″ሰው ፓርቲ ″ እናቋቁምና የዘር ፖለቲካን እንቀበረው – ሲና ዘ ሙሴ

በብልፅግና  ሥም  በአምባገነንነት ጥቂቶችን በማበልፀግ ፣ በመላው ኢትዮጵያ  ድህነትን  እያስፋፋ  ያለውን  ገዢውን  ፓርቲ ፣ በጠብ መንጃ ሳይሆን፣ በምርጫ ፣  ለማሶገድ ፣  ፖለቲካ ሣይንስ መሆኑን በቅጡ የሚያውቅ  አዲስ  አሥተሳሰብ  ያለው ፓርቲ ወይም ህሊና ያላቸው ሰዎች የሚመሩት የሰው ስብስብ ፓርቲ   ያሥፈልገናል  ″

 ሲና    ሙሴ

″ ሰው ፓርቲ ″ ( human party ) የተሰኘ የአገሬን ዜጋ ሁሉ ያለ ልዩነት የሚያሳትፍ ፓርቲ ለመመስረት እፈልጋለሁ ። ልብ በሉ ፍላጎቴን እየተናገርኩ ነው ። አንዳችም እንቅሥቃሤ አላደረኩም ። ላድርግም ብል አልችልም ። አቅም የለኝም ። ሆኖም ሃሳብ አለኝ ። እጅግ ጠቃሚ ሃሳብ ።

ይኽንን ጠቃሚ ሃሳቤን ዛሬ ለአገሬ ካላቀረብኩ እና ከጥፋት እንድትድን የራሴን አስተዋፆ ካላደረኩላት ልጇ ነኝ ማለት እንዴት እችላለሁ ?  ዛሬ እኮ ፣ አገሬ እየሞተች ነው ። መሪዎቿ ለውጪ አገር ሀብታሞች  መዝናኛ እና ሲወጡ ሲገቡ ለሚያዩት አርቴፊሻል ውበት እንጂ ለሰው ውበት  ደንታ ቢስ ሆነዋል ። በመሆኑም ብዙ ውብ ወጣቶች በከንቱ እየረገፉ ነው ። በጅል ፣ በጅለአንፎ ና በቂል ፊትአውራሪነት  በሚመራ የወንድማማች ጦርነት ።

በሚያናድድና በሚያስቆጭ ሁኔታ  እቺ አገር ለሥልጣናቸው ዘላለማዊነት እንጂ ፣ ለወንድማማቾች ደንታ በሌላቸው ፤     ህሊናቸው በሱስ በደነዘዘ ጥቂት ማስተዋል ባልፈጠረባቸው  ሰዎች በኃይል ተገፍታ ገደል አፋፍ ደርሳለች ። ትቂት ፣ ሆዳሙና ህሊና ቢሱ የብልፅግና ቁንጮ አመራሮች እንደቀድሞው ኢህአዴግ 60 ዓመት በነበረ ያረጀ ና ያፈጀ የጨቋኝ ተጨቋኝ ትርክት እያሳበቡ ፣  በቋንቋ ፖለቲካ ካልገዛው ሞቼ እገኛለሁ በማለት ጥቂት ዘራፊዎችን በማፍራት ላይ ተጠምደዋል ። አገሪቱን በጎሳና በመንደር እንድትከፋፈል መንገድ እየጠረጉ ነው ። በተግባር ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊያንን እየገደሉ ነው ።

ከዚህ ሰውን በረሳ እና ከቀደመው ኢህአዴግ ባህሪ ያልተሻለ ″ ስመ ብልጽግና ″  እና በሠለጠኑት መንግሥታት ዘንድ ″  እንደ ተነጂ ″  ከሚቆጠር አገዛዝ አገሬን ነፃ የሚያወጣት አንድ ሁሉን አቀፍ “ሰው ” የተሰኘ ፓርቲ መመሥረት ያሥፈልጋል ።እናም በሰው ና ለሰው የተፈጠረ   ታላቅ የፓለቲካ ተቋም በአገሬ ለመገንባት የኢትዮጵያ ሰዎች በህብረት ትነሱ ዘንድ ጥሪዬን አቀርባለሁ ።

