“ ድምፅና ቁንጫ ባዶ ቤት ይወዳል ። …” አዳም ሀይለአብ

ፕሮፊሰር መሥፍን እንዳሉት ” በዶ ቤት በቁንጫ ይወረራል ። ” እናም ሀገሬ ዛሬ በየትኛውም ተቋም ፤ በመንፈሳዊ ተቋማት  ጭምር ፤ ምሁራኑ በሰበብ አስባብ ተጠርገው እየወጡ ፣ አሰስ ገሰሱ የአገልግሎት መድረኩን ይዞ  መሪነትን የልጅ መጫውቻ ሲያደርገው እያሥተዋልን ነው ።

እስቲ ዓለማዊ ተቋማቱን ተመልከቱ ። በህግ አውጪው ፣ በህግ ተርጓሚው እና በህግ አሥፈፃሚው የመንግሥት ሥልጣን ተቋም ውሥጥ ያሉ ሰዎችን በአንክሮ አሥተውሉ ፣ 98%  ለሆዳቸው የተገዙ ፣ ከራሥ በላይ ነፋስ በማለት ” ጎመን በጤና ! ” በማለት የሚሞዝቁ አይደሉምን  ?

ህዝብ በየዕለቱ በሚያሻቅብ የዋጋ ንረት የተነሳ መኖር  እያቃተው ነው ። በጣም ጥቂቱ በቀን ሦሥቴ የሚበለው ወደ ሁለቴ መብላት ተንከባሏል ። ጥቂቱ  ሁለቴ ይበላ የነበረው ደሞ  አንዴ  መብላት ግዴታ ሆኖበታል ።  የዕለት ጉርሱን ለማግኘት ተቀጥሮ የሚሰራ እና በቀን ሥራ የተሰማራው የሚያገኘው ለቤት ኪራይም አልበቃውም ። “… ባገኝም በልቼ ባጣም ተደፍቼ …” በማለት በገሃድ በለቅሶ ሲያዜም ውሎ ሲያዜም ማደሩን ቀየቀበሌው ያለ ካድሬና አጫፋሪ ወይም አሥገፋፊ ያውቃል ። ከአጠቃላይ ህዝቡ  እጅግ በጣም ጥቂቱ ብቻ ነው  ፤ በአፓርታይድ ፓለቲካዊ  ሆያ ሆዬ እየዘረፈ ፣ ያለአግባብ ተጠቃሚ ሆኖ ያለፋበትን እየበላ በቁንጣን እየተቸገረ መኖሩን ዘወትር የምንመለከተው ።

አገሬ ፈፅሞ ኃላፊነት በማይሰማቸው በነዚህ እፍኝ  በማይሞሉ የፓለቲካ ፣ የኢኮኖሚ የማህበራዊ ኑሮ ፅንሥ ሃሳብ ያልሰረፀባቸው ፤  ሆዳቸው ጭንቅላታቸው በሆነ ሰዎች እየተመራች ወደ መፍረስ እየተቃረበች ነው ። ታላቋ አገር ታሪክ ለመሆን እየተደረደረች ነው ።

ይኽንን ድርዳሮት ዛሬ የተነቃቃው አዲሱ ትንታግ ትውልድ ( በመከላከያ ውስጥ ያለውን ይጨምራል ) እንደሚቀለብሰው ባምንም ያለመሰዋትነት ሠላምሟዴሞክራሲ፣ፍትህ፣ነፃነት እና እኩልነት እንደማይመጣ ግን እገነዘባለሁ ።

በምጣኔ ሀብት አገር እየደቀቀች ፤ ዜጎች “ አገራቸው አገራችሁ አይደለችም “ እየተባሉ ከቀያቸው ሲባረሩ ፤ ሰውነታቸው ተዘንግቷ በቋንቋቸው ሲገደሉ ፤ የአፓርታይድ ሥርዓታችን ማን እንደሚኖርበት ና እንደሚዝናናበት የማይታወቅ የቅንጦት መዝናኛ ይገነባል ። ቤተ መንግሥትም  በትሪሊዮን ብር ልሥራ ነው ብሎ በማንአለብኝነት ይነሳል ።

ዜግነት በዲንጋይ ራሥ ፓለቲከኞች ተክዶ በነፃ አውጪ ሥም አጋንንቶች በማህል አገር ተሠማርተው በጠራራ ፀሐይ ሰው የሚረሽኑበት ፣ የሚያርዱበት ምቹ ሁኔታ ከእውቀት በፀዳው  መንግሥት ተመቻችቶላቸው ሣለ እና ህዝብ ጎመን አሮበት በረሃብ እየተሰቃየ ሣለ ፣ አምባገነኖቹ ፣ ህዳሙን የፓርላማ አባልና ሚኒስትር በሥጋ ምቾት ጠፍረው  በቅንጦት ቤተ መንግሥት ግንባታ ላይ ለመሠማራት ዳር ሯ ዳር እያሉ ነው ። ይኽ ድርጊት የሚያሳየን  አእምሮ ቢሥነት ብቻ አዬደለም ፣ ማን አለብኝነትን እና  የህዝብ ንቀትን ነው ። ህውብ ተንቋልም ተዋርዷልም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ትንሽ ሰዓት በመቃብር ስፍራ - መስከረም አበራ

እግዜር ያሳያችሁ ፣ ወታደራዊ ተቋማቱ አንዳችም ሎጀስቲክ ሣይኖራቸው ፣ የተከበረው ወታደር ህይወቱን ለህዝብ ለመሳዋት በሲኖ ትራክና በአይሱዙ እንደ እቃ እየተጫነ እያየን ፣ ህዝብን ካልናቁ እንዴት በቀን አንድ ጊዜ ህዝብን  ማብላት  ያቃተው መንግሥት ፣   በዘጠኝ ቢሊዮን ብር ቤተ መንግሥት ለመሥራት ተነስቻለሁ ብሎ ይለፍፋል ። ይኼ ያለማፈር ነው ። የሚኒሥቴሮች ምክር ቤት እንደሌለ እንቁጠረውና    ? ፓርላማው ( የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ) እንዴት ዝም ብሎ በህግ ያልተደገፈ ተግባሩን ይመለከታል  ? ( ጠቅላዩ እናንተን አይመለከትም ለምኜ ነው ፣ ያገኘሁት እያሉ ሲናገሩ ፣ የመለመን ፈቃድ ማነው የሰጣቸው ? ህገ መንግሥቱ ላይ የፀደቀ የልመና ህግ አለን እንዴ ? ጠቅላዩ ራሳቸውን ንጉሥ ካላደረጉ በሥተቀር ፓርላማው ሳይፈቅድላቸው  ህግ ፣ መመሪያና ደንብ ሳያግዛቸው በአምባገነንነት በኢትዮጵያዊያን ምድር እንደአሻቸው ከህግ ውጪ የመጋለብ መብት የላቸውም ። )

በገልባጭ “ ሲኖ ትራክ “ እና በጭነት  አይሱዙ  የሚጓጓዙ ፣ በቂ አልባሳትና ሥንቅ የሌላቸው የመከላከያና የፖሊስ  አባላት እያሉን ፣ “ በ9 ቢሊዮን ዶላር የፊደራል መንግሥት ቤተ መንግሥት እሠራለሁ ። “ ማለት እብደት አይገልፀውም  ። ከዚህ አንፃር “ ቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ከዛሬው የኢትዮጵያ ጠ/ሚ ወይም “ ራሱን ንጉሥ ካደረገው “  ከአብይ አህመድ የባሰ ግፍ በወታደሩ ላይ አልፈፀሙም ማለት ይቻላል ። “ ብለን ብንናገር ሐሰት የሚል አንድም ሰው በዓለም አይገኝም  ። ንጉሥ ቀዳማዊ ግርማዊ ጃንሆይ  “ በሥንቅ ፣ በትጥቅ ፣ በሎጀሥቲክ ወታደሩን አልበደሉም ። ወታደሩን እንደ ዕቃ በሲኖ ትራክ እና በአይሱዙ አልጫኑም ። በደረቅ ኮሾሮ ለቀናት አላስራቡም ።   የተጋነነ ኢ ሰብዓዊነት በአገዛዛቸው የታየው በሥልጣናቸው ለመጡባቸው ብቻ ነበር ። “  አቶ ሽመልሥም ቢሆን የኦሮሞ ህዝብ በችጋር ውሥጥ እያለ ፣ በመጠጥ ውሃ ችግር ጉሮሮው እየተቃጠለ እና ከእንሥሣ ጋር እየጠጣ ፣ የ3 ቢሊዮን ቤተ መንግሥት ለመገንባት መነሳታቸው ፣  ማንን  ለማሥደሠት አስበው ነው ? በውስጡ የመኖር ህልም ያላቸው ከቶ እነማን ናቸው ?

