ባሁኑ ሰዓት በአማራው ወገናችን ላይ እየደረሰ ያለው አማራን የማጥፋት ሴራ፤ ኢትዮጵያዊነትን ለማጥፋት የሚካሄደው ተግባር ዋናው አካል ነው – ክፍል ፫

አማራው ያለበትን ዕለታዊ የስቃይ ሁኔታ፣ ለምን ይህ በአማራው ላይ እየተፈፀመ መሆኑንና ለምን ይኼን የስቃይ ሁኔታ የወገን ማጥፋት ወንጀል እንዳልነው ባለፉት ሁለት ተከታታይ ዕትሞቻችን ዘርዝረናል። በዚህ የዛሬው እስከመቼ እትማችን ደግሞ፤ ለዚህ መፍትሔ በማሰብ ምን መደረግ አለበት የሚለውን እንጠቁማለን።

የአማራው ጉዳይ ከሌሎች የኢትዮጵያ ጉዳዮች ተለይቶ መልስ የሚሠጠው፤ መፍትሔው ደግሞ በተናጠል ፈላጊ የሚቋቋምለት ጉዳይ አይደለም፤ ጉዳዩ አማራው ኢትዮጵያዊ ነኝ ማለቱ ነውና! እንደማንኛውም የኢትዮጵያ ጉዳይ ሁሉ፤ እያንዳንዳችን ኢትዮጵያዊያን ጉዳዬ ብለን የምንታገልለት ነው።

ከአማራው ጉዳይ በተጨማሪ፤ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ጉዳይ አለ። የገዳማት ጉዳይ ሌላው ትልቁ የኢትዮጵያዊያን ጉዳይ ነው። በትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት የሚደረጉት ፀረ_ኢትዮጵያና ፀረ_ኢትዮጵያዊያን ተግባራት ከፍተኛ ደረጃ ደርሰዋል። ባጠቃላይ ባሁን ሰዓት፤ ከዴሞክራሲ መብት ጥያቄዎች አልፎ የሀገር ሕልውናና የሕዝብ ዘር በማጥፋት መረብ መጠመዱ ስለሆነ፤ የነፃነት ጥያቄ ነው። ባሁን ሰዓት በኢትዮጵያ ያለውን ሀቅ በዴሞክራሲ መብቶች ጥያቄ ዙሪያ መመልከት ቅንጦት ነው። በዚህ እንድንስማማ ነው የኛ የመጀመሪያው መልዕክታችን።

ከዚህ ቀጥሎ ደግሞ ሁለተኛ መልዕክት አለን። ይኼ አሁን ኢትዮጵያዊያን የምናደርገው የነፃነት ትግል፤ የዛሬ ትግል ነው። እናም ጉዳዩ የዛሬ ነው። የነፃነት ጉዳይ ነው። ታዲያ ትግሉ የሚደረገው በዚያው በሀገራችን ውስጥ ነው። የምንታገልለት ዓላማ አሁን የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት በሚያደርገው ተግባር የተመሠረተ ነው። ይህ ደግሞ፤ የዘር ማጥፋት ተግባር፣ የሃይማኖት ተከታዮችን የማሰቃት ተግባር፤ የሕዝብን ሥልጣን የመንጠቅ ተግባር፤ የሕግ የበላይነትን መርገጥ ተግባር፣ ኢትዮጵያዊያንና ኢትዮጵያን ለማጥፋት የሚደረግ ሴራ፣ የኢትዮጵያዊያንን ማናቸውም የመተንፈስ ሆነ ሠርቶ የማደር ቀን መንፈግ፤ . . . ዝርዝሩ ይቀጥላል። ይኼንን በየዕለቱ የሚጋፈጡት ኢትዮጵያዊያን በተቻላቸው መጠን፣ ባገኙት ቀዳዳ፣ ባላቸው አቅም፤ በሀገሪቱ እየታገሉ ነው። ከነሱ ጥረት አንፃር፤ በውጭ የምንኖር ኢትዮጵያዊያን አስተዋፆዖዋችን አነስተኛ ነው። እዚህ ላይ ነው ሁለተኛው መልዕክታችን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጭራቅ አሕመድ ኦነግ ሸኔ እና የሂትለር ኤስ ኤስ - መስፍን አረጋ