ይኽንን ታላቅ እና ከዘመናት በፊት ለእኛ የተሰጠ ሰው የተሰኘ ታላቅ ሥምን ፓርቲ አድርጎ በመላው ኢትዮጵያ ለመንቀሳቀስ ደግሞ  የአገሬ ምሁራን እና ባለሀብቶች በንቃት ለማገዝ ቁርጠኛ ሁኑ ። አሁን ያሉትም ፓርቲዎች ወደፊት “ የኢትዮጵያ  ሰው ዴሞክራሲ ና ህብረተሰባዊ ፓርቲ “ በሚባለው ፣ ፓርቲ ሥር  እንዲደራጁ ማድረግም ሌላው የቤት ሥራ ሊሆን ይገባል ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያልተገታ ምላስ አማራውን ይጎዳዋል አክሎግ ቢራራ (ዶር)

አሁን እና ዛሬ የቋንቋ ፓለቲካን አለቅም ብሎ ፣ ቋንቋን እንደዘር መገለጫ በማድረግ በቋንቋ ከፋፍሎ አገርን ለጥቂት ፓለቲከኞች በወርቅ ሰሐን በመሥጠት በገዛ ላብና ደማቸው ጥረው ግረው እስከጊዜው የሚኖሩትን ዜጎች የሚያባላውን ና ጥቂቶችን   እያበለጸገ ያለውን የአንድሰው አበገነንነት የሚፀባረቅበትን  መንግሥት ከኢትዮጵያዊው ሰው ጫንቃ በህጋዊ ምርጫ አሽቀንጥሮ ለመጣልም ይኽ ፓርቲ በአሥቸኳይ መቋቋም አለበት ።

ይኽ ወደፊት ሊቋቋም የሚችለው  ” ሰው ፓርቲ ወይም Human party “  ሁሉን ዜጋ አቃፊ በመሆኑ ከዝንት ዓለም ንትርክ ዜጎችን ይገላግላቸዋል ። ሰው መሆናቸውን በማሳወቅ ። ሁሉም ኢትዮጵዊ ሰው መሆኑንን አውቆ ፣   ለፓርቲው ደጋፍ ያደርግለታል ።  ይኽንን በሰዎች እና ለሰዎች የሚቋቋም ፓርቲን እውን ለማድረግም አያሌ ምሁራን እና የፖለቲካ ሊቃውንት በቅንነት  ይሳተፋሉ ብቻ ሳይሆን ከልባቸው እንደሚጥሩ  አምናለሁ ይኽ ሰው  የተሰኘ  ፓርቲ ፣ የራሱ ፕሮግራም ፣ የተለያዩ ዕቅዶቹና አገርን በተመለከተ የሚያወጣቸው ፖሊሲዎች ይኖሩታል ። እነሱም  ወደፊት በአባላቱ ተሳትፎ  የሚዘጋጁና ለህዝብ ይፋ የሚሆኑ ይሆናሉ ።

በታላላቅ የፖለቲካ ሊቃውንት እና የተለያዩ ምሁራን ታግዞ ፤   በጥልቅ ጥናት እና ምርምር ላይ ተመሥርቶ ፤ የሚዘጋጀው  ለአገር የሚበጅ ሰነድም ከአሜሪካ ህገመንግሥት እኩል የኢትዮጵያ ዜጎች የሚኮሩበት እና የሚመኩበት የፖለቲካ ሀሁ ሰነድ ይሆናል ። የዚህ ፓርቲ ርዕዮትም   በመላው ዓለም  ቅቡልነት  ካላው ርዕዮት ጋር አንድ አይነት የሆነ ፣ የጠራና አንዳችም ብዥታ የማይፈጥር ህኖ ይዘጋጃል ። በአጭር ጊዜ በዓለም ላይ እጅግ ቅቡልነት ያለው በመሆንም ለጠቅላላው አፍሪካ ሁሉ እንደምሣሌ የሚቆጠር በመሆኑ ፤  ዜጎችን በማንቃት “ሀ” ብለው ህይወትን እንዲያጣጥሙ ሥለ ኑሮ እንዲረዱ ያደርጋቸዋል ።