አቶ ሽመልሰሰ  ለመሆኑ “ ሚዶ ለመላጣ ምን ይሰራለታል ? “ ብለው ነው ?

ሃቁ ሁለቱም ህዝብ አገልግሉን ያላቸው መሪዎች  ፣ ከህዝብ አሁናዊ ፍላጎትና ዘላቂ  ጥቅም አንፃር ሣይሆን ከውጪ ሀብታሞች የወደ ፊት ህልም አንፃር ነው ቤተመንግሥት ለመገንባት ያቀዱት ። ቤተመንግሥታቸው በዛሬው የአፓርታይድ ሥርዓት እውን ከሆነ ግን  ” የአውሬ መፈንጫ ” ይሆናል እንጂ ወደፊት ሰው ሊኖርበት አይችልም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወገኔ ይጮሃል !

በበኩሌ ወታደሩ ሮቦት ካልሆነ በሥተቀር የአብይንም ሆነ የሽመልስን የእብድ ፕሮጀክት እውን እንዲሆን አይፈቅድም ። በሠላም ጊዜ ፣ የተሟላ መቀመጫ የሌለው ።… በቂ ማደሪያ ቤት ንፁህ አንሶላና ፍራሽ ይቅርና ፣ ምግብ ፣ መጠለያ ና ልብስ በወቅቱ የማያገኘው መከላከያ በተቀደደ ዩኒፎርም አገርን እያገለገለና ፤ እየተራበና እየተጠማ ፣ በሲኖትራክ እየተጫነ ፣ ይህንን የዕብድ ሥራ በዝምታ በማለፍ ቢሊዮን ዶላሮችን እነአብይ ሲያቃጥሉ ዝም ብሎ ያያቸዋል ብዬም አላሥብም  ። መቼም አገር በቁንጫና በትሆን መወረሯን የሚያጣው አይመሥለኝም ።

ሌላው የዚች አገርን በቁንጫ እና በትሆነ  መወረር የሚያሣዩን የእምነት ተቋማት ናቸው ። በተለይም ዛሬ የኦርቶዶክስ ኃይማኖት በአንዳንድ  ፃድቅ ፣ ብፁዕ በተሰኙ በተግባር ግን የዳቢሎስ ልጅ በሆኑ ፣ በዓለማዊ ሥልጣን ጥም በናወዙ ፣ እግዚብሔርን በካዱ ዘረኞች ክብሯ እየተደፈረ ብቻ ሣይሆን ዓለማዊ እንድትሆን እየተገደደች ነው ።

እነዚህ ጳጳስ ነን ፣ ሥልጣነ ፈጣሪ አለን የሚሉ ሆኖም ግን በሥልጣነ ዳቢሎስ የሚመሩ ዘረኞች የሰውን በዘፍጥረት አንድነት በመካድ በጎሳው ከፋፍለው ገንዘብ መሰብሰቢያ ሊያደርጉት ቆርጠው ተነሥተዋል ። በትግራይም ፣ ኦሮሚያ በተባለው ክልልም ።

የትግራዮቹ እሥከ አሜሪካ ድረሥ ጳጳስ እንሾማለን ብለዋል ። የኦሮሚያዎቹ ደግሞ እሥከ ደቡብ የኦርቶዶክስ አገረሥብከት ጳጳሳትን  ለመሾም አሥበዋል ።

እኔም እላለሁ ፣”  እውነተኞቹ ለእግዚአብሔር የተገዙ የኦርቶዶክስ ኃይማኖት ልጆች ፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቅዱስ ፓትርያርክ እውቅና ባልተሰጣቸው ጳጳሶች በሚመሩ ቤተክርስቲያናት ውስጥ  እግራቸው ለመግባት እንደሚጠየፍ ይወቁት ። “ ይኼ  ከወዲሁ ሊነገራቸው  ይገባል ። ምእመናኑ የሤጣን መሥቀል የሚሳለምበት አንዳችም ግዴታ የለበትም ።

በዛሬው ዓለም ሴጣን ዘመናዊ ሆኖ መምጣቱንም በዚህ አጋጣሚ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ልጆች ሁሉ ተገንዘቡ ። በዚህቺ ምድር  የምትኖሩት አንዴ እንጂ ሁለቴ አይደለም ። ለፈጣሪ ታምነን ለመሞት እና የድል አክሊል ለመጎናፀፍ እንነሣ !!

አብይም ሆነ ሽመልስ ሰዎች ናቸው ። ትላንት ህፃን ነበሩ ። እድገታቸውም እንደብዙዎቻችን ደሃ ኢትዮጵያዊያን መሆኑ ይታወቃል   ። ከሰማይ የወረዱ መልዕክት አይደሉም ።    የመንግሥት ሥልጣን ላይ በአጋጣሚ … ሥለወጣ ማንም መለኮታዊ ኃይልን አይጎናፀፍም ። ዘላለማዊ ህይወትም የለውም ። ፈረሽ ገላ ተሸክሞ የሚዞር ነው ። ሞት አይቀርለትም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአንባ ገነን የስልጣን ጥም አባዜ (ገዛኸኝ አበበ ከኖርዌይ)

“ከቶ  አይቀርም ሞቱ ፣ ምንም ቢታክቱ ፣ ምን ቢሰነብቱ ! … “ ከመሞታቸው አስቀድሞ ግን አሁን እንደሚያደርጉት ፣ ጥቂት  ለሆዳቸው ያደሩ ፤ እንደ ቀኃሥ የአገዛዝ ዘመን አይነት “ ባሮች “ ከጎናቸው አሠልፈው አብይና ሽመልሥ ሊመፃደቁ ይችላሉ ። ነገ እነዚሁ  ባሮች መጠቀሚያነታቸውን ያወቁ ጊዜ ግን አፈሙዙን ወደ እነሱ እንደሚያዞሩ አልጠራጠርም ። በትግራይም እንዲሁ ነው የሚሆነው ። የአፍሪካ “ ማን ከማን ያንሣል ? “ ጫዎታ በኢትዮጵያም ይጀመራል ። ዛሬ ጨዋውን የትግራይ ሰው ፕሬዝዳንት ሆኖ  እየመራ ያለው ማን ነው ? በእምነትስ እንደትግራዋይ ያለ ኩሩ ነበር እንዴ ? ዛሬ ፈጣሪን ክዶ ካድሬ የሆነ ጳጳስና ቄስ ምን ይባላል ? ይኽ ለትግራይ ህዝብ ሞት ነው ። ከእምነት ታሪክ አንፃር ፣ ፈጣሪውን ዘግይቶ  ካወቀው ይልቅ ፣ የቁጣ እሣት  የሚዘንበው በትግራይ ህዝብ ላይ መሆኑን መገንዘብ መልካም ነው ።

በበኩሌ እጅግ የማዝነው “ ጊዜ የሰጠው ቅል ዲንጋይን ሲስብር “ በማየቴ ብቻ ሣይሆን ኃቀኛ የሆነ ፣ ምሁር ፣ ጥበበኛ ና አዋቂ ከኢትዮጵያ ተቋማት ቁልፍ ቦታ ሁሉ ድርሽ እንዳይል ተደርጎ ፣ ቤቱን ማሥተዳደር የማይችል ግብዝ ሁሉ ከቀበሌ ጀምሮ በመንግሥት ሥልጣን ላይ ተቀምጦ ፣ ዘወትር ለከርሱ ብቻ በማሠብ ደሃን ሲበድል ፣ሲዘርፍ ፣ ሲያሥለቅስ ና ሲገድል በማየቴ ነው ። ኢትዮጵያ በዚህ አምሥት ዓመት ብቻ 40 ዓመት ወደ ኋላ ሄዳለች ። ከሞራል አንፃር ደግሞ ከደርግም ከወያኔም የባሱ ጥቂት እፍረተ ቢሥ አመራሮችን አፍርታ ወደፊት አምጥታለች ።  ይኽንን ግን በሚሊዮን የሚቆጠረው ጨዋና ኩሩው ወጣት ኢትዮጵያዊ ! በቃ ! ሊለው ይገባል ።

እውነት ነው ፣ ” በዶ ቤት የቁንጫ መራቢያ ነው ። ” ደሞም በበገና ዝማሬ   ድምፅና ቁንጫ ባዶቤት ይወዳል ፤ ያትልቅ ወንበርም በትሆን ተሞልቷል ። ” ተብሎ ሲዜም ሰምተናል  ። እናም ቤታችንን ከቁንጫና ከትሆን ለማፅዳት ሳይረፍድብን መነሳት አለብን !!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share