሻል ይልቅ በእጅጉ እየባሰበት የመጣው ውድቀታችን አይደለም ወይ ሃይማኖቶቻችን ከፍተኛ ፈተና ላይ እየጣላቸው የሚገኘውይህንን እጅግ አሳሳቢና አስፈሪ ሁኔታ በጥሞና እና አርአያነትን በተላበሰ የሃይማኖት አርበኝነት ማስተካከል የሚገባቸው የሃይማኖት መሪዎችና ሊቃውንት ራሳቸው ሆነው ሳለ በሥልጣነ መንበር ላይ እየተፈራረቁ  የመከራውንና የውርደቱን ዘመን በአስከፊ ሁኔታ እያራዘሙ ካሉት ባለጌና ጨካኝ ገዥ ቡድኖች ጋር  እየተሻሹ ዘመን ጠገብ የሆነውንና የማይደፈረውን ሃይማኖታዊ  ዶግማና ቀኖና በአፍ ጢሙ ሲደፉትና ሲያስደፉት ማየትና መስማት የሃይማኖት ምንነትንና እንዴትነትን ከባድ ፈተና ላይ ቢጥል ለምን ይገርመናል?

 

 

6)   በተለይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስና የእስልምና ሃይማኖቶች ከነችግራቸውም ቢሆን ለረጅም ዘመን ከመኖቸው ጋር ተያይዞ የጋራ የሆኑ ማህበራዊ፣ ትውፊታዊ፣ ባህላዊ፣ ሥነ ልቦናዊ፣ ሥነ ምግባራዊ ፣ ወዘተ እሴቶችን አጣምረው የያዙ ከመሆናቸው አንፃር የባለጌና ጫካኝ ገዥ ቡድኖች ርካሽ የፖለቲካ ጨዋታ ሰለባዎች ሲሆኑ ማየት ከምር የማያስበን ከሆነ ስለየትኛው ሃይማኖትና የሃይማኖት ነፃነት ነው የምናወራው?

 

7)    የትኛውም ሃይማኖት  ከማሰቢያ አእምሮና ከብቁ የማከናወኛ አካል ጋር በክርስቶስ አምሳል የተፈጠረው የሰው ልጅ  (የአገሬ ሰው) የገዛ ምድሩ በባለጌ፣ ሸፍጠኛ፣ ሴረኛና ጨካኝ የጎሳና የቋንቋ አጥንት ስሌት ፖለቲካ  ገዥ ቡድኖች ምድረ ሲኦል ስትሆንበት በጋራ ቆሞ ቢያንስ ነውር ነው ካላለና ካልገሰፀ ምን አይነትና እንዴት አይነት ሰብአዊ ሃይማኖት እንደሆነ ለመረዳት አያስቸግርም እንዴ?

 

8)    ሲኖዶስን እና መጅሊስን የባለጌና ጨካኝ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ነጋዴዎች መፈንጫ ከማስደረግ የከፋ የሃይሃይማኖት መሪነት (አባትነት) ኪሳራ ይኖራል እንዴ?  ሃይማኖታዊ ሃላፊነትና ተልእኮ ባፍ ጢሙ ሲደፋ ማየትና መስማት  እውነተኛ ሃይማኖተኛ ነኝ ለሚል ወገን የሚያስከትለውን የህሊና ህመም የምንረዳው ስንቶቻችን ነን?

ተጨማሪ ያንብቡ:  በሳንሆዜ ከተማ ለወራት የታቀደው የወያኔ የማጭበርበር ሴራ በሚያሳፍር መልኩ ተጠናቀቀ

 

