“ብላቴናኢቱ ተኝታለች እንጂ አልሞተችም” ማቴ9፡24 – ከመኳንንት ታዬ (ቤተ-ክርስቲያን ስላለመከፈሏ)

ከመኳንንት ታዬ(ቤተከርስቲያን ስላለመከፈሏ)

ጌታችን መድሃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላስተምሮ በነበረበት  ግዜ” ከያኢሮስ ቤት  በደረሰ ግዜ ብዙ ሰዎች  ሲያለቅሱ ሲወጡ ሲገቡ አገኘ፤ ሹም ቢሞት ሃምሳ የሹም ልጅ መቶ ሃምሳ እንዲሉ፤ ወይቤሎሙ ተገሃሡ እሰመ ኢሞተት  ሕፃን አላ ፤ትነውም(ህፃኒቱ ተኝታለች እንጂ አልሞተችም ብሎ አረጋገቸው። እያለ ይቀጥላል። በዚህ እውነትም  በሚያሰኝ ሁኔታ  በቅርቡ  “ቤተክርስቲያናችን ከሁለት  አልተከፈለችም” በሚል ርዕስ ፕሮፌሰር ጌታቸው  ባወጡት ፅሁፍ ላይ  ተንትረሶ ሌሎች የሠጡትን  አስተያየት ለመጋራት  በሚል  ይህቺን  አጠር ያለች መጣጥፍ እንደ  ወትሮ ሁሉ ነፃ የሆነ አስተያየቴን  ለመግለፅ ወደድኩ።

የ ኢ/ አ/ተ/ቤ/ በአይነቱ የመጀመሪያና  መስመር ለመያዝ  ከማስቸገሩም  በላይ  ልጆቿን አሳዘነ እና በገዛ ልጆቿም  የተፈተነችበት  ግዜው  ያሳለፍነውና  የያዝነው  ዘመናችን  ነው። ለዚህም ችግሩን  ለመፍታት የቋጠሮው  ውሉ ለንግግር ቃሉ ለክብር አንቱ የሚባሉ ጠፍቶንና  ጠፍተውብን  ሁላችንም በያለንበት  ሆነን ድምፅ  በሠማንበት ሮጠን የሁሉም  አላማ ግራ ገብቶን አለን። እርግጥ ነው ቁልፍ ወዴት እንዳለ ቁልፉን ለያዘውም የያዙልን አደራ ላለውም  ግልፅ ነው።ግን ምን ያደርጋል  ቤተክርስቲያን እና ክርስቲያን  እንደባቢሎን  ዘመን ቋንቋችን  በየግል ፍላጎታችን  ሆነ።

ሁሉም በዚህ ይሁንና የክቡር ፕ/ር ጌታቸው  ሃይሌን  “ቤተክርስቲያን ከሁለት አልተከፈለችም “በሚለው ፅሁፋቸው  ሥር መከፈል ማለት ከምን እንደሚጀምርና እንደሚጨርስ ከዚህ  በፊት  በዚህ  ዙሪያ ላይ አንስተዋቸው የነበረውን ነጥብ አሁን ካለው ሂደት ጋር አቆራኝተው  ብዙ ቁም ነገሮችን ተዝቆ ከማያልቅ አውቀታቸው  ላይ አከፍለውናል።እርግጥ ሁሉም  የሳቸውን ሃሳብ ይጋራል ማለት ሞኝነት እንደሆነ እውነት እውነት ነው ።እንደ አብነት ያህልም  አንድና ሁለት  የሆኑ ወገኖች የፕሮፌሰር ጌታቸው  ፅሁፍ  ከፋፋይ ነው  ሲሉም  ተደምጠዋል።እኔም ደግሞ እንደሃሳቤ የምለው ቢኖር  አለመስማማትንና  እውነትን ለይቶ አለማወቅ  አውቀት የሆነበት  ዘመን ሆኖ እንጂ የፅሁፉ አላማ እንኳን እንዲያ አደለም። እንደመጨመሪያም  በአህያ ተከልሎ ጅብን  ለመግደል  የሚደረግው ሙከራ ዘመኑ አልፎበት  አዲሱ ጅብ አህያንም  ገዳይንም ጨምሮ መብላት ጀምሮአልና ፤ጅብን በጅብነቱ  ፊት ለፊት መጋፈጡ የተሻለ ሥለሆነ ፖለቲካ  ለሚያቀነቅኑ ሠዎች የፕሮፌሰርን አባባል እንደማይዋጥላቸው  ለማስቀመጥ የሞከሩትን  ስመለከት  ገርሞኛል። ለመሆኑ የቤተክርስቲያን መከፈል ማለት  ምን ማለት ነው? ተከፈለ ለማለት ልዩነቱን  ማየትና መረዳት  የተረዳ  ህዝብም ያስፈልግ ይመስለኛል። ለዚህም  ከስሙ መጀመር  ደግ ነውና ከብዙ በጥቂቱ ተራ  በተራ እንመለከት።

የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ፤- በዚህ ስም  አዲስ አባበ ጨምሮ በመላው አለም የኢትዮጲያ ቤ/ክ  በምትገኝበት  ሃገር መጠሪያ ሆኖ  የተሰደደውን የፓትሪያሪክ አቡነ መርቆሪዮስን የሚመሩት ቤ/ክ ጨምሮ ገለልተኛው ይጠቀምበታል። ይህ ማለት ደግሞ የአንድ እናት ልጆች በአንድ ትሪ ላይ ለሶስት ተቋርሶ እንደመብላት ማለት ነው። ታዲያ በአንድ መሶብ ተቋርሶ እየበሉ ተከፋፈልን ተለያየን ማለት ይቻላል ወይ? ተለየ ወይም ተከፈለ ለማለት በስሙ እንኳን ልዩነት መኖር የለበትም  ወይ? የቦታ አቀማመጥ ወይም ርቀት  ተከፈልን ሊያሰኘው የሚችል አንድም ክፍተት በሌለበት መስመር ውስጥ የግል ስሜት የፈጠረውን  መነሳሳት  ትልቅ ለውጥ ለማምጣት መጠቀም  አግባብስ ይሆናል ወይ? መከፈል የሚለው ስሜት ለምትጋሩ ቤተሰቦች መመዘኛችሁ የብፁነታቸው በግፍ  ከሀገር መሰደድ ከሆነ ይህ አንድ ትልቅ አባት ሊሸከመው ከሚችለው በታች መሆኑ ይሰማኛል።ከአቡነ ጴጥሮስ ጋር ሳነፃፅረው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢህአዴግና የሻዕቢያ ድርድር ተበጠሰ

ስርአቱ፦የቅድስት ቤ/ክ ስርአት የተመለከትን እንደሆነ የዶግማ ልዩነት ከሌለበት በስተቀር እስካሁን ባለው ሁኔታ በየትኛውም የኢ/አ/ተ/ቤ/ክ ውስጥ በማንኛውም ግዜና ሰአት የሚደረጉ  ከዚህ እስከዚህ የተባሉ ስራቶች  በምንም መመዘኛ  ልዩነት የላቸውም። እርግጥ ነው  ስርአቱን የሚያካሂዱት ካህናት ሆነኝ ብለው ሊያሳንሱትም ሊያሳድጉትም ይችላሉ። ያ ማለት ግን በለውጥ ደረጃ የሚታወቅና  ልዩነት እንዳለ የሚያሳይ  ምንም ነገር አለ ማለት አደለም። ታዲያ በዚህ መርህ ተከፈለች የሚያሰኝ ምን ቁም ነገር ልናነሳ እንችላለን? እናም የለም አልተከፈለችም የሚሉ ወገኖችን ስም ለማጉደፍ ሮጥን?።

የህዝቡ አምልኮ ሁኔታ፦

የህዝበ ክርስቲያኑ የአምልኮ ሁኔታ ምንም ሳይጓደል ጥንት በነበረውና ዛሬም ባለው መልኩ ፍሰቱን እንደቀጠለ ባለበት ሰዐት፤ ለምሳሌ የባዕላት አከባበር፤ አምልኮው፤ የቁርባን አቀባበሉ የፆም መግቢያና መውጫው፤ ስብከተ ወንጌሉ፤ አዲስ አባባ ያለው ክርስቲያን አሜሪካ ሲመጣ  ባጥቢያው ቤተከርስቲያን የመሄዱ  ነገር ወዘተ …ከፍም ዝቅም አድረገው ቢያዩት  አንድ በሆነበት  ሁኔታ ተከፈለ ለማለት የሚያበቁ ሚስጥሮች  የቱጋ እንደሆኑ በእውነቱ ግር ሳይል እንደማይቀር ማወቁ ግድ ይላል።