ይኽ ፓርቲ ኢትዮጵያዊያን ፓለቲካዊ ሥልጣንን ለመጨበጥ የግድ ዘረኛ  ወይም ቋንቋኛ መሆን እንደማያስፈልጋቸው በዕውቀት ላይ የተመሠረተ ትምህርት ይሰጣል ። የፓርቲው ዓባላት ህዝብን ወክለው   ሥልጣንን ለመጨበጥ  የሚፈልጉትም ለአጠቃላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ” ለሰው ” ሠላም፣ ፍትህ፣ነፃነት፣እኩልነት ፣ዴሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብት መከበር እንጂ ለግል ጥቅማቸው እንዳልሆነ በተግባር ያሳያሉ ። በኢትዮጵያ እየተዛባ ያለው የሀብት ክፍፍል   ፍትሃዊ እንዲሆን እንጂ መደመር እያሉ እየቀነሱ ለራሳቸው እና ለዘመዶቻቸው ሀብት ለማካበት የሚሯሯጡ ሰዎች በሰው ፓርቲ ውሥጥ  ቦታ እንደማይኖራቸውም በተግባር ያሳያል ። አምልኮተ ሰው እንዲፈጠር በፍፁም አያደርግም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አማራው በዐይጧ የጨከነለት … ብሥራት ደረሰ

” ሰው ፓርቲ ” የተለያዩ የማንቂያና የማስተማሪያ መንገዶችን ተደራሽ በሆነ መልኩ አዘጋጅቶ በማቅረብ ” ለካ እንዲህ ነን ። ” ብሎ ሰው እንዲያስብ በማድረግ ዛሬ ካለንበት ኢ ምክንያታዊ መገዳደል ነፃ ያደርገናል ። የግለሰብ አምልኮትንም ያስቀርልናል ።

የሰው ፓርቲ የሰውን መገዳደል ለማሥቆም የሚያሥችሉ ተከታታይ ትምህርቶች ፣ በተለያዩ የሚዲያ አውታሮች ይሰጣል ። ሥለ ፖለቲካ ሥለ ኃይማኖት፣ሥለቋንቋ ጅማሮ በሰ ውና በጥልቀት  ያሥተምራል ።

የአገሬ ሰው ሥለ ሰው  ፣ ሥለ ቋንቋ፣ሥለ ኃይማኖት አፈጣጠር ከሳይንስና ከእምነት አንፃር በሚገባ ካላወቀ በምክንያታዊነት ህይወትን መኖር አይችልም ። እናም ያሉን ውስን ምሁራን ዕውቀታቸውን ለመላው ህዝብ የሚያካፍሉበትን መድረክ ይፈጥራል ።

ፖለቲካም ሣይንሥ መህኑንን ተገንዝቦ ፣ መንግሥትን የመምረጥና የመሻር መብት ህዝብ እንዳለው በመገንዘብ የሚያገለግለውን ይመርጥ ዘንድ የማንቃት ሥራዎችን ህዝቡ ውሥጥ ገብቶ ይሰራል ።

ይኽ ብቻ አይደለም የዳርዊንን ቲዎሪ በአንድ ወገን  ኃይማኖታዊ ታሪክን  በሌላ ወገን በንፅፅር አሥቀምጦ በጨዋነት በማከራከር ለኢትዮጵያ ሰው   ዕውቀትን በምክንያታዊነት እንዲገነዘብ  ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል  ።

ይኽንን እና ሌሎች ጥበቦችን ለመዝራት እና የሰው ህሊና እንዲበለፅግ የሚተጋውን “ ሰው ፓርቲ “ እውን እንዲሆን የአገሬ ሰው ዛሬውኑ ተንቀሳቀስ ። ዛሬ ለዚህ ፓርቲ እውን መሆን ካልተቀሳቀስክ ነገ አገር አልባ ትሆናለህ ።