9)   የሃይማኖት “መሪዎችና  ሊቃውንት”  በየራሳቸው ጊዜና  ተጨባጭ ሁኔታ በታሪክ ሂደት ከተፈፀሙት ስህተቶች በአግባቡና ከምር ትምህርት በመውሰድ  የዛሬውንና የነገውን ትውልድ የሚጠቅሙ  ሥራዎችን ሠርቶ መገኘት ሲገባቸው  የክስተቶችን ትኩሳት እየተከተሉ  በግልብ ስሜት የመነዳት ሰለባዎች የመሆናቸው ግዙፍና መሪር እውነታ ህሊናውን የማይኮሰኩሰው እውነተኛ አማኝና አገር ወዳድ የሚል የአገሬ ሰው ይኖር ይሆን?  “ክርስቶስ ነን የሚሉ ሃሳዊያን ይነሳሉና ተጠንቀቁ ተብሏልና አስተውሉ” እያሉ ሲሰብኩን የኖሩ የሃይማኖት መሪዎች ውድቀት ግልፅ የሆነው ለአሽከርነት ክድርና ፍፁም በሚመቹ ብአዴን ተብየ የአገር ጉዶች ተባባሪነት የህወሃትን የበላይነት አስወግዶ  ቤተ መንግሥቱን የተረከበውንና የፖለቲካ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ የሰብዕና ዝቅጠት የተጠናወተውን  አብይ አህመድን ለመገምገም የሚያስችል ጊዜና ትእግሥት ሳይወስዱ የኢትዮጵያ “ትንሳኤ ብርሃን” አድርገው የነገሩን  እለት አይደለም እንዴ?

 

10)        ምንም እንኳን ይህንን ስህተት ለመከላከል የሚያስችል አሳማኝ ምክንያት ባይኖርም ሊያጋጥም እንደሚችል ቆጥረን እንዳናልፈው የሥልጣነ መንበሩን አራጊነቱንና ፈጣሪነቱን (ጠርናፊነቱን) የጠቀለለው ተረኛ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቡድን (ኦህዴድ/ኦነግ/ብልፅግና) ይኸውና ለአምስት ዓመታት አገርን ምድረ ሲኦል እያደረገ ሲቀጥል እንኳንስ ስህተታቸውን አርመው ሃላፊነታቸውንና ተልእኳቸውን በአግባቡ ሊወጡ ይባስ ብለው የሃይማኖት አሿሿሙንና የሥራ ቦታ አመዳደቡን “ጥንብ ነው” እያሉ የሚሰብኩን የጎሳና የዘር አጥንት ስሌት ፖለቲካ ሥርዓት አካል የማድረጋቸው መሪር እውነት ልቡን የማያደማው እውነተኛ አማኝ ይኖር ይሆን?

 

11)        እረኛው ነን የሚሉትን አማኝ ህዝብ ጉድፍ (ስህተት) የመረዳትና በንስሃ ለማንፃት  መንፈሳዊ ሥልጣንና አቅም እንዳላቸው የሚሰብኩን የሃይማኖት መሪዎችና ሰባኪዎች  ለአምስት ዓመታት              የመጡበትንና አሁንም እጅግ አስከፊና በሆነ ፈተና ውስጥ የምገኙበትን በተቃርኖ የተሞላ አስተሳሰባቸውንና አካሄዳቸውን ከተግባር ጋር በተዋሃደ  ፆምና ፀሎት ለማስተካከል ጥረት  ከማድረግ         ይልቅ ድርጊት አልባ ፀሎተ ምህላ አዋጅ በማወጅና ተሰብስቦ በእንባ የታጀበ እግዚኦታ በማስተጋባት ለምድሩም ሆነ ለሰማያዊው ህይወት የሚበጅ ለውጥን እውን ለማድረግ እንዴት እንደሚቻል         ለማመን አያስቸግርም እንዴ?

 

12)        ከዚህ የፀሎተ ምህላ አዋጅ ጋር ተያይዞ ፈፅሞ ለመግለፅ በሚያስቸግር ፖለቲካ ወለድ ወንጀል የበሰበሰውን (የከረፈውን) የፖለቲካ ሥርዓት በልፍስፍስ የአንተም ተው የአንተም ተው ሽምግልና ወደ         የእርቅና  የሰላም ጠረጴዛ ለማምጣት የሰላም ኮሜቲ ወይም ግብር ሃይል መሰል ቡድን የማቋቋም  አስፈላጊነት ዜናን ሰምተናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሁለት ደብዳቤዎች ወግ ከአዲስ አበባ እና ከመቀሌ - መሳይ መኮነን

በምሥራችነት በተነገረን ዜና  እና ዜናውን የሚነግሩን የሃይማኖት መሪዎች    በመጡበትና በሚገኙበት እጅግ ደካማ አቋምና ቁመና  መካከል ያለውን  ርቀት በምን ይሉኛል ደካማ አቀራረብ ሳይሆን እውነተኛና ዘላቂ መፍትሄንና  አስተሳሰብን ግምት ውስጥ በሚያስገባ ሚዛናዊ  ህሊና  ለሚያስተውል  ሰው የሃይማኖታዊ እምነት ነፃነት  ከብልሹ ሥርዓት መወገድ ወይም አለመወገድ  ጋር በጥብቅ የተያያዘ መሆኑን ለመገንዘብ ይሳነው ይሆን ?