በጥቅሉ እናውሳ ካለን  እንኳን በወረቀት በመሬት ላይ ብንፅፈው ይበቃል ብዬ አላምንም። ነገር ግን ለአብነት ያህል ይህን ካልኩ በሗላ መከፈሏን ሊያወሱ የወደዱ ወገኖች ነጥብ ያደረጉት ፀረ-እምነት በሆነ  አስተዳደር ቤተክርስቲያን በደረሰባት በደል ምክንያት የጳጳሳቱ ቡድን እኛ ማለት ሁሉም ነን፤ ብለው ምናልባትም ፕ/ር ጌታቸው እንዳሉት ”የተሰደደውን ህዝብ የፖለቲካ ብሶት መጠቀሚያ ከማድረግ የዘለለ” ቤ/ክ ስለመከፈሏ የሚያሳይ ማስረጃ ለማግኘት አለ ለማለት  አልታይህ  እንዳለኝ ለማሳየት ልሞከር። ለዚህም አንድ “ፕ/ር ጌታቸው ዛሬስ ምን እያሉ ነው?  ብለው አስተያታቸውን  የሰጡ ወንድም ከላይ እስከታች ተከፈለ ለማለት የሚያነሱት ነጥብ  በቤተክርስቲያኗ ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና እንዴት ታግለን ከዛ መላቀቅ እንዳለብን  እንጂ ከላይ ሊነሱ የተፈለጉትን መሰረታዊየ የሆኑ የዶግማና የቀኖና ጉዳይ  አደለም። ማለትም  የተከፈለችበት ቦታና ነፅቡ አልተዘረዘረም። እንደውም በገፅ አንድና በገፅ ሁለት ላይ ካነሷቸው ውስጥ አንስተን ለማየት  እንሞከር “…በግፍ በተሰደዱ ወንድሞቻችን ላይ አጠቆሩባቸው? እነሱ የተወለዱበት  መንደርም እኮ ቢሆን  የእርሳቸው  ነው።እርሳቸውም  የተወለዱበትም  እንዲሁ የእነርሱ ነው:፡እያሉ  ይቀጥሉና ገፅ ሁለት ላይ”…….ስለዚህ  እኛ  በስደት  የምንገኝ  የኢትዮጲያ አ/ተ/ቤ ልጆች……  ከመንደርተኝነት በሽታ  ተላቀን  አመራሩን  እየተቀበልን ወደ ተስፋኢቱ ምድር ቅድስት ኢትዮጲያ  ስክንመለስ ድረስ አብረነው ቆመን  መለየት አለብን“ ሲሉ እርስ በእርሱ የሚጣረስ  ነገራቸውን በማቅረብ  ቤተክርስቲያን ተከፍላለች ለማለት የሚያስችል  መረጃ ይመስል  እሳቸውም የሚቃወሙት ዘረኛውን አገዛዝ  ባልሸሹም ዞር አሉ በኩል ሲቀላቀሉት  ለማየት እንዲያስችል የተሰመረባቸውን ሃረጋት  መመለከት በራሱ በቂ ነው። ስለዚህ “ያም መጣ ያም  መጣ ለእኔ እናት እንደው የበጃት የለም ሁሉም አፈር ጫነባት  እንዳለው “ሰውየው   በአቶ ከበደ ፅሁፍ ፕ/ር ለመቃወም የሚያስችል  ነጥብ አላገኘሁበትም ። ነገር ግን ቤ/ክ የአጥቢያ ፖለቲከኞች  ምሽግ ስትሆን  የሚያሳይ ድርሰት ተነቦኛል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጃዋር የሳተላይት ጠለፋና ስለላ ጉድ፦‼

ይህ ደግሞ የአቶ ከበደና መሰል ወንድሞቻችን ሜዳውን ያለማወቅ ችግር ሰዎች በፀጋቸው እንዳያገለግሉ ከማድረጉም በላይ በቅድስት ቤተክርስቲያን ላይ የተዘረጋውን ፈተና የከበደ እና በቀላሉ የሚወገድ እንዳይሆን የሚያደርገው ይመስላል። በእውነቱ እኛ ስንሰደድ ሲኖዶስ አብሮን  ተሰደደ ከሆነ እንደ ሱናሜ ያለ መዓት ቢመጣና ቢጠራርገን  ሲኖዶስም  አብሮ ውሃ ሊበላው ነውን? ወይስ ይዘውኝ የተሰደዱት ውሃ ባለቸው ብሎ ሃገሩ ሊገባ ነውን?። ውድ አቶ ከበደና መሰሎቻቻው  ይህን መሰረታዊ የሆነ ነገር ልብ ብለው ሊመከቱት ይገባል ሲኖዶስን የሚያክል የኢትዮጲያ ህልውና መገለጫ  ዛሬ ላይ የተረከቡት ሃላፊነታቸውን  መወጣት ያቃታቸው ግለሰቦች  ቢያቃልሉት የሆነውን እውነት አድርጎ ማቅረብ ለራስ ግዜ ሰጥቶ አለማሰብን ያሳያል።ይልቅ ትግሉ መከፈልን  እና መከፋፈልን ገንዘብ ለማድረግ መቻኮል ባይሆንና  በዚህ ተሰደው የሚገኙ አባቶች ፕ/ር እንዳሉት  ማህበረ ካህናት ወይም የካህናት ጉባኤ አቋቁመው  መልካም ዘመን አስኪመጣ ኑና ተቀላቀሉን ባሉና በውጭ የምትገኛዋን የኢ/ኦ/ተ/ቤ ጠቅለው በመሯትና ትልቅም ስራ በተሰራ። ነገር ግን አሁን ባለው ሁኔታ ቤተክርስቲያን ውስጥ የገባውን ፖለቲካ ለይቶ ለማስወጣት ከሳር ውስጥ ጤፍ የመልቀም ያህል የሚከብድ ሳያደርገው እንደማይቀር እሙን ነው። በሌላ መስመር ሊሰመርበት የሚገባ አንድ ነገር ቤ/ክ  የማንም ግለሰብ ወይም የፓትርያርክ ወይም የመንግስት አደለችም። ያ ቢሆን አባ ጳውሎስ ሲሞቱ አብራ ትሞት ነበር። ግለሰቦች የራሳቸውን ስሜት የሚጋራ ስራ ለመስራት ተጠቅመውባታል፤ እና ጥለናት ወጥተን ሌላ እንመስርት አይባልም። ባሉበት ሆኖ ሰንኮፉን እየነቀሉ ቅድስት ቤተክርስቲያንም እስከምፅአት ድረስ ባለችበት ፀንታ እንደትቆም ማድረግ ከሁላችን የሚጠበቅ ግዴታ ነው። በዚህ አጋጣሚ ስለገለልተኛው አካሄድ ማንሳት የግለሰቦች ፍላጎት ብዬ ከላይ ለጠቀስኩት ማሰናነሰያ የሚሆን ምሳሌ ልስጥ።ገለልተኛ ቤ/ክ።

ገለልተኛ፦ ይህ የ/ቤ/ክ ስርአት የተመሰረተው አቡነ ጳውሎስ  በደርግ መንግስት ታስረው  ከተፈቱ በሗላ  ወዲዚህ  ወደ አሜሪካን ሐገር ኮብልልው ስለነበር፤ በዛ ሰዐት የተሾሙት ፓትርያርክ በደርግ ስለሆነ አልቀበልም፤ ሲሉ ገለልተኛ የሚለውን  ቤ/ክ  መጀመሪያ በኒዮርክ ሗላም በዳላስ ቴክሳስ እንዳቋቋሙ አንዳንድ መረጃዎች ያስረዳሉ። ነገር ግን አቡነ ጳውሎስ ከመንግስት ለውጥ ጋርና ሹመታቸውን ህጋዊ አለመሆኑን ተከትሎ ሌሎች ወገኖች  ደግሞ  የሳቸውን ሲመት እንቃወማለን ለማሰኘት ገለልተኛ የሚል የቤተክርስቲያን  ስያሜ በመስጠት ይኸው እስከዛሬ ድረስ መጠሪያ አድርገው ያቡነ ጳውሎስን ራዕይ እውን ሲያደርጉ ይስተዋላል። ነብሳቸውን  ይማረውና በህይወት በነበሩበት ግዜ ገለልተኛው ቤ/ክ የሚጠይቀውን ሁሉ በአንድም በሌላም መልኩ እያሟሉለት ጳጳሳት እየተላኩ እንዲባርኩት በማድረግ ተመቻችቶ እንዲቀመጥና የሳቸውን ጅማሮ ይዞ እንዲጓዝ አድርገውታል። ነገር ግን ምሽጋቸውን ቤ/ክ ውስጥ የሰሩ ካለማስተዋላቸው የተነሳ ገለልተኛውን እነሱ የመሰረቱት እየመሰላቸው ገለልተኛነታቸው ባለበት እንዲቆይ ዛሬም ድረስ ይታገላሉ። ”ሱሪ ባንገት አውልቁ ስራቸውን ቢረዱት ይህን ባላደረጉ። ልብ እንበል ይህ ሁሉ ሲሆን  እኛ ምእመናን  እንደ ብላቴናዋ ተኝተናል እንጂ አልሞትንም። በዚህም ምክንያት የነቃ የሚያደርገውን አላደረግንም፤ ጭራሽ ስለቤተክርስቲያን ሲነሳ ቶሎ ብለን የሐገር ቤቱን  የዚህን ዘመን የቤ/ክ ፈተና አንስተን  መፍትሔውም  በተሰደደ ሲኖዶስና በገለልተኛ ቤ/ክርስቲያናት ውስጥ ተሸሽገን ውጊያውን ሟጧጧፍ ነው;; ነገር ግን  ሜዳውን ያለመለየት  አባዜ ስቃዩን  የከፋ ያደርገዋል።የሚገርመው አለማቸውን አንድ ያደረጉ ፖለቲከኞች  ኑና  ተቀላቀሉን አውድማው  ወዲ ነው እያሉ ጥሪአቸውን ሲያቀርቡ የአጥቢያ ፖለቲከኞች  ደግሞ እዚህም አለው እዛም ምንተማሪያም ብለው መፅሃፍ ቅዱሱ ሳይቀር እነሱ በሚፈልጉት መስመር  እንዲሰበክ ይፈልጋሉ፡፡ ሌላው ሁለተኛው ፀሃፊ ታዛቢው ብለው እራሳቸውን ያስቀመጡ ሲሆን  የፕ/ር ጌታቸው  ሃሳብ ለመቃወም  ጠቅላላ ጉዞውን  ያደረገው ያንኑ ከመንግስት ጋር በተያያዘ  ቤ/ክኗ ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍ እንደ ምክንያት አድርጎ ያስቀመጠ ነው። ምንም እንኳን አባባሉ እውነትነት ቢኖረውም  ቤተክርስቲያን  ስለመከፋሏ የሚያስረዳ ነገር ስለሌለ “ከመጠምጠም ማሰብ ይቅደም  በሚል “ቀለል ያለ ቢህል ተጠቅመን የእርስዎን ፋይል ቢዘጋ መልካም እንደሆነ አበስሮታለሁ። የቤተክርስቲያንን ችግር ለመቅረፍ ነገር አጠልጥሎ መሮጥ ሁሉን እርባነ ቢስ እንዲሆን ከማድረጉም በላይ መከራዋ ላላባራው ቤ/ክ ሌላው የችግር እጅ እንዳይሆን  ስጋቴን እገልፃለሁ።
በጥቅሉ አንዲት ቤ/ክ ተከፍላለች የሚባልበትንና አልተከፈለችም የተባለበትን ነጥብ መሰረታዊ የሆነውን አጃንዳ በመያዝ ለመተርጎምና ግልፅ ለማድረግ የተሞከረ እንደው ለሰሚው ግር እንደማይል የፕ/ር ሃሳብ ለተቃወማችሁ ወገኖች የበኩሌን ለማለት ስሞክር ቅድሚያ ያደረኩት የቤተክርስቲያኔ ጉዳይ እኔንም ያገባኛልና መከፈልን እንደሞት ስለቆጠርኩትም  አልተከፈለችም(አልሞተችም) ስል ብላቴናይቱ ተኝታለች እንጂ አልሞተችም የሚለውን የወንጌልን ቃል መነሻ አድርጌ ጀምሬ ጨርሻለሁ። ጌታ ጣቶቹን ልኮ ያፀዳታል “ሁላችንም ባለንበት ነቅተን እንፅና”ንቁም በበህላዌነ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከአዲስ አበባ አስተዳደር የተባረሩት ከ800 በላይ ሠራኞች ከባድ ማህበራዊ ቀውስ ውስጥ ገብተዋል ተባለ
Share