” ብልፅግና ፓርቲ ማለት በተግባር የድህነት ፓርቲ መሆኑንን አይተሃል ።  ሰውን አውድሞ እንዴት መበልፀግ እንደሚቻል ሊያሳይህ ሲባዝንም ታያለህ ።  ከኢህአዴግ ወደ ብልፅግና ከተቀየረ ማግሥት አንሥቶ የንፁሐን ደም አእምሮ በሌላቸው ፣ ሰውነታቸውን በካዱ ሰዎች  በከንቱ ሲፈስ ፤ ሲሰቃዩ፣ ሲጨፈጨፉ ፣ ሲቃጠሉ፣ ተ ቅዝቀው ሲሰቀሉ እያየ ገዳዮችን ለፍርድ ያላቀረበ ፤ የባስ ግድያው ክልላዊ እንዲሆን ያደረገ ። በትግራይ ወንድማማቾችን ያፋጀ ። ይኽንን በማድረጉ መፀፀቱን ሳይገልፅ ፤ የጦርነቱ ዋና አክተር ሆኖ ከአክተሮቹ ጋር ታርቀናል ያለ ።  ” ጦርነቱ ቲያትር ነበር ። “ ያለን  በትወራ ብቻ  ህዝብ መበልፀግ ይችላል ፤ ብሎ የሚያምን መሪ ያለው  የኢማጂኔሽን እና “ የባዛር “መንግሥት ነው ። “ ብልፅግና ! ( ፕሬዝዳንት ኢሣያሥ አፈወርቂ እንዳሉት ።)

ዛሬ በተግባር የብልፅግና ፓርቲ አገር እያፈረሰ ያለውም ከዚህ አሥተሳስብና ባህሪው የተነሳ ነው ። በተለይም ጠቅላዩ  ከዚህ በዛራዊነትና ኢማጅኒስትነት የተነሳ ፣ ሁሉንም ችግር በኢማጂኔሽን በማየትና ከነባራዊው እውነት በማፈንገጥ ፤  ድሮን እና ዙ 23  የኢትዮጵያን ውሥጣዊና ውጫዊ ችግሮች ይፈቱልኛል በሚል  አባዜ ውሥጥ ገብተው በማጥ ውሥጥ እየዳከሩ ነው ። ይኽም ድካሮ የክልል መሪዎቹን ሁሉ በማወናበድ ፣ እራሳቸውን ብቻ ሳይሆን አገሪቱን ወደ ገደል አፋፍ እያስጠጋት ነው ።

ሰውየው ፣ በአሰቃቂ ሁኔታ ጠፍተው አገርን ሊያጠፉ ከቀድሞ ቅኝ ገዢዎች ጋር የተማማሉ እሥኪመሥለን ድረስ የገዛ ወገናቸውን በግድ ለማሥገበር ወንድም ወንድሙን እንዲገድል ትዕዛዝ ሲሰጡ እያየን ነው ።  ይኽንን ሴጣናዊ  ትዕዛዝ ግን የመከላከያ መሪዎች አናሥፈፅምም ብለዋል ። ( የሳን ዙን የጦር ጥበብ በሚገባ የተረዱ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ሥላሉን እድለኞች ነን ። ) ለዚህ አሥተዋይነትና ታላቅነት  የከበረ ምሥጋና ይኽ ፀሐፊ ያቀርብላቸዋል ። ወደፊት የሚቋቋመው ” ሰው ፓርቲ ” የላቀ የሰብዓዊነት  የጀግንነት መዳሊያ ይሸልማቸዋል  ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አሁንስ ሊመጣ ላለው ዝግጁ ነን?። - ዳዊተ ዳባ።

ሰው ፓርቲ አማራ ፣ ኦርሞ ፣ ሱማሌ፣ ትግሬ ፣ ሲዳማ ወዘተ ። መባባል አገር በመመራት ደረጃ ይቅር ።  የኢትዮጵያ ሰው የሚኖርበትን አካባቢ እንደ ባህሉ፣ ወጉ ፣ቋንቋው እራሱ በሚመርጣቸው ተወካይቹ ያሥተዳድር ።

የገጠር ቀበሌዎች በነፃ ምርጫ  የራሳቸውን መሪዎች ይምረጡ ። የከተማ ቀበሌዎችም የራሳቸውን ከንቲባ ራሳቸው ይምረጡ ። እኛ እንጂ ህዝብ አያውቅም ይብቃ ። እኛ እንጂ የሚሉን እኮ ትላንት በኢማጂኔሽን መኪና እየነዱ ወደሱቅ የሚሄዱ ከተርታው ህዝብ መሐል የተገኙ ሰው እኮ ናቸው  ¡¡

ይኽንን ሃቅ በማሳወቅ ፣ ወደፊት  በጭፍን የመነዳት ፣ በመንጋ የመወገን ፣ በሥሜት ብቻ የመደገፍን የኋላቀሮች ፓለቲካን   የሰው ፓርቲ በማሥቀረት   ኢትዮጵያውያን አንድ ልብ እንዲኖራቸው እንደሚያስችል አስባለሁ ። ኢትዮጵያዊያን በሙሉ ፕሬዝዳንታቸውን በግልፅ ውድድር ፣ በምርመራ ጋዜጠኞች ጭመር በታገዘ የእጩ ፕሬዝዳንቶች ሥብዕና ምርመራ በውል አውቀው ለአራት ዓመት ብቻ እንዲያገለግላቸው ይመርጣሉ ። አንዴ የተመረጠ ለሁለተኛ ጊዜ ዕድል የሚያገኘው በአራት ዓመት የሰራው ሥራ ተመዝኖ ሲሆን በምርጫ ፉክክር ካሸነፈ ለተጨማሪ አራት ዓመት ፕሬዝዳንትነቱ ይራዘምለታል ።   ( በነገራችን ላይ ይኽ ፓርቲ ሥልጣን እንደያዘ ከጋዜጠኞች ጋር ተባብሮ የሚሰራ ና የመናገርን ተፈጥሯዊነት የሚያከብር ይሆናል ። አወራችሁ ፣ ተናገራችሁ ፣ ተሳደባችሁ በሚል  ተፈጥሮ አንደበትን ለመዝጋትም አይዳዳም ። አሁን ብልፅግና ተብየው በሁሉም ነገር የደኸየ ፓርቲ የሚፈፅመውን ከቶም አይደግምም ። )

እንግዲህ የዛሬውን  “ የበለው !ፍለጠው  ! ቁረጠውን  አገዛዝ ለማሶገድ , ብቸኛው አማራጭ ሰላማዊ ትግል ቢሆንም ፣ የአንዱን ጠባብ እና አውሬአዊ አሥተሳሰብ በሌላው ተመሳሳይ ጠባብነት እና ትምክህት  ለመተካት እንዳይሆንም የሰው ፓርቲ ይጠነቀቃል ። የሠለጠነ እና ሁሉም ሰዎች በእኩልነት የሚሳተፉበት እና “ የእኔ ነው ። “ የሚሉት  ፓርቲ በመሆንም የሰለጠነውን ዓለም ያስገርማል ።  የኢትዮጵያ ዜጎች ሁሉ ፣ በሰው ፓርቲ ዙሪያ ይሰባሰባሉ  ። የፓለቲካ ንቃታቸው ብቻ ሳይሆን ልባቸውን በተቻለ መጠን የሚመረምር መስፈርት አዘጋጅቶም ዓባላትን ይመለምላል ። ″ በሥነምግባር የኮሰመኑ እና በሆዱ የሚስብ የፓርቲው አባል አይሆኑም ። ″ የሚልና ሌሎች   ጠቃሚ ና ቅቡልነት ያላቸው መሥፈርቶች የአባልነት መመዘኛ ይሆናሉ ።

ይኸንን ″ ሰው የተሰኘ ና ለሰው ክብርና ልልና የሚተገል ፓርቲ ″  በውጪ አገር ያላችሁ በኣባልነት መቀላቀል ትችላላችሁ  ። መስፈርቶቹን ካሟላችሁ ። ይኽ ፀሐፊም መሥፈርቱን ካሞላ ብቻ ነው የሚሆነው ። በአገሬ ኢትዮጵያ ፣ እጅግ ምጡቅ እና ድንቅ  አእምሮ ያላቸው ዜጎች  ከፓለቲካ ጨዋታ ውጪ ናቸውና ወደ ጫወታው እንዲገቡ ና ይኽንን ፓርቲ በማቋቋም ሃሳቡን እውን እንዲያደርጉ በታላቅ አክብሮት እጠይቃለሁ ። ጠንካራ ፓርቲ ሳይኖረን ፣ በአምባገነንነት እና በአንድ ሰው ፈላጭ ቆራጭነት እየተመራ ፣ ድህነትን የሚያስፋፋውን ፣ ″ ግጭትና ጦርነት የሚጠምቀውን ″ ብልፅግና  የተሰኛ ፓርቲን  በምርጫ  ከቶም ልንቀይር  እንደማንችልም ከወዲሁ ብንገነዘብ መልካም ነው ።

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share