አስተዋፅዖዋችን አነስተኛ የሆነበት ምክንያት፤ ሀገር መውደዱና ለወገናችን ያለን ፍቅር አንሶ ሳይሆን፤ የዓላማ አንድነትና ብሎም የትግል አንድነት ባለመያዛችን ነው። በሚያስገርም መንገድ፤ ድርጅቶቻችንን ከሁሉ በላይ በማድረግ የትግላችንን መንገድ ቅደም ተከተል ስተናል። እናም በአንድ ሆነን ወገናችን ነፃ ለማውጣትና ሀገራችንን የኢትዮጵያዊያን ለማድረግ መጣር ሲገባን፤ አንድም የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት ለሚሠጠን የቤት ሥራ ትጉ ተማሪዎች ሆነን ተጠምደናል፤ ሌላም እርስ በርሳችን የኔ ድርጅት ይበልጣል የኔ ይበልጣል ንትርክ ገብተናል። ሁላችን አንድ ነን። ትግሉ የጋራችን ነው። ታጋዩ በሀገሩ ያለው ሕዝብ ነው። የኛ ዋና ሚናችን፤ በሀገር ውስጥ ላለው ትግል ቀኝ እጅ መሆን ነው። በርግጥ የትግሉ አካል ነን። መሪም ታጋይም መሆን እንችላለን። ነገር ግን፤ በአንድነት፣ እዚህ፣ ባሁን ሰዓት ልናደርገው የሚገባን፤ የመታገያ ዕሴቶቻችንን በአንድነት ነድፈን፣ ያለ የሌለ ጉልበታችንን በአንድነት አሰባስበን፣ አንድ የመታገያ ድርጅት አቋቁመንና አንድ የትግል ማዕከል ኖሮን፤ መነሳት ነው። በተደጋጋሚ በእስከመቼ የመታገያ ዕሴቶች ብለን ያስቀመጥናቸው የሚከተሉት ናቸው።

፩ኛ፤   የኢትዮጵያ ህዝብ አንድነትና ሉዓላዊነት፤

፪ኛ፤   የኢትዮጵያ ሀገራችን ዳር ድንበር መጠበቅ፤

፫ኛ፤   በኢትዮጵያ የሕግ የበላይነት መስፈን፤

፬ኛ፤   የግለሰብ ዴሞክራሲያዊ መብት መከበር፤

፭ኛ፤   የትስስረ-ትውልዱ አምባገነን የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር መንግሥት መወገድና መሪዎቹ ለፍርድ መቅረብ፤ ናቸው።

እነኚህ የፖለቲካ ፓርቲ አይፈልጉም። እነኚህ መሠረታዊ የወገንና የሀገር ፍቅር ያላቸው ኢትዮጵያዊያን የሚሰባሰቡባቸው ዕሴቶች ናቸው። መጨመር ይቻላል። መጀመሪያ ግን እስኪ በነዚህ ላይ ስምምነት ላይ ደርሰን፤ ከወገናችን ጎን እንሠለፍ!

የአማራ ወገናችንን በሚመለከት፤ ይኼን አምባገነን መንግሥት ልመና አንገባም። ሆን ብሎ እያደረገ ያለውን ወንጀል፤ እባክህን ተው ለኛ ስትል ብለን መማፀን አንይዝም። በእንግልት ላይ ያሉትን ወገናችንን መርዳት አለብን። በተቻለ መጠን ዝርዝር ዘገባዉን ማጠናቀር አለብን። በምናገኘው መንገድ ሁሉ፤ ኢትዮጵያዊያን በአንድነት፤ ይኼ ያገራችን ጉዳይ ነው ብለው እንዲነሱ መቀስቀስ አለብን። ከሁሉ በላይ ግን፤ እያንዳንዳችን፤ እኔን ይመለከተኛል በማለት መቆጠር አለብን። ከዚህ የበለጠ አጀንዳ የለም። በየከተማችንና በየምንኖርበት ሀገር፤ በየቤተክርስትያናቱና በየመስጊዶች የምንወያየው ይኼው ይሁን። መዋጮ እናሰባስብ። እግረ መንገዱን ግን፤ ዘላቂ መፍትሔውን ለማምጣት እንዋቀር። እኛንም አስተምሩን፤ ንገሩን። ሕዝቡ ያቸንፋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊነታቸው የማያምኑ በኢትዮጵያ ቅርሶች ስም መጠቀም የለባቸውም

eske.meche@yahoo.com

Share