July 15, 2022
21 mins read

ሰው እና ጀምበር – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

Ethiopian weather 1024x782 1

ሰው ነኝ።  ፈጣሪ ፍቃዱ ከሆነ በወግ ልክ እንደ ጀንበሯ ፣ ጥዋት   ወጥቼ ማታ ልጠልቅ እችላለሁ ። ይኽ የሰው ልጅ ዕጣ ፈንታ ነውና !   አዳም እና ማቶሣላ ሺ ለመድረሥ ጥቂት ቁጥሮች የቀራቸው ዘመናትን ኖረው ፣ ዕድሜ ጠግበው መሞታቸውን ሣሥብና የዛሬው ሰው ዕድሜ ከ 70 ከዘለለ ድካም እንጂ ተርፍ የለውም ተብሎ በድጋሚ በፀሐፍ ቅዱስ መጠቀሱን ሣሥተውል እግዜሩ ለምን የዕድሜ ሥሥታም ሆነ እላለሁ ? ( ወይሥ ራሣችን ነን በምድራዊ ጥበብ የተነሠሠ ዕድሜዬችንን በየሚሊኒየሙ እያሣጠርነው የመጣነው ?)

ሰባን የማይሻገሩ የሰው እድሜዎች፣ ከጀንበር ፍንጥቀት እስከ ሥርቀት ያለውን ጉዞ ገላጭ ናቸው   ። ይሁኑ እንጂ ሰው እነዚህን የጤዛ ያህል ቆይታ ያላቸውን ቀናትን ሰው ፣ ሰው ሆኖ እንዳይኖርባቸው ተረግሟል ። በተለይም በአፍሪካ ። በባሰ መልኩ ደግሞ በኢትዮጵያ ።

በኢትዮጵያ    “ የሱም ሆነ የኔ ሰው መሆን ነው  እንጂ ዋናው ቁም ነገሩ  ሌለው  በዘመን ውስጥ ሰዎች የፈጠሩት ኮተትና ቆዳ ማዋደድ  እኔን አይመለከተኝም ። … ቋንቋ  ፣ዘር፣ጎሣ ኃይማኖት፣ ወዘተ ። ከሰው ተራ አያወጡኝም ። አማራ ፣ ትግሬ ፣ ኦሮሞ እያሉ በከፋፍለህ ግዛ እና ሽጥ ዘዴ ፣ የሌሎች የጋለ  የእንጀራ ምጣድ አያደርገኝም ። “ የሚል ሰውነቱን በቅጡ የተገነዘበ ፣ ከተሜ በብዛት የለም ። በአርሶ አደሩ ቀዬ ደግነትና ርህራሄ ትላንት ሞልቶ ተትረፍርፎ ነበር ። ዛሬ ግን ዕድሜ  ለሥግብግብ  እና ዘረኛ  ሊሂቃን እና ለመብላት ተቧድነው ለሚያሤሩ ፖለቲከኞች በባላገሩም ቀዬ ጥርጣሬ ና ሰው ጠልነት ለመንገሥ እያኮበኮበ ነው ። ለአገዛዝ እና ለምዝበራ ሲባል የመለሥ ዜናዊ እና የአሜሪካው ሲአይኤ የፈጠረው በቋንቋ ፣ በጎሣ ና በነገድ ላይ የተመሠረተ የዘመነ ከፋፍልቲ አገዛዝ “  የገሃነም  እሣት ነው ። “ ለባለአገሩ ።

ይኸንን “ የገሃነም እሣት “   ኢሳያስ አፈወርቂ ያልወደደው ሰው የተባለውን የጋራ መጠሪያ እና ሰውነትን እራሱን የሚያሥክድ በመሆኑ ለአንድነት ና ለፍቅር ፀር በመሆኑ መተላለቅን በሰዎች ዘንድ በእጅጉ የሚያበዛ መሆኑንን አሥቀድሞ ሥለተገነዘበ ነው ። ይኽ የዘመነ ከፋፍልቲ መንገድም  ፤ ጂቡቲን እና እራሷን  ኤርትራን እንዳሳጣትም  “ ከኢሱ “ የተሰወረ አይደለም ። በእንጊሊዝ መንግሥት ሥውር ሴራ ፣ በሲአይኤ ና በሞሳድ እሥፖንሰርነት ነው ፣ ቀኃሥ በቀላሉ ፍርክስክስ ያሉት ።   መንጌም አገር ጥሎ ሀራሬ የገባው በእነዚህ አገራት “ ነጭ ለባሾች “ ታላቅ ሴራ ነው ።

ሲጀመር ፣ መንጌ  ሥልጣንን ያገኛት ሻሞ ተብላ በአየር ላይ ሥንትሣፈፍ ነው ። ይኽንን ሃቅ  ሥንቶቻችሁ ታውቃላችሁ ?የጦር ክፍሉ ከሚገኝበት  ከሐረር ጦሩ ከእነ ሃምሣ አለቃ ለገሰ አሥፋው ጋር ጦሩ የላከው ሌላውን ተራ ነገር ተውትና “ ነውጠኝነቱን እና አንደበተ ርዕቱነቱን “  በማሥተዋል ነው ፣ ጦር ሠራዊቱ ብሶቱን እንዲያሰማለትና መፍትሄ እንዲያመጣለት መርጦ የላከው  ። እርሱም ፣ ድንገት ነው ሥልጣንን ጠቅልሎ መያዝ እንደሚቻል የተገለፀለት ። በሴራ እና ለምሣ ያሠቡትን ቁርሥ በማድረግ ለንግሥና መብቃት እንደሚቻል የተከሠተለት በወቅቱ በወታደራዊው ኮሚቴ ውሥጥ ለሚከሰቱ ችግሮች ፈጣን የመፍትሄ ሃሳቦችን ሲያቀርብ የጦሩን ቀልብ በመግዛቱን በማሥተዋሉ ነው ። ከእርሱ የተሻለ አንደበተ ርዕቱ በወታደራዊው ደርግ ውሥጥ ያለመኖሩን ሲረዳማ በልቡ “ የኃይሌ ዙፋን የእኔ ናት  ። “ ሣይል እንዳልቀረ ገምቱ   ። የአፍሪካ መንግሥታት ሥልጣን እንዲህ እንደዋዛ በብልጣ ብልጥነት ና ለምሣ የሚያሥቡህን ያለርህራሄ ለቁርሥ በማድረግ የምታገኛት ናት ። በአፍሪካ እነ ሙጋቤ እንደመሠከሩልን ፣   ደፋር ፣ ቆራጥ አብዮታዊ መሪ ከሆንክ ከአርባ ዓመት በላይ ሁላ መግዛት ትችላለህ ።   ።

ተርታው ህዝብ በዕውቀት እና በጥበብ ባለመበልፀጉ ፣ በተራራ ፣ በዛር ፣ በቃልቻ ፣ በደብተራ ፣ በመፀሐፍ ገላጭ ፣ በጠንቋይ ፣ ወዘተ ። ከማመኑም በላይ ዛሬም ፈጣሪ ደሃ እንዳደረገው በማሰብ ኃላፊነቱን ለእርሱ ሰጥቶ ፣ “  አንተ  ታውቃለህ “ ። … የአርባ ና የሰማኒያ ቀን እድሌ ነው ። ይኽ የእኔ ዕጣ ፈንተ ነው ። … ባይ  ነው ። ህዝቡ   ፣ በመሠረታዊ ፍላጎቶች እጦት የሚሰቀይ እና ያለ ንቃተ ህሊና የሚኖር በመሆኑም ለመገዛት ምቹ ነው   ። ( ይኽንን ሃቅ አለማየሁ ገላጋይ “ በየተጠላው እንዳልተጠላ “ መፀሐፉ በጥልቀት ገልፆታል ። ብራቮ ! አሌክስ ። ፈጣሪ ሰው ያለመሆኑንን እና በዚህ የተነሣም  ሐሜት ፣ ሰብቅ ፣ አሽሙር ወዘተ የመሣሠሉትን ተንኮሎች ብቻ ሣይሆን የንፁሐኖችን ግድያ በተመለከተ እጁን በምድራዊ ፍርድ እንደማይከት ለማሣየት ብዙ እርቀት ሄደሃል ። እኔም ምድር ጥረን ግረን እንድንበላ እንጂ ተቀምጠን አበሣ እንድንቆጥር አልጋበዘችንም ። እላለሁ ። ሰው የምድር እንግዳ ነውና ።   ደሞም ለሐጢያት የሚመጣ ለፃድቃንም እንደሚደርስ አሥቀድሞ በቅዱስ መፀሐፍ የተፃፈውን አንብቡ ።   የሰው ጠላት ራሱ ሰው ነው ። ጠላትነቱም ከሥግብግብ ባህሪው ና መሞቱን በቅጡ ካለመገዘቡ ይመነጫል ።  አንዴ የቋንቋና   ከሁሉም ሰው ጋራ ተግባብቼ  ለመኖር የቻልኩትም  በተአምር አይደለም ።  ሰውን በሰውነቱ ብቻ በመቅረቤ እንጂ ነው።    የዓለም ሰው ሁሉ  በሰውነቱ  አንድ ነው ። ቆዳው ይለያይ እንጂ የወል መጠሪያው ሰው ነው ። ይህ ሰው በመባል የሚታወቀው፣የተለያየ የቆዳ ቀለም ከፈጣሪ የተለገሰው ፣ የዓለም ህዝብ በሙሉ ፣ ወንድሜና እህቴ ነው ። ብዬ የማምን  ነኝ ። አምኜም ቋንቋው ሣይገድበኝ በወዳጅነት ቀርቤ ና ቀርቦኝ ፣ቋንቋውን ባልችል  እንኳ በምልክት ቋንቋ ፍቅሬን ና አክብሮቴን ገልጬ ከተግባባው ምን እፈልጋለሁ ???  ሲጀመርም የዓለም እውነት ይኸው ነው ። …ከምልክት ቋንቋዋ ነው የመላው ዓለም ቋንቋዋ የመነጨው ፡፡ በየሀገሩ የተለያየ ባህል ቋንቋ ና ሀይማኖትን በዘመን እርጅና ውስጥ የፈጠሩትም የትላንት እህትማማችና ወንድምማች ሰዎች ከምልክት ቋንቋዋ ተነስተው ነው ፡፡

በኢትዮጵያ አማርኛ ብቻ አንደበቱ የሚናገር ሆኖም ኦሮምኛ ቋንቋ ከሚናገሩ የተወለደ ግለሰብ  “እኔ እኮ… ! ” ብሎ ኦሮሞነቱን  በአማርኛ ማስረዳት ቢጀምር ሰሚ የሚያጣው የቋንቋን ጅማሮ እና የተለያየ መሆን ደማዊ የሆነ መስሎ በመገኘቱ ነው ግን አይደለም ፡፡  በእውነቱ ይኽ ያልተገባ  አፍቅሮተ ቋንቋ  ነው ። ቋንቋ ሰው ከተፈጠረ በኋላ የሚለማመደው ፣ የሚኮርጀው እና የሚማረው እንጂ በደሙ ውስጥ ፣ በአንጎሉ ውስጥ ከመወለዱ በፊት ያለ አይደለም ፡፡

ፀሐፊው ይኽንን  ጽሑፍ የፃፈው ሰዎች፣ ቋንቋ ሳይሆኑ ፣ ሰው መሆናቸውን ተገንዝበው ከሁሉም ሰው ጋር በፍቅር እንዲኖሩ ጥቂት የብርሃን ፍንጠቂ በጨለመው መንገዳቸው ላይ ለማኖር አስቦ ነው ፡፡ሰው ሁሉ ምሥኪን ተራ ሟችነቱን ተገንዝቦ ፣ እስከ መቃብር  ከአምሳያው ጋር ያለውን ትስስር እና ንሮውን ለማሸነፍ የሚደርገው ጥርት እንዳይስተጓጓል በሰውነቱ እንጂ በቋንቋው ሌ እነዳይሟዘዝ ትሁት ምክሩን በመለገስ   በማስተዋል እንዲሞላ ለማድረግ ነው ፡፡

ከራሴ ሰውነት ተነስቼ እውነት ልናገር ፡፡ በበኩሌ ፤  አማራ፣ኦሮሞ፣ ትግሬ ፣  ኢትዮ ሱማሌ ፣ደቡብ  ውስጥ ካሉትም ጎሣ ነኝ ከሚሉት የአንዱም ነገድ አይደለሁም ።   ዘግይቶም ሆነ ፈጥኖ ወደመቃብር የሚገባ ጠፊ ሰውነት ይዢ ለግዜው በህይወት የምንቀሳቀስ ተራ ሰው ነኝ ።  የህይወት  ጉዞዬም እንደሁሉም ሰው  ከጀንበር ፍጥቀት  እሥከ ሥርቀት ነው ። ዘግይቶም ሆነ ፈጥኖ  ከአፈር በመሠራቴ ወደአፈር የምመለሥ ።  ሰው ሁሉ  እንደ እኔ ተራ ሟች እንደሆነም አምናለው ። ዛሬ ሲሞት ነገ በሚሞተው ተራ ሞች ታሪኩ ቢነገርም ተስካርና ዘካ ቢወጣለትም ፤  በምድር ቆይተው ከአፈር የተገኘውን ሲበላ እንደኖረ ሁሉ ፣ በተረው ደግሞ በአፈር ይበላል ፡፡ ሁሉ ከአፈር የተገኘ ነውና ሰው በቁሙ የሚንቀሳቀስ አፈር አይደለሁም ለማለት አይችልም ። …

“…ምንም ብንጓጓለት ብንስገበገብለት፣ይፈርሳል በግዜይቱ ሥጋ ነውና ከንቱ።…” ብላ እንዳዜመችው አፈር የሆነችው ብዙዬ ነገ ሁላችንም አፈር፣ወይም አመድ እንሆናለን። (አሥከሬን አቃጣዮች ሥላሉ ነው – አመድ ያልኩት።!)     ጥላሁን ገሠሠም    “ሀብቴ ተርፎ በዝቶ ብዙ ቢያደረጀኝ፣ሥሞት ሥንቅ አይሆነኝ ኋላ ምን ሊበጅኝ??? ” በማለት   ” እራቁታችንን ወደዓለም መጥተናል ከዓለምም አንዳች ይዘን አንሄድም ። ” በማለት አዚሟል ። እነዚህ በድምፃቸው ወርቅነት የማንረሳቸው የኪነት ሰዎች ፣እውነቱን በውብ ዜማ  ቢያሳውቁንም ፣ ሁሌ የሚሞተው በሬሣ ሣጥን ውሥጥ ያለው አሥከሬን ሥለሚመስለን ዛሬ እንደምንሞት ለማሰብ አንፈልግም ። ሞትን ለማሰብ ባንፈልግም ሞት ሁሌም አብሮን ይጓዛል ፡፡ መሞታችንን ሳናምንም ወደመቃብር  እንወርዳለን ፡፡ አብዛኞቻችን ከሰው ይልቅ ለቁስ ትልቅ ክብር በመስጠት እየኖርን ነው ሞት በድንገት የሚወስደን ፡፡

“…ሰው ሞኝ ነው ተላላ፣ይጨነቃል ለሀብቱ— ነገ ትቶት ለሚሄደው  ወደ ማይቀረው ሞቱ። “ የሚባለውም ለዚህ ይመስላል ፡፡

ሰው ልጅ አበክሮ  መጨነቅ የሚገባው ፣ለሀብቱ ሳይሆን ከሱ ሞት በኋላ ሀብትና ንብረቱን ለሚረከበው ትውልድ መሆን ነበረበት ። ትውልዱ የሱን ንብረትና ሀብት ከነበረው አልቆ የማያስቀጥል ከሆነ ልፋቱ ከንቱ ፣ ከንቱና የከንቱ ከንቱ ነው ፡፡ ባክኖ ነው የሚቀረው ። የሰው ደም፣እንባና ሰቆቃን በውሥጡ ያከማቸ የግፍ ሀብት ከሆነ ። ትውልዱም የሀብቱን ምንጪ  ሥለሚያውቅ ለዛ ሀብት ና ንብረት ደንታ ቢስ ነው የሚሆነው ፡፡ ሀብቱና ንብረቱም   የኋላ፣የኋላ ላለፋበት ባዳ ሰው  ሲሳይ ሆኖ ያርፈዋል ።

እናም   ሰዎች ሆይ አንዘናጋ ፡፡   ህይወት አጭር ናት ። በዚች አጭር ህይወት ፣የግፍ፣የሥርቆት ና የዘረፋ ሐብት ፣በማከማቸት ለልጆቻችን መከራን አናውርሳቸው ። … ህይወት  እንደ ጠዋት  ጀምበር   ፈንጥቃ ፡፡ በረፋድ ሞቃ ፡፡ በቀትር ደምቃ ። በማታ አዘቅዝቃ ። በመጨረሻም በጨለማ ተውጣ ፤ አካላዊውን  ሥጋ በምድር ጥላ  ፣ በነፍሥ ተመስላ ወደ ሠማያዊው ሠማይ ትነጉዳለች  ። እንደ እምነታችን ፡፡

 የጀንበር ጉዞ  ህይወት

ያ -የጀንበሪቱ፣የስርቀት ውበት

ያፈዘኛል ያ -ልዩው ፍካት

የከሰል ፍም አይነት…

ልብን የሚያሞቅ ድምቀት ፡፡

—————————— ይመስጣል

የማታ ጀንበር ውበትዋ

ስትጠልቅ የምናስተውለው ..

ደም ግባትዋ ፡፡

ህሊናን የሚያሸፍተው …

ማራኪ ብርሃኗ …

እንድናያት ግድ የሚለን …

ወርቃማ ጨረሯ ፡፡

” የአትሸኙኝም ወይ? “ የማታ ግብዣዋ ፡፡

የታጀበው በውብ ፈገግታዋ ፡፡…

ፍዝዝ አድርጎኝ እባባለሁ

በሀሳብ ባህርም  እመሰጣለሁ ።

በጀምበር ውስጥም ጠልቄ እገባለሁ ።

ለአፍታ ከሥጋዬ አለያለሁ ።

ህይወት እንደዚች ጀምበር ናት እላለሁ ።

 

………………………………………..

“ጀንበር ለእኛ ብርሀኗን ስትነፍገን

ለሌሎች ደግሞ እንደምታበራ

ህይወትም ከህይወት ተጎዳኝታ

ሌላ ህይወት እንደምታፈራ

እንዲሁ ነው……….

እዛኛው ቤት ፣ ልጅ ሲወለድ

እዚህኛው ቤት ፣ እናት ሞታ …

እዚህኛው ቤት ፣ የሠርግ ድግስ …

እዛኛው ቤት ፣ ለቅሶ እሪታ…

እዚኛው ቤት ፣ እፍኝ ቆሎ

እዛኛው ቤት ትልቅ ቅልጥም

ሁሌ ቡፌ…”ዶሮ ፋንታ ! “

ህይወት ሁሌም እንዲሁ ነች …

በተቃራኒ እውነታ የተሞላች ፡፡

እስቲ ለአንድ አፍታ ፣ እናስተውላት

ለደቂቃ ቆም ብለን ፣ እንመልከታት ፡፡

” ሞትና  – ህይወት …… ”

የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ !

በጨለማና በብርሃን ይመሰላሉ

በተቃራኒ እውነታ !

ጨለማን ማንም አይወደውም

ተንኮልና ሸርን መጠንሰሻ…

በመሆኑ የሞት ጓዳ ፡፡

በጨለማ ተሸሽጎ እኮ ነው …

ሰው ለጥፋት የሚሰናዳ ፡፡

እርግጥ ነው ፡፡ …

ሰው ጨለማ ለብሶ አምሳያውን ቢያጠፋ

እርሱም ፀሐይ ሳትጠልቅ ነው ፤

በአፍጢሙ  የሚደፋ ፡፡

ሰው ቢያልም በግፍ ለመክበር

ህይወቱ  እንደሆን አጭር ናት

ከጀንበር ፍንጥቀት –እሥከሥርቀት

አጭር  የዝንጋታ ፤ የጉዞ ፍታት ።

በሐዘን፣ በደስታ ፤ በፍቅርና በጥላቻ…

ደምቃ የምናያት ።

ከፀሐይ ፍንጥቀት እስከ ሥርቀት …

ጧት ተጥዳ ፣ ማታ የምታከትም ናት ።

የኛዋ ህይወት ፡፡

አንድ ቀን እኮ  ናት  የኛ ህይወት

ጣፋጭ ሆና ሥቃይ ያየለባት ፡፡

የቀዝቃዛ ፣የለብታ፣ የግለት …

የሞቅታ ፣ የስከነት …

የሥክነት ፤ የእረጋታ ፤ የአንቅልፍ ፤ የእፎይታ ፡፡

እንደዛች ጀንበር ፣አጭር ጉዘት ፤

ከጎህ መቅደድ ፣ እሰከ ጀንበር ሥርቀት ፡፡

 

1983  ( በደሌ _ ኢሉባቦር )

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

289659386 10159901026834393 7717595044600991369 n
Previous Story

“ጥቃት እና ሞት በቃ” ! “ሞት ለገዳይ”

174708
Next Story

የህወሃቱ የአቶ መለስ ዜናዊ ታሪካዊ ስህተት በጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አህመድ ሊደገም ቋፍ ላይ ይመስላል

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop