ግንቦት 7 “የወያኔ ስርአት እስካልተወገደ ድረስ በአማራው የተጀመረው ጭፍጨፋ በሌሎችም ማህበረሰቦች ላይ ይቀጥላል” አለ

በዶ/ር ብርሃኑ ነጋ የሚመራው ግንቦት 7 ንቅናቄ “ይህ የወያኔ ስርአት እስካልተወገደ ድረስ በአማራው የተጀመረው ጭፍጨፋ፣ እንግልት፣ ስደት፣ መከራና ግድያ፤ ህወሃት በሌሎችም አጠናክሮ ይቀጥልበታል ብሎ” እንደሚያምን በሳምንታዊው የድርጅቱ ልሳን ላይ ገለጸ። “በወያኔ ያልተበደለ፣ ያልታሰረ፣ ያልተደበደበ፣ ያልተሰደደ፣ ያልተፈናቀለ፣ ያልተራበ፣ ያልተዋረደ፣ ያልተገደለ ህዝብ የለም።” ያለው ግንቦት 7 ” የኢትዮጵያ ህዝብ በወያኔ ጨካኝ ስርአት አማካኝነት በጨለማ ሂዎት ውስጥ እየኖረ ነው” ብሏል።

የግንቦት 7 ሙሉ መልዕክት እንደወረደ የሚከተለው ነው፦

ወያኔ ለአማራ ህዝብ፤ ባህልና ታሪክ ያለዉን ጥላቻ ከተራ ጥላቻ አልፎ በተግባር አማራዉን ወደ ማጥቃት ዘመቻ አደገ እንጂ ለአንድም ቀን ቀንሶ አያውቅም። አማራው እንደ ሰው ልጅ የመኖር መብቱ፣ ስብእናው ተገፎ ከቀየው፣ ከመንደሩ የአፈራውን ንብረትና ገንዘብ እየተቀማ መባረሩ፣ መሰደዱ፣ እንግልቱ ሁሉ የወያኔ የበቀል እርምጃ ነው።

በአሶሳ፤ በደኖና በአርባጉጉ ውስጥ አማራ በመሆናቸዉ ብቻ ህጻናት፤ሴቶችና አረጋዉያን በግፍ ተገድለዋል። ባለፈዉ አመት በደቡብ ክልል ጉራ ፈርዳ እየተባለ በሚጠራዉ አካባቢ ለረጂም አመታት ከአካባቢዉ ኢትዮጵያዊ ወገናቸው ጋር ተግባብተዉ ይኖሩ የነበሩ የአማራ ብሄረሰብ አማራ በመሆናቸዉ ብቻ ለአመታት ያፈሩትን ንብረት ይዞ የመሄጃ ግዜ እንኳን ሳይሰጣቸዉ አከባቢዉን ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ለቅቀዉ እንዲወጡ እንዲፈናቀሉ ተደርጓል።

ከመጋቢት ወር መጀመሪያ ጀምሮ ወያኔ በአማራዉ ህዝብ ላይ አዲስና ሰፋ ያለ የጥቃት ዘመቻ ጀምሯል። በደቡቡ የአገራችን ክልል በጉራፈርዳ የጀመረዉን አማራውን ነጥሎ የማጥቃትና የማንገላታት ዘመቻ አሁን ደግሞ በሰሜን ምስራቅ የአገራችን ክፍል በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቀጥሏል።

የቅርብ ግዜው ደግሞ ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ተፈናቅለው በምእራብ ጎጃም ዞን በፍኖተሰላም ከተማ ሜዳ ላይ ወድቀው የሚገኙት አማራ አርሶደአሮች የድረሱልን ጥሪ ማሰማታቸውና፤ ብሄረ አማራን እወክላለሁ ባዩ ብአዴን (የህወሃት ቡችላ) ጠበንጃ ደቅኖብን ወደ መጣችሁበት ተመለሱ ከዚህ ጥፉ ሲል አዋከበን፤ የወገን ያለህ ድረሱልን የት እንግባ ልጆቻችን የአውሬ ራት ሆኑ ሲሉ ስቃያቸውን አሰምተዋል። በርግጥ የህወሃት ተለጣፊው ብአዴን ሆዳቸው ስለሞላ ህሊናቸው ታውሮ ይህ በደል የሰው ልጅን የማጥፋት ሴራ መሆኑን እና በዘር ማጥፋት ወንጀል እንደሚያስጠይቅ የተረዱ አይደሉም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ "መንግስት ለኔና ለቤተሰቤ ጥበቃ ያድርግልኝ" ሲሉ ተማጸኑ

ሰሞኑን በቤንሻንጉል ጉሙዝ ለረጂም አመታት ከአካባቢዉ ህብረተሰብ ጋር ተቀላቅለው ይኖሩ የነበሩ አያሌ የአማራ ብሄረስብ ተወላጆች ያፈሩትን ንብረት ለመሰብሰብ እንኳን ግዜ ሳይሰጣቸዉ የኔ ብለው ከሚጠሩት የመኖሪያ ቦታቸዉ እንደባዳ እየተገፉ እንዲወጡ ሲደረጉ በአንጻሩ በባህርዳር ከተማ ብአዴን የቱባ ባለስልጣናቱን ከርስ ለመሙላት የክልሉን ህዝብ ጮኸት ጀሮ ዳባ ብሎ ሽርጉድ ሲል የነበረ መሆንን ያገናዘበ ኢትዮጵያዊ ቁጭት በርካታ ነው ።

የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ፡ እርግጥ ነው ይህን ዘረኛ ቡድን ለማስወገድ በሚደረገው መራራ ትግል ሂደት ውስጥ በደልና ሰቆቃው እየበዛ እንደሚሄድ ቢታወቅም ተባብረን ከታገልነው ግን ይህን ልናሳጥረው እንችላለን። አለበለዚያ ግን እስከ መቼ ነው ወገኖቻችን በትውልድ መንደራቸው የሀገር ውስጥ ጥገኛ ጠያቂ የሚሆኑት? የአማራ ብሄረሰብ ተወላጆች ከቀያቸው የተባረሩት በኢትዮጵያዊ ዜግነታቸው ነው።

ግንቦት 7 ንቅናቄ ይህ የወያኔ ስርአት እስካልተወገደ ድረስ በአማራው የተጀመረው ጭፍጨፋ፣ እንግልት፣ ስደት፣ መከራና ግድያ፤ ህወሃት በሌሎችም አጠናክሮ ይቀጥልበታል ብሎ ያምናል። ስለዚህ ምን እንጠብቃለን በወያኔ ያልተበደለ፣ ያልታሰረ፣ ያልተደበደበ፣ ያልተሰደደ፣ ያልተፈናቀለ፣ ያልተራበ፣ ያልተዋረደ፣ ያልተገደለ ህዝብ የለም። የኢትዮጵያ ህዝብ በወያኔ ጨካኝ ስርአት አማካኝነት በጨለማ ሂዎት ውስጥ እየኖረ ነው።

የሀገራችን ወጣት ሆይ፡ ወጣትነት ሀገር ተረካቢ፣ ባላደራ፣ ለውጥ ፈላጊ፣ ሀገሩን ጠባቂ ነው። ወገንህ ሲገረፍ ሲንገላታ ሲሰደድ ማየት እና ከንፈር መምጠት እሰከ መቼ ይሆን? ሰቆቃቸው፣ ቁስላቸው የድረሱልን ዋይታቸው መቼ ይሆን ተሰምቶን እንባቸውን በአለንላችሁ የወገን ደራሽነት የምንደርስላቸው? የምንጠርግላቸው? ግንቦት 7 ትግሉን የማቀጣጠያ ሰአት ጊዜው አሁን ነው ይላል። ወጣት፣ አዋቂ፣ ጎልማሳ፣ ሽማግሌ፣ ዘር ጾታ ቋንቋ ሳይለየን ወያኔን ለማስወገድ በሚደረገው ትግል ምላሽ ስጡ፣ ተቀላቀሉ። በኢትዮጵያ የጠቆረውን ጨለማ በብርሃን መተኪያ ጊዜ ዛሬ ነው። ይህ ትውልድ የታሪክ ባለእዳ አይሁን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያና የጠፋው 8.5 ቢሊዮን ዶላሯ - በእስክንድር ነጋ

በወያኔ ውስጥ ያላችሁ ይህ በደል ና ሰቆቃ የሚሰማችሁ ወገኖቻችን የውስጥ አርበኛ የምትሆኑበት ሰአት ላይ ናችሁ። ራሳችሁን እና ወገናችሁን ከቀን ጅብ ስርአት አድኑ። ከነጻነት ማግስት በኋላ ከሚመጣባችሁ ከየት ነበራችሁ ክስ ለመጽዳት ከነጻነት ታጋዮች ጋር አብሩ። ወያኔ ለ21 አመታት ህዝቡን ለማጋጨትና ለማባላት የሚያደርገው ስልት መሆኑን ተረድታችሁ የውስጥ ታጋዮች መሆናችሁን ማሳያ ጊዜው አሁን ነው። አሊያ ግን በአማራው ህዝብና በሌላው ማህበረሰብ ላይ እየተፈጸመ ባለው እጅግ አስከፊ ወንጀል በግልም ሆነ በቡድን፣ የንጹሀንን ደም እያፈሰሳችሁ ያላችሁ ወንጀለኞችና ተባባሪዎች ተብላችሁ፣ ከያላችሁበት ታድናችሁ ለፍርድ እንድትቀርቡ ንቅናቂያችን የሚቻለውን ሁሉ ለማድረግ ያለውን ቁርጠኝነት በግልጽ እንድታውቁት ይገባል።

የሀገራችን ህዝብ ሆይ፡ ዛሬ ኢትዮጵያን ከገባችበት ዘረኛ መቀመቅ ስርአት ውስጥ የሚያወጣት ብቸኛ መፍትሄ፣ ፍርሃታችንን በጥሰን በተባበረ ጉልበትና ድፍረት ወያኔን በሚገባው ቋንቋ ስናናግረው፣ ታግለን ስናስወግደው ብቻ ነው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ኩራትና ክብርን፣ ተሳስቦና ተፈቃቅሮ፣ ተከባብሮና ተቻችሎ የመኖር ጸጋን የምናመጣው። ስለሆነም በየትኛውም አቅጣጫ የሚደረገውን የነጻነት ጉዞ ትግል ትቀላቀሉ ዘንድ ግንቦት 7 የፍትህ የነጻነትና የዴሞክራሲ ንቅናቄ ጥሪውን በድጋሜ ያቀርባል።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

1 Comment

Comments are closed.

Share