 

13)      ቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረትና ርብርብ የሚጠይቀውን የመከረኛ ወገን ህይወት ከመታደግ ይልቅ ባህርና ውቅያኖስ ማዶ ለሚሠራ ቤተክርስቲያንና ገዳም በብዙ ሚሊዮኖች የሚገመት ዶላር ብትሰጡ “ገነት ትገባላችሁ” በሚል  ዘመቻ ላይ መጠመድ እውን የእውነተኛ ሃይማኖታዊ ምንነታችንንና እንዴትነታችንን ይመጥናል እንዴ ለመሆኑ በየዋህነትም ሆነ በአንዳንድ የግልና የቡድን ጥቅም አሳዳጆች የሚካሄደውን ይህንን ዘመቻ “ልጆቻችንና ባልደረቦቻችን ሆይ፦ እስካሁን ከቆየንበት (ከኖርንበት) አይብስምና እባካችሁ መፅናኛ ላጣው ወገናችን የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት ሰጥተን እንረባረብ ፤ ሌላው ቀጥሎ ይደርሳል/ይሆናል ” የሚል የሃይማኖት መሪና ሊቀ ሊቃውንት እንዴት ይታጣል?

 

14)   አዎ! በእውነት ከተነጋገርን የክርስቶስ ማደሪያዎች ወይም ቤተ መቅደሶች የሆኑ በአያሌ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ንፁሃን ወገኖች ህይወት እየተደረመሰ (እየወደመ) ባለበት መሪር ሁኔታ ውስጥ የሚገነባው  ቤተ ክርስቲያን ወይም ገዳም ለየትኛው እግዚአብሔር ነው ማረፊያና ማደሪያ የሚሆነው? ፈጣሪን ጨምሮ ለመከረኛ ፍጡሮቹ ቅድሚያ ከመስጠት ይልቅ በየባህርና በየውቅያኖስ ማዶ ድንቅ ህንፃዎችን (ቤተ ክርስቲያናትንና ገዳማትን) በማሠራት የሚደሰት ጨካኝ ለምን እናስመስለዋለን?

ከችግራችን ዘመን ጠገብነትና ውስብስብነት የተነሳ ልቀጥል ብል ጥያቄን ጥያቄ እየወለደው እቸገራለሁና ለማሳያነት ይሆናሉ ያልኳቸውን ካነሳሁ ይበቃኛል።

አያሌ የዋህ አማኝ ወገኖች እና የህዝብ መከራና ሰቆቃ እንደሌለ በሚያስመሰል አኳኋን በባህርና በውቅያኖስ ማዶ የእግዚአብሔርን ቤት ለመሥራት በሚል ዘመቻ የተጠመዱ ወገኖች ከላይ እንደ ዋነኛ ማሳያ ያነሰኋቸውን ግልፅና ቀጥተኛ ጥያቄዎች እንደ እግዚአብሔር አልባነት ወይም እንደ መርገምት  በመቁጠር የውግዘትና የእርግማን ናዳ ቢሰነዝሩ ያሳዝነኝ እንደሆን እንጅ ከቶ አይገርመኝም። ለምን ቢባል  ያፈጠጠውንና ያገጠጠውን የገዛ ራሳችንን የውድቀት አዙሪት በዓለማዊና በመንፈሳዊ የአርበኝነት አቋምና እና ቁመና  በመጋፈጥ ለምድራዊውም ሆነ ለሰማያዊው ህይወት የሚበጀንን ሥርዓተ ማህበረሰብ አምጠን ከመውለድ ይልቅ የጥንካሬና የስኬታማነት እሴቶችን አጣምሮ የያዘውን ሃይማኖታዊ እምነት የድክመቶቻችን መሸፈኛ (መሸሸጊያ) የማድረግን እጅግ አስቀያሚ  ድክመት  በፍፁምነት ማስወገድ ባንችልም ከቁጥጥራችን እየወጣ ተገዥው እንዳያደርገን ለማድረግ ገና ብዙ እንደሚቀረን እረዳለሁና ።

የሃይማኖታዊ እምነቶቻችን ምንነት፣ ለምንነትና ለማንነት ፣ እንዴትነት እና ወዴትነት ሊያሳስበን የሚገባውም ከዚሁ መሠረታዊ እሳቤ አንፃር ነው የሚል ፅዕኑ እምነት አለኝ።

ከፈጣሪ እገዛ ጋር ከዘመን ጠገቡና ከአስከፊው ውድቀታችን ተምረን ለሁላችንምና ለሁሉም አይነት ነፃነትና እኩልነት የምትመች ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያንና አኩሪ የሆነ እኛነነትን እውን እንደምናደርግ እየተመኝሁ አበቃሁ!

 

 

3 Comments

  1. መከራህን በላህ ኦርቶዶክሳውያን ከሀገር ውጭ ቤተ ክርስቲያን አቁመው አምላካቸውን ማምለካቸው የእግር እሳት ሁኖብሀል። ደጋግግመህ አልከው አልከው ጥልህ ኦርቶዶክስ ላይ ነው ይህንን ያሳልጣል ያልከው እሸቱም ዋናው ፍንትው የተወረወረበት የህዝብ ልጅ ነው ። ወዳጄ ነብስህን አታስጨንቃት እረፍት ውሰድ ቀና ቀናውን አስብ ለጤንነትህም መልካም አይሆንም እንዲህ የችግር አረንቋ ውስጥ ሰጥመን ዘወትር እረፍት የነሳህ የቤተ ክርስቲያን መገንባት ከሆነ ተልእኮህ ሌላ ነው ማለት ነው። መንፈሳዊና ስጋዊ እረፍት ይስጥህ ከማለት ውጭ ምን ይባላል።

  2. በቅድሚያ የምታምንበትን/ኝበትን ጉዳይ መግለፅህ/ሽ እና በአስተያየቴም ላይ በገባህ/ሽ መጠንና ችሎታ አስተያየት በመስጠትህ/ሽ አመስጋኝ እንጅ አካኪ ዘራፍ ባይ አይደለሁምና አመሰግናለሁ።
    የዚህ ምላሼ ዓላማ አላስፈላጊ እሰጥ አገባ ለመጋበዝ ሳይሆን ይበልጥ ግልፅ ለመሆን ስለመሆኑ ግልፅ ይሁንልኝ።
    1) የምንነጋገረው የጋራ የሆነው እና እጅግ አስከፊና አስፈሪ እየሆነ የመጣው አገራዊ እውነታ (የወገን መከራና ስቃይ) ከሁሉም ሃላፊነታችን ፣ግዴታችንና ሥራችን መቅደም አይኖርበትም ወይ? እውነተኛው ፈጣሪ የምናስብበት ረቂቅ አእምሮ እና የምናከናውንበት ብቁ አካል የሰጠን እንደዚህ እያሰብንና እያደረግን የእርሱን ድጋፍና በረከት እንድንጠይቅ አይደለም ወይ? እንኳንስ እኛ የደመ ነፍስ እንስሳትም በዚያው የደመ ነፍስ ስጦታቸው የሚሰጡት የቅድሚያ ቅድሚያ ይኖራቸው የለም እንዴ? ሊገድላቸው ወይም ሊያሳድዳቸው የሚሄድባቸውን ሰው ወይም ሌላ አውሬ መምጣቱን ሲያዩ ርቧቸው እየበሉት የነበረውን ነገር ትተው ቅድሚያ ለመሸሽና በህይወት ለመቆየት ይሸሹ የለም እንዴ? የሚል እንጅ እንኳንስ ቤተ እምነት ሌላም የቅንጦት (ከታደልን) አገልግሎት ሰጭ ተቋማት አያስፈልግም የሚል በፍፁም እንዳልሆነ ለመግባባት ካልቻልን አስቸጋሪ ነው ።
    2) “ውጭ አገር ያሉ ኦርቶዶክሶች ቤተ ክርስቲያን አቁመው አምላካቸውን እንዳያመልኩ እሳት ሆነብህ ” የምትይው/የምትለው በፅሑፌ ላይ ያልኩትንና ከላይ (ቁጥር 1) ግልፅ ያደረኩትን ወይ ካለመረዳት ወይም ካለመፈለግ ወይም ከስሜታዊነት (ከየዋህነት) የሚነሳ ካልሆነ በስተቀር እንኳንስ ተከታይ የሆንኩበት ታላቅ ሃይማኖት በህዝብና በአገር ላይ የሚያስከትለው ጉዳት እስከሌለ ድረስ ወይም የህዝብን ስቃይና መከራ ወደ ኋላው አስቀምጦ ለፅድቅ ይሆነኛል የሚል ከንቱ ውዳሴ እስካልሆነ ድረስ የየትኛውም ሃይማኖት ቤተ እምነት በዓለም ቢስፋፋ ከቶ የሚከፋኝ ሰው አይደለሁም። እንኳንስ እሳት ሊሆንብኝ። ይህ አይነት ደምሳሳ የሆነና ከግልብ ስሜት የሚነሳ የሃሳብ ልውውጥ ጨርሶ አይጠቅመንም!
    3)”ጥልህ ከኦርቶዶክስ ጋር ነው” ለሚለው ሁሉንም ነገር ለሚያውቀውና “እውነቱን እውነት እና ሃሰቱን ሃሰት” በሉ የሚለው እርሱ እውነተኛው አምላክ ስለሚያውቅ ለእርሱው እተወዋለሁ። እውነተኛው አምላክ በፖለቲካ ወለድ ጨካኝ ሰይፍ ደሙ የሚፈሰውንና የደም እንባ የሚያነባውን አያሌ ሚሊዮን ወገን ከሁሉም በፊት እንድንታደገው ፈቃዱ ብቻም ሳይሆን የአማኘነት ግዴታ ጥሎብናልና ይህንኑ ሆነንና አድርገን እንገኝ ማለት እንዴት የኦርቶዶክስ ጥላቻ እንደሚሆን አላውቅም።
    4) “በእሸቱ ላይ ፍላፃው … ” ለሚለው አሁንም “ለምን እሸቱ ይተቻል” ከሚልና እጅግ እንጭጭ (immature) ከሆነ እሳቤ የሚነሳ ካልሆነ በስተቀር እሸቱ የህዝብ ልጅ የሚያሰኘው ሥራ ፈፅሞ አልሠራምና የህዝብ ልጅም አይደለም የሚል ሃሳብ ፈፅሞ አልወጣኝም። ያልኩትና አሁንም የምለው በፖለቲካ ወለድ ወንጀል እና በሃይማኖት መሪዎች እጅግ አሳሳቢና ልፍስፍስ አቋምና ቁመና ምክንያት አያሌ ሚሊዮኖች የገዛ ሰፈራቸውና አገራቸው ምድረ ሲኦል ሆነውባቸው የወገንና የሃይማኖት አባት ያለህ በሚሉበት በዚህ እጅግ አስጨናቂና አስተዛዛቢ ወቅት ምንም እንዳልሆነ በሚያስመስል የመድረክ (የማህበራዊ ሚዲያ) ዘመቻ ላይ መጠመድና ለባህር ማዶ ቤ/ክርስትያን ወይም ገዳም መሥሪያና ማሠሪያ “ሚሊዮኖች ዶላር ስጡንና የገነትን ቁልፍ ውሰዱ” ማለት እንኳንስ እውነተኛው አምላክ ሚዛናዊ ወይም ጤናማ ህሊና ያለው ሰውም አሜን ብሎ የሚቀበለው አይደለም ነው።
    5) “እረፍት ውሰድ፣ ነፍስህን አታስጨንቅ፣ ቀና ቀናውን አስብ” ለሚለው አገርና ህዝብ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ አጥቃላይ ቀውስና ውርደት ውስጥ ናቸውና ከምንም በላይ የቅድሚያ ቅድሚያ ሰጥተን ተስፋ የምናደርገውን ከሞት በኋላ ህይወት እንውረስ፣ የፈጣሪ መቅድሶች የሆኑ የአያሌ ሚሊዮን ንፁሃን ህይወቶች (ወገኖች) እንዳልነበሩ እየተደረጉ ባሉበት እጅግ ግዙፍና መሪር ሁኔታ ውስጥ ጊዜ ሊሰጠው የሚገባውን የቤተ እምነት ህንፃ “አሁንኑ ካልገነባነው መንግሥተ ሰማያት ሊያመልጠን ነው” በሚል አይነት ዘመቻ ተውኔት መጠመድ ትክክል አይደለም ማለት ረፍት የማይሰጥና ቀናም ነገር ካልሆነ ሌላ ምን? ምነው በስሜት መጋለቡን በቅጡ ብናደርገው ምናለበት? የፈጣሪን ቃል (የታላቁን መጽሐፍ) ጨምረን ዘቅዝቀን እያነበብን የት ነው የምንደርሰው?
    6) “ከአጠገብህ ያለውን/ችውን ወንድምህን/እህትህን በእውን ካላፈቀርክ እኔን እንዴት ለማፍቀር ይቻልሃል/ይቻልሻል ” ተብሎ ተነግሮናል እያልን አይደል እንዴ የምንሰብከው? ታዲያ አገራችን ውስጥ የሆነውና እየሆነ ያለው አጠቃላይና ሁለንተናዊ መከራና ውርደት ይህንን ጥያቄ ከሁሉም በፊት ቅድሚያ ትከኩረት ሰጥተን ተገቢውን ምላሽ እንድንሰጥ ካላስገደደን ስለ የትኛው እውነተኛ አማኝነት ነው የምናወራው? ይህንን በግልፅና በቀጥታ ከመግለፅና ከመናገር የበለጠ ሌላ ምን ቀናነት አለና ነው ቀና ቀናውን ያሳስብህ የምትይው/የምትለው ወዳጄ???
    የገዛ ራሳችንን ግዙፉና መሪር እውነት በግልፅና በቀጥታ ከመግለፅና ከመተቸት የበለጠ ምን አይነት የህሊና ረፍት እንደሚኖር ለመረዳት አያስቸግርም?
    ከመሪሩ እውነታ በመሸሽ የሚደልብ (የሚደነድን) ሥጋ እና ሃሴት የሚያደርግ ነፍስ የትክክለኛ ሰብእና ባህሪያት አይደሉም እኮ! ትክክለኛው ሰብአዊ ባህሪ ለመከረኛው ወገን የሚገደውና ለዚህም ረፍቱን ሰውቶ የሚችለው የሚያደርግ በመሆኑና ይህም የጤንነት እንጅ የጤና ጉድለት ፈፅሞ እንዳልሆነ በሚገባ እረዳለሁና የሃሳብ ልውውጦቻችንና የትችቶቻችን አስቸጋሪነት አይገርመኝም። ለምረዳ ፈፅሞ አያሳስበኝም። ይህ ማለት ግን በእጅጉ ሊያሳዝነንና ሊያሳስበን አይገባም ማለት አይደለም። እንዲያ ከሆነማ ፍኖተ የመፍትሄውን ፈልገን ማግኘት አይቻለንም።
    7) በመጨረሻም “ተልእኮህ ሌላ …” ለተባለው ያለኝ ምላሽ መሠረታዊ የመረዳት ችሎታ ያለኝ የኦርቶዶክስ ተከታይ ስለመሆኔ መማልና መገዘት የሚያስፈልገኝ አይመስለኝም። ተራ ተከታይነቴ ግን ትክክል ያልሆነውን በግልፅና በቀጥታ ትክክል አይደለም ለማለት የሚከለክለኝ ሊሆን አይገባም የሚል ፅዕኑ እምነት አለኝ። ይህ ደግሞ ማንም የሚለግሰው ወይም የሚነፍገው ሳይሆን ፈጣሪ ራሱ በሰብአዊ ፍጡርነት የሰጠንና የሚሰጠን መብት ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share