February 10, 2023
8 mins read

አራጅ ሆይ! ላንተም ቢሆን ኦርቶዶክስ ትሻልሃለች (ከአሁንገና ዓለማየሁ)

በተለይ ከኢንደስትሪያል አብዮት ወዲህ ሃይማኖት ማስፋፋት በቀጥታ የኢኮኖሚ ብዝበዛን ከማስፋፋት ጋር ተያያዥ እየሆነ መጥቷል። ለአህጉር ወረራ የተመቸ ወታደራዊ መሰል ተቋም ከነበራት የካቶሊክ ተጽእኖ ለካፒታሊዝማዊ ብዝበዛ ምቹ መደላድል ነው ወደ ተባለው ፕሮቴስታንቲዝም የተደረገው ሽግግር የኢኮኖሚ ሥርዐትን ታሳቢ ያደረገ ነበር። ግለኝነትን እና ዓለማዊነትን ብዙም የማይቃወመው በተለያየም መንገድ በነጻነት በየሰፈሩ ከማእከላዊነት ውጭ ሊቋቋምም የሚችለው የፕሮቴስታንት ሃይማኖት መዋቅር ኢንደስትሪያል አብዮቱ ለወለደው ከፍተኛ የሸቀጥ ማምረት፣ የሸቀጥ ማጠራቀምና የሸቀጥ ማራገፍ ግፊት ተስማሚ ሆኖ ተገኘ።

እንደ መልካም እድል ኢትዮጵያውያን የብዙ ግሩም ነገሮች ጅማሬ መሆናችን የታወቀ ሲሆን በተቃራኒው ደግሞ  እንደ  ክፉ እድል ሆኖ አንዳንድ ርእዮተ ዓለምና ዝንባሌ እኛ  ሀገር የሚደርሰው ከታኘከና ከተተፋ በኋላ ነው። ኮሚኒዝም የሩሲያን የዘውድ አገዛዝ አንኮታኩቶ፣ የሕዝቡንም ማንነት ድራሹን ካጠፋ በኋላ በሌሎችም ሀገራት ተመሳሳይ ውድቀት አስከትሎ ብዙ ማጣጣር በሚሰማበት ጊዜ እኛ ሀገር ገና የምሥራች ሆኖ ደረሰ። የብሔር ፌደራሊዝም እነ ዮጎዝላቪያን ማፍረሱ በተረጋገጠበት አመት ኢትዮጵያ ውስጥ እንኳን ደህና መጣህ ተባለ። መታወቂያ ላይ ብሔርን መጻፍ በሩዋንዳ ለጄኖሳይድ ማሳለጫ ውሎ ሚሊዮኖች ባለቁበት አመት ኢትዮጵያ ላይ በሥራ ዋለ። ይታያችሁ እነዚህ ሀገር ማፍረሻ መርዞች በሙከራ መልኩ ሳይሆን ተሞክረው ፍቱን መሆናቸው ከታወቀ በኋላ ነው እኛ እንድንቅማቸው የተደረጉት።

የነባር እምነቶች መዳከም ከተወላጁ የምእራብ ሕዝብም አልፎ አዲሱን የምእራብ ስደተኛም በብዛት እለታዊ የድበታ፣ የድብርትና የእብደት መድኃኒት ተጠቃሚና ጥገኛ ባደረገበት ደረጃ መንፈሳዊና ሥነ አእምሯዊ ጤንነቱን አዛብቶት እያየን  ይህንን ቀውስ ለሀገራችን በብርቅዬነት ለማስገባት ስንጋጋጥ እናሳዝናለን። እነሱ እኛ ልናስፋፋ የምንደክምበትን የእምነት መንገድ ተከትለው ዛሬ ምን ላይ ናቸው? የሕዝብቸው መንፈሳዊና ሥነ ልቡናዊ ጤንነት ምን ይመስላል? ብለን መጠየቅ ይገባናል።

እሺ ምእራባውያን በተትረፈረፈ ምርታቸው አማካኝነት ተብረቅራቂ፣ ተብለጭላጭ፣ ሸቀጥ አግበስባሽ ትውልድን መፍጠር ለኢኮኖሚያቸው ሞተር ይጠቅማል እንበል። ሰውንም ከማንነቱ በማዛባት፣ ራሱ ወንድ ይሁን ሴት ግራ በማጋባት ትልቅ የኬሚካል ኢንዱስትሪ ጥገኛ የሆስፒታል ቁራኛ በማድረግም ትርፍ ያጋብሳሉ እንበል። በሽታንም ጦርነትንም የንግድ እና የኢንዱስትሪ ዘርፋቸው ስላደረጉት።  እኛ የተትረፈረፈ ምርት ቀርቶ በቂ የሚላስ የሚቀመስ የሌለን የኢንዱስትሪ ውጤታችን በንጽጽር (per capita/ proportionately) ከኃይለ ሥላሴ ዘመን እንኳን ያሽቆለቆለ ሕዝብ ምን ሲባል ነው የሚያግበሰብስና በልቶ የማይጠረቃ፣ በአቋራጭ ለመክበር የሚጓጓ ትውልድ ለመፍጠር የምንራወጠው?

ባለው የኑሮ ችግር አብዛኛው የሕዝባችን ክፍል ኦርቶዶክስ ወይም በኦርቶዶክሳዊ ክርስትና እሴቶች የተቃኘ* ባይሆን ይሄንን  ሁሉ መንግሥታዊ መከራ ይሸከም ነበር ወይ?

በቂ የእህል አቅርቦት የለም። ከፍተኛ የዋጋ ግሽበትም አለ። በአመት እኩሌታውን በጾም፡ በቀን አንዴ ወይም ሁለቴ በልቶ የሚውለው ምእመን ስለኖረ ነው ችግሩን ዋጥ አድርጎ መንግሥትን ሳይረብሽ መኖር የቻለው።

ከፍተኛ የፍትሕ እጦት አለ። “እግዚአብሔር ይይላቸው!” ብሎ ወደ ቤቱ የሚገባ በመሆኑ ነው ባለሥልጣናት በዚህ ለከት የለሽ ብልግናቸው በሰላም የሚኖሩት

ባለፉት አመታት ከፍተኛ ጭፍጨፋ፣ ዘረፋና ማፈናቀል በመንግሥት ሽፍታዎች ተካሄዷል። በቀል የእግዚአብሔር ነው ብሎ አልቅሶ ዝም የሚል ሕዝብ መኖሩ ነው አራጅ ሆይ! ላንተም የበጀህ።

እና ሌላ ሀገር ሲለበስ ያየኸው ፋሽን እኛም ላይ ያምራል ብለህ ተዋሕዶን አፍርሰህ ወደ ክሪስላም ይሁን ወደ ብልጽግና ወንጌል የምታደርገው ጉዞ ነገ እንደዛሬው የማይታገስህ፣ ለራሱ ብቻ የሚያስብ በልቶ የማይጠረቃ ትውልድን ነውና የምትፈጥረው ለራስህ ስትል አድብ።

ቄሮን እንዴት እንዳስታገስክ ታውቀዋለህ። በየደረጃው የዘረፋው ተጠቃሚ በማድረግ። ይሁን  እንጂ ያንን አላምጦ ውጦ ተለመማዶት አይኑ ሌላ ቀላውጦ እያገሳ እየመጣልህ ነው። የሁለት ሚሊዮን ተፈናቃይ አማራ ንብረትና መሬት፣ ጥቂት የደነበሩ ትግሬዎች ሃብትም ዝርፊያ ሁለት አመት ያህል ብቻ ነው ያስታገሰው። አሁንም የቤተክርስትያን መሬት፣ ሙዳየ ምጽዋትና ሕንፃ ኪራይ ልትወረውርለትና ትንሽ ልትተነፍስ የዘየድከው መላ አንድ ሁለት አመት ትንፋሽ ይገዛልህ ይሆናል። ሰፊው በላተኛ ካድሬህ ግን መልሶ ያገሳል፣ ያኔ አንተን ከነቤተሰብህ ከነዘር ማንዘርህ ይጎርሳል።

ስለዚህ  አራጅ ሆይ! ላንተም ኦርቶዶክስ መቆየቷ ነው የሚበጅህ።

*የተዋሕዶ ምእመናን ባሕል በቅድመ ተዋሕዶ እምነት እሴቶች የተቃኘ መሆኑ በተመሳሳይም የተዋሕዶ ተከታይ የነበሩት አማኞች በኋላ የተቀበሏቸውን እምነቶች ሲከተሉ በተዋሕዶ ተከታይነታቸው የነበሯቸው ብዙ እሴቶችን እያንጸባረቁ መቀጠላቸው የታወቀ ነው።

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Latest from Blog

የኦህዴድ መራሹ ብልፅግና  መንግስት  በአማራ እና በኦሮሚያ ክልል በንጹሀን  ዜጎች ላይ እየወሰዳቸው ያሉ የነፃ እርምጃ  ግድያዎች  መንግስት ያሰበውን የፖለቲካ ግብ ያሳካለታል  ወይ ? በኔ አመለካከት እነዚህ የንፁሃን ዜጎች  የጅምላ ግድያዎች  በሁለት በኩል እንደተሳለ ቢላዎ (double edge sword) ናቸው:: ፩- መንግስት እያሰላው

 የኦህዴድ መራሹ ጅምላ ግድያዎች ስሌት (ሸንቁጥ- ከምዕራብ ካናዳ)

January 24, 2025
እነዶ/ር ደብረፅዮን እና በጠ/ሚ ዐብይ አህመድ በተሾሙት የትግራይ ጊዜያዊ መንግሥት መሪዎች እነጌታቸው ረዳ መካከል የነበረው አለመግባባት ተካርሮ ሰራዊቱን ወደውግንና አስገብቷል። የትግራይ ሐይል አዛዦች ትላንት ባወጡት መግለጫ ውግንናቸው ከእነዶ/ር ደብረፅዮን ጋር መኾኑን አስታውቀዋል።

በትግራይ የተፈጠረው ምንድነው?

January 23, 2025
የድሮ መሪዎች ያላደረጉትን ምሁር ጳጳሳቱ ያላስተዋሉትን ከፈረሰች ጎጆ ከባልቴት ቤት ገብቶ ክብሩን ዝቅ አድርጎ ውሀዋን ጠጥቶ ምግቧንም ተጋርቶ ያላለቀሰ ሰው ያንን ትይንት አይቶ ማን ይኖራል ከቶ? በዉሸት ፈገግታ ፊቱን አስመስሎ ፀሀይ የበራበት

ሰው በሰውነቱ – ከ ይቆየኝ ስሜ

Go